Print this page
Saturday, 12 October 2013 12:27

እናታቸው አንድ ያልሆነች ልጆች - አንዱ “ቁይልኝ!” አንዱ “አንጉችልኝ”

Written by 
Rate this item
(10 votes)

ከዕለታት አንድ ቀን አለቃ ገብረሃና ታመው ቤታቸው አልጋ ላይ ይውላሉ፡፡ አንዲት በሞጥሟጣነቷ በሰፈሩ የምትታወቅ ሴት ልትጠይቃቸው ትመጣለች፡፡
“አለቃ እንደምን አረፈዱ?”
“ደህና ነኝ - እግዚሃር ይመስገን” አሉ አለቃ፡፡
“ሰውኮ አጥብቆም አልነገረኝ፡፡ ለመሆኑ ምንዎትን ነው ያመመዎ?” አለቻቸው፡፡
አለቃ ላለመለስ ፈልገውም ይሁን፣ ግራ ተጋብተው ዝም ይላሉ፡፡ ሴትዮዋ፤
“አለቃ?”
“አቤት?”
“ምነው ዝም አሉኝ? አይመልሱልኝም እንዴ?”
“የዛሬ ህመም ከሚነገር ባይነገር የተሻለ ነው ብዬ ነው፡፡ ብመልስልሽም የምትፈይጅልኝ ነገር የለም፡፡ ህመሜን ላትታመሚልኝ፤ ይሄን አመመኝ ብልሽ ምን ይጠቅመኛል?”
“ቢሆንም፤ እምንዎ ላይ ነው?”
“እኔም አንቺም ያለን ቦታ ላይ ነው”
“አንገትዎ ላይ?”
“አደለም”
“ብብትዎ ውስጥ?”
“አይደለም”
“ንፍፊትዎ ላይ?”
“ደርሰሻል፣ ግን አደለም”
“አይ እንግዲህ፤ እራስዎ ይንገሩኝ?”
“ታፋዬ ላይ ነው ያመመኝ”
“እንዴት አመመዎት?”
“ብጉንጅ ወጥቶብኝ”
“በሞትኩት አለቃ አሁን እንዴት ሊተኙ ነው?”
“አንቺ እንዳልሽ!”
“እርሶ ደግሞ በቁም ነገር ላይ ቀልድ ይጨምራሉ”
“አይ የኔ ቆንጆ እሱም ተጨምሮ በገባሽና እሺ ባልሺኝ”
“እርሶ ጉደኛ ነዎት እናቴ! በሉ እግዜር ምህረቱን ይላክልዎት!” ብላ ለመሄድ ስትነሳ፤
“እንዳፍሽ ያርግልኝ!” አሏት፡፡
ወጥታ ሄደች፡፡ አለቃን የሚያውቅ የሠፈር ሰው ስትወጣ መንገድ አገኛትና፤
“አለቃን ጠይቀሽ መውጣትሽ ነው?”
“አዎን”
“ምን አሉሽ?”
“ብንጉጅ ታፋዬ ላይ አብጦ ነው አሉ፡፡ እግዚአብሔር ይማርዎት አልኳቸው “እንዳፍሽ ያርግልኝ” አሉኝ፡፡
ሰውዬው ከት ብሎ ስቆ፤
“አዬ ቀልደው ብሻል - እንዳፍሽ ሙጥሙጥ ያርግልኝ ማለታቸውኮ ነው” አላት
ሴትዮዋ ተናዳ ወደ አለቃ ተመለሰችና
“እንዴት እንዲህ ይሰድቡኛል አለቃ” ብላ ጠየቀች፡፡
“ለዚህ ነው የመጣሽ? “አይ እህቴ ልሰድብሽ ብፈልግ ኖሮማ ‘ሞጥሟጣ’ እልሽ ነበር” አሏት፡፡
                                                   * * *
ህመም ለህመም ካለመደማመጥ ይሰውረን፡፡ የተነገረንን ሳንረዳ በየዋህነት ከመሄድ ያውጣን፡፡ የሚነገርና የማይነገር ህመም ከማማረጥ ያድነን፡፡ ህመማችንን ተጋግዘን ከማዳን በሽሙጥና በወፍ አፍ ስንሸነጋገል፤ በሽታችን ካንሰር - አከል እንደሚሆን ማስተዋል ይገባናል፡፡
የፖለቲካ በሽታችን የጋራ መተሳሰብ ይፈልጋል፡፡ የኢኮኖሚ ድቀታችን የጋራ መደጋገፍ ይጠይቃል፡፡ ማህበራዊና ባህላዊ አኗኗራችን ለውጥ - ተኮርና አፈር - አቀፍ መሆንን ይሻል፡፡ አያሌ ብሔራዊና ሀገራዊ አጀንዳዎች ስላሉን፤ “አውቀን በድፍረት፣ ሳናውቅ በስህተት” የምናሳየው ቸልተኝነት የሀገራችንን ዕድገት እያዘገየን እንደሆን የመገንዘቢያ ሰዓት ነው!!
የቻይና መንግሥት ብሔራዊ ፍልስፍና ይበጀን ከሆነ ለእኛ እንደሚያመች አድርገን የማንወስድበት ምክንያት የለም፡፡ ሶስቱ ጭብጦቹ ሀ) ህግና ደምቦችን (በሶሺዮ - ኢኮኖሚ ደረጃችን አኳያ) በሚገባ ሥራ ላይ ማዋል፤ ለ) ገንዘብን ለሀገር ጥቅም በሚውልበት አኳያ መጠቀም፤ ሐ) ሁነኛ ባለሙያዎችን በሁነኛ ቦታ አስቀምጦ ማሠራት፤ ናቸው፡፡
በተለይ የሶስተኛው መርህ ትርጉም የሚኖረው፤ ሁነኛ ባለሙያ ማለት ቦታው ከሚፈልገው ያነሰ (Underqualified እንዲሉ) ብቻ ሳይሆን፣ ቦታው ከሚፈልገው በላይ (Overqualified እንዲሉ) መሆን፤ የየራሱ አበሳ አለው፡፡ አንዳንዴ “ቦታው ራሱስ አስፈላጊ ነወይ?” ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡
ተቃዋሚ ብለን ከፈረጅናቸው ወገኖች ጋር አብሮ የመሥራት እሳቤ ከሀገር ፋይዳው አንፃር መጤን ይኖርበታል፡፡ የሚሞሉት ክፍተቶች/ቀዳዳዎች በርካታ ናቸው፡፡ የአንድ ወገን ርብርቦሽ ብቻ አይሞላቸውም፡፡ እነዚህን ክፍተቶች ሙሉ በሙሉ ለመገላገልና ፍሬ ለማፍራት የሚጠብቀን መንገድ ቀላል አይደለም፡፡ ፍሬ የራሱ ባህሪ አለው፡፡ ያገራችን ገጣሚ እንዳለው
“ፍሬ በስሎ እሚበላው
…ወይ በራሱ ጊዜ ሲወድቅ፣ ወይ እኛ ስንለቅመው ነው!”
መረጃ ለህዝብ መስጠት መፍትሔ ለማግኘት የሚያስችል አጋዥ መሣሪያ ነው፡፡ መብራት ሲበላሽ ምክንያቱን ለህዝብ መንገር ነው፡፡ ኔት - ዎርክ እምቢ ሲል ምን እንደሚሆን ማንም ለመገመት አያቅተውም፡፡ መግለጽ ነው ችግሩ የደም - ሥሮቹ ይደፋፈናሉ፡፡ ሥራዬ ብሎ አትኩሮ ማየት ይገባል፡፡ ደህና መሥመር የያዙ ጉዞዎች ይወለጋገዳሉ፡፡ ሲከፋም ይበጣጠሱና ወደኋላ ይመልሱናል! የውስጥ ደም - መፍሰስ (Internal - bleeding) እያለ አዲስ ደም - ቅያሬ (New - blood - injection) ሙሉ በሙሉ ይሠራል ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው!
የህዝብ ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ምንጊዜም መዘንጋት አይገባም፡፡ ይሄን ለማየት የኢትዮጵያ ህዝብ ለስፖርተኞቻችን የሚሰጠውን ማበረታታትና ጭንቀት ማስተዋል ነው፡፡ በአንድ ጀንበር ሳይሆን የረዥም ጊዜ ውጣ ውረዱን አስቦ፣ ታግሶ፣ ሆደ - ሰፊ ሆኖ፣ ሌሎች የሚሉትን በጥሞና አድምጦ መሄድ ውጤት ላይ እንደሚያደርስ መገንዘብ ዋና ነገር የፖለቲካውን መድረክና የኳሱን ሜዳ አመሳስሎና አነፃጽሮ መሄድ አገራችንን ለመለወጥ በር ከፋች መንገድ ነው፡፡
ሕግ፣ ዳኛ፣ አራጋቢ፣ ተመልካች፣ አሰልጣኝ…አዳጊና ወራጅ ቀጠና …የፌዴሬሽን ሥርዓት… ልብ ላለ - መሬት ለረገጠ ለውጥ - ማስገንዘቢያዎች ናቸው!
(ለብሔራዊ ቡድናችን ቀናውን ሁሉ እንመኛለን!)
ሀገራዊ በሆነ ጉዳይ ፍፁም አንድነቱን ይሰጠን ዘንድ ዐይናችንን ከፍተን የሀገርን ደግ እንይ! አለበለዚያ፤ “እናታቸው አንድ ያልሆነች ልጆች - አንዱ “ቁይልኝ”፣ አንዱ “አንጉችልኝ” ይሆናል፡፡ ከዚህም ይሠውረን!

Read 5619 times
Administrator

Latest from Administrator