Monday, 16 September 2013 07:35

ዛዮን ሬብልሥ “ፕሮቫ” አልበም አወጡ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በሙዚቃው በመንቀሳቀስ የ11 ዓመታት ልምድ ያለው ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ባንድ የአዲስ አልበም “ፕሮቫ” ለአዲስ ዓመት ገበያ አቀረበ፡፡
ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ባንድ ለገበያ ያበቃው ፕሮቫ አልበም አራት ዘፈኖች ያሉት ሲሆን፤ ሚክሲንግና ማስተሩን ናቲ ሲምስ እንደሰራው ታውቋል፡፡ ከአራቱ ዘፈኖች የመጀመሪያው ‹‹አዲስ ዓመት›› የተባለው እና ጭብጡ አዲስ ተስፋ አዲስ ትውልድ በሚል የተሰራ ሲሆን ግጥምና ዜማ የሰሩት ዛዮን ሬብልሥ እና ናቲ ሲምስ ናቸው፡፡ ሁለተኛው ‹‹አፍሪካ›› በሚል ለአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዮ የተሠራ ዘፈን ሲሆን፤ ግጥምና ዜማውን በመሥራት ዛዮን ሬብልሥ፣ ናቲ ሲምስ እና ዶቭ ቤንጂ ተሳትፈዋል፡፡
ሦስተኛው፤ ‹‹ላቭ ዊዝ ዋት ዊ ኒድ›› የተባለው ዘፈን ሲሆን፤ በዩቲዩውብ ተጭኖ ከሁለት ሺ አምስት መቶ በላይ ተመልካች ያገኘ ነው፡፡ በዚሁ ዘፈን ግጥምና ዜማ ሥራ ላይ ዛዮን ሬብልሥ፣ ናቲ ሲምስ እና ዶ/ር ቢ (ብሩክ ቦካ) ተሳትፈዋል፡፡ አራተኛው ዘፈን ‹‹ሳባዊት›› በሚል የተዘጋጀ ሲሆን፤ ግጥምና ዜማውን የሰሩት ዛዮን ሬብልሥ እና ናቲ ሲምስ ናቸው፡፡
ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ቡድን ሁሉንም ዓይነት ሙዚቃ ይሰራሉ፡፡ ሬብልስ የተባሉት ለአገራቸው መልካም እና ጥሩ ነገሮች በማሰብ ያዳበሩት የታጋይነት መንፈስ ሲሆን በተለይ በሬጌ ሙዚቃቸው የተካኑና ጥሩ መልዕክት እና አህጉራዊ አጀንዳ ያላቸው ዘፈኖችን በመሥራት ከፍተኛ ልምድ ያዳበሩ ናቸው፡፡ በዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ቡድን ያሉት ዘፋኞች ውቅያኖስ ፍቅሩ፣ ቴዎድሮስ ኃይሌ እና ይስሃቅ ኤልያስ ናቸው፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በአዲስ አበባ፣ በድሬደዋ እና በሀዋሣ በርካታ ተመልካች ያገኙ የሙዚቃ ዝግጅቶችን የሠራው ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ቡድን ከተለያዩ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር አርቲስቶች ጋር በመሥራትም ይታወቃል፡፡
አራት ዘፈኖች ያሉበት የዛዮን ሬብልሥ ፕሮቫ አልበም በ2006 ዓ.ም ለገበያ የሚበቃው ሙሉ ዓልበም ማስተዋወቂያ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

 

Read 9662 times