Print this page
Saturday, 07 September 2013 10:25

ኢህአዴግ “ጉልቤ” ነው እንዴ? (ጥያቄ ነው!)

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(23 votes)

   ቴሌ የኩኩ ሰብስቤን “ቻልኩበት ዘንድሮ ቻልኩበት የኑሮ አያያዙን እኔም አወቅሁበት” ጋብዞናል!
ሰሞኑን ከቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሙት ዓመት ጋር ተያይዞ ምስላቸው በተደጋጋሚ በኢቴቪ እየቀረበ ነው (ለምን ቀረበ አልወጣኝም!) አንድ የአራት ዓመት ህፃን ይሄን ዓይቶ በንፁህ የጨቅላ አንደበቱ ምን እንዳለ ታውቃላችሁ? “መለስ አሁንም አልተሻለውም? እንደሞተ ነው?” አንጀት የሚያንሰፈስፍ ንግግር ነው፡፡ (ህፃኑ የገባውን ያህል መጠየቁ እኮ ነው!) አሁን “ነፍስ ይማር” ብለን ወደ ዛሬው አጀንዳችን እንግባ፡፡ (እሳቸው የሚሰሩትን ሰርተው አልፈዋልና ኢህአዴግም ወደ ስራው ቢገባ ሸጋ ነው!)
አንዳንድ የኢህአዴግ በጐ ነገር ፈጽሞ የማይታያቸው (ፓርቲው ጨለምተኞች ይላቸዋል!) ሰዎች ምን ይላሉ መሰላችሁ? “ኢህአዴግ ከሁለት አስርት ዓመታት የስልጣን ዘመን በኋላም ምንም ለውጥ አላመጣም፤ አልተሻሻለም” (የእኔ ሃሳብ አለመሆኑ ይታወቅልኝ!) ከምሬ እኮ ነው … እኔ በዚህ ሃሳብ ፈጽሞ አልስማማም፡፡ ሌላው ሁሉ ቢቀር እንኳ “ተራ ፓርቲ” ሆኖ መጥቶ “አውራ ፓርቲ” ለመሆን መብቃቱን እንክዳለን? (በእርግጥ ራሱ ነው “አውራ ፓርቲ ሆኛለሁ” ያለን!) እናላችሁ…አውራው ፓርቲያችን ለውጥ አላመጣም የሚለው አሉታዊ አስተያየት “የምቀኞች ወሬ ነው” ባይ ነኝ፡፡ (“አውራ ፓርቲ ሳይሆን አውራ ዶሮ ነው” ያሉት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ማን ነበሩ?) እንደሚመስለኝ “ጉልቤ ነው” ሊሉ ፈልገው ነው፡፡
እንዴ ምን ነካቸው? የአገሪቱ ገዢው ፓርቲ መሆኑን እረሱት ልበል! መንግስት እኮ ሁሌም “ጉልቤ ነው” (የአፍሪካን መንግስት ማለቴ ነው!) እስቲ በጦቢያ ታሪክ መንግስት ሆኖ “ጉልቤ” ያልነበረ አንድ ገዢ እንኳን ጥቀሱልኝ፡፡ (ኢህአዴግ ዕድሉ ሆኖ ነገር ይከርበታል!)
ሰሞኑን በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ከአንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ጋር ስናወጋ የኢህአዴግን “ጉልቤነት” ደጋግሞ ነገረኝ-በቁጣ እየተግተረተረ፡፡ (የተቃዋሚዎች “ፖለቲካዊ ውሳኔ” ይሆን እንዴ?)
“እስቲ ስሜትህን ትተህ ሃሳብህን ንገረኝ” አልኩት - ጭፍን ጥላቻ እያንፀባረቀ እንዳይሆን በሚል ስጋት (ከስጋት ነፃ የሆነ ዓለም ናፈቀኝ!)
“ጉልቤ እኮ ሌላ አይደለም፤ ከህግ በላይ ልሁን የሚል ነው” ብሎ አፈጠጠብኝ (ራሱ “ጉልቤ” የሆነ መሰለኝ!)
“መረጃና ማስረጃ ልትጠቅስልኝ ትችላለህ?” ስል ጠየቅሁት ስፈራ ስቸር (“ህጋዊነትና ህገወጥነትን ያጣቅሳሉ” የተባሉት ተቃዋሚዎች መስለውኝ!)
“ሺ ማስረጃዎች እጠቅስልሃለሁ … ሩቅ ሳንሄድ በእሁዱ ሰላማዊ ሰልፍ እንኳን ህገመንግስቱን ጥሷል…ለምን ያላወቃችሁ ትመስላላችሁ…ለነገሩ ብትፈሩ አይፈረድባችሁም…በአንድ የስልክ ጥሪ ከህትመት ውጭ ያደርጋችኋል!” (ኢህአዴግን ትቶ ወደ ግሉ ፕሬስ!)
“ነገሩን ብታብራራው አይሻልም?” ኮስተር ብዬ ጠየቅሁት፤ የተቃዋሚ ፓርቲውን መሪ፡፡
“በራሳችሁ ጋዜጣ የወጣውን ጉዳይ እኮ ነው የምነግርህ!… ‘ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ማሳወቅ ብቻ አይበቃም፤ ማስፈቀድ ያስፈልጋል’ በማለት የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ ህገወጥ መሆኑን የተናገሩት በናንተ ጋዜጣ አይደለም እንዴ? እስቲ አሳየኝ የትኛው ህግ ላይ ነው እንዲህ የሚለው?” በቁጣ ድምፀት ጠየቀኝ (ተወንጃዩ እኔ ነኝ ኢህአዴግ?)
“ስማ …ራሱ ያረቀቀውን ህግ የሚጥስ ጉልበተኛ ያልተባለ…ማን ሊባል ነው? ልንገርህ አይደል…ኢህአዴግ የለየለት ጉልበተኛ ነው!” በንዴት እየተንተከተከ ነው የሚናገረው፡፡
ባለፈው ቅዳሜ ማታ፣ የሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ተከብቦ አመራሮቹ ታስረው ተደበደቡ የሚለው “ዜና” ትዝ አለኝና ሰቀጠጠኝ፡፡ መቼም ለዜጐች መብትና ነፃነት የታገለ ፓርቲ፤ ይሄንን ፈፀመ ሲባል ማመን ያዳግታል (ያልታወቁ ኃይሎች ቢሆኑስ? አልኩ-ለራሴ) ከክስተቱ በኋላ ተቃዋሚዎች ያወጡት መግለጫ ግን አስደስቶኛል፡፡ ጥሰቱን ማንም ይፈጽመው ለህገመንግስቱ መከበር በጋራ ማበራቸው ይበል ያሰኛል፡፡ (ኢህአዴግም እኮ ሳንሰማው አውግዞት ሊሆን ይችላል!) (ፓርቲ ቢኖረኝ ብዬ ተመኘሁ!) በእርግጥ መኢአድ እግረመንገዱን “ሰማያዊ ፓርቲ ከተቃዋሚዎች ጋር አልሰራም” ማለቱን በቅሬታ ጠቅሷል፡፡ (ያዝኩህ” እንደማለት እኮ ነው!) ግን እኮ ሰማያዊ ፓርቲም ወዶ አይደለም፡፡ አደረጃጀቱ ከሌሎች ተቃዋሚዎች ስለሚለይ ብቻ ነው (ቀለማዊ ፓርቲ እኮ ነው!) አንዳንዶች ግን “ፓርቲው ምድራዊ አይደለም፤ ሰማያዊ ነው” ሲሉ ሰምቻለሁ (“ዕጣ ክፍሉ ከሰማያዊው ዓለም ነው” ለማለት ነው!) በዚህ እንኳን አልስማማም (“የመላዕክት ስብስብ” ፓርቲ አይሆንማ!)
“እስቲ አሁን ደሞ ስለ አዲስ ዓመት ህልሞችና ተስፋዎች እንጨዋወት …እርግጠኛ ነኝ…2006 የተሻለ ዓመት ይሆናል! በጐ በጐውን መመኘት መቼም ጥሩ ነው…አይደል?” አልኩት ለተናደደው የተቃዋሚ መሪ፡፡
ሰውየው በአንድ ጊዜ ሁለመናው ተቀያየረ - አራስ ነብር መሰለ፡፡ ዓይኑ ተጐልጉሎ ሊወጣ ምንም አልቀረው፡፡
“በጐ መመኘት ነው ያልከው? ‘ያልተነካ ግልግል ያውቃል’ አሉ” ከተቀመጠበት ተስፈንጥሮ ተነሳ፡፡ በዚህች ቅጽበት አንድ ነገር ትዝ አለኝ፡፡ የአዲሱ ሚሊኒየም መጥቢያ ላይ ይመስለኛል፡፡ በአዲሱ ሚሊኒየም የኢህአዴግ ምኞት ምን እንደሆነ የተጠየቁ አንድ የፓርቲው ከፍተኛ አመራር “ፓርቲያችን በምኞት አያምንም፤ በትግል እንጂ!” ብለው ነበር፡፡ ይሄም የተቃዋሚ መሪ ተመሳሳይ ነገር እንዳይል ሰጋሁኝ፡፡ (ዕድሜ ልክ መታገል እኮ “ፍርጃ” ነው!)
የጠረጠርኩትም አልቀረ፡፡ በሚያስፈራ ዓይኑ ቁልቁል እያጉረጠረጠብኝ “ትሰማኛለህ… ጉልበተኛ ፓርቲ በምኞት ተሸንፎ አያውቅም፤ ነፃነትና ዲሞክራሲ ቁጭ ብሎ በማለም አይመጣም…በትግልና በመስዋዕትነት ብቻ ነው!” አለና በንቀት ገርምሞኝ ፊቱን አዞረ - መንገድ ሊጀምር፡፡
“ምን ዓይነት ትግል? ማለቴ…” ሳያመልጠኝ ጠየቅሁት (ከአፌ ያመለጠችኝ ጥያቄ ናት!) የተቃዋሚ ፓርቲው መሪ ቀጥ ብሎ ቆመና ወደ እኔ ዞር ብሎ በነገረኛ ዓይኖቹ ትክ ብሎ እያየኝ “ጐሽ! አንቺም የሆዳሞቹን ሊግ ተቀላቀልሽ ማለት ነው” አለኝ - የለበጣ ፈገግታ እያሳየኝ፡፡ (“የሆዳሞች ሊግ” ተቋቁሟል እንዴ?)
“ለማንኛውም የትግሉ ዓይነት ሰላማዊ ነው፤ መስዋዕትነቱም እንደዚያው! ኢህአዴግን የምንታገለው ራሱ በሰጠን መሳሪያ ነው፡፡ በህገመንግስቱ እንታገለዋለን! ይሄንንም በደንብ ንገራቸው እሺ… ሆዳም ትውልድ!” ብሎኝ በፍጥነት እየተራመደ ሄደ፡፡ (“ሰላማዊ ትግል በአዲስ መልክ ጀምረናል” ያለኝ መሰለኝ!)፡፡ በጣም ገረመኝ፡፡ ሰውየው ለምን እኔን በኢህአዴግነት እንደጠረጠረኝ ፈጽሞ አልገባኝም፡፡ (እሱም እኮ ከሚከሰው ኢህአዴግ የባሰ “ጉልቤ” ሆነብኝ) ከተቀመጥኩበት ከመነሳቴ በፊት አንድ ነገር ተመኘሁ - ጦቢያ የ“ጉልበተኞች” ሳይሆን የነፃነት ወዳዶችና የዲሞክራቶች አገር እንድትሆንልኝ! (እኔ በምኞት አምናለኋ!)
እኔ የምላችሁ … አዲሱ ዓመት ከተፍ አለ አይደል! ለመሆኑ የአዲሱ ዓመት ምኞታችሁ ምንድነው? (እንደ ኢህአዴግ በትግል የምታምኑትን አይመለከትም!) እኔ ምን ተመኘሁ መሰላችሁ? የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽንን በ “ልማት አደናቃፊነት” ለማስፈረጅ! (በፓርላማም ባይሆን በማህበር!) እስቲ አስቡት … ዓመቱን ሙሉ የአገሪቱን ልማት ሲያደናቅፍ እኮ ነው የከረመው፡፡ አንዳንዴ በመንግስት ተቋቁሞ ፀረ-መንግስት አጀንዳ የሚያራምድ ተቋም ይመስለኛል (ኧረ ጀርባው ይጠና!) እንዴ የስንቱን ድርጅት ሥራ እንዳስተጓጐለ … ያው የምታውቁት ነው፡፡ ስንቱን የውጭ ኢንቬስተር ሃሳብ እንዳሰረዘም አስቡት፡፡ (ወደ ኩራዝ ዘመን የምትጓዝ አገር ላይ ማን ኢንቨስት ያደርጋል!)
በነገራችሁ ላይ ኢትዮ ቴሌኮምን በ “ፍቅር አደናቃፊነት” ለማስፈረጅ የተዘጋጁ ዜጐች መኖራቸውንም ሰምቻለሁ፡፡ በኔትዎርክ መጥፋት የፍቅረኞች ህይወት ተቃውሷላ! (ፍቅርና ትዳር የማፍረስ ድብቅ አጀንዳ ያራምዳል እንዴ?) ስንት ቢዝነሶች በኔትዎርክ ችግር እንደሚዘገዩም እያየነው ነው፡፡ በቅርቡ ደግሞ የሃይማኖት መዝሙሮችን ለሞባይል ጥሪ አገልግሎት መስጠቱን አቁሞ የኩኩ ሰብስቤን “ቻልኩበት ዘንድሮ ቻልኩበት የኑሮ አያያዙን እኔም አወቅሁበት” የሚል ዘፈን ተክቷል መባሉን ሰማሁ (“ፖለቲካዊ ውሳኔ” ይሆን?) አንዳንዶች ግን የቴሌኮም የአዲስ ዓመት ገፀበረከት ነው ሲሉ ፎትተዋል፡፡
እኔ ግን ሌላ ጥርጣሬ አለኝ፡፡ በኑሮ ውድነት የተማረረውን ዜጋ ለማፅናናት ወይም ምሬቱን ለማባባስ ታልሞ የተደረገ ይመስለኛል (ግምት እኮ ነው!) መጪው የኢትዮጵያ ፕሬዚዳንት ሊሆኑ ይችላሉ ተብለው ከተጠረጠሩ እንስቶች አንዷ የሆኑ ሴት ስለቴሌኮም ያሉትን ልንገራችሁ፡፡ “በሞባይሌ ሁሉ ስደውል ሴትየዋ … የደወለሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም ትለኛለች፡፡ አንድ ቀን ግን “ኧረ ደንበኛ አይደለም … ወንድሜ ነው” … አልኳት” አሉ፡፡(እሷጋ ሁሉም ደንበኛ ነው!)
በነገራችሁ ላይ በልማት አደናቃፊነት መፈረጅ ያለበት መብራት ሃይል ብቻ አይመስለኝም፡፡ ሌሎች የመንግስት ተቋማትም አሉ፡፡
ለምሳሌ ታክሲዎችን ወደ ቀጣና (ታፔላ) አሰራር የመለሰው መ/ቤት ተጠቃሽ ነው። (የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮን ማለቴ ነው!) እንዴ … ከዚያ በኋላ እኮ ነው ነዋሪዎች በደርግ ዘመን የቀረውን የትራንስፖርት ሰልፍ የጀመሩት! (እንደውም “ልማት አደናቃፊ” ብቻ አይበቃውም!) በአዲሱ ዓመት ከጨለማና ከታክሲ ወረፋ እንዲገላግለን ተመኘሁ! (ዕዳውን ለኢህአዴግ ጥያለሁ!)

Read 4252 times