በየዓመቱ በነሐሴ ወር የሚዘጋጀው የሸራተን የስዕል አውደ ርዕይ ሊቀርብ ነው፡፡ “Art of Ethiopia 2013” በሚል ርዕስ የሚቀርበው አውደ ርዕይ፤ በኢትዮጵያ ያሉ የጥበቡ ፈርጀ ብዙ ገፅታዎችን የሚያሳዩ 500 ያህል ሥዕሎች ይቀርቡበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ከነዚህ ስራዎች ከመቶ አስር እጅ በቅርፃ ቅርፅ ላይ ያተኩራል የተባለለት ትልቅ አውደ ርዕይ፤ በሚቀጥለው ዓርብ ነሐሴ 24 ቀን 2005 ዓ.ም ተከፍቶ እስከ ነሐሴ 27 በየእለቱ ከቀኑ 4 ሰዓት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት ለህዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡ በዝግጅቱ 450 ሰዓሊዎች ስራዎቻቸውን እንዲታይላቸው አቅርበው “የምርጦቹ ምርጥ” ለአውደርዕዩ መቅረቡንና ከነዚህም ሩቡ እጅ የሴት ሰዓሊያን ስራ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሸራተን አዲስ ላለፉት አምስት ዓመታት በየዓመቱ ታላቅ የስዕል አውደርእይ እያሳየ ይገኛል፡፡ አውደርእዩ በአዲስ አበባ የሚገኙ የስዕል ትምህርት ቤቶችን ለማጠናከር ያለመ ነው፡፡