Saturday, 03 August 2013 10:32

ወደፊት መሄዱ ይቀራል እንጂ ወደኋላማ አንመለስም!

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(6 votes)

የኔትዎርክ አለመኖር ከጉድ አወጣኝ”
ዕድሜና ጤንነት ያልበገረው የሥልጣን ፍቅር (የ89 ዓመቱ ሙጋቤ!)

የዚምቧቡዌው ፕሬዚዳንት የ89 ዓመቱ ሮበርት ሙጋቤ፤ ዛሬም ሥልጣንን የሙጥኝ ማለታቸው አይገርማችሁም? (ሥልጣን ሃሺሽ ሳይሆን አይቀርም!) እንዴ --- አገራቸው ከእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ነፃ ከወጣች በኋላ እኮ የሥልጣኑን መንበር ለማንም አላስነኩም። እናላችሁ--- ይኸው ለ33 ዓመት ከቤተመንግስት አልወጣም ብለው አሻፈረኝ ብለዋል። (የአገር ልጅ ቅኝ ግዛት ማለት እኮ ነው!) እድሜም ሆነ ጤና ከሥልጣን አያግደኝም ብለው የተፈጠሙት ሙጋቤ፤ ባለፈው ረቡዕ ለሰባተኛ ጊዜ ለፕሬዚዳንትነት መወዳደራቸውን ሰምተናል። (ሥልጣን የምሰጠው ሞቼ ነው ቆሜ በሚል እልህ!) ባለፈው መጋቢት ወር የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የሥልጣን ዘመን በሁለት ዙር የተገደበ ቢሆንም ህጉ ወደ ኋላ ተመልሶ ስለማይሰራ ሙጋቤን “አሁንስ በቃዎት” ለማለት አለመቻሉን ምንጮች ጠቁመዋል። እናም በዘንድሮው ምርጫ መወዳደር ብቻም ሳይሆን ምርጫውን እንዳሸነፉ ከፓርቲያቸው የወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ተፎካካሪው ፓርቲ “ሙቭመንት ፎር ዲሞክራቲክ ቼንጅ” በበኩሉ፤ ምርጫው መጭበርበሩንና ውጤቱ ፈፅሞ ተቀባይነት እንደሌለው አስታውቋል - “ትልቅ ቧልት ነው” በማለት። የምርጫ ታዛቢዎች በሰጡት አስተያየት ደግሞ አንድ ሚሊዮን የሚደርሱ ዚምባቡዌያውያን እንዳይመርጡ የሙጋቤ ፓርቲ ጫና ማድረጉን ገልፀዋል። “ድሉ የእኛ ነው” ለማለት የተጣደፈው የሙጋቤ ፓርቲ፤ “ምርጫው ነፃ ፤ፍትሃዊና ተዓማኒ ነበር” ብሏል። (የልቡን ሰርቷላ!) እኔ የምለው ግን---- የዚምባቡዌ ፓርቲዎች ሌላው ቢቀር የመተካካት ስትራተጂን እንኳን ከእኛ አይማሩም እንዴ? (ከኢህአዴግ ማለቴ ነው) በነገራችሁ ላይ --- 89 የመኢአድ ፅ/ቤቶች ራሳቸው በፃፉት ደብዳቤ ተዘግተዋል የሚል ነቀፌታ የሚሰነዘርባቸው ኢንጂነር ኃይሉ፤ በቅርቡ ከፕሬዚዳንትነት ሥልጣናቸው የወረዱት በመተካካት ስትራቴጂ ነው ወይስ ደክሟቸው? (ኸረ ይበቃቸዋል!)

አንድ ጎልማሳ ባለትዳር ነው አሉ። ምሽቱን ሲጠጣ ይቆይና ወደ ቤቱ እየሄደ ሳለ ምን እንዳሳሰበው አይታወቅም የድሮ ፍቅረኛው ድንገት ትዝ አለችው። (አብሾ ይኖርበት ይሆን?) ጎልማሳው ትንሽ ያስብና ሞባይሉን ከኪሱ ውስጥ መዥረጥ አድርጎ ያወጣል - ሊደውልላት (“አደጋ አለው” ማለት ይሄኔ ነው!) ቢሞክር ቢሞክር ግን እምቢ አለው። ኔትዎርክ የለም። ተስፋ ቆርጦ ወደ ቤቱ ያመራል - ወደ ትዳሩ። ጠዋት ስካር በርዶለት ከእንቅልፉ ሲነቃ የማታው ትዝ አለው። የደወለ መስሎት ለአፍታ መደንገጡ አልቀረም። በደንብ ሲያስታውስ ግን አልደወለም። ዕድሜ ለኢትዮ- ቴሌኮም - ኔትዎርክ አልነበረም። እፎይ ያለው ይሄን ጊዜ ነው። ያን ሰሞን ለጓደኞቹ ከዚህ ሌላ ወሬ አልነበረውም “እናንተ ጉድ ሆኜላችሁ ነበር---- ኔትዎርክ አለመኖሩ እኮ ነው ያተረፈኝ” እያለ የኢትዮ - ቴሌኮምን ውለታ ሲደሰኩር ሰነበተ። (ከዚያን ጊዜ በኋላ በኔትዎርክ ተማርሮ አያውቅም!) ወዳጆቼ --- አንዳንዴ የኔትዎርክ አለመኖር ከ“አደጋ” ሊያድናችሁ ይችላልና ዝም ብላችሁ አትማረሩ ለማለት ያህል ነው። (ብትማረሩም ለውጥ የለውማ!) በነገራችሁ ላይ ይሄ ለውሃና ለመብራት አይሰራም። ለምን መሰላችሁ? እስካሁን በውሃ ወይም በመብራት አለመኖር “ከጉድ ዳንኩኝ” ያለ አልሰማንማ!
እኔ የምላችሁ ---- የኦሮምያ ውሃና ኮንስትራክሽን ፅ/ቤት ሃላፊዎች በሙስና ተጠርጥረው መያዛቸውን ተከትሎ የጠፋችው ውሃ እንደቀልድ እኮ ሳምንት አለፋት (ምን ይሆን መላው?) እናንተ “የመንግስት ሌቦች” ጉድ አፈሉ አይደለም እንዴ? የሚገርመው እኮ ምን መሰላችሁ? አንድ መ/ቤት ውስጥ በሙስና የሚጠረጠሩ ግለሰቦች አሉ ከተባለ፤ ከዋናው ሃላፊ አንስቶ እስከሹፌሩ ድረስ ያልተነካካ ማግኘት አዳጋች እየሆነ ነው ተብሏል። አሁን እኮ ተጣርቶ እስኪነገረን ድረስ የምናምነው ሰው ሁሉ ልናጣ ነው (ሁሉም “የመንግስት ሌባ ነው” አልወጣኝም!) እውነቴን ነው የምላችሁ---- ዛሬ ማታ በኢቴቪ ስለ ኪራይ ሰብሳቢዎችና ህገወጦች ለጥናት ፅሁፍነት የሚበቃ ቶፕ ጉደኛ ዲስኩር ሲደሰኩር የሰማችሁት ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊ፤ ነገ ጠዋት በፀረ ሙስና ኮሚሽን የምርመራ ቡድን ቁጥጥር ሥር ውሎ ክው ያደርገናል። (ጠላታችሁ ክው ይበልና!)
በነገራችሁ ላይ አዲሱ የጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መንግስት በ“መንግስት ሌቦች” እና በ“ግል ሌቦች” ላይ እየወሰደ ያለው ቁርጠኛ እርምጃ ምስጋና ሊቸረው ይገባል። ራሳቸው ጠ/ሚኒስትሩም ቢሆኑ “ሙስናን የደፈሩ መሪ” ብንላቸው የሚበዛባቸው አይመስለኝም። እስቲ አስቡት--- በኢህአዴግ የሁለት አስርት ዓመታት የሥልጣን ዘመን፤ በዘንድሮ መጠን ሞሳኝ የመንግስት ባለሥልጣኖች ተይዘው ለፍርድ የቀረቡበት ጊዜ እኮ የለም። እኔ እንደውም አሁን አሁን እያሳሰበኝ የመጣው ምን መሰላችሁ? ሙሰኞችን እያደኑ መያዙ ራሱ የሙሉ ጊዜ ሥራ መሆኑ ነው። ወደፊት ግን ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ በአባላት ምልመላውም ሆነ በአሿሿሙ ላይ ልዩ ጥንቃቄ ማድረግ የሚገባው ይመስለኛል። (ሞሳኞች ከሰማይ አልወረዱማ!) እንዴ --- በሃላፊነት የተሰጣቸውን መ/ቤት ተባብረው የሚዘርፉ ሹማምንት እንዲህ ሲበዙ እኮ የፓርቲውንም ገፅታ ያበላሻሉ። በአፍሪካ “ተወዳዳሪ አይገኝለትም” የተባለ ፓርቲ፤ኪራይ ሰብሳቢነት በተጠናወታቸው የራሱ አባላት ሲሰናከል ማየት ያንገበግባል (አባል ሳይሆኑ መቆርቆር አይቻልም እንዴ!) እናላችሁ --- ኢህአዴግ ነፍሴ የአባላቱን ቁጥር ሰማይ አደርሳለሁ ብሎ በቅጡ ሳያበጥር መመልመሉ ቢቀርበት ነው የሚሻለው (ዳፋው ለእኛ ተረፈና! )
እኔ የምላችሁ ---- በአዲሱ የጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መንግስት ያየናቸውን ሌሎች አበረታች ለውጦች መግለፅ ተገቢ አይደለም እንዴ? (ጥፋት ስናይም እኮ አንምርም!) “የምን ለውጥ - ነው ያላችሁት?” እሺ አድምጡኝና (መደማመጥ እኮ ነው የጠፋው!) የምትሉትን በሉ። አንደኛው ለውጥ በፓርላማ የታየው አዲስ መነቃቃት ነው። (አቦይ ስብሃትና አትሌት ኃይሌ መስክረውለታል!) ሌላው ለውጥ በኢቴቪ ላይ የተስተዋለው ነው - ዘገባውን ሚዛናዊ ከማድረግና የተቃዋሚዎችን እንቅስቀሴ ሽፋን ከመስጠት አንፃር ቀላል የማይባል መሻሻል አሳይቷል። (ህዝባዊነቱን በቅጡ ማሳየት ቢቀረውም) እንደቀድሞው ጊዜ በ“ሚዲያ ዳሰሳ” ላይም የግል ሚዲያውን ጋዜጠኞች ማወያየትም ጀምሯል! (ወረት እንዳይሆን እንጂ!) በሶስተኛነት የሚጠቀሰው ለውጥ ደግሞ ለስምንት ዓመታት ታግዶ የቆየው ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብት መፈቀዱ ነው (ህገመንግስታዊ መብት መሆኑ ቢታወቅም!) ስለዚህ ወደ አመራሩ ከመጣ ወደ አንድ ዓመት ገደማ ሊያስቆጥር አንድ ወር ብቻ የቀረውን የጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መንግስትን፤ “በርታ ወደፊት እንጂ ወደ ኋላ አትመልከት” ልለው እፈልጋለሁ (ህገመንግስታዊ መብቴ መሰለኝ!)
እኔ የምላችሁ ግን---- የመንግስት ሠራተኞች በግድ ኢህአዴግ ሁኑ፤ “ያለዚያ የደሞዝ እድገትም ሆነ ሹመት አታገኙም” ይባላሉ እንዴ? እርግጠኛ ነኝ --- ኢህአዴግ ምን የዋህ ቢሆን ይሄን አያደርገውም ብዬ አምናለሁ ፤ ካደረገው ግን ራሱን ለውድቀት እያዘጋጀ ነው ማለት ነው። (ደርግ በግዳጅ አባል ያደርግ ነበር ልበል) በነገራችሁ ላይ --- ኢህአዴግም ሆነ ተቃዋሚዎች ፖለቲካዊ አመለካከትን ሰው ላይ በግድ ለመጫን ሲሞክሩ --- ህገመንግስቱን እየጣሱ መሆኑን ሊያስታውሱ ይገባል። የነፃነትና የመብት አፈናም ነው። የሰብዓዊ መብት ድፍጠጣ ልትሉትም ትችላላችሁ! (ወደፊት መሄዱ ይቀራል እንጂ ወደ ኋላማ አንመለስም!)

Read 3954 times