Saturday, 03 August 2013 10:16

ጉቦ እየተቀበለ የፈተና ውጤት የጨመረ መምህር በሙስና ተከሰሰ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(5 votes)

ከ10 ዓመት በላይ እስር ሊያስቀጣ ይችላል 

በአየር ጤና ሁለተኛና መሰናዶ ት/ቤት ለ11 የዘጠነኛ ክፍል ተማሪዎች ጉቦ እየተቀበለ የፈተና ውጤት በመጨመር ከክፍል ወደ ክፍል እንዲዘዋወሩ አድርጓል የተባለው የባዮሎጂ መምህሩ አቶ ፈቃዱ ቢጀጋ በሙስና ወንጀል ክስ ተመሠረተበት፡፡
የፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህግ፣ የክስ ዝርዝር እንደሚያስረዳው፤ በመምህሩ ላይ ሁለት ክሶች የቀረቡበት ሲሆን በአንደኛው ክስ በ2005 የትምህርት አመት የ9ኛC ክፍል የክፍል ሃላፊ ሆኖ የተመደበበትን ስልጣን ያለአግባብ በመጠቀም፣ ከሰኔ 28 እስከ ሐምሌ 7 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ ለአስራ አንድ ተማሪዎች ዘጠኝ የሚደርሱ የትምህርት አይነቶች ላይ ለእያንዳንዱ የትምህርት አይነት መምህራን ሳያውቁ እስከ 91 ነጥብ በመጨመር ከክፍል ወደ ክፍል ማለፍ የማይገባቸው ተማሪዎች እንዲያልፉ ለማድረግ በማሰብ፣ ከስልጣኑ በላይ በሆነ አሠራር በመንግስት የትምህርት ጥራት ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረሱ፣ በፈፀመው በስልጣን ያለአግባብ መጠቀም የሙስና ወንጀል እንደተከሰሰ ተመልክቷል፡፡
በሁለተኛነት በቀረበው ክስ ላይም ሃላፊነቱን ያለአግባብ በመጠቀም የግል ተበዳይ የሆነ አንድ ተማሪ ካርድ እንዲሰጠው ሲጠይቀው “ውጤትህ የተሟላ አይደለም፤ የተሟላ ውጤትህን የያዘ ካርድህን እንድሰጥህ ከፈለግህ ገንዘብ አምጣ” በማለት ጠይቆ፣ ሐምሌ 8 ቀን 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 3 ሰአት ሲሆን በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4፣ አንድ ግሮሰሪ ውስጥ ከግል ተበዳይ 200 ብር ተቀብሎ “ካርድህን እልክልሃለሁ፤ ገንዘብ ግን ስለሚያንስ ትጨምራለህ” በማለት በነጋታው ከምሽቱ 12 ሰዓት ሲሆን ተጨማሪ 150 ብር ከዚሁ ተበዳይ ሲቀበል እጅ ከፍንጅ በመያዙ በሙስና ጉቦ በመቀበል ወንጀል ተከሷል፡፡
ክሱ እንደደረሰው ለፍ/ቤቱ ያረጋገጠው ተከሳሽም፣ በችሎቱ በተገኙና ሊረዱት በፈለጉ ጠበቆች አማካይነት የተከሰሰበት የህግ አንቀጽ ዋስትና የማያስከለክል በመሆኑ፣ “ፍ/ቤቱ ጉዳዬን በዋስ ሆኜ እንድከታተል ይፍቀድልኝ” ሲል የጠየቀ ሲሆን አቃቤ ህግም በዋስትና ጥያቄው ላይ ተቃውሞ እንደሌለው አመልክቷል፡፡
ይሁን እንጂ ተከሳሹ ከ10 አመት በላይ በሚያስቀጣ ወንጀል የተከሰሰ በመሆኑ የዋስትና ጥያቄውን ባለመቀበል፣ መዝገቡን ለነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

Read 33528 times