Saturday, 03 August 2013 10:00

በጎርፍ የተወሰዱት እናት አስከሬን አልተገኘም

Written by  ሰላም ገረመው
Rate this item
(1 Vote)

ዘንድሮ ብቻ 41 ሰዎች በጎርፍ ተወስደው ሞተዋል
በልደታ ቤተክርስቲያን አካባቢ በሚገኝ ወንዝ ውስጥ ገብተው በጐርፍ የተወሰዱት ሴት አስከሬን እስካሁን አልተገኘም፡፡ የልደታ ቤ/ክ አካባቢ ነዋሪ የሆኑት የ69 ዓመቷ አዛውንት ፀዳለ አለባቸው፤ ልደታ ቤተክርስቲያን ቆይተው ሲመለሱ የጫማቸውን ጭቃ ለማጠብ ወደ ወንዙ ሲጠጉ የረገጡት መሬት ተደርምሶ ወንዝ ውስጥ በመግባታቸው ደራሽ ጐርፉ ይዟቸው እንደሄደ የአይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ 

በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የእሳትና ድንገተኛ አደጋ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ በበኩላቸው፤ የወ/ሮ ፀዳለ አስከሬን ሊገኝ ያልቻለው ቤተሰብ በዕለቱ ባለማመልከቱ መሆኑን ገልፀው፣ ብዙ ጊዜ በጎርፍ የሚወሰዱ ሰዎች አስክሬን በሌላ አካባቢ ጎርፉ ሲተፋቸው እንደሚገኝና የወ/ሮ ፀዳለን አስክሬንም ለማግኘት ወንዙ የሚሄድበትን አቅጣጫ እየተከተሉ ፍለጋቸውን እያከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ጎርፉ ራቅ ያለ አካባቢ ወስዶ ከጣላቸው በኋላ ቶሎ መገኘት ካልቻሉ አስከሬኑ በአውሬ የመበላት እድል እንደሚገጥመው ገልፀው፤ አብዛኛውን ጊዜ ግን የሚጠፋ አስክሬን እንደማይኖር ተናግረዋል፡፡
ዘንድሮ በጎርፍ አደጋ ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች 41መሆናቸውን የገለፁት ባለሙያው፤ ባለፈው ዓመት 34 ሰዎች በጐርፍ ተወስደው መሞታቸውን ተናግረዋል፡፡

Read 21504 times