Saturday, 03 August 2013 10:09

አዋሽ ኢንተርናሽናል ባንክ 639 ሚ. ብር ማትረፉን አስታወቀ

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(1 Vote)

ተቀማጭ ገንዘቡ ወደ 3.5 ቢሊዮን ብር አደገ
ከአንድ ሚሊዮን በላይ ደንበኞች አፍርቷል
አዋሽ ኢንተርናሽናል ባንክ ዘንድሮ በባንኩ ታሪክ ከፍተኛ የተባለ የ639 ሚሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡ በውጭ ኦዲተሮች መረጋገጥ ይቀረዋል የተባለው የትርፍ መጠን ከአምናው ጋር ሲነፃፀር በ180.6 ሚሊዮን ብር ወይም በ18 በመቶ ብልጫ እንዳለው ተገልጿል፡፡
በ115 ቅርንጫፎቹ ከአንድ ሚሊዮን ለሚበልጡ ደንበኞቹ ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን የገለፀው ባንኩ፤ በዚህ አመት ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች 2.2 ቢሊዮን ብር ብድር መስጠቱንና እስከ አሁን የሰጠው ብድርም ከ7.7 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡
ዘንድሮ የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ ወደ 3.5 ቢሊዮን ያደገ ሲሆን፣ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ37 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘብም ባለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ 13.1 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ በዚህ ዓመት የባንኩ ጠቅላላ ገቢ ከብር 1.4 ቢሊዮን በላይ የደረሰ ሲሆን፣ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ28 በመቶ ወይም የ309 ሚሊዮን ብር ዕድገት ማስመዝገቡ ገልጿል፡፡
የባንኩ የተከፈለ ካፒታል ከ1.2ሚሊዮን ብር በላይ የደረሰ ሲሆን፣ አምና ከነበረው 912ሺህ ብር ጋር ሲነፃፀር የ27 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ባለ አክሲዮኖች በወሰኑት መሠረት በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት የተከፈለ ካፒታሉን ወደ 1.5 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ ታቅዷል፡፡
የባንኩን የቴክኖሎጂ አቅም በማሳደግ ረገድ ማይሲስ ከተባለ የእንግሊዝ ድርጅት ጋር የ3.5 ሚሊዮን ዶላር የቴክኖሎጂ ማስፋፊያ (ኮር ባንኪንግ) ሥራዎች በማከናወን ላይ ሲሆን፣ ከአይቢ ኤም ድርጅት ጋር የ2.5 ሚሊዮን ዶላር የሶፍትዌር፣ የሃርድዌርና ተዛማጅ ግዢዎችና ሥልጠናዎች ስምምነት ላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡
ዘመናዊ የካርድ ቴክኖሎጂን በተመለከተ፣ አዋሽ ኢንተርናሽናል ባንክ፣ ንብ ኢንተርናሽናል ባንክና ሕብረት ባንክ በጋራ ባቋቋሙት ፕሪይመር ስዊች ሶሉሽን አማካይነት “አዋሽ ካርድ” ያዘጋጀ ሲሆን በዚህ ካርድ በሦስቱም ባንኮች ባሉ የክፍያ ተርሚናሎች (ኤቲኤም) በመጠቀም ደንበኞች ጊዜአቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ ማስቻሉን አስታውቋል፡፡

Read 21695 times