Saturday, 27 July 2013 14:06

ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች ችግራቸው - “የልማድ እስረኞች” መሆናቸው!

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(13 votes)

*ዶ/ር ነጋሶ ለአትሌት ኃይሌ ሃሳብ አቀረቡ -“ አንድነት ፓርቲ ይሻልሃል!”

ፖለቲካዊ ወጋችንን የምንጀምረው ሰሞኑን የተፈጠረች አንድ “ህዝባዊ ቀልድ” በመጋራት ነው፡፡ ምን ሆነ መሰላችሁ? ባለፈው ሳምንት የኦሮምያ ክልል ውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ሃላፊዎች በሙስና ተጠርጥረው መያዛቸውን ተከትሎ በአካባቢው ውሃ ጠፍቶ ነበር አሉ፡፡ ህዝቡ ምንም ምርጫ ሲያጣ ነገሩን ለበላይ ሃላፊዎች ለማመልከት ተገደደ (ካለመናገር ደጃዝማችነት ይቀራል አሉ!) የተሰጠው ምላሽ ግን ከእስከዛሬው ለየት ያለ ነው፡፡ “ውሃ የጠፋው በኤግዚቢትነት ተይዞ ነው” ተባለ፡፡ ይሄን እንደሰማው ምን ትዝ እንዳለኝ ታውቃላችሁ? በሙስና ተጠርጥረው የተያዙት ዘጠኙ የኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ሃላፊዎችና ሲጠፋብን የነበረው መብራት! ከዚያማ የሞኝ ነገር በዚያው ቀጠልኩ፡፡ የዚያን ሰሞን የተከሰተውን የወርቅ መወደድና የዶላር መጥፋት ከታሰሩ የባንክ ሃላፊዎች ጋር አገናኝቼው ቁጭ አልኩ፡፡ (እቺን እቺንማ ማን ብሎኝ!) ከ97 ምርጫ ቀውስ ጋር ተያይዞ የቅንጅት አመራሮች ከታሰሩ በኋላ የፖለቲካ ድርቀት ተከስቶ እንደነበረ ትዝ አይላችሁም ? እኛ ግን በጣም ትዝ ይለናል (በእንጀራችም መጥቶብን ነበራ!) እንዴ ጋዜጣ የሚገዛ እኮ አልነበረም (ፖለቲካ ጠፍቶ ነበራ!) እና ያኔ ፖለቲካው የት ገብቶ ነበር ብዬ አሰብኩ፡፡ ወዲያው መልሱ ብልጭ አለልኝ “ፖሊስ በኤግዚቢትነት ይዞት ነበር!” (ከፖሊስ ማረጋገጫ ባይገኝም) በኋላ ሲፈቱ እኮ በኤግዚቢትነት የተያዘውም ተፈታ፡፡ እኛም እንጀራ መብላት ጀመርን - የአንባቢን የፖለቲካ ጥማት ለማርካት እየሞከርን፡፡ (በኤግዚቢትነት የተያዘው ውሃ አልተለቀቀ ይሆን?)

እስቲ አሁን ደግሞ ወደ ቁም ነገር እንግባ - ፖለቲካዊ ቁም ነገር፡፡ (አይዟችሁ በፈገግታ ታጅቦ ነው) መቼም ሰሞኑን ወዳጄ ሰጥቶኝ እያነበብኩት ያለ አንድ መፅሃፍ፣ ለዚህች አገር የፖለቲካና ፓርቲዎች ችግር መፍትሄ ካላመጣ ምን አለ በሉኝ፡፡ በቻርለስ ዱሂግ የተዘጋጀው መፅሃፍ The Power of Habit ይላል፡፡ መፅሃፉ እንደሚለው፤ በህይወታችን ብዙዎቹን ነገሮች የምንፈፅመው እያሰብን ይምሰለን እንጂ በልማድ ነው አንዴ ከነገሩ ጋር ከተዋወቅን በኋላ ማሰብ ሳያስፈልገን በደመነብስ እንፈፅመዋለን - ልማድ ትልቅ ኃይል አለው፡፡ (ልማድ ሲሰለጥን ተፈጥሮ ይሆናል እንዲሉ) በመፅሃፉ ታሪኩ የተዘገበ በመዘንጋት በሽታ የተጠቃ አንድ አባወራ ላይ በተካሄደው ጥናት፣ መኝታ ቤት ተቀምጦ ወጥቤቱ ወይም ባኞቤቱ በየት አቅጣጫ ነው ተብሎ ሲጠየቅ ፈፅሞ እንደማያስታውስ የተናገረ ሲሆን ለመብላት ሲፈልግ ግን ያለማንም ረዳት በቀጥታ ወጥቤት ገብቶ ፍሪጅ ከፍቶ የሚፈልገውን ያሰናድ ነበር፡፡ ባኞ ቤት መጠቀም ሲፈልግም እንዲሁ፡፡ እነዚህን ተግባራት በመደጋገም ብዛት ልማድ አድርጓቸዋል፤ ስለዚህ በቀላሉ ይፈፅማቸዋል፡፡
ለመሆኑ እንዴት ነው The Power of Habit ለፖለቲከኞቻችን ወይም ለፓርቲዎቻችን ችግር መፍትሄ የሚሆነው? እንዴት መሰላችሁ ---- አሁን ለምሳሌ ለምንድነው ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎች ፈፅሞ ተስማምተውና ተግባብተው የማያውቁት? አንዳቸው ሌላኛቸውን ተሳስተው እንኳን “ደግ ሰርተሃል” ብለው ሲደናነቁ ሰምተን አናውቅም፡፡ ግን ለምን? መልሱ ቀላል ነው - ልማድ ነዋ! ሁለቱም ወገኖች እርስ በርስ መወቃቀስ መነቃቀፍ መወጋገዝ እንጂ መደናነቅ መሞጋገስ መከባበር አለመዱም - ላለፉት 20 ዓመታት፡፡ የ20 ዓመታት ክፉ ሱስ ልትሉት ትችላላችሁ፡፡ ኢህአዴግ ልክ “ተቃዋሚዎች” የሚለውን ቃል ሲሰማ ከመቅፅበት -- ፀረ- ሰላም፣ ፀረ- ህገ መንግስት፣ ለልማት ያልቆሙ ኃይላት ወዘተ የሚሉ አፍራሽ ፍረጃዎች ከአንደበቱ ወይም ከብዕሩ ይፈስለታል (አያችሁልኝ የልማድን ኃይል!) ተቃዋሚዎችም “ኢህአዴግ” የሚባል ነገር ከሰሙ --- አምባገነን፣ እኔ ብቻ ላገር አሳቢ ባይ፣ የአገሪቱን ታሪክ ያዋረደ፣ አጨብጭቡልኝ ባይ ወዘተ---በማለት ዘለፋቸውን ያወርዱታል፡፡ ልማድ ከፍተኛ ኃይል እንዳለው የሚነግረን መፅሃፉ፤ ብልሃት ይሻል እንጂ ማስቀረት ወይም ማስወገድ የማይቻል ልማድ ወይም ሱስ የለም ይላል (መፅናኛችንም ይሄ ነው!) ግን አንዱን ልማድ ለማስወገድ ምትክ ይፈልጋል፤ እሱ ካልተተካለት ንቅንቅ አይልም - የድሮው ልማድ፡፡ ስለዚህ የአራችን ፖለቲካ ፓርቲዎች የከረመውን የጥላቻና የመናናቅ ልማድ (ሱስ ደረጃ ደርሷል) ከውስጣቸው ለማስወገድ ካሰቡ፤ እንደ ሲጋራ ወይም አልኮል ሱስ ምትኩን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡

አንዷ አጫሽ ከሲጋራ ሱስ የተገላገለችው በአካል እንቅስቃሴ በመተካት እንደሆነ The Power of Habit ይገልፃል፡፡ ፓርቲዎችም የድሮውን ልማድ በአዲስ ልማድ መተካት አለባቸው - በአዲስ የተሻለና ለአገርና ለህዝብ በሚጠቅም ልማድ፡፡ የእስከዛሬውማ አጥፊ ልማድ ነው - ያውም ጅምላ ጨራሽ፡፡ እናም የጥላቻና መናናቅ ልማድን በፍቅርና መከባበር ልማድ መተካት አለባቸው፡፡ ሂደቱ ፈታኝ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ለምን ቢሉ--- የሁለት አስርት ዓመታት ሱስ ነዋ! ግን ይቻላል ይለናል- መፅሃፉ፡፡
እኔ የምላችሁ --- አትሌት ኃይሌ ቀወጠው አይደል? እንዴ ፒፕሉን አንጫጫው እኮ! (በተለይ ፖለቲከኞቹን) አትሌት ፕሬዚዳንት መሆን አይችልም ሊባል ነው ወይስ? እንዴ--- ህገመንግስቱ እንደሚፈቅድለትማ እኔም እናንተም ፖለቲከኞቹም ---ሁላችንም እናውቃለን፡፡ ችግሩ ግን ሁሌ መች በህጉ መሰረት እንሄዳለን፡፡
(የአፈፃፀም ችግር አለብን ብለን የለ!) በህጉ መሰረት ብንሄድማ ---- የስልጣኔ ወጉ ነበር፡፡ በእኔ በኩል የኃይሌን ወደ ፖለቲካ ማተኮር በተመለከተ ባለፈው ሳምንት የምለውን ብያለሁ (የተቆርቋሪነቴን ያህል!) ዛሬ የተመለስኩበት የአቋም ለውጥ ስላደረግሁ እንዳይመስላችሁ፡፡
ይልቁንም በአትሌቱ ወደ ፖለቲካው መግባት ዙሪያ የተቃዋሚዎችን ግራ የተጋባ አስተያየት ለመቃኘት ያህል ነው (ግራ ያልተጋባም እኮ አለ!) አንዳንዱ ደግሞ ተስፋ አስቆራጭ ነው - “በኋላ ነግሬአለሁ፣ እጅህን ወደ ፖለቲካ ባትሰድ ነው የሚሻልህ፣ ጉድ ነው የምትሆነው” የሚል ዓይነት ነው፡፡
ደግነቱ ባለፈው እንዳልኳችሁ ሰውየው ጀግናው የዓለም አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ ነው፡፡ ሌላ ሰውማ ቢሆን ኖሮ ዝም ብዬ አላይም፡፡ (ጨለምተኛ አልወድማ!) “ማንም የሚለውን አትስማ፣ በተለይ የኢትዮጵያ ፖለቲከኞችን፣ ዝም ብለህ በእቅድህ መሰረት ግፋ” እለው ነበር፡፡ እስቲ የጦቢያ ፖለቲከኞች ስለአትሌቱ ወደ ፖለቲካ የመግባት ሃሳብ፣ ለአንድ ጋዜጣ የሰጡትን አስተያየት እንመልከት - ክፉውንም ደጉንም!
ኃይሌ ወደ ፖለቲካ መግባቱ መብቱ መሆኑን ያልካዱት ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ እንደ ስፖርቱ በፖለቲካውም የሚያንፀባርቅ አይመስለኝም ብለዋል (ማንፀባረቅ እፈልጋለሁ አለ እንዴ?) የመድረክ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፤ ለሃገሩ ብዙ የደከመ፣ ላቡን ያንጠፈጠፈ ሰው በመሆኑ ወደ ፖለቲካው መምጣቱ የሚደገፍ ነው ካሉ በኋላ ማስጠንቀቂያ ይሰጣሉ (ለራሱ ለኃይሌ ይመስለኛል!) በአገሪቱ የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል የለም፤አገሪቱ የጡንቸኞች አገር ናት፤ የአገሪቱ ፖለቲካ ያልሰከነ ፤ሊገመት የማይችል ነው፤ የጎበዝ አለቃ ሁሉ ፖለቲከኛ ነኝ የሚልበት አገር ነው፤ ስለዚህ ሻለቃ ኃይሌም ገብቶ ይሞክረው” አሁን ይሄን ምን ትሉታላችሁ? ምርቃት ወይስ እርግማን? ማበረታታት ወይስ ተስፋ ማስቆረጥ? አንድ ጥያቄ አለኝ - ለፕሮፌሰሩ፡፡

(ወይም ለጦቢያ ፖለቲከኞች ሁሉ) ለፖለቲካው እንዲህ መሆን ተጠያቂው ማነው? ለመወቃቀስ እኮ አይደለም---- ችግሩ ያለው የት እንደሆነ ለማወቅ ያህል ነው፡፡ ችግሩን በትክክል ማወቅ የመፍትሄውን ግማሽ የማግኘት ያህል ነው ይባል የለ! ለጊዜው ወደ ፖለቲከኞቹ አስተያየት እንመለስ፡፡ የአንድነት ሊ/መንበርና የቀድሞው የፓርላማ የግል ተወዳዳሪ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንዲህ ብለዋል፡፡“ለግል ተወዳዳሪ የሚኖረው መብት እጅግ በጣም የተመጠነ ከመሆኑም በላይ የሚያመጣው ለውጥ የለም ” ዶ/ር ነጋሶ ሲቀጥሉም “ለኃይሌ ጥሩ አማራጭ እራሱን በፓርቲ አደረጃጀት ውስጥ ለማስገባት ቢሞክር ነው” ሲሉ ምክር ለግሰዋል፡፡ ምክር በመለገስ ብቻ ግን አያበቁም - ዶ/ር ነጋሶ፡፡ የትኛውን ፓርቲ ቢቀላቀል እንደሚበጀውም ሃሳብ ያቀርባሉ፡፡“ ኃይሌ በአሁኑ ወቅት ባለሃብት ሆኗል ከዚህ አኳያ የካፒታሊስት ርዕዮተ ዓለም አቀንቃኝ ይመስለኛል ለዚህ ደግሞ አመቺው የሊብራል ዲሞክራሲ አስተሳሰብ ነው፤ ስለዚህ ለአትሌቱ ጥሩ ፓርቲ ሊሆን የሚችለው እንደ አንድነት ያሉ ፓርቲዎች ነው” ያሉት ዶ/ር ነጋሶ፤ እሳቸው ኃይሌን ቢሆኑ የመጀመርያ ምርጫቸው አንድነት ፓርቲ እንደሚሆን ገልፀዋል፡፡
እናንተ ---- ለካ ዶ/ር ነጋሶ የዋዛ አይደሉም፡፡ አትሌት ኃይሌን በምን ዓይነት ብልሃት ወደ ፓርቲያቸው እንደጠሩት አያችሁልኝ? (አድናቂያቸው ነኝ!) ሁሉም ግን እንደ ዶ/ር ነጋሶ ብልህ ከመሰሉን ተሳስተናል፡፡ አንዳንድ ፖለቲከኞች ደሞ አሉ - እንደ ሰካራም ከተገኘው ጋር ሁሉ የሚጋጩ (ፖለቲካ ላይ ስካር ተጨምሮ!) የኃይሌን ነገር በቀጣዩ ወግ እንቋጨውና ወደ ሌላ አጀንዳ እንሂድ፡፡
አንድ ወጣት ሚኒባስ ታክሲ ውስጥ “ኃይሌ ገ/ሥላሴ ወደ ፖለቲካው ሊያተኩር ነው” የሚለውን ወሬ ጮክ ብሎ ለጓደኞቹ ያወራል፡፡ ከጓደኞቹ መካከል ይሄንኑ ጨዋታ ከጎኑ ለተቀመጡ አዛውንት ሊያጋራ የፈለገ ወጣት ወደሳቸው ዞር ብሎ--
“ይሄን ታሪክ ሰሙ አባባ?”
“የትኛውን?”
“ኃይሌ ገ/ሥላሴ ወደ ፖለቲካ ሊያተኩር ነው የሚለውን”
አዛውንቱም “ምን ነካው እሱ ደግሞ--- ከእውነት ወደ ውሸት ይሄዳል?” (ተቆጭተው!)

Read 3535 times