Print this page
Saturday, 20 July 2013 10:31

አትሌት ኃይሌ በፖለቲካ ፍቅር ተማርኳል! (አንድዬ ይሁነው)

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(39 votes)

እንኳንም ኦክስጂን በኤሌክትሪክ የሚሰራ አልሆነ --- (አበሻ አልቆለት ነበር!)
የመብራት መቆራረጥ በክረምት ተሳበበ (climate change አይሻልም ?)

ባለፈው ሳምንት አርብ ምሳ ሰዓት ላይ ነው፡፡ ቁጭ ብዬ የኢቴቪን ዜና እየኮመኮምኩ ነበር፡፡ ዓይኔ ቲቪው ላይ ተተክሎ ቀልቤ ግን በሌላ የግሌ ሃሳብ ተወስዶ ኖሮ ድንገት ወደ ጆሮዬ ዘሎ የገባው ትኩስ የሙስና ወሬ ቲቪውን በሙሉ ልብ እንድከታተል አነቃኝ፡፡ “የኢትዮጵያ መብራት ኃይል ኮርፖሬሽን ዘጠኝ ሃላፊዎች በ450ሚ. ብር ሙስና ተጠርጥረው ተያዙ” ይላል የኢቴቪው ዜና፡፡ ወዲያው ምን አልኩ መሰላችሁ? “ሙስና በየተራ!” ይሄን ያልኩት ግን ለሰው አይደለም ፤ ለራሴ ነው (አጠገቤ ማንም አልነበረማ !) እኔ የምለው ግን--- ይሄ እየተባባሰ የመጣው የመብራት ብልጭ ድርግም (የገና መብራት መሰለ እኮ!) የሙስናው ውጤት ይሆን እንዴ? መሠረተ ቢስ አሉባልታ የሚባለው ዓይነት እንዳይመስላችሁ፡፡ የሰማሁትን ሰምቼ እኮ ነው፡፡ የኮርፖሬሽኑ ሃላፊዎች ከተጠረጠሩባቸው ወንጀሎች አንዱ ---- አዲስ ትራንስፎርመሮች እንዲገዙ ቢታቀድም ትራንስፎርመሮቹ ተገዝተው ሲመጡ “አሮጌ ሆነው ተገኙ” ተብሏል፡፡ እንደኔ የዋህ ከሆናችሁ “ትራንስፎርመሩ የተገዛው ከህንድ ስለሆነ በአስማት አጭበርብረዋቸው ይሆን እንዴ?” ልትሉ ትችላላችሁ፡፡ ግን እድሜ ለፀረ- ሙስና ኮሚሽን! ነገርየው ምንም አስማት እንደሌለበት ታውቋል፡፡ (ሙስና ራሱ እኮ የለየለት አስማት ነው!) 

አይገርማችሁም ግን ---- ከፊሉ አባይን ለመገደብ መከራውን ሲበላ፣ ከፊሉ “ሆዱን ለመገደብ” ይሯሯጣል፡፡ ይሄ ባለፈው ጊዜ ኢህአዴግንና ተቃዋሚዎችን “ሲያባላቸው” የነበረው ኮንሰንሰስ (ብሄራዊ መግባባት) የሚሉት ነገር እንደገና መመርመር ያለበት መሰለኝ፡፡ ወይም የቃሉ ትርጉም በይፋ ይቀየር፡፡ (በቃሉ ላይም ኮንሰንሰስ ያስፈልጋል !) እውነቴን እኮ ነው---- እንኳንስ ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች ቀርቶ ራሳቸው ኢህአዴጎች መች ኮንሰንሰስ ላይ ደረሱ? እንዴ---- አንዱ እያለመ ሌላው እያወደመ “ብሔራዊ መግባባት” አለ ይባላል እንዴ? ከፊሉ ኢህአዴግ ልማታዊ፣ ከፊሉ የልማታዊነትን ካባ የደረበ ኪራይ ሰብሳቢ፣ የቀረው ደግሞ ዓይኑን በጨው የታጠበ ኪራይ ሰብሳቢ በሆነበት አገር ምን ዓይነት “ኮንሰንሰስ” ነው አለ የሚባለው? እንግዲህ ራሱ ኢህአዴግ የሾማቸው የራሱ አባላት ናቸው የሙስና አረንቋ ውስጥ ገብተው እየዳከሩ ያሉት? ይቅርታ አድርጉልኝና --- እንደውም እኮ “ኮንሰንሰስ” የተፈጠረ የሚመስለው በሌላ ላይ ሳይሆን በሙስና ላይ ነው፡፡ (ሁሉም ተዘፈቀበት እኮ!)
እኔ የምለው --- ለመሆኑ የመብራት ነገር እንዴት እያደረጋችሁ ነው? ሰሞኑን ለኢቴቪ ምሬታቸውን የገለፁ የመዲናዋ ነዋሪዎች፤ የመብራት መቋረጥ በሥራቸው ላይ ትልቅ እንቅፋት እንደሆነባቸው ተናግረዋል፡፡

(ፀረ-ልማት ማለት ይሄው አይደል!) አንድ ወይዘሮ እንደውም ሥራ ብቻ ሳይሆን እህልም ከልክሎናል ብለዋል - አብስለው መብላት እንኳን መቸገራቸውን በመጥቀስ፡፡ ወይዘሮዋ አክለውም ሊጋግሩት ያዘጋጁት ሊጥ በመብራት መጥፋት ሳቢያ፣ እየተበላሸ ለመድፋት መገደዳቸውን በምሬት ተናግረዋል፡፡ ሌላዋ ወይዘሮ ደግሞ መብራት ከጠፋ በኋላ ድንገት የሚለቀቀው ከፍተኛ ኃይል ንብረቶቻቸውን እያቃጠለባቸው መሆኑን ገልፀው “እቃ እቃ እየተጫወቱ ነው” ሲሉ መብራት ኃይልን ወቅሰዋል፡፡ (አቃጥሎ ቢከፍል ደሞ የአባት ነው!) ምን ይሄ ብቻ--- የመብራት ኃይል ጦስ በቴሌኮምና በውሃና ፍሳሽ ሳይወሰን ለኢቴቪ መትረፉን ሰሞኑን ራሱ ኢቴቪ ዘግቧል፡፡ በወሎና አካባቢዋ ፣ ነዋሪዎች የሬዲዮና ቴሌቪዥን ሥርጭት እንደተቋረጠባቸው የገለፁ ሲሆን የመቋረጡ መንስኤም የመብራት መቋረጥ መሆኑ ተጠቁሟል (ሬዲዮም አላሰማ፣ ቴሌቪዥንም አላሳይም እኮ ነው!)
እየተባባሰ መጥቷል ስለተባለው የመብራት መቆራረጥ ችግር የተጠየቁት የኮርፖሬሽኑ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ፣ ከወትሮው የተለየ አዲስ ሰበብ ፈጥረዋል (በፈጠራ ክህሎታቸው ተደምሜአለሁ!) አዲሱ ሰበብ ምን መሰላችሁ? የክረምቱ የአየር ንብረት ነው! (እንኳንም climate change ነው አላሉ) ሃላፊው እንደሚሉት፣ ነፋስ የቀላቀለ ሃይለኛ ዝናብ የኃይል መቋረጥ እያስከተለ ነው፡፡ ምን እንደጠረጠርኩ ታውቃላችሁ? የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው፣ በበጋ ወቅት አገር ውስጥ የነበሩ አልመሰለኝም (“በዚያ በበጋ በዚያ በክረምት--እጮኛ ጠፍቶ በፍለጋ--” የሚለው የልጅነት መዝሙር ትዝ አላችሁ?) እዚህ ቢኖሩማ ---- ዓመቱን ሙሉ ክረምት ከበጋ ሳይል በመብራት መጥፋት ምን ያህል መከራችንን እንደበላን ያውቁልን ነበር፡፡ (መግለጫ ከመስጠታቸው በፊት መረጃ ቢጠይቁ ሸጋ ነበር!) በእርግጥ ለኃይል መቆራረጡ ሌሎችንም ምክንያቶች ጠቅሰዋል - የኃይል ማሰራጫና ማከፋፈያ የጥራት ችግሮችን፡፡ (9 የኮርፖሬሽኑ ሃላፊዎች በሙስና መጠርጠራቸውን ያዙልኝ!) እኔ የምለው ግን----አንድ ነገር ከአቅም በላይ ሲሆን “አልቻልኩም--- አቅቶኛል!” ማለት ነውር ሆነ እንዴ? (ቢሆን ነው እንጂ!) ያለዚያማ የኮርፖሬሽኑ ዋና ዋና ኃላፊዎች፣ እስካሁን ለሚችል አስረክበው ወደሚችሉት ሥራ ይገቡ ነበር፡፡ (ኦክስጂን በኤሌክትሪክ የሚሰራ ቢሆን ኖሮ አበሻ በአየር እጦት አልቆ ነበር!)
ሰሞኑን ሰምቼው በአግራሞት የሞላኝ ዜና ምን ይላል መሰላችሁ? “በመንግስትና በፓርቲው (ኢህአዴግ ለማለት ነው) መካከል ጥብቅ ትስስር ለመፍጠር ታቅዷል” እንዴ--- ኢህአዴግና መንግስት ከዚህ በላይ ምን ዓይነት ጥብቅ ትስስር ሊፈጥሩ ነው? “ኢህአዴግ ማለት መንግስት፣ መንግስትም ማለት እኮ ኢህአዴግ ነው” እንግዲህ አዲሱን ዓይነት ትስስር ደግሞ እድሜና ጤና ይስጠንና አብረን እናየዋለን፡፡ ሌላም አስገራሚ ዜና ሰምቼአለሁ - በዚሁ ሳምንት፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰጠው መግለጫ መሰረት፣ የፀረ- ሽብር ህጉን በሰላማዊ ትግል ለማሰረዝ የአንድ ሚሊዮን ሰዎችን ፊርማ የማሰባሰብ ዘመቻ መጀመሩን በይፋ የገለፀው ፓርቲው፤ ሰሞኑን በዚሁ እንቅስቃሴ ላይ የነበሩ 42 አባላቱ ፈቃድ የላችሁም በሚል ተይዘው ከታሰሩ በኋላ በዋስ መለቀቃቸውን በመጠቆም “ለተፈፀመብን ህገወጥ ተግባር የሚመለከተውን አካል እንከሳለን” ብሏል፡፡ (የህግ የበላይነት የሚከበርባት አገር ስለሆነች መብቱ ነው!) አንድነት ፓርቲ የተፈፀመብን ህገወጥ ተግባር ነው ይበል እንጂ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ፤ “ከቤት ውጭ የሚደረግ ማንኛውም ቅስቀሳ ፈቃድ ያስፈልገዋል፤ ካለፈቃድ የሚደረግ እንቅስቃሴ ህገወጥ ነው” ብሏል፡፡
እኔ የምለው--- ፓርቲው ህጋዊ አይደለም እንዴ? (ለጠቅላላ እውቀት ነው!) ለማንኛውም ግን ህገወጥ ነው የተባለው የእንቅስቃሴ ዓይነት በግልፅ ቢታወቅ ጥሩ ይመስለኛል (በእውቀት እጥረት መታሰር ደስ አይልማ !) አሁን ለምሳሌ ሩጫም እንቅስቃሴ ነው (በታላቁ ሩጫ የታሰሩ እንደነበሩ ልብ ይሏል) ወደ ት/ቤት መሄድም እንቅስቃሴ ነው፣ የሃይማኖት ስብከትም እንቅስቃሴ ነው፣ ራሱ ህይወትም እኮ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ለመኖርም ፈቃድ አውጡ እንዳይባልና “ወይ እቺ አገር!” እንዳንል፡፡

ከስንት ዓመት ይፋ ያልሆነ እገዳ በኋላ በቅርቡ የተፈቀደው የተቃውሞ ሰልፍ የማድረግ ህገመንግስታዊ መብት ይሄ መንግስት ልብ እየገዛ ነው ብለን አመስግነን ስናበቃ፣ ከአንድነት ፓርቲ “አባላቴ ታሰሩብኝ” የሚል ስሞታ መስማት “ምስጋናዬን መልስልኝ” ያሰኛል፡፡ (የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ዳያስፖራዎችን ሲያነጋግሩ፣ “ቢሮክራሲው ቢያስቸግራችሁም ሌላ አማራጭ አገር ስለሌላችሁ አኩርፋችሁ መሄድ አትችሉም፤እዚሁ መታገል እንጂ” ያሉት አፅናናኝ!)
በዚሁ ሳምንት የሰማሁት ሌላ ዜና ደግሞ ምን መሰላችሁ? ጀግናው አትሌታችን ኃይሌ ገ/ሥላሴ ፕሬዚዳንት የመሆን ፍላጎት እንዳለው መግለፁ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ጠ/ሚኒስትር የመሆን ፍላጎት እንዳለው መናገሩ ትዝ ይለኛል፡፡ ያኔ የተፈጠረች አንድ ቀልድ ላውጋችሁ፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ (ነፍሳቸውን ይማረውና) “ኃይሌ ጠ/ሚኒስትር መሆን እፈልጋለሁ አለ” ተብሎ ይነገራቸዋል፡፡ እሳቸው ምን ቢሉ ጥሩ ነው? “ አይ ኃይሌ! ፖለቲካ እንደ ሩጫ በትራክ ላይ የሚሮጥ መሰለው --- በእሾህ ምንጣፍ ላይ እኮ ነው” (ኮፒራይቱ የህዝብ ነው!) ጠ/ሚኒስትሩ እውነት ብለዋል፡፡ ግን እኮ ኃይሌም ቢሆን በፅናቱ አይታማም፡፡ (“ኢንዱራንስ” የሚል ፊልም እኮ ያለነገር አልተሰራለትም!)
ደግነቱ እሱም ሃሳቡን ቀየረ --- ጠ/ሚኒስትር የመሆኑን ነገር እርግፍ አድርጎ በመተው ሩጫው ላይ ተጋና ዓለምን አጃኢብ ያሰኘ አያሌ ስኬቶችን ተቀዳጀ፡፡ በቢዝነስ መስኩም ዓይናችን እያየ በተለያዩ ዘርፎች ተሰማርቶ የስኬት ማማ ላይ ጉብ አለ፡፡ ከዚህ ሁሉ በኋላ ነው (ሩጫ ሰለቸው እንዴ?) ሰሞኑን ደግሞ የኢትዮጵያ ርዕሰ ብሔር የመሆን ፍላጎት አለኝ ያለው (በፖለቲካ ፍቅር ተማረከ እንዴ?)
በነገራችሁ ላይ ኃይሌ ፕሬዚዳንት ለመሆን መፈለጉን የቁም ቅዠት ወይም ቀቢፀ ተስፋ ነው የሚል ድፍረት የለኝም፡፡ ለምን መሰላችሁ? ሰውየው ኃይሌ እኮ ነው! ከፈለገ ያደርገዋል፡፡ እስካሁን ያከናወናቸው ተግባራት እኮ የአገር ፕሬዚዳንት ከመሆን የሚልቁ ተግባራት ናቸው፡፡ እሱ ደግሞ አንዴ ከተናገረና ካለመ ወደ ኋላ እንደማይል እኛ ብቻ ሳንሆን ዓለምም ያውቀዋል፡፡

እናላችሁ --- እኔን ያሳሰበኝ “ኃይሌና ፖለቲካ ይስማማሉ ወይ?” የሚለው ነው - የጦቢያን ፖለቲካ ታውቁት የለ! (ያለእዳው ዘመቻ እንዳይሆን ሰጋሁ!) ለዚህም ነው “ የዓለማችን የሩጫ ንጉስ ምን ሲል ፖለቲካን አሰበው?” ብዬ የተጨነቅሁ የተጠበብኩለት፡፡ ከጭንቀቴም ብዛት ለአንድ ወዳጄ አወያየሁት (እኔም እኮ ያለዕዳው ዘመቻ ሆንኩላችሁ) ወዳጄም እንዲህ አለኝ “እሱ እኮ ስማርት ነው ! ፕሬዚዳንት መሆን የፈለገው ከፖለቲካ ለመራቅ አስቦ ነው” ጨርሶ አልገባኝም ፡፡ አሁን ይሄ ምን ይሉት ንግግር ነው አልኩ - በሆዴ፡፡ ወዳጄ ማብራሪያውን ቀጠለበት “አየህ -- በኢህአዴግ አገዛዝ ፕሬዚዳንት መሆን እኮ ነፃነትህን ማወጅ ነው ---ይሄ ሥልጣን በምንም መንገድ ከሃይማኖትም ሆነ ከፖለቲካ አያነካካህም-- ቢበዛ መስከረም ላይ ለፓርላማ የመክፈቻ ንግግር ታደርጋለህ -- የድሮዎቹ ነገስታት ባሳነፁት ውብ ቤተመንግስት ውስጥ ደግሞ ከዓለም ዙርያ የሚመጡ እንግዶችን እየተቀበልክ ታነጋግራለህ -- አልፎ አልፎ የመሰረት ድንጋይ ለማስቀመጥ ትጋበዝ ይሆናል --በተረፈ ግን የራስህ ሆቢ ባይኖርህ እንኳን ከመፃህፍትም ላይ ቢሆን ፈልገህ እዚያ ላይ ማተኮር ነው” አለኝ ኮስተር ብሎ፡፡ ለእኔ ይሻለኝ የነበረው ቢስቅ ነበር፡፡ “ትቀልዳለህ እንዴ” ብዬ እንዳልጠይቀው መንገዱን ዘጋብኝ፡፡
አንዳንድ ሰዎች ግን ሲያሙት ሰምቻለሁ “ፕሬዚዳንትነቱን የፈለገው የጡረታ ዘመኑ መደበርያ ሊያደርገው ነው” በማለት፡፡ ይሄ እንኳን የማይመስል ነገር ነው፡፡ (ሰው እንዴት አገር የመምራት ትልቅ ሃላፊነትን ለመደበርያነት ያስበዋል?)

Read 6746 times