Saturday, 20 July 2013 09:49

የህብር ስኳር ባለአክሲዮኖች ንግድ ሚኒስቴር ጣልቃ እንዲገባ ጠየቁ

Written by  ሰላም ገረመው
Rate this item
(2 votes)

በአክሲዮን ሽያጭ ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ አቅዶ በአምስት አመታት ከ80 ሚ.ብር በላይ ለማግኘት ያልቻለው የህብር ስኳር አክሲዮን ማህበር፤ የባለአክሲዮኖች እልባት ያጣ ውዝግብ ተባብሶ የቀጠለ ሲሆን፤ በርካታ ባለአክሲዮኖች ለንግድ ሚኒስቴር በድጋሚ አቤቱታ አቀረቡ፡፡ ከጠቅላላው የአክሲዮን ሽያጭ 8 በመቶ ድርሻ ያላቸው ባለአክሲዮኖች በድጋሚ ባቀረቡት አቤቱታ፤ የንግድ ሚኒስቴር ጣልቃ እንዲገባ የጠየቁ ሲሆን፤ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጣልቃ ገብቶ ምርመራ ማካሄድ የሚችለው ቢያንስ አስር በመቶ ድርሻ የያዙ አባላት አቤቱታ ሲያቀርቡ ነው ተብሏል፡፡

አክሲዮን የገዛነው የምስረታ ሂደቱን የሚመሩ የቦርድ ሃላፊዎች በውሸት ማስታወቂያ ስላታለሉን ነው በማለት በፍርድ ቤት ክስ የመሰረቱ አባላት፤ የተሰበሰበው ገንዘብ በዝግ አካውንት መቀመጥ ሲገባው ለብድር አገልግሎት ውሏል ይላሉ፡፡ “መስራቶቹ ለስኳር ምርት መሬት ተሰጥቶናል ብለው ዋሽተውናል” የሚሉት አባላት፤ በፍ/ቤት እየተከራከሩ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ የአክሲዮኑ መስራቾች በበኩላቸው፤ የተሰበሰበው ገንዘብ ያለአገልግሎት ከሚቀመጥ ለጊዜው ደህና ወለድ ቢገኝበት ይጠቅማል ማለታቸው ይታወሳል፡፡

መጀመሪያ ላይ ቃል የተገባልንን መሬት ልናገኝ ባንችልም ምትክ መሬት ተሰጥቶን ነበር ብለዋል፡፡ አቤቱታ አቅራቢ ባለአክሲዮኖች ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ ከመነሻው የአክሲዮኑ ምስረታ በቂ ጥናት ያልተደረገበት ሰነድ በማቅረብ የተጀመረ ስለሆነ ለጉዳት ዳርጐናል የሚሉት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ በሦስት አመት ውስጥ ከአክሲዮን ሽያጭ 600 ሚሊዮን ብር፣ ከመንግስት ብድር ደግሞ 1.4 ቢሊዮን ብር በማሰባሰብ የፋብሪካ ተከላና የስኳር አገዳ ልማት ይጀመራል የሚለው እቅድ ፈቅ አላለም ብለዋል፡፡

የስምንት በመቶ ድርሻ ያላቸው ባለአክሲዮኖች አቤቱታቸውን በደብዳቤ ሲያቀርቡ ከንግድ ሚኒስትር አቶ ከበደ ጫኔ ጋር እንደተነጋገሩ ገልፀዋል፡፡ የንግድ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ምክትል ሃላፊ አቶ አብዱራህማን ሰኢድ፣ ባለአክሲዮኖቹ የአቤቱታ ደብዳቤ እንዳስገቡ ገልፀው፤ በንግድ ህግ መሠረት ንግድ ሚኒስቴር ጣልቃ የሚገባው ቢያንስ አስር በመቶ የሚሆኑ ባለአክሲዮኖች ቅሬታ ሲያቀርቡ ነው ብለዋል፡፡ የማህበሩ አካሄድ ላይ የማታለል ድርጊቶች የሚፈፀሙ ከሆነ ወይም የተወሰኑ ባለአክሲዮኖችን ለይቶ የሚጐዳ ነገር የሚሰራ ከሆነ ሚኒስቴሩ ጣልቃ እንደሚገባ አቶ አብዱራማን ጠቅሰው፣ በህብር ስኳር ጉዳይ የቀረበውን አቤቱታ ከህጉ ጋር ተገናዝቦ ውሳኔ እንደሚሰጥበት ተናግረዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ የህብር ስኳር ምስረታ ሃላፊዎችን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡

Read 13064 times