Saturday, 20 July 2013 09:50

በአዲስ አበባ ለመልሶ ማልማት የታጠሩ ቦታዎች የወንጀለኞች መሸሸጊያ እየሆኑ ነው

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(0 votes)

በአዲስ አበባ የፈረሱና ለመልሶ ማልማት ሥራ የተዘጋጁ የተለያዩ ቦታዎች የወንጀለኞች መሸሸጊያ እየሆኑ መምጣታቸውንና ህገወጦች ለዝርፊያና ወንጀሎችን ፈፅሞ ለመሸሸጊያ እያዋሏቸው እንደሆነ ተጠቆመ፡፡ አስተዳደሩ ችግሩን ለማስወገድ ጥረት አደርጋለሁ ብሏል፡፡ በከተማው ለኮንደሚኒየም ቤቶች ግንባታና ለተለያዩ የልማት ሥራዎች በሚል ምክንያት እየፈረሱ ባሉት ቦታዎች በህገወጥ የዘረፋና የስርቆት ተግባር ላይ የተሰማሩ ሰዎች እየተገናኙ የሚሸሸጉበት፣ ዘርፈው ከፖሊስም ሆነ ከህብረተሰቡ እይታ የሚሰወሩበት እንዲሁም የተለያዩ ጥቃቶችን ለማድረስ የሚገለገሉበት ስፍራ እየሆነ መምጣቱን የጠቆሙት ነዋሪዎች፤ ችግሩን መንግሥት በቸልተኝነት ሊመለከተው እንደማይገባ አሳስበዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ ፀጋዬ ኃ/ማርያም ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ይህንኑ ጉዳይ አንስተው ሲናገሩ፤ ከተማዋ በፈጣን እድገት ላይ በመሆኗ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ ህገወጥ ተግባራት መኖራቸውን ጠቅሰው፤ እነዚህን ህገወጥ ተግባራት ለማስወገድና ህብረተሰቡ በሰላም ወጥቶ የሚገባበትን ሁኔታ ለመፍጠር ተግተን እንሰራለን ብለዋል፡፡ የተማዋን የፀጥታ ጉዳዮች አስመልክተው ሲናገሩም፤ አስተዳደሩ የከተማዋን ፀጥታ አስተማማኝና ቀጣይ ለማድረግ ካለበት ከፍተኛ ኃላፊት በመነሳት፣ የነዋሪውን ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በከተማዋ በኃይማኖት ሽፋን የሚፈፀሙ ህገወጥ ድርጊቶችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ከከተማ እስከ ወረዳ ላሉ ለስድስቱም ሃይማኖቶች የጋራ ምክር ቤት አባላት ስልጠናዎች መስጠታቸውንም ገልፀዋል፡፡ በከተማዋ ውስጥ በርካታ የጥበቃ ማዕከሎች ግንባታ የተከናወነ ሲሆን ጥበቃዎችን በመቅጠር የአካባቢውን ሰላምና ደህንነት አስተማማኝ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡

Read 13882 times