Saturday, 29 June 2013 09:04

የአስካሉካን ትሬዲንግ ባለቤት 6 አመት ከ6 ወር እስራት ተፈረደባቸው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(7 votes)

በደቡብ አፍሪካ ተካሂዶ በነበረው የ2010 የአለም ዋንጫ ወደ ደቡብ አፍሪካ መግባት የሚያስችል የ10ሺህ ሰዎችን ቪዛ ልሰጣችሁ እችላለሁ በሚል 1200 ከሚደርሱ ዜጉች ከ25-37ሺህ ብር በነፍስ ወከፍ በመቀበል አጭበርብረዋል ባላቸው የአስካሉካን ትሬዲንግ ባለቤት አቶ ግርማዬ ገ/ሚካኤል ላይ ፍርድ ቤት የ6 አመት ከ6 ወር ጽኑ እስራት እና የ8ሺ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጡ ባለፈው ማክሰኞ ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

አቃቤ ህግ በተከሳሹ ላይ ካቀረባቸው ስምንት ክሶች መካከል ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛ ያላቸው በሰባት ክሶች ሲሆን ከህዳር 7 እስከ ግንቦት 2002 ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ግለሰቡ ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት ከ25ሺህ እስከ 37ሺህ ብር ከመውሰዳቸውም በተጨማሪ የተሳሳተ መረጃ በመስጠት ዜጐች እንዲጉላሉ በማድረግ እና የንግድ ፍቃዳቸው የአስመጪነትና ላኪነት ሆኖ ሳለ ባልተፈቀደላቸው የስራ መስክ ተሰማርተው ወንጀል በመፈፀም ከሀገር ለመኮብለል ሞክረዋል ሲል ክሱን አጠናክሮ አቅርቧል፡፡

አቃቤ ህግ ግለሰቡ የፈፀሙት ከባድ የማታለል ወንጀል መሆኑን በመጥቀስ 11 የሰው ምስክሮችንና 20 የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤት በማቅረብ አስረድቷል፡፡ ተከሳሹ አቶ ግርማይ በበኩላቸው፤ ወንጀሉን አልፈጸምኩም ሲሉ ክደው የተከራከሩ ሲሆን በወቅቱ የደቡብ አፍሪካ ቪዛ እሰጣለሁ ያልኩት በእጄ የተገኘን መረጃ ምክንያት አድርጌ ነው ካሉ በኋላ ይህም ሆኖ ለተበዳዮቹ ሃብትና ንብረቴን ሸጬ የሚገባቸውን ካሳ ከፍያለሁ ከማለታቸውም በተጨማሪ ሰባት የመከላከያ ምስክሮችንና ሰነዶችን አቅርበው ተከራክረዋል፡፡

የግራ ቀኙን ክርክር ሲያዳምጥ የቆየው ችሎቱ፤ ጉዳዩን መርምሮ ተከሳሹን ጥፋተኛ ናቸው ያለ ሲሆን እንደ ቅጣት ማቅለያ አቅርበውት የነበረውን ለተበዳዮች ካሳ ከፍያለሁ የሚለውን የመከራከሪያ ሃሳብ እሳቸው ፈቅደውና ተፀፅተው ሳይሆን የፍትሐብሄር ክስ ተመስርቶባቸው በመረታታቸው የፈፀሙት በመሆኑ እንደቅጣት ማቅለያነት አልቀበለውም ብሏል፡፡ተ ከሳሹም በሰባት ክሶች ጥፋተኛ ተብለው በድምሩ ስድስት አመት ከስድስት ወር ፅኑ እስራት እና በስምንት ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጡ ሲል ወስኗል፡፡

Read 10259 times