Saturday, 22 June 2013 11:32

ቢጫ ካርድ እና ቢጫ ወባ

Written by  አንተነህ ይግዛው
Rate this item
(4 votes)

ከላቦራቶሪው ውጤት ይልቅ የብሔራዊ ቡድኑ ውጤት ነው ያጓጓው፡፡ ጓደኞቹ ከስቴዲየም ደውለው ስለ ተመልካቹ ወረፋ አጋነው ነገሩት፡፡ ህዝቡ ለነገው ጨዋታ ከዛሬ ጀምሮ ሰልፍ ይዟል፡፡ ስጋት ገባው። እሱ ክሊኒክ ውስጥ ቁጭ ብሎ የምርመራ ውጤቱን ሲጠባበቅ፣ ስቴዲየሙ ሊሞላ ይችላል፡፡ የጓጓለትን የብሔራዊ ቡድኑን ጨዋታ በስቴዲየሙ ተገኝቶ ላይመለከት ይችላል፡፡ ሰአቱን ተመለከተ፡፡ ከምሽቱ አንድ ሰአት ከሩብ ይላል፡፡ ከዚህ በላይ መጠበቅ አልቻለም፡፡ ከክሊኒኩ ወጥቶ ወደ ስቴዲየም ሄደ - ቢኒያም፡፡

                                               ***

 ድል የጠማው ህዝብ፡፡ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የለበሰ … አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የተቀባ … ከ21 ሰአታት በላይ ወረፋ ጠብቆ ወደ ስቴዲየሙ ለመግባት የወሰነ ተመልካች፡፡ የነገውን የብሔራዊ ቡድኑን ድል ለማጣጣም ጓጉቶ በጋለ ስሜት “ማታ ነው ድሌ” የሚል ተሰልፎ አዳሪ ደጋፊ፡፡ የአዲስ አበባ ዝናብ የማይቀዘቅዘው፣ ትኩስ ስሜት በደም ስሩ የሚዘዋወር የአዲስ አበባ ኳስ አፍቃሪ፡፡ ቢኒያም ከዚህ ተመልካች ጋር ነው፡፡ እያጨበጨበ፣ እየዘመረ፣ እየዘፈነ … ብርድ እያንዘፈዘፈው፣ ወጨፎ እየገረፈው፣ … ሌሊቱ እስኪጠባ፣ ሰአቱ ደርሶ ስቴዲየም እስኪገባ፣ ቡድናችን ጐል እስኪያገባ ጓጉቶ (ህመሙን ረስቶ)

                                                  ***

 ብሄራዊ ቡድኑ አሸነፈ፡፡ አገር በደስታ ስታብድ አምሽታ አደረች፡፡ ቢኒያምም ከአገር ጋር ሲያብድ ውሎ ብቻውን ሲሰቃይ አደረ፡፡ “ኑሮ ወሸባ”ውን ጨርሶ ወደ ቤቱ ሲገባ ወባው ተነሳችበት፡፡ ቅዳሜ ምሽት የላብራቶሪ ውጤቱን ሳይቀበል ወደ ስቴዲየም መሄዱን ያስታወሰው ሰኞ ጠዋት ነው፡፡ ህመሙ ሲያገረሽበት፡፡ ህመሙ ሲጠናበትና የሰራ አካላቱ በላብ ሲዘፈቅ ወደ ጓደኞቹ ደወለ፡፡ “ድረሱልኝ” አላቸው፡፡ ደረሱለት፡፡ ብሔራዊ ቡድናቸውን በልዩ ሁኔታ ደግፈው ከድል እንዳደረሱት፣ ጓደኛቸውን ቢኒያምንም በአግባቡ ደግፈው ክሊኒክ አደረሱት፡፡ *** የክሊኒኩ ግቢ በትርምስና በውዝግብ ታመሰ። የውዝግቡ ሰበብ ለቢኒያም አዲስ የታካሚ ካርድ አውጡ፣ አናወጣም የሚል ነው፡፡ የቢኒያም ጓደኞች “ቅዳሜ እለት አውጥቶ ስለተመረመረ ለአዲስ ካርድ መክፈል አይገባንም” ሲሉ ተከራከሩ፡፡ ያለፈው የምርመራ ውጤት ውድቅ ተደርጐ ተጨማሪ ዋጋ እንድንከፍል መደረጉ አግባብ አይደለም በማለት ተሟገቱ፡፡ የክሊኒኩ አስተዳዳሪ ጉዳዩን ለማጣራት ሞከሩ፡፡

                                                         ***

የላብራቶሪ ቴክኒሻኑ፡- ቅዳሜ ዕለት የቢኒያምን ደም መርምሬ ቢጫ ወባ እንዳለበት በማረጋገጥ ለሚመለከተው ሃኪም ውጤቱን ልኬያለሁ፡፡ እኔ ተጠያቂ አይደለሁም፡፡ ውጤቱን አይቶ የቢጫ ወባ ስላለብህ ስቴዲየም መሄድ የለብህም ማለትም ሆነ ጥንቃቄ እንዲያደርግ መምከር የሃኪሙ ሃላፊነት ነው፡፡ ሐኪሙ፡- ቢኒያም ቢጫ ወባ እንዳለበት የሚገልፀው ወረቀት በወቅቱ አልደረሰኝም፡፡ ቢደርሰኝ ኖሮ ወደ ስቴዲየም እንዳይሄድ በማሳሰብ እረፍት አድርጐ እንዲያገግም አደርግ ነበር፡፡ ነርሷ፡- በእለቱ ከላቦራቶሪ የተላከው የምርመራ ውጤት እንደደረሰኝ አልክድም፡፡ ይሄም ሆኖ ግን በወቅቱ ስራ በዝቶብኝ ስለነበር፣ ወረቀቱ የት እንደገባ ሳላውቀው ጠፍቶብኛል፡፡ ለሐኪሙ ወረቀቱን ባለማድረሴ ጥፋተኛ ነኝ፡፡ ቢኒያም፡- በወቅቱ የምርመራ ውጤቱን አይተው “ቢጫ ወባ ስላለብህ ወደ ቤትህ ሄደህ ማገገም እንጂ ወደ ስቴዲየም መሄድ የለብህም” ማለት የነበረባቸው ሐኪሙ ናቸው፡፡ እርግጥ እኔም ብሆን በተደጋጋሚ የያኋቸውን የቢጫ ወባ ምልክቶች በማስታወስ፣ ስቴዲየም ከጓደኞቼ ጋር ከመሰለፍ ይልቅ ወደ ቤቴ ሄጄ ማረፍና የሚታዘዝልኝን መድሃኒት መውሰድ ይገባኝ ነበር፡፡ ጓደኞቹ፡- ሐኪሙም ሆኑ ሌሎች የክሊኒኩ ሰራተኞች ቢኒያም ቢጫ ወባ እንዳለበት እያወቁ ነው፣ ህክምናውን ሳይጨርስ ወደ ስቴዲየም እንዲሄድና እንዲሰለፍ የፈቀዱለት፡፡ የክሊኒኩ ሰራተኞች፡- እንግዲህ ምን እናድርግ! … ችግር እንደሚገጥመው ብናውቅም ጓደኞቹ በጉጉት እየጠበቁት እንደሆነ እያወቅን “አትሂድ”፣ “አትሰለፍ” ለማለት ከበደን፡፡ በመጨረሻ ሁሉም በአንድነት የጋራ መግለጫ ሰጡ። “ስህተት ሰርተናል!”

Read 3177 times