Saturday, 04 May 2013 10:27

በ“ግንቦት 7” አባልነት የፈንጂ ስልጠና ሰጥተዋል የተባሉ ተከሰሱ

Written by 
Rate this item
(8 votes)

መንግስት “ሽብርተኛ” ብሎ ከፈረጃቸው ድርጅቶች አንዱ የሆነውና በዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የሚመራው የግንቦት 7 አባል በመሆን የፈንጂ ስልጠና ሰጥተዋል በተባሉት ሻለቃ ማሞ ለማና አቶ አበበ ወንድማገኝ ላይ የቀረበው ክስ ከትላንት በስቲያ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተሰማ፡፡ በእለቱ በተነበበው የክስ መዝገብ ላይ አቶ አበበ ወንድማገኝ፤ በእንግሊዝ ሃገር ከሚገኙት ሻለቃ ማሞ ለማ ጋር በተደጋጋሚ በዱባይና ለንደን በመገኘት የፈንጂ ጥቃት ለማድረስ የሚያስችል ስልጠና በኤርትራ ወስደዋል ይላል፡፡

ወደ አዲስ አበባ ከተመለሱ በኋላ፣ ግለሰቦችን በመመልመል የትጥቅ ትግል ለማድረግ በማሰልጠን ለሽብር ተግባር አነሳስተዋል በማለት አቃቤ ህግ ባቀረበው ክስ፣ አቶ አበበ ወንድማገኝ ጥር 15 ቀን 2005 ዓ.ም ቦሌ ሰሚት አካባቢ መኪና ውስጥ 10 “c4” የተሰኙ ፈንጂዎችንና ማቀጣጠያ ገመዶችን ይዘው ተገኝተዋል ብሏል፡፡ የተከሳሽ ጠበቃ ባቀረቡት መቃወሚያ፤ የአቃቤ ህግ ክስ በየትኛው አዋጅ እንደቀረበ ክሱ እንደማያመለክት ጠቁመው፤ ደንበኛቸው የፈንጂ ስልጠና መስጠቱን እንዳልካደ በመግለፅ፤ አቃቤ ህግ ያቀረበው የክስ አንቀፅ እንዲያሻሽል ፍ/ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ስልጠና መስጠትን ብቻ የሚመለከት ስላልሆነ ራሱን አንዲያሻሽል ጠይቀዋል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ የተከሳሽ ድርጊት በሰው ህይወት፣ በአካልና በንብረት ላይ ጉዳት ሊያስከትል የሚችል እንደነበር የሚያካትት ክስ እንዳቀረበ ገልጿል፡፡ “ተከሳሹ ስልጠና ብቻ ነው የሰጠው” የሚባለው ጉዳይ ማስረጃ የምናረጋግጠው ነው በማለት አቃቤ ህግ አክለው ገልፀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ብይን ለመስጠት ለፊታችን ሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Read 4634 times