Saturday, 04 May 2013 10:05

አፀያፊ ስድብ የተሳደበች ተቀጣች

Written by 
Rate this item
(6 votes)

የአረብ ሃገር ተጓዧን ያታለሉት በእስራት ተቀጡ የ14 ዓመቷን የቤት ሠራተኛ የደፈረው 10 አመት ተፈርዶበታል በአዲስ አበባ ጐማ ቁጠባ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ሂሩት አጽበሃን “ሸርሙጣ” ብላ የሰደበችው ኪሮስ ሃይሉ በ15 ቀናት የጉልበት ስራ እንድትቀጣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ተወሰነ፡፡ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት በቀረበው የክስ አቤቱታ ላይ እንደተመለከተው፤ ተከሳሽ የ50 አመቷ ወ/ሮ ኪሮስ ተበዳይን ሸርሙጣ፣ ሌባ፣ ቡዳ የሚሉ ስድቦችን የሰደበቻት ሲሆን ይህም በሰው ምስክር መረጋገጡ ተጠቁሟል፡፡ ፍርድ ቤቱም ድርጊቱ ደረጃ እና እርከን ያልወጣለት መሆኑን በመግለጽ፣ ተከሳሽ ለ15 ቀናት የግዴታ የጉልበት ስራ እንድትሰራ የወሰነ ሲሆን ውሳኔው በቀበሌ 12/14 እንዲያስፈጽምና ውጤቱን እንዲያሳውቅ ፍ/ቤቱ አሳስቧል፡፡ አቃቤ ህግ የቅጣት ማክበጃ ባለማቅረቡ እንጂ ቅጣቱ ከዚህም የከበደ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች ምስሬ ጌትነት መንግስቱ የተባለው ወጣት እና ግብረ አበሩ ሰዓዳ ሙሃቢን የተባለች ግለሰብ ላይ ለፈፀሙት የማጭበርበር ወንጀል እስራትና የገንዘብ ቅጣት ተበይኖባቸዋል፡፡ ሚያዚያ 2 ቀን 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 3 ሰዓት ላይ 1ኛ ተከሳሽ:- ሰአዳ ሙሃቢን የተባለች የግል ተበዳይን በተለምዶ አሜሪካን ግቢ በሚባለው ቦታ አግኝቷት ወደ ጋምካ እንደምትሄድ ስትገልጽለት፣ እኔም የእህቴን ዶክመንት ይዤ ልሄድ ነውና አብረን እንሂድ በማለት ጋምካ ከደረሱ በኋላ፣ ከ2ኛ ተከሳሽ ጋር በመሆን ተበዳይን ሁለት መቶ ብር ተከፍሎ የሚወሰድ ትኬት አለ፤ ይህን ትኬት ካልያዝን ማለፍ አንችልም፣ ትኬቱ ሲገዛም እቃ ወይም ንብረት ይዞ መግባት አይቻልም በማለት፣ ሁለተኛ ተከሳሽ ተበዳይዋን ይዟት ትኬት ይቆረጣል ወደተባለበት ቦታ ሲወስዳት፣ ሁለተኛ ተከሳሽ የግል ተበዳይ ይዛው የነበረውን 10,800 ብር፣ እንዲሁም 2ሺ 400 ብር የሚያወጣ ኖኪያ እና መታወቂያ ካርድ ተቀብሎ ከአካባቢው የተሰወረ በመሆኑ በአታላይነት ተከሰው በ1 አመት ከ3 ወር እስራት እና በ200 ብር እንዲቀጡ ተወስኗል፡፡

በዚያው በፌዴራል ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 7ኛ ወንጀል ችሎት በተሰጠ ሌላ ውሣኔ አቶ ተከስተ ዘሪሁን ለገሠ የተባሉት አባወራ በ26/01/2005 ዓ.ም ከሌሊቱ በግምት ስድስት ሰአት ሲሆን በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታ ኮንዶሚኒየም ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ፣ የ14 አመቷን ህፃን የቤት ሠራተኛውን፤ ሚስቱ ያለመኖሯን በማረጋገጥ በሹራብ አፍኖ በመድፈር፣ ክብረንፅህናዋን በመገርሰሱ በፈፀመው ወንጀል በ10 ዓመት እስራት እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

Read 6472 times