Monday, 25 March 2013 14:58

ዋልያዎቹ መሪነታቸውን ለማስጠበቅ ዜብራዎቹን ይገጥማሉ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

በ2014 እኤአ ላይ በብራዚል ለሚካሄደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ በሚደረገው የምድብ ማጣርያ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከቦትስዋና ሊገናኙ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለጨዋታው መደበኛ ልምምዱን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ሲጀምር የግብ አዳኝ ሰላዲን ሰይድ ተቀላቅሎታል፡፡የቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን ትናንት አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ በአፍሪካ ዞን በ10 ምድቦች በሁለት ዙር ግጥሚያዎች 40 ግጥሚያዎች ተደርገው 83 ጎሎች ከመረብ ያረፉ ሲሆን በ3 ግቦቹ የማጣርያው ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ የሚመራው ኢትዮጵያዊው ሳላዲን ሰኢድ ነው፡፡ ሳላዲን ሰኢድ በዓለም ዋንጫው የምድብ መማጣርያ ሁለት ጎሎችን በመካከለኛው አፍሪካ ላይ 1 ደግሞ በደቡብ አፍሪካ ላይ እንዳገባ ይታወሳል፡፡

ዋልያዎቹ እና መሪነታቸው በምድብ ማጣርያው መልካም አጀማመር ያሳየው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የሚያስፈልገውን ትኩረት ተነፍጎ ከያዘው ወርቃማ እድል እንዳይሰናከል መታሰብ ይኖርበታል፡፡ ዋልያዎቹ ዝግጅታቸውን ከ3 ሳምንታት ቀደም ብሎ ለመስራት ታቅዶላቸው የነበረ ቢሆንም ለብሄራዊ ቡድኑ ከተመረጡ ተጨዋቾች ብዙዎቹ የቅዱስ ጊዮርጊስና የደደቢት ተጨዋቾች በመሆናቸውና ሁለቱ ክለቦች በአህጉራዊ የክለብ ውድድሮች በነበራቸው ተሳትፎ ምክንያት ሙሉ ቡድኑን ለመሰብሰብ ባለመቻሉ የዝግጅት ጊዜው እንዲያጥር አስገድዷል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫው በሚደረገው የምድብ ማጣርያ በምድብ 1 መሪነቱን እንደያዘ ነው፡፡ ነገ ቦትስዋናን በሜዳው የሚያስተናግደው ደግሞ መሪነቱን ለማስጠበቅ ነው፡፡

ሌሎቹ የምድብ አንድ ተፋላሚዎች ደቡብ አፍሪካ እና መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ በሶስተኛው ዙር የዓለም ዋንጫ ማጣርያ ጨዋታቸው ኬፕታውን ላይ ይገናኛሉ፡፡ ደቡብ አፍሪካ፤ ቦትስዋና እና መካከለኛው አፍሪካ የሚገኙበትን ምድብ 1 የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሁለት ጨዋታዎች በሰበሰበው አራት ነጥብና ሁለት የግብ ክፍያ እየመራ ነው፡፡ መካከለኛው አፍሪካ በ3 ነጥብ ሁለተኛ ፤ ደቡብ አፍሪካ በሁለት ነጥብ ሶስተኛ እንዲሁም ቦትስዋና በ1 ነጥብ የመጨረሻ ደረጃውን በቅደም ተከተል ይዘዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በዓለም ዋንጫ ማጣርያው እዚህ አዲስ አበባ ላይ ከቦትስዋና አቻው ጋር ነገ የሚገናኝበት ግጥሚያ 3ኛው የምድብ ጨዋታ ነው፡፡ አራተኛው የምድቡን ጨዋታ ከዚህ ጨዋታ 10 ሳምንታት በኋላ ከሜዳው ውጭ በጋብሮኒ ቦትስዋናን መልሶ የሚገጥምበት ነው፡፡

በሳምንቱ ደግሞ በምድቡ አምስተኛ የዓለም ዋንጫ ማጣርያ ጨዋታ ለማድረግ ደቡብ አፍሪካን በሜዳው ያስተናግዳል፡፡ ከ6 ወራት በኋላ ከመካከለኛው አፍሪካ ጋር በሚያደርገው ስድስተኛው የምድብ ጨዋታ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያው ሂደት የሚያበቃ ይሆናል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ አሁን በያዘው የመሪነት እድል እንዲጠቀም በሰፊ የዝግጅት እቅድ ፤ በተሟላ የፋይናንስ አቅም፤ በተጨዋቾቹ አጠቃላይ ደህንነት እና ጤና ላይ በሚደረግ ጥብቅ ክትትል እና ለውጤት በሚሰጡ የማበረታቻ ሽልማቶች መደገፍ ይኖርበታል፡፡ በየጊዜው በሜዳው እና ከሜዳው ውጭ አቋሙን የሚፈትሽባቸው የወዳጅነት ጨዋታዎችንም በግድ ማድረግ ያስፈልገዋል፡፡ በፊፋ ኦፊሴላዊ ድረገፅ ስለ ኢትዮጵያ የዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ተሳትፎ በቀረበ አሃዛዊ ዘገባ ብሄራዊ ቡድኑ ከቅድመ ማጣርያው አንስቶ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ምንም ሽንፈት ሳይገጥመው፤ በሁለቱ ሲያሸንፍ በሁለቱ አቻ ሲወጣ በተጋጣሚዎቹ ላይ ስምንት ጎሎች አግብቶ የተቆጠረበት አንድ ብቻ መሆኑ ተመልክቷል፡፡

ከስምንቱ ጎሎች አምስቱ በቅድመ ማጣርያው በሶማሊያ ላይ እንዲሁም በምድብ ማጣርያው ሁለቱ ጎሎች በመካከለኛው አፍሪካ ላይ እዚህ አዲስ አበባ ላይ ዋልያዎቹ በሜዳቸው ሲጫወቱ ያገቧቸው ሲሆን ከሜዳ ውጭ በማጣርያው ለኢትዮጵያ የተመዘገበችው ጎል የምድብ ማጣርያው ሲጀመር ከደቡብ አፍሪካ ጋር አንድ እኩል አቻ በተለያዩ ጊዜ ነው፡፡ በ2014 ብራዚል ለምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ በሚደረገው የምድብ ማጣርያ ኢትዮጵያ ለሚኖራት ውጤታማነት ሁለቱ ቁልፍ ተጨዋቾች ሳላዲን ሰኢድ እና ኡመድ ኡክሪ እንደሆኑም የፊፋ ዘገባ ገልጿል፡፡ በዓለም ዋንጫው ማጣርያ ከቅድመ ማጣርያው አንስቶ በተደረጉት አራቱ ጨዋታዎች ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 24 ተጨዋቾች አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ በሁሉም አራት ግጥሚያዎች በቋሚ ተሰላፊነት 360 ደቂቃዎች ተሰልፈው ለመጫወት የበቁት አበባው ቡጣቆ እና የቡድኑ አምበል ደጉ ደበበ ብቻ ናቸው፡፡ አሉላ ግርማ 246 ደቂቃዎች፤ ስዩም ተስፋዬ 235 ደቂቃዎች ብርሃኑ ቦጋለ 188 ደቂቃዎች እንዲሁም መሱድ መሃመድ 154 ደቂቃዎችን እያንዳንዳቸው በሶስት ጨዋታዎች ተሰልፈው ተጫውተዋል፡፡

በምድብ 1 ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ በተደረጉ የመጀመርያዎቹ ሁለት ዙር ግጥሚያዎች ከፍተኛ ተመልካች ያገኘው ጨዋታ ኢትዮጵያ በአዲስ አበባ መካከለኛው አፍሪካን 2ለ0 ያሸነፈችበት ጨዋታ ሲሆን ግጥሚያውን በአዲስ አበባ ስታድዬም ከ20ሺ በላይ ተመልካች ታድሞታል፡፡ ደቡብ አፍሪካ እና ኢትዮጵያ በሩስተንበርግ በሚገኘው የሮያል ባፎኬንግ ስታድዬም አንድ እኩል አቻ የተለያዩበትን ጨዋታ 13611 ተመልካች ነበረው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያው በሚቀሩት 3 ጨዋታዎች ላይ ከፍተኛውን የነጥብ ውጤት ካስመዘገበ ወደ መጨረሻው የጥሎ ማለፍ ግጥሚያ ከሚደርሱት አስር ቡድኖች አንዱ ይሆናል፡፡ ካፍ በየምድባቸው መሪ ሆነው ለሚጨርሱት 10 ቡድኖች በሚያወጣው በደርሶ መልስ ግጥሚያዎች የሚገናኙት ቡድኖች ተለይተው ጥለው የሚያልፉት በ20ኛው የብራዚል ዋንጫ አፍሪካን በመወከል የሚሳተፉ 5 ቡድኖች ተለይተው ይታወቃሉ፡፡ የዜብራዎቹ ተስፋ ዜብራዎቹ በሚል ቅፅል ስሙ የሚታወቀው የቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን ከኢትዮጵያ ጋር ለሚያደርገው ጨዋታ በቂ ዝግጅት አለማድረጉን ዋና አሰልጣኙ ስታንሊ ትሾስሳኔ ያማርራሉ፡፡ ባለፈው ማክሰኞ በዋና ከተማዋ ጋብሮኒ ከማላዊ ጋር የወዳጅነት አድርጓ 1ለ0 ያሸነፈው ቡድኑ ሰፋ ያለ ዝግጅት ባይኖረውም ከኢትዮጵያ በሚደረገው ጨዋታ ሙሉ ነጥብ ማግኘት ወደ ብራዚል ለሚደረግ ጉዞ ወሳኝ እንደሆነ በማመን መስራቱን ሜሜጊ የተባለ የአገሪቱ ጋዜጣ ገልጿል፡፡

ባለፈው ሰሞን አሰልጣኙ ለብሄራዊ ቡድኑ በአገር ውስጥ ክለቦች የሚገኙ ተጨዋቾችን ጠርተው የካምፕ ዝግጅታቸውን ሲቲያሰሩ ቆይተዋል፡፡ አሰልጣኙ አንዳንድ ክለቦች ተጨዋቾችን ለመልቀቅ በማመንታታቸው አሰልጣኙ ደስተኛ አልነበሩም፡፡ ሰሞኑን ደግሞ ብሄራዊ ቡድን ለማጠናከር ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ የሆነውን የ21 ዓመቱ ቦቢ ሽልንዴ ቡድናቸው ለማካተት ፍላጎት አሳይተው ተጨዋቹ የእንግሊዝ ፓስፖርት በመያዙ ያሰቡት ሁሉ እውን ሳይሆን መቅረቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የእንግሊዙ ኤፍሲ ዊምብልደን ክለብ ተጨዋች የሆነውን ቦቢ በቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን ለመቀላቀል የተፈለገው በቡድኑ የፕሮፌሽናል ተጨዋች ልምድ ባለመኖሩ እንደሆነም ይገለፃል፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር ለሚደረገው ጨዋታ ከባድ ግምት መሰጠቱን የገለፀው አንድ የአገሬው ጋዜጣ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በካፍ ሻምፒዮስ ሊግ የማሊውን ዲጆሊባ 2ለ0 ካሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ የተውጣጡ በርካታ ተጨዋቾች መያዙ ስጋት እንደሆነም አውስቷል፡፡ የቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን አሉኝ የሚላቸውን ምርጥ ተጨዋቾች በጉዳት እና በተለያዩ ምክንያቶች ለኢትዮጵያ ጨዋታ ማድረስ አልቻለም፡፡ ዋና አሰልጣኙ በተጨዋቾች ስብስባቸው በኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዙም የተሳትፎ ልምድ የሌላቸውን ማብዛታቸው ደግሞ ተጨማሪ ጭንቀትን አምጥቶባቸዋል፡፡

ቦትስዋና በማጣርያ ባደረገቻቸው ሁለት ጨዋታዎች በመጀመርያው ከሜዳዋ ውጭ በመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ 2ለ0 ተሸንፋ በሁለተኛው በሜዳዋ ከደቡብ አፍሪካ ጋር አንድ እኩል አቻ በመለያየት አንድ ነጥብ ይዛ በምድቡ የመጨረሻ እርከን ላይ ትገኛለች፡፡ የባፋና ባፋና አስጨናቂ ፈተና ደቡብ አፍሪካ ለዓለም ዋንጫ ከሚደረግ የምድብ ማጣርያ መጥፎ አጀማመሯ አገግማ ምድቡን በመሪነት በመጨረስ በጥሎ ማለፍ ወደ የሚደረገው የመጨረሻ የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር መቻሏን የምትወስነው በመጭው ሰኔ ወር ከሜዳዋ ውጭ ከኢትዮጵያ እና ከመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ጋር በምታደርጋቸው ግጥሚያዎች እንደሆነ ይገለፃል፡፡ የባፋና አሰልጣኝ ጎርደን ሌጀሰንድ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለሩብ ፍፃሜ የደረሱበት ስብስባቸውን አጠናክረው ከመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ቡድን ጋር ለመገናኘት ወስነዋል፡፡ የደቡብ አፍሪካ እና የመካከለኛው አፍሪካ ጨዋታ በኬፕ ታውን የሚደረግ ሲሆን ከተማው ለባፋና ባፋና ውጤታማነት አያመችም የሚል ወሬ በዝቷል፡፡ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድን በኬፕታውን ባደረጋቸው የመጨረሻዎቹ ሶስት ኢንተርናሽናል ጨዋታዎች በዛምቢያ 3ለ1፤ በአሜሪካ 1ለ0 እንዲሁም በኖርዌይ 1ለ0 እንደተሸነፉ ያስታወሰው ኪኮፍ የተባለ መፅሄት በጉዳት ሳቢያ እስከ 3 ወሳኝ ተጨዋቾች ለግጥሚያው ካለመድረሳቸው ጋር ተዳምሮ ውጤቱን እንዳያበላሸው ያሰጋል ብሏል፡፡

Read 4837 times