በኢትዮጵያ የመጀመርያው እንደሆነ የሚነገርለት ደብረዳሞ ገዳም “ሕዳሴ አቡነ አረጋዊ ዘደብረ ዳሞ” በሚል መሪ ቃል ሰሞኑን እንደሚያከብር ገለፀ፡፡ የገዳሙ ልማት ኮሚቴ ለአዲስ አድማስ እንደገለፀው ከአንድ ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ በአካባቢው ለ1469 ዓመት የተቀመጡ ቅርሶች የሚቀመጡበት ቤተመዘክር ይገነባል፡፡ የኮሚቴው ፀሀፊ አቶ ተወልደብርሃን ታደሰ እንደገለፁት የገዳሙ መንፈሳዊ እሴቶች፣ እና ታሪካዊና ሐይማኖታዊ ቅርሶች ተጠብቀው ምዕመናን እንዲሁም የሐገር ውስጥና የውጭ ሀገር ጎብኚዎች የሚተሙበት ኢትዮጵያዊ መስሕብ ይደረጋል፡፡ ከቅርሶቹ መሃል የአቡነ አረጋዊ 1469 ዓመት ያስቆጠረ ቆብ እና የብራና መፃሕፍት ይገኙበታል፡፡ እስካሁን ኢትዮጵያ ላይ በተቃጡ የውጭ ወረራዎች እና የርስ በርስ ጦርነቶች እንዲሁም ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ሳይደርሱበት እስካሁን የዘለቀ ብቸኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ገዳም ደብረዳሞ ነው፡፡