አንደኛ መውጣቴ ከፍተኛ ሽልማት ካላስገኘልን ምን ዋጋ አለው ብሎ ነው ያለቀሰው፡፡ በሚቀጥለው ዓመት በዝውውር መስኮት ለመሹለክ አስቧል፡፡
ለጥበብ በመቆርቆር ቆረቆር የወረሰው - ጥበብ አድጓል ሲሉት ..መንግስተ ሰማይ መጥታለች.. እንዳሉት ቆጠረውና ፈረሱ ሳቀ፡፡ ዘሩ ሲዘራ ባይመለከትም መብቀሉ ራሱ አስፈነደቀው፡፡ ..የታል የበቀለው?.. ብሎ ሲጠይቅ አይዶልን ተመልከት አሉት፡፡ ተመለከተ፡፡ እውነትም የሆነ ነገር በቅሏል፡፡ እጅ እና እግሩ ባይለይም፤ እያቆጠቆጠ ነው፡፡ ..ተመስገን.. ብሎ ሳቀ፡፡
ያለቀሰው ..እኛ ነን ጥበቡን ያበቀልነው.. የሚሉ የሚመስሉ አላዋቂ ኮትኳቾች መድረኩን ሲቆጣጠሩት ነው፡፡ የማስታወቂያ ሰራተኞች የጥበብ አትክልተኛ ሆነው ያቆጠቆጠውን እንጂ ፍሬ ያልሰጠውን በቆልት መቀስ ይዘው ሲቀርቡት ፍርሀቱ አገረሸበት፡፡ አለማልቀስ አልቻለም፡፡
የስነ ጽሑፍ ትንሳኤን ናፋቂ - የሥነ ጽሑፍ አይዶል በመቀጠል ይዘጋጃል፤ የሚል የህልም ማር ቀምሶ እየሳቀ ከእንቅልፉ ነቃ፡፡ ድርሰት ተሰቅሎ ከሞተ በኋላ ይነሳል የሚል ንግርትን የሚያምን ተስፈኛ ፈረስ ስለሆነ፡፡ ከሞት፤ በሦስተኛው ቀን መቃብሩን ፈነቃቅሎ ሲነሳ የወረቀት፣ የህትመት ዋጋ፣ ከአእምሮ ነፃነት ዋጋ ጋር አንድ ላይ ተወድዶ ጠበቀው፡፡ ከሞት ቢነሳም ወደ ሰማይ ማረግ ግን አልቻለም፡፡ ተመልሶ መስቀሉ ላይ መቸንከር ወይንም መቃብሩ ውስጥ ሞቶ መጠበቅ ግዴታ ሆነበት፡፡ አለቀሰ፡፡ አምርሮ አለቀሰ፡፡