Administrator

Administrator

Saturday, 19 April 2014 11:44

የዓውዳመት ገበያ

   ሰፊ የበአል ሸመታ ከሚከናወንባቸው የአዲስ አበባ የገበያ ስፍራዎች የአቃቂ እና የሳሪስ ገበያዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ማክሰኞ እና ቅዳሜ በሚውለው የአቃቂ ገበያ እንዲሁም ረቡዕና ቅዳሜ በሚውለው የሳሪስ ገበያ የበግ ዋጋ ከአነስተኛ እስከ ትልቅ ከ900 እስከ 2200 ብር ሲጠራ፣ በሬ ከ7ሺህ እስከ 12ሺህ ብር፣ ዶሮ ከ85 እስከ 170 ብር፣ እንቁላል አንዱ 2፡50 ብር፣ ቅቤ 1ኛ ደረጃ 160ብር በኪሎ፣ 2ኛ ደረጃ 145ብር፣ ሽንኩርት 15.50 እና 16 ብር በኪሎ ሲሸጡ ሰንብቷል፡፡
በሸመታ ወቅት ስለ ግብይቱ ካነጋገርናቸው ሸማቾች አንዷ ወ/ሮ ቀለሟ ደጉ፤ ለበአል አስፈላጊ የሆኑትን ግብአቶች አስቀድመው መሸመታቸውን ገልፀው፣ የሽንኩርት ዋጋ በቀናት ልዩነት ከ7.50 ወደ 15.50 ብር ከፍ ከማለቱ ውጪ ካለፈው የገና በአል የተለየ የዋጋ ልዩነት በአብዛኞቹ ሸቀጣ ሸቀጦች ላይ አለማስተዋላቸውን ገልፀዋል፡፡ በሳሪስ ገበያ አግኝተን ያነጋገርናቸው ሌላዋ እማወራ የዘንድሮው በአል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን ጠቅሰው የዳቦ ዱቄት ላይ ዋጋ ባይጨመርም በአብዛኞቹ ሱቆች የለም እንደሚባልና እጥረት መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡
በሳሪስ ገበያ የሸቀጣ ሸቀጥ ነጋዴ የሆነው ወጣት በበኩሉ፤ በዘንድሮው የፋሲካ በአል ላይ መንግስት ከውጭ የሚያስገባቸው ባለ 3 እና ባለ 5 ሊትር ዘይት እጥረት መፈጠሩንና አብዛኛው ሸማች በሊትር 42፡50 የሚሸጠውን የኑግ ዘይት ለመሸመት እንደተገደደ ገልጿል፡፡ ወደ ሱቁ ጐራ የሚሉ ደንበኞች ከውጭ የሚገባው ዘይት በቀላሉ እንደማይገኝ እንደሚጠቁሙት የተናገረው ነጋዴው፤ እጥረቱ የተፈጠረው ጅምላ አስመጪዎች ለቸርቻሪዎች በሚፈለገው መጠን እያቀረቡ ባለመሆኑ ነው ባይ ነው፡፡  
የበዓል ገበያ በሾላ
ወደ አዲሱ ገበያ መስመር ሲጓዙ በሚገኘው ሾላ ገበያ በዓሉን ሞቅ ደመቅ ለማድረግ ዶሮ፣ ሽንኩርት፣ ቅቤና በግ ለመግዛት አባወራዎችና እማወራዎች ከወዲህ ወዲያ ይላሉ፡፡ ወ/ሮ ሰላማዊት አበራ፤ ሽንኩርት 16 ብር መግባቱ ሻጩና ሸማቹ ያመጣው ትርምስ እንጂ የሽንኩርት እጥረት ተከስቶ እንዳልሆነ ይናገራሉ “ከዚህ በፊትም በእንቁጣጣሽ ጊዜ ሽንኩርት 20 ብር መግባቱን አስታውሳለሁ፡፡ ሸማቾችም በዓል ሲሆን እናበዛዋለን፡፡ ሻጩም የሸማችን ፊት እያየ ዋጋ ይቆልላል” ሲሉ አማረዋል፡፡ በመሆኑም ደረቅና ጥራት ያለው ሽንኩርት በ16 ብር ሲሸጥ መለስ ያለ ጥራት ያለው በ14 እና በ15 ብር እየተሸጠ ነው፡፡
ሀሙስ ዕለት ነው ያነጋገርነው የዶሮ ነጋዴው አቶ ለሚ፤ በዓሉ እየቀረበ ሲመጣ ቅዳሜ ዶሮ እየተወደደ እንደሚሄድ ይናገራል፡፡ በሾላ ገበያ ባለፉት ስምንት ዓመታት በተለያዩ በዓላት ዶሮ በመሸጥ ስራ ላይ መሰማራቱን የሚናገረው አቶ ለሚ፤ ነጋዴው የሸማቹን ፍላጎትና ሽሚያ እያየ ዋጋ እንደሚጨምር በመግለፅ፣ የወ/ሮ ሰላማዊትን ሀሳብ ይጋራል፡፡ “ረቡዕ እለት ጥሩ ስጋ አለው የሚባለውን ትልቅ ዶሮ በ190 ብር እንደሸጠ የሚናገረው አቶ ለሚ፤ ዛሬ (ሐሙስ) ከዚያው ዶሮ ጋር ተመጣጣኝ የሆኑ ዶሮዎችን በ240 ብር እየሸጠ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ተዘዋውረን ለማየት እንደሞከርነው ዶሮ ከ110 ብር እስከ 235 ብር ድረስ እየተሸጠ ነበር፡፡
በሾላ ገበያ ለጋ ቅቤ በ180 ብር ሲሸጥ መካከለኛው 160 ብር በሳሉ ደግሞ 145 ብር በመሸጥ ላይ ይገኛል፡፡ ወ/ሮ ወርቅነሽ አባተ የተባሉ ቅቤ ነጋዴ፤ ከበዓል በፊትና በኋላ የቅቤ ዋጋ ብዙ ልዩነት እንደሌለው የገለፁ ሲሆን በበዓል ሰሞን በኪሎ ከአምስት ብር በላይ እንዳልጨመረ ተናግረዋል፡፡ ከነጋዴዋ ጋር ስለዋጋ በምንነጋገርበት ጊዜ ጣልቃ የገቡ አንድ እናት፤ በበዓሉ የቅቤ ዋጋ መጨመሩን ገልፀው ከአንድ ወር በፊት ጥሩ የሚባለው ቅቤ በ130 ብር ይሸጥ እንደነበር መስክረዋል፡፡
ከመቼውም በበለጠ በበዓል ሰሞን ገበያ የሚደምቀው ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጀርባ የሚገኘው ሾላ ገበያ ለዘንድሮው ፋሲካ በሰው ተጨናንቋል፡፡ እንቁላል በ2.50 እየተሸጠ ሲሆን የተዘጋጀ በርበሬ በኪሎ 85 ብር፣ በግ ከትንሽ እስከ ትልቅ ከ850 ብር እስከ 2800 ብር መሆኑን የገለፁልን በግ ነጋዴዎች፤ በዓሉ ቀረብ እያለ ሲመጣ የበግ ዋጋ ሊጨምር እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ዘመናዊ ገበያዎች የበዓል አማራጮች ሆነዋል
ድሮ ዓመት በአል ሲመጣ አብዛኛው ሴት ወደ መርካቶ ነበር የሚሮጠው፡፡ አሁን ጊዜው ተለውጧል፡፡ በየአካባቢው በተከፈቱ ሱፐር ማርኬቶች የሚፈልጉትን ስለሚያገኙ መርካቶ መሄድ ትተዋል፡፡ መገናኛ ሸዋ ሃይፐር ማርኬት ዕቃ ስትገዛ ያገኘኋትን ሴት “ከመርካቶና ከዚህ ገበያው የቱ ይሻላል?” አልኳት “ያው ነው፤ እንዲያውም እዚህ ይሻላል፡፡ ምክንያቱም መርካቶ የምታገኘውን ሁሉ እዚህም ታገኛለህ፡፡ ጥራጥሬው፣ ቅመማ ቅመሙ፣ አትክልቱ፣ ፍራፍሬው፣ ዱቄቱ፣ ዶሮው፣ ሥጋው፣ አይቡ፣ የልጆች ልብስ ብትል፣ ጌጣጌጡ፣ … ኧረ ሁሉም ሞልቶአል፤ በዚህ ላይ መንገዱ ስለተቆፈረ መርካቶ መሄድ ስለማይፈልጉ ትራንስፖርት አስቸጋሪ ነው፡፡ ዋጋውስ? ያልክ እንደሆነ የትራንስፖርቱን፣ ያውራጅ ጫኚውን ስትደምርበት ያው ነው፡፡ በዚህ ላይ ፀሐይዋ! አናት ትበላለች ሳይሆን ልብን ነው የምታጥወለውለው፡፡ ኧረ ምን አገኝ ብዬ ነው የምንከራተተው?...” አለች፡፡
በሸዋ ሃይፐርማርኬት የሀበሻ ዶሮ 84 ብር፣ የፈረንጅ እንደኪሎው ከ136 ብር እስከ 178 ብር፣ በጣም ትልቁ ደግሞ 202 ብር፣ የክትፎ ሥጋ አንድ ኪሎ 126 ብር፣ የወጥ 110 ብር፣ የበግ ሥጋ አንድ ኪሎ 93 ብር፣ አንድ ኪሎ አይብ 60 ብር፣ ትልልቅ ቀይ ሽንኩርት 22 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት 45 ብር ይሸጣል፡፡  
ገርጂ መብራት ኃይል አካባቢ ባለው ኦልማርት ያገኘኋትን ሴት፣ “ገበያው እንዴት ነው? ከዚህና ከውጪው የቱ ይሻላል?” አልኳት፡፡ “ያው ነው፤ ብዙ ልዩነት የለውም፡፡ አንዳንድ ዕቃ ጥራቱን ስታይ እዚህ ይሻላል፤ ውጭ ደግ ጥራቱ ቀነስ ያለ በቅናሽ ዋጋ ታገኛለህ” እስቲ ለምሳሌ ምን? አልኳት “ለምሳሌ ቀይ ሽንኩርት ብንወስድ እዚህ 21 ብር ከምናምን ነው፡፡ ትልልቅ ነው ጥራቱም ጥሩ ነው፡፡ ውጭ ከሆነ ከ15 እስከ 16 ብር ታገኛለህ፡፡ ነገር ግን መካከለኛ ወይም አነስ ያለ ነው፡፡…”
ለፋሲካ ዶሮ ገዝታ እንደሆነ ጠየኳት፡፡ እንዳልገዛች ነገረችኝ፡፡ ከየት ለመግዛት እንዳሰበች ስጠይቃት፣ ከሱፐር ማርኬት እንደምትገዛ ነገረችኝ፡፡ ለምን? አልኳት፡፡ “እኔ የኮንዶሚኒየም ነዋሪ ነኝ፡፡ እዚያ ዶሮ ለማረድና ለመገነጣል አይመችም፡፡ ቆሻሻ መድፊያው ያስቸግራል፡፡ ከላይ ታች መመላለሱም ይሰለቻል፡፡ ዋጋውም ያው ነው፤ የታረደውን ከዚሁ እገዛለሁ” በማለት ምርጫዋን ነገረችኝ፡፡
በኦል ማርት ሱፐር ማርኬት የፈረንጅ ዶሮ በኪሎ 133 ብር፣ የሀበሻ ዶሮ የተበለተ ከ133 እስከ 139 ብር፣ ቀይ ሽንኩርት 21.70፣ አንድ ኪሎ የበግ ስጋ 100 ብር፣ የበሬ 138 ብር፣ የጥጃ 110 ብር፣ የጭቅና ሥጋ 210 ብር፣ ቅቤ የተነጠረ 165 ብር (1 ኪሎ ግን አይሞላም)፣ ዕንቁላል 2.65 ይሸጣል፡፡ እዚያው አካባቢ የጎንደር የተጣራ የኑግ ዘይት አንድ ሊትር 44 ብር፤ አምስት ሊትር 235 ብር፡፡
ገርጂ ሰንሻይን ኮንዶሚኒየም ፍሬሽ ኮርነር በተባለ ሱፐርማርኬት የፈረንጅ ዶሮ በኪሎ 115 ብር፣ የተገነጣጠለ ሙሉውን የሀበሻ ደሮ 125 ብር፣ ያልተገነጣጠለ 100 ብር፣ አንድ ዕንቁላል 3 ብር፣ 10 ዕንቁላል 35 ብር፣ አይብ አንድ ኪሎ 60 ብር፣ ሽንኩርት በኪሎ 16 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት 48 ብር፣ የተነጠረ ኪሎ ቅቤ 200 ብር፣ ሎሚ በኪሎ 35 ብር፣ ግማሽ ኪሎ 17 ብር፣ ለወጥ የሚሆን ሥጋ 100 ብር፣ የጥብስ 140 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

“አንድ ቀን” የቤተሰብ ፊልም በቅርቡ ለተመልካች ይቀርባል

በደራሲ፣ዳይሬክተርና ፕሮዱዩሰር አለማየሁ ታደሰ እንዲሁም በኤክስኪዩቲቭ ፕሮዱዩሰር ማርታ ጌታቸው የተዘጋጀው ‹‹የኔታ›› የተሰኘ ድራማ ኮሜዲ ፊልም፤ የፊታችን ሰኞ በ11 ሰዓት በብሔራዊ ትያትር ይመረቃል፡፡ በፊልሙ ላይ ራሱ አለማየሁ ታደሰን ጨምሮ  ኮሜዲያን ደረጄ ሀይሌ፣ ቃልኪዳን ጥበቡ፣ አስናቀ ንጉሴ፣ማርታ አሰፋ እና ሌሎች ተዋንያን ተሳትፈውበታል፡፡
በሌላ በኩል በደራሲና ፕሮዲዩሰር ሜላት ነብዩ እና በዳሬክተር ቢኒያም ወንድይፍራው የተዘጋጀው “አንድ ቀን” የተሰኘ የቤተሰብ ፊልም፣ ሚያዚያ 23 ከቀኑ በ11 ሰዓት በጣይቱ ጃዝ አምባ አዳራሽ  የሚመረቅ ሲሆን በቅርቡ ለተመልካች ይቀርባል ተብሏል፡፡
በሜሊያም መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን በተሠራው በዚህ ፊልም ላይ ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን  የተሳተፉበት ሲሆን ፊልሙን ለማጠናቀቅ አንድ ዓመትና ከ500ሺ ብር በላይ እንደፈጀ አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡

      በዓለም  የአትሌቲክስ  ስፖርት  በረጅም ርቀት፤ በጎዳና ላይ ሩጫ እና በቤት ውስጥ ውድድሮች በኢትዮጵያውያን አትሌቶች የተያዙ የዓለም ሪከርዶች የሚሰበሩበት እድል እየተመናመነ መምጣቱን የተለያዩ ጥናቶች አመለከቱ።  በተለይ በረጅም ርቀት በወንዶች   10ሺ ሜትር እና በሁለቱም ፆታዎች በ5ሺ ሜትር በኢትዮጵያውያን የተመዘገቡት 3 ሪከርዶች በመላው ዓለም ውድድሮቹ ካለመካሄዳቸው በተያያዘ የሪከርድ ሰዓቶቹ በቅርብ ዓመታት መሻሻላቸው ያጠያይቃል ተብሏል፡፡ ቀነኒሳ በቀለ  በ5ሺ እና 10ሺ ሜትር ውድድሮች ያስመዘገባቸው ሁለት የዓለም ሪከርዶች ሳይሰበሩ 10 ዓመታት ያለፏቸው ሲሆን ፤ አትሌቱ በተመሳሳይ ርቀቶች በዓለም ሻምፒዮና የኦሎምፒክ  መድረኮች ያስመዘገባቸውን ሪከርዶች  እንደተቆጣጠረ ነው፡፡  በሌላ በኩል በሴቶች 5ሺ ሜትር ውድድር ጥሩነሽ ዲባባ የያዘችው ክብረወሰን ከተመዘገበ 6 ዓመታት ያለፉት ሲሆን አትሌቷ በረጅም ርቀት በኦሎምፒክ እና በዓለም ሻምፒዮና ያስመዘገበቻቸው ሪከርድ ሰዓቶች የከፍተኛ ብቃት መለኪያ እንደሆኑ ቀጥለዋል፡፡  በአትሌቲክስ ውድድሮች ሪከርዶችን ካስመዘገቡ የኢትዮጵያ አትሌቶች መካከል ለ20 አመታት ባሳለፈው የሩጫ ዘመኑ ከ27 በላይ ሪከርዶችን ከ2 ማይል እስከ ማራቶን ባሉ ርቀቶች በማስመዝገብ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሆነው አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ከሳምንት በኋላ 41ኛ ዓመቱን የሚይዝ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ከትራክ ውጭ በተደረጉ ውድድሮች የተመዘገቡ  ከ3 በላይ የአለም ሪከርዶችን እንደያዘ ነው። በሴቶች 5ሺ ሜትር የትራክ ውድድር በኦሎምፒክ እና በዓለም ሻምፒዮና ከፍተኛ ውጤት ያላት መሰረት ደፋር በ5 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ያስመዘገበችው ሪከርድ ያልተሰበረ ሲሆን በዓለም የቤት ውስጥ ውድድሮች በ1500 እና በ3ሺ ሜትር የነበሩ ሪከርዶችን ባለፉት 3 እና 4 አመታት እንደተቆጣረች ቆይታ ዘንድሮ የተሰበረባት በኢትዮጵያዊቷ ገንዘቤ ዲባባ ነው፡፡ ገንዘቤ ዲባባ ዘንድሮ በ1500ሜና በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች እንዲሁም በ2 ማይል ሩጫ ሶስት የዓለም ሪከርዶችን የጨበጠች ሲሆን  በተለይ ሰሞኑን በአይኤኤኤፍ ማረጋገጫ ያገኘችበት የ3ሺ ሜትር ው ሪከርድ በድጋሚ ለመሰበር ቢያንስ 5 አመታትን እንደሚፈጅ ይገለፃል፡፡
በተለያዩ ጊዜያት የተሰሩ ጥናቶችን በመዳሰስ ለመረዳት እንደተቻለው በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚካሄዱ የአትሌቲክስ ውድድሮች ከ100 ሜትር እስከ ማራቶን ርቀቶች በየጊዜው ሪከርዶችን በማሳካት የሚሆንላቸው አትሌቶች ከተወሰኑ አገራት የሚገኙ ናቸው፡፡ በመካከለኛና ረጅም ርቀት ሩጫዎች የኢትዮጵያ እና የኬንያ አትሌቶችን  የውጤት የበላይነትና የሪከርድ ባለቤትነት ላለፉት 20 አመታት የሚቀናቀን ጠፍቷል፡፡ በአጭር ርቀት ውድድሮች ደግሞ የጃማይካ እና የአሜሪካ አትሌቶችን ስኬት የሚስተካከል አልተገኘም።  ከላይ ከተጠቀሱት አራት  አገራት የሚወጡ አትሌቶች በአትሌቲክስ ውድድሮች ያስመዘገቧቸው ሪኮርዶችን የማሻሻሉ እድል በየዓመቱ በ0.5 በመቶ እንደተወሰነ በጉዳዩ ላይ ስፖርትሳይንቲስትስ የተባለ ድረገፅ የሰራው ትንታኔ አመልክቷል፡፡  የላቀ ብቃት፤ የላቀ ፍጥነት እና የላቀ ጥንካሬ በሚለው የኦሎምፒክ መርህ  መሰረት የእነዚህ 4 አገራት ምርጥ አትሌቶች በአትሌቲክስ ስፖርት በሰው ልጅ ተፈጥሯዊ ብቃት ሊሳካ የሚችለውን የሪከርድ አቅም 99 በመቶ አሟጥጠውታል የሚል ድምዳሜን የስፖርትሳይንቲስት ባለሙያዎች በጥናታቸው አረጋግጠዋል፡፡ በስፖርቱ አለም የ147 ውድድሮች ሪከርድ በሰው ልጅ ብቃት ሊመዘገብ የሚችለው ማጣርያ በ2027 እኤአ  እንደሚያበቃ ያረጋገጡ ጥናቶች አሉ፡፡ አይኤንኤስኢፒ የተባለ እና በፓሪስ ተቀማጭ የሆነ የስፖርት ኢንስቲትዩት በሰራው ጥናት አረጋግጧል።  በአሁኑ ወቅት በስፖርቱ አለም በተለይ በአትሌቲክስ ውድድሮች ሪከርዶችን ለማስመዝገብ እጅግ ወሳኝ ከሆነው ተፈጥሯዊ ክህሎት ባሻገር፤ ለፍጥነት የሚመደቡ አሯሯጮች፤ በቴክኖሎጂ የታገዙ የመሮጫ ጫማዎች፤ ዘመናዊ ህክምናዎች እና መድሃኒቶች፤ እጅግዘመናዊ የስልጠና፤ የአመጋገብ እና የስነልቦና ዝግጅቶች እንዲሁም በስኬት  የሚገኝ ገቢ አስፈላጊ ይሆናሉ፡፡ በዘመናችን በህክምና ረገድ ያሉ አገልግሎቶች እና መድሃኒቶች አትሌቶች ለረጅም ጊዜ እየተወዳደሩ በመቆየት ካላቸው ልምድ ሪከርዶችን የመስበር እድላቸውን ከማስፋቱም በላይ፤ ከጉዳቶች ሙሉ ለሙሉ ለመዳንና ለማገገም በሚኖራቸው እገዛ ስፖርተኞች ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ በሌላ በኩል እንደ ጂን ቴራፒ አይነት ዘመናዊ ህክምናዎች ስፖርተኞች በጡንቻዎቻቸው አላግባብ ጉልበት የሚያፈሱበትን ሁኔታ እና ድክመታቸውን በመፈወስ ብቃታቸውን ያግዛል፡፡ በአጠቃላይ የአትሌቶች ብቃት እያደገ ሲቀጥል፤ የቴክኖሎጂ እና የሳይንስ ድጋፍ እየመጠቀ ሲሄድ በርካታ የአትሌቲክስ ሪከርዶች መሻሻላቸው አይቀርም፡፡ በእርግጥ  በዓለም የአትሌቲክስ ውድድሮች በዓለም ሻምፒዮና እና በኦሎምፒክ መድረክ  የወርቅ ሜዳልያዎችን ከማግኘት በላቀ ሁኔታ እንደከፍተኛ ስኬት የሚቆጠረው ሪከርዶችን ማስመዝገብ ነው፡፡ ለምን ቢባል  የየትኛውንም የአትሌቲክስ ውድድር ሪከርድ ማስመዝገብ በውድድር አይነቱ ያለተቀናቃኝ የበላይነት መያዝ መቻሉን የሚያረጋግጥ ስኬት በመሆኑ ነው፡፡ ሪከርዶች የሩጫ ውድድሮችን የፉክክር ደረጃ ከማሳደጋቸውም በላይ ለተመልካቾች የማይረሳ ልዩ ስሜት በመፍጠርና የስፖርቱን ተወዳጅነት በመጨመር አስተዋፅኦ አላቸው፡፡  ሪከርድ የሚያስመዘገቡ አትሌቶች በተለያዩ የውድድር የቦነስ ሽልማቶች ይጠቀማሉ፡፡ የትጥቅ እና የመሮጫ ጫማዎችን በሚያቀርቡላቸው ስፖንሰሮች ተጨማሪ ክፍያ እና የገቢ እድል ይፈጠርላቸዋል፡፡ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በሚካሄዱ ውድድሮች በቀጥታ ተጋባዥ የሚሆኑበትንም እድል ያገኛሉ፡፡
ባለፉት 15 አመታት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከ1500 ሜትር እስከ ማራቶን፤ ከ2 እስከ 10 ማይል ፤ በተለያዩ የጎዳና ላይ ሩጫዎች እንዲሁም ከ2ሺ  እስከ 5ሺ ሜትር በሚደረጉ የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ውድድሮች በአሸናፊነት ፍፁም የበላይነት በማሳየት እና ሪከርዶችን በማስመዝገብ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር (አይኤኤኤፍ) በአሁኑ ወቅት በአትሌቲክስ ስፖርቶች 53 ሪከርዶች ተመዝግበዋል፡፡ አይኤኤኤፍ በትራክ ላይ የሚደረጉ የሩጫ ውድድሮችን ሪከርዶች በኦፊሴላዊ ደረጃ መመዝገብ የጀመረው በ1912 እኤአ ሲሆን ቤት ውስጥ የአትሌቲከስ ውድድሮች ደግሞ ከ1987 እኤአ ወዲህ እውቅና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡  በትራክ ላይ የሩጫ ውድድሮች  አይኤኤኤፍ  በወንዶች ከመዘገባቸው ሪከርዶች መካከል አራቱ በሁለቱ የኢትዮጵያ አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ኃይሌ ገብረስላሴ ሲያዙ፤ በሴቶች ደግሞ ሶስት ሪከርዶች ሁለቱ በጥሩነሽ ዲባባ እንዲሁም አንደኛው በድሬ ቱኔ እንደተያዙ ናቸው።  በዓለም የቤት  ውስጥ የአትሌቲክስ ውድድሮች ደግሞ በወንዶች ቀነኒሳ በቀለ በ5ሺ ሜትር ሪከርድ ሲኖረው፤ በሴቶች ምድብ የተመዘገቡት ሶስት ኢትዮጵያዊ ሪከርዶች ደግሞ ዘንድሮ  በገንዘቤ ዲባባ አማካኝነት በ1500 ሜትር እና በ3ሺ ሜትር የተያዙትና  በመሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር ያስመዘገበችው ናቸው፡፡  ከዚህ በታች በዓለም የአትሌቲክስ ስፖርት የኢትዮጵያ አትሌቶች ያስመዘገቧቸው የዓለም፤ የዓለም ሻምፒዮና እና የኦሎምፒክ እና የልዩ ልዩ ውድድሮች ሪከርዶች ተቀነጫጭበው ቀርበዋል፡፡
ኢትዮጵያዊ የዓለም ሪከርዶች
በ5ሺ ሜትር የትራክ ውድድሮች  በሁለቱም ፆታዎች  የዓለም ሪከርዶች በኢትዮጵያውያን የተያዙ ናቸው፡፡ በወንዶች 5ሺ ሜትር  ከ1884 እኤአ ጀምሮ 37 ሪከርዶች ተመዝግበዋል፡፡ በዚህ የሪከርድ መሻሻል ሂደት 5 ጊዜ ኢትዮጵያን ስድስት ጊዜ ደግሞ ኬንያውያን አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ ከ1994 እስከ 1998 እኤአ ድረስ ለአራት ጊዜያት የ5ሺ ሜትር ሪከርዶችን በማሻሻል ከፍተኛውን ድርሻ የተወጣ አትሌት ነበር፡፡  በ2004 እኤአ በሆላንድ ሄንግሎ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በ12 ደቂቃ ከ37.35 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ሪከርድ ግን ላለፉት 10 ዓመታት ሳይሰበር የቆየ ነው፡፡ በራንኒንግ ዎርልድ ጥናታዊ ዘገባ በሰው ልጅ ብቃት በ5ሺ ሜትር ሊመዘገብ የሚችለው ሪከርድ ከ14 ዓመታት በኋላ 12 ደቂቃ ከ09.39 እንዲሁም ከ26 ዓመታት በኋላ ደግሞ 11 ደቂቃ ከ56.19  ሰኮንዶች ሊሆን እንደሚችል ሲገመት 11 ደቂቃ ከ11.61 ሰከንዶች የመጨረሻው የሪከርድ ወሰን ነው፡፡ በሌላ በኩል በሴቶች 5ሺ ሜትር ከ1922 እኤእ ጀምሮ 27 ጊዜ ሪከርዶች ሲመዘገቡ ከ2004 እኤአ ጀምሮ የተመዘገቡ አራት ክብረወሰኖች በትውልድ ኢትዮጵያዊ በሆኑ አትሌቶች አሳክተዋቸዋል፡፡ በ2004 እኤአ የርቀቱን ክብረወሰን 14 ደቂቃ ከ24.68 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ አስመዝግባ የነበረችው በትውልድ ኢትዮጵያዊ ብትሆንም በዜግነት ለቱርክ የምትሮጠው ኢልቫን አብይ ለገሰ ነበረች፡፡ የኢልቫን አብይ ለገሰን ሪከርድ በ2006 እና በ2007 እኤአ አከታትላ ለመስበር የበቃችው ደግሞ መሰረት ደፋር ናት፡፡ ከእሷ በኋላ ላለፉት 6 ዓመታት ሳይሰበር የቆየውን ሪከርድ በ2007 እኤአ በኖርዌይ ኦስሎ በተካሄደ ውድድር 14 ደቂቃ ከ11.15 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በጥሩነሽ ዲባባ  የተመዘገበው ነው፡፡ በራንኒንግ ዎርልድ ጥናታዊ ዘገባ በሰው ልጅ ብቃት በ5ሺ ሜትር በሴቶች ሊመዘገብ የሚችለው ሪከርድ  ከ14 ዓመታት በኋላ 13 ደቂቃ ከ41.56 ሰከንዶች ከ26 ዓመታት በኋላ ደግሞ 13 ደቂቃ ከ37.25 ሰኮንዶች ሲሆን 12 ደቂቃ ከ33.36 ሰከንዶች የመጨረሻው የሪከርድ ወሰን ነው፡፡
በ10ሺ ሜትር የትራክ ውድድር በወንዶች  ከ1847 እኤአ ጀምሮ 47 ሪከርዶች ሲመዘገቡ የኢትዮጵያ ሁለት አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ኃይሌ ገብረስላሴ ለአምስት ጊዜያት  የሪከርድ ሰዓቶቹን በማሻሻል አስተዋፅኦ ነበራቸው።  በ2005 እኤአ ላይ ቤልጅዬም ብራሰልስ ላይ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ያስመዘገበው 26 ደቂቃ ከ17.53 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በርቀቱ ላለፉት 9 አመታት ተይዞ የቆየውን ሪከርድ  አስመዝግቧል፡፡ በራንኒንግ ዎርልድ ጥናታዊ ዘገባ በሰው ልጅ ብቃት በ10ሺ ሜትር ሊመዘገብ የሚችለው ሪከርድ  ከ14 ዓመታት በኋላ 25 ደቂቃ ከ32.27 ሰኮንዶች ከ26 ዓመታት በኋላ ደግሞ 25 ደቂቃ ከ04.36 ሰከንዶች ሲሆን 23 ደቂቃ ከ36.89 ሰከንዶች የመጨረሻው የሪከርድ ወሰን ነው፡፡
በዓለም የቤት ውስጥ  የአትሌቲክስ ውድድሮች በወንዶች 5ሺ ሜትር ኃይሌ ገብረስላሴ ለሶስት ጊዜ ሪከርዶች ቢያስመዘግብም አሁን ያለውን ሪከርድ በ2004 እኤአ በእንግሊዝ በርሚንግሃም 12 ደቂቃ ከ49.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በተመሳሳይ በሴቶች የ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር ብርሃኔ አደሬ በ2004 እኤአ፤ ጥሩነሽ ዲባባ በ2005 እና በ2007 እኤአ ካስመዘገቧቸው ሶስት ሪከርዶች በኋላ አሁን ተመዝግቦ ያለውን ሪከርድ ከ2009 እኤአ ጀምሮ ተቆጣጥራ የምትገኘው በስቶክሆልም ርቀቱን በ14 ደቂቃ ከ24.37 ሰኮንዶች የጨረሰችው መሰረት ደፋር ናት፡፡ ዘንድሮ በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ውድድሮች ሁለት አዳዲስ ሪከርዶች ያስመዘገበችው ደግሞ ገንዘቤ ዲባባ ናት፡፡ ገንዘቤ በስዊድን ስቶክ ሆልም የ3ሺ ሜትር የዓለም ሪከርድን 8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ከማስመዝገቧም በላይ በካርሉስርህ ጀርመን በተካሄደ የ1500 ሜትር ውድድር ደግሞ ርቀቱን በ3 ደቂቃ ከ55.17 ሰከንዶች የሆነ የሪከርድ ጊዜ አስመዝግባ ማሸነፏ ይታወሳል፡፡
በጎዳና ላይ ሩጫዎች እና በልዩ የአትሌቲክስ ውድድሮች በኢትዮጵያውያን የተመዘገቡ ሌሎች ክብረወሰኖችም አሉ፡፡  ኃይሌ ገብረስላሴ በዚህ ምድብ ሶስት ሪከርዶች ተመዝግበውለታል፡፡ የመጀመርያው በ20ሺ ሜትር የትራክ ውድድር በ2007 እእእ በቼክ ኦስትራቫ 56 ደቂቃ ከ25.98 ሰከንዶች በማስመዝገብ የያዘው  ሲሆን ሌላው ደግሞ በ10 ማይል የጎዳና ላይ ሩጫ  በ2005 እኤአ በቲበርግ ሆላንድ ውስጥ 44 ደቂቃ ከ23 ሰከንዶች የጨረሰበት ናቸው፡፡ በ2007 እኤአ ላይ በቼክ ኦስትራቫ በ1 ሰዓት ውስጥ በሚሸፈን ርቀት የተመዘገቡ ሁለት ሪከርዶችንም ኢትዮጵያውያን አስመዝግበዋል፡፡ ይሄውም በ1 ሰዓት ውስጥ በኃይሌ ገብረስላሴ የተሮጠው 21285 ሜትር እና በድሬ ቱኔ የተሸፈነው 18517 ሜትር ርቀት ናቸው፡፡ በተያያዘ በዓለም ትልልቅ ማራቶኖች የቦታዎቹን ሪከርድ በማስመዝገብ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከኬንያውን ይፎካከራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ወንዶች  ከተያዙ የትልልቅ ማራቶኖች የቦታ ክብረወሰኖች መካከል ባለፈው ሳምንት ቀነኒሳ በመጀመርያው ማራቶኑ ፓሪስ ላይ  ያሸነፈበት 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ 4 ሰከንዶች፤ በዱባይ ማራቶን በ2008 እኤአ ላይ አትሌት ኃይሌ ያስመዘገበው 2 ሰአት ከ04 ደቂቃ ከ53 ሰከንዶች፤ በኒውዮርክ ማራቶን በ2001 እኤአ ላይ ተስፋዬ ጅፋር በ2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ43 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የበርሊን፤ የቦስተንና  የሮተርዳምን የቦታ ሪከርዶች ኬንያውያን ይዘውታል፡፡
ኢትዮጵያዊ የዓለም ሻምፒዮና የኦሎምፒክ ሪከርዶች
በዓለም አትሌቲክስ  ሻምፒዮና ላይ በወንዶች ምድብ   ኬንያውያን በ800፤ በ3ሺ መሰናክል፤ በ5ሺ ሜትር እና በማራቶን ያሉ ሪከርዶችን በመቆጣጠር ከኢትዮጵያውያን ይልቃሉ፡፡ በወንዶች ምድብ  በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ  ሪከርድ ይዞ የሚገኝ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ሲሆን በ2009 እኤአ በርሊን ላይ ርቀቱን በ26 ደቂቃ ከ46.31 ሰኮንዶች በመሸፈን ባስመዘገበው ጊዜ ነው፡፡ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ   በሴቶች ምድብ ከተመዘገቡ ሪከርዶች የኢትዮጵያ አትሌቶች በሁለት ውድድሮች ሲጠቀሱ አንዲትም ኬንያዊ አትሌት የለችበትም፡፡ ጥሩነሽ ዲባባ በ5ሺ ሜትር ሴቶች 14 ደቂቃ ከ38.59 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜን  ሄልሲንኪ ላይ በ2005 እኤአ  እንዲሁም በ2003 እኤአ ፓሪስ ላይ ብርሃኔ አደሬ በ10ሺ ሜትር 30 ደቂቃ ከ04.18 ሰኮንዶች በሪከርድ እንደተመዘገበላቸው ነው፡፡ በኦሎምፒክ መድረክ በወንዶች  በ5ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር ሁለት ክብረወሰኖችን የያዘው  ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ ቀነኒሳ በቀለ ሁለቱንም የኦሎምፒክ ክብረወሰኖች እኤአ በ2008 በቤጂንግ በተካሄደው 29ኛው ኦሎምፒያድ ሲያስመዘገባቸው በ5 ሺ ሜትር 12 ደቂቃ ከ57.82 ሰኮንዶች እንዲሁም በ10ሺ ሜትር 27 ደቂቃ ከ04.7 ሰኮንዶች የሰፈሩ ናቸው፡፡ ኬንያውያን በ800፤ በ1500፤ በ3ሺ መሰናክልና በማራቶን የተያዙ የኦሎምፒክ ሪከርዶችን በመቆናጠጥ የተሻለ ውክልና አላቸው፡፡ በኦሎምፒክ መድረክ በሴቶች ምድብ በተመዘገቡ ሪከርዶች ኢትዮጵያ በሁለት አትሌቶች ስትጠቀስ ኬንያ ግን አንድም አላስመዘገበችም፡፡ በኢትዮጵያውያን የተያዙት ሁለት የረጅም ርቀት የኦሎምፒክ ሪከርዶች በ2008 እእአ ላይ በቤጂንግ ኦሎምፒክ ጥሩነሽ ዲባባ በ10ሺ ሜትር  29 ደቂቃ ከ54.66 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበችውና በ2012 እኤአ ላይ በለንደን በተካሄደው 30ኛው ኦሎምፒያድ ቲኪ ገላና በማራቶን ስታሸንፍ ርቀቱን የሸፈነችበት 2 ሰዓት ከ23 ደቂቃ ከ07 ሰኮንዶች ናቸው፡፡

Monday, 14 April 2014 09:59

የቀልድ - ጥግ

አንድ ባለመደብር ሰውዬ ወደ ሁሉን - አዋቂ ነኝ ባይ (Know it all) ወዳጁ ጋ ሄዶ፤
“ጠዋት ጠዋት ስነሳ ጤና አይሰማኝም፡፡ የዞረ-ምድር እንዳለበት ሰው ጥውልውል ያደርገኛል” አለው።
ሁሉን አዋቂው ሰውም፤ “ማታ ስትተኛ ወተት ጠጣ” አለው፡፡
ባለመደብሩ፤ “እኔማ በየማታው ወተት ሳልጠጣ አድሬ አላውቅም”
ሁሉን አዋቂነኝ - ባዩም፤ ወዲያው እጥፍ አለና፤ “ይሄውልህ ዋናው ችግርህ እሱ ነው፡፡”
“እንዴት”
“ቆይ ላስረዳህ፡፡ አየህ ወተቱን ትጠጣና አልጋህ ላይ ትወጣለህ ከዚያ ከግራ ወደቀኝ ትገላበጣለህ። ስትገላበጥ ወተቱ አይብ ያወጣል። ደሞ ስትገላበጥ ስትናጥ አይቡ ደግሞ ቅቤ ይወጣዋል፡፡ ከዛ ቅቤው ወደ ስብነት ይለወጣል። ስቡ ደወ ስኳርነት ይለወጣል። ቀጥሎ ስኳሩ ወደ አልኮልነት ይቀየራል። ስለዚህ ጠዋት ስትነሳ የዞረ-ምድር ናላህን ያዞረዋል። ለዚህ ነው የሚያጥወለውልህ!” አለና አብራራለት፡፡
*       *       *
አንድ ባለመደብር ሰውዬ ወደ ሁሉን - አዋቂ ነኝ ባይ (Know it all) ወዳጁ ጋ ሄዶ፤
“ጠዋት ጠዋት ስነሳ ጤና አይሰማኝም፡፡ የዞረ-ድምር እንዳለበት ሰው ጥውልውል ያደርገኛል” አለው።
ሁሉን አዋቂው ሰውም፤ “ማታ ስትተኛ ወተት ጠጣ” አለው፡፡
ባለመደብሩ፤ “እኔማ በየማታው ወተት ሳልጠጣ አድሬ አላውቅም”
ሁሉን አዋቂነኝ - ባዩም፤ ወዲያው እጥፍ አለና፤ “ይሄውልህ ዋናው ችግርህ እሱ ነው፡፡”
“እንዴት”
“ቆይ ላስረዳህ፡፡ አየህ ወተቱን ትጠጣና አልጋህ ላይ ትወጣለህ ከዚያ ከግራ ወደቀኝ ትገላበጣለህ። ስትገላበጥ ወተቱ አይብ ያወጣል፡፡ ደሞ ስትገላበጥ ስትናጥ አይቡ ደግሞ ቅቤ ይወጣዋል፡፡ ከዛ ቅቤው ወደ ስብነት ይለወጣል፡፡ ስቡ ደወ ስኳርነት ይለወጣል። ቀጥሎ ስኳሩ ወደ አልኮልነት ይቀየራል። ስለዚህ ጠዋት ስትነሳ የዞረ-ምድር ናላህን ያዞረዋል። ለዚህ ነው የሚያጥወለውልህ!” አለና አብራራለት፡፡

ከኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት
P.O Box 320608
Alexandera, Virginia 22320 USA
Email: This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
Cellphone:+1(202)32982503

“የንጉሱ ገመና” በሚል ርዕስ ስለታተመው መጽሐፍ ከኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ

በአሁኑ ጊዜ በሕይወት በሌሉት አቶ ስዩም ጣሰው ተፃፈ ተብሎ የሚነገርለትና በአቶ ግርማ ለማ ለሕትመት የበቃውን “የንጉሱ ገመና/ን/ ዳሰሳ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ያነበብኩት በአግርሞትና በኅዘን ተውጬ ነበር፡፡
መጽሐፉ የቀ.ኃ.ሥ አልባሽ የነበረ ሰውና በዚሁ ሥራው ንጉሱን ከማንኛውም የቤተመንግሰት ሠራተኞች በተሻለ ሁኔታ ሊቀርባቸው ይችላል በሚል መላ ምት ከቀ.ኃ.ሥ ስብዕና ጋር የማይዛመድ ተራ የመንደር ወሬና ስድብን የቋጠረ ዶሴ ሆኖ እንደሚፈረጅ ለአፍታም ጥርጣሬ የለንም፡፡
ከሟች አቶ ሥዩም ጣሰው በተሻለ ንጉሱን በቅርብ የሚያውቁ በሕይወት ያሉ እንደዚያን ዘመን አጠራር “የእልፍኝ አሽከሮች” መጽሐፉ ውስጥ የሰፈሩትን አሉባልታና ስድቦች “ተረት ተረት” ነው በማለት ብቻ ከመወሰን አልፈው ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ የአይን ምስክርነታቸውን ዘገባ በማቅረብ የዜግነት የውዴታ ግዴታቸውን እንዲወጡ በዚህ አጋጣሚ ወገናዊ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ፡፡
እዚህ ላይ መታወስ የሚባለው አንዱ ቁም ነገር አለ፡፡ ይኸውም ግፈኛው የደርግ አገዛዝ ቀ.ኃ.ሥ./ን/ በመግደል ብቻ ሳይወሰን የቀ.ኃ.ሥ./ን/ ስምና ሌጋሲ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ጥላሸት ማልበስን ሥራዬ ብሎ ተያይዞታል፡፡ ግፈኛው ሥርዓት የተገረሰሰ ቢሆንም ዘርቶ የሄደው ክፋት፤ ምቀኝነትና ስም ማጥፋት ግን ሕብረሰባችን ውስጥ ተንሰራፍቶ ስለሚገኝ የንጉሱ ገመናም የዚሁ ነፀብራቅ እንደሆነ አያጠራጥርም፡፡
ደግነቱ ግን ዛሬ የቀ.ኃ.ሥ ትክክለኛ ማንነት እውቅና ባገኙ ዓለምአቀፍ የታሪክ ፀሐፊዎች፤ የቀ.ኃ.ሥ ሕይወት ታሪክ ፀሐፊዎች (biographers) እንዲሁም የዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ለሕትመት እየበቃ የሚገኝበት ወቅት ላይ ስለምንገኝ የኢትዮጵያ ሕዝብ የንጉሱ ገመናን ግኝቶች ውድቅ እንደሚያደርገው እምነቴ ነው፡፡
መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ለአራት አስርተ ዓመታት ለቀ.ኃ.ሥ. ወደር የሌለው ፍቅርና ከበሬታን ቸሯቸው ኖሯል፡፡ የግል ሕይወታቸውም ቢሆን ከሕብረተሰቡ የተሰወረ አልነበረም፡፡ ሰው ናቸውና ስህተት አልሰሩም አይባልም፡፡ ቁም ነገሩ የፈፀሟቸው ስህተቶች ከአስገኟቸው የሶሽዮ ኢኮኖሚክ ድሎች ጋር ሲመዛዘኑ ግን ኢምንት ሆነው ይገኛሉ፡፡ ቀ.ኃ.ሥ ፈሪህ እግዚአብሔር ያደረባቸው አገር ወዳድና ባለ ራዕይ የነበሩ መሪ መሆናቸውን ዛሬ ታሪክ እየመሰከረ ይገኛል፡፡
ለዚህም ነው አንባቢያን ለንጉሱ ገመና ጊዜያቸውንና ገንዘባቸውን እንዳይቸሩት በትህትና ላሳስብ የምፈልገው፡፡ ታሪክ ደግሞ ደጋግሞ የሚያስተምረው ቁምነገር የሰው ስም ጥላሸት በመቀባት የሚገኝ ትርፍ አለመኖሩን ነው፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ
ልዑል ኤርምያስ ሳህለሥላሴ ኃይለሥላሴ  

 አንድ የህንድ አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ወደ አመሻሹ ላይ አንድ የህንድ የመንደር አለቃ በድንገት ሴት ልጁ ወደምትተኛበት ድንኳን ጥልቅ ይላል፡፡ ለካ ሴት ልጁ ከሰፈሩ ቆንጆ ጎረምሣ ጋር ተቃቅፋ ተኝታ ኖሯል፡፡ ያ ጎረምሣ በሰፈሩ ዝነኛ ጀግና በመባል የሚታወቅም ነው፡፡ “እንግዲህ” አለ አባትዬው “ልጄን አቅፈህ እስከ መተኛት ከደረስህ በሥርዐቱ ልታገባት ይገባል፡፡ ሆኖም በሥርዓቱ እንድታገባትም ብፈቅድልህ እንዲሁ አልሰጥህም”
ጎረምሣው ጀግናም፤
“ምን ማድረግ አለብኝ ጌታዬ?” ሲል ጠየቀ፡
አባትየው፤
“ፈተና እሰጥሃለሁ፡፡ ያንን ፈተና ካለፍክ ልጄን እድርልሃለሁ”
ጎረምሣው ጀግና፤
“ለእሷ ፍቅር ስል ማናቸውንም ፈተና እቀበላለሁ!” አለ በሙሉ ልብ፡፡
አባትየውና ጎረምሣው ጀግና ተያይዘው መንደሩ ውስጥ ወደሚገኘው ሐይቅ ሄዱ፡፡ ክረምት ስለገባ ብርዱ እጅ ይቆርጣል፡፡ ቅዝቃዜው በድን ያደርጋል፡፡ ሁለቱም ደራርበው ለብሰዋል፡፡ ከፊታቸው በስተቀር የሚታይ ሰውነት የለም፡፡
ያ ሀይቅ ረግቶ በረዶ ሰርቷል፡፡ ጠርዙ ላይ ቆሙ፡፡
አባትየው፤
“ይህን በረዶ ከስክሰህ ገብተህ፣ ወደዚያኛው የሐይቁ ዳርቻ ዋኝተህ፣ ሁለቱን ኪሎ ሜትር ጨርሰህ፣ እዚህ ተመልሰህ ትመጣለህ፡፡ ስትመለስ ታላቅ ፌሽታ አደርግልሃለሁ፡፡ ከዛ ልጄን በሠርግ ታገባታለህ” ይለዋል፡፡
ጎረምሣው ጀግናም፤
“ለእሷ ያለኝ ፍቅር ይህንን ወንድነቴን (manhood) የሚፈታተነውን ፈተና እንዳልፍ እንደሚያበረታታኝ አልጠራጠርም” አለ፡፡
ከዚያም በረዶውን እየከሰከሰ ቆፍሮ በበረዶው ውሃ ውስጥ ዋና ጀመረ፡፡ ከሶስት ሰዓት በኋላ የጎረምሳው ጀግና ወሬ ደብዛው ጠፋ፡፡ እምጥ ይግባ ስምጥ የሚያቅ ሰውም ጠፋ፡፡ በስምምነታቸው መሠረት አባትየው ምሽቱ ዐይን እስኪይዝ ድረስ  ጠበቀው፡፡ ለአንዴም ለሁሌም እንደሄደ፤ እንዳበቃለት አወቀ፡፡ ያን ቅዝቃዜ ተቋቁሞ ያ ጎረምሣ ለፍቅረኛው አልደረሰላትም፡፡
የመንደሩ አለቃ፤ ለዚያ ጎረምሳ፣ ለልጁ እጮኛ ማስታወሻ ይሆን ዘንድ ሐይቁ ስም እንዲወጣለት አደረገ፡፡
ይኸው እስከዛሬ ያ ሐይቅ፤
“ደደቡ ሐይቅ” በመባል ይታወቃል፡፡
*       *      *
ደደቡ ሐይቅ ላለመባል ግራና ቀኝ ማየት፤ አርቆ ማስተዋል፤ ግትር አለመሆን ይጠበቅብናል፡፡ አንድና አንድ ነገር ላይ ብቻ አተኩረን፣ እሱም ላይ ግትር ሆነን አንችለውም፡፡ ምክንያቱም ከየአቅጣጫው የሚቦረቡሩንን ችግሮች ስራዬ ብለን ስለማናያቸው አወዳደቃችን አያምርምና ነው፡፡ የምናደንቀውና የምናወራለት ነገር ሳናስበው ከወደቀ “ወርቅ ከዛገ ብረት ምን ሊሆን ነው?” እንዳለው ቻውሰር፤ “ያመኑት ፈረስ ጣለ በደንደስ” ይሆንብናል፡፡
በድህነት ላይ ሙስና ተጨምሮ የት እንደሚያደርስ ማንም ጅል አይስተውም፡፡ “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” ነው፡፡
“ከተማ ኢኮኖሚዋን በኮንትሮባንድ ላይ ከመሰረተች፤ አይዟችሁ፤ የጉምሩክም ሰራተኞች የደምቡን ጉርሻ ብቻ ነው የሚወስዱት” እያለ ይሳለቃል የአሜሪካው ተጓዥ ፀሀፊ ፒተር ማቴይሶን፡፡ ድርሻ ድርሻችንን ከወሰድን በኋላ፤ አገራችን እያደገች ነው ብሎ መለፈፍ ምን ያህል ቀላል እንደሚሆን መተማመን አያዳግትም፡፡ ትላልቆቹ አሳዎች የበሉትን በልተው ትናንሾቹ አሳዎች ላይ ቢላክኩ፤ የ “አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ” ታሪክ ያህል አስገራሚ ነው፡፡ (እርግጥ ትናንሾቹ አሳዎችም ትርፍራፊ አልለቃቀሙም ማለት አይደለም፡፡) ህዝብም ያንን አይቶ “ወይ አገሬ!” የሚል ቁጭት ቢያሰማ አይገርምም፡፡ ቁጭቱን ሲለማመደው ግን “እገሌ ከበላው፣ እገሌ የበላው ይበልጣል፤ እንወራረድ!” እያለ የዕለት ኑሮ ያደርገዋል፡፡
የፈረንሳዩ ፀሀፊ ዣን ዣክ ሩሶ፤
“በፈጣሪ እጅ የተሰራው ፍፁም ነበር፡፡ እሰው እጅ ሲገባ ይነክታል ይነትባል” ይለናል፡፡ ወይም በእኛ ቋንቋ “ይቸከላል!”፤ ወይም የድሮው መሪ እንዳሉት “ብታምኑም ባታምኑም ሞተናል!” ያሉት ዓይነት ነገር ይሆናል፡፡
“ቀይ የመንገደኛ መብራት ሲበራ ማለፍ ክልክል ነው” የሚል የእንስት ድምፅ በየመንታ መንገዱ መብራቶች ዙሪያ ይሰማል፡፡ ማንም ባለመኪና ባይሰማውም የሴትየዋ ድምጽ፤ ከመንገዱ መብራት ጋር ብቅ ይልና እንደማንኛውም የድምፅ የአየር ብክለት፤ ማለትም እንደጡሩምባው፣ እንደ ጩኸቱ፣ እንደ አውቶብሱ ገዝጋዥ ድምፅ ወዘተ መወትወቱን ይቀጥላል፡፡ ባለመኪናውም አይሰማም፤ እግረኛውም አይሰማም፡፡ መንገዱም አይሰማም፡፡ በማይሰማ ማህበረሰብ መካከል የቴክኖሎጂ ፋይዳ ምን ያህል እንደሆነ ሳይጠቁመን አይቀርም፡፡
ሙስና ቁመቱና ዐርቡ እንዲሁም ስፋቱ አህጉራችንን ያጥለቀለቀ ነው፡፡ እንደተስቦ ድንበርተኞቹን አገሮች ያዳርሳል፡፡ የእኛ ውስጥ ውስጡን በተምችም፣ በምችም፣ በምሥጥም ጀምሮ አሁን አሁን መስረቅም ሆነ መንጠቅ አሊያም መዝረፍ፤ ወደ ብዝበዛ ተሸጋግሮ እንደ ናይጄሪያና ኬንያ ዐይን-ያወጣ የሆነበት ደረጃ ለመድረስ አንድ ሐሙስ የቀረን ይመስላል፡፡
ኦባፌሚ አዎሎዎ የተባለው የናይጄሪያ ጠበቃና ፖለቲከኛ፣ “ብዙዎቻችን የምንስማማበት አንድ ነገር አለ፡፡ ይኸውም በአፍሪካ ማህበረሰብ ሙስናን ማጥፋት አዳጋች ሥራ መሆኑ ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም ዋናው ጣጣ፤ የማይቻል ዓላማ ማለማችን ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ የታችኛውን ሌባ የሚያስረው የላይኛው ሌባ መሆኑ ነው” ይለናል፡፡ እንግሊዞቹ who guards the guards እንደሚሉት መሆኑ ነው (ጠባቂዎቹን ማን ይጠብቃቸዋል እንደማለት ነው፡፡) ሥርዓቱ የፈቀደውን ሌብነት ያካሂዱ ዘንድ ዕድሉን አትከልክሏቸው፡፡ የሁላችንም የጋራ ሀብት ሌብነት ነውና ብንልም ያስኬዳል፡፡
ዛሬ መታሰርም እየቀለለ መጥቷል ይባላል፡፡ አንድ የአሥር ዓመት ፍርደኛ ያሉት ነገር እዚህ ላይ ተጠቃሽ ነው፡፡ “አይዟችሁ ብትታሠሩም የሰረቃችሁት ገንዘብ ያኖራችኋል፡፡” አንድ የዱሮ ባለሥልጣን እሥር ቤት ሲጎበኙ፤ “ይህ እሥር ቤት መታደስም፣ መስፋፋትም ይገባዋል፡፡ የወደፊት ቤታችን‘ኮ ነው!” አሉ፤ አሉ፡፡ አሉ ነዋ ነገራችን ሁሉ፡፡
The Strongest Poison ever known
Came from Caesar’s Laurel Crown
(auguries of Innocence)
“በዓለም ከታወቁት መርዞች፣ እጅግ በልጦ የተገኘው
ከቄሣር የወይራ ጉንጉን፣ ከዘውዱ የሚመጣው ነው” የሚለው ይሄ የዊሊያም ብሌክ ግጥም፤ የዓሳ ግማቱ ከጭንቅላቱ” ከሚለው የአማርኛ ተረት ጋር አብሮ-አደግ ነው፡፡ እኛ ስለዕድገት፣ ስለልማት ጧት ማታ እያወራን፣ ስለመልካም አስተዳደርና የሕግ የበላይነት እያወራን፤ ላይና ታች ሳይባል በየዕለቱ የሚሰማው የሙስና ጀብድ፤ አሳዛኝም አስደንጋጭም እየሆነ ነው፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የሚወሳለት ዕድገት በዚህ ሁሉ ሙስና ማህል አቋርጦ እንዴት እንደሚሸጋገር አሳሳቢ ነው፡፡ እንዴት ያገሳ ይሆን ያሉት በሬ እምቧ ይላል፤ እንደሚባለው እንዳይሆን ዐይናችንን ገልጠን እንይ!

‘ዘ ናይንቲ ናይን ሲሪየስ’ የተሰኘው የአይዳ ሙሉነህ ስራ

የታዋቂዋ ኢትዮጵያዊት ፎቶግራፈር አይዳ ሙሉነህ እና የኢትዮ-አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱ የስነ-ጥበብ ስራዎች፣ በፍራንክፈርት የሞደርን አርት ሙዚየም (MMK) ውስጥ  በተከፈተ አለም አቀፍ ኤግዚቢሽን በመታየት ላይ እንደሚገኙ ታዲያስ ከኒውዮርክ ዘገበ፡፡
ታዋቂ አፍሪካውያን ዘመናዊ አርቲስቶች ስራዎቻቸውን ያቀረቡበትና ጣሊያናዊው የ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን  ገጣሚ ዳንቴ በጻፈው ‘ዘ ዲቫይን ኮሜዲ’ የተሰኘ የግጥም ስራ የተሰየመው ‘ሄቨን፣ ሄል፣ ፑርጋቶሪ ሪቪዚትድ ባይ ኮንቴምፖራሪ አፍሪካን አርቲስትስ’ የተባለው አለም አቀፍ የስነ-ጥበብ ኤግዚቢሽን፣ እስከ መጪው ሃምሌ አጋማሽ ድረስ ለተመልካች ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡
በታዋቂው የስነ-ጥበብ አጋፋሪ ሲሞን ጃሚ እና በሞደርን አርት ሙዚየም ትብብር በተዘጋጀው በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ የቀረቡት ስራዎች፣ በቀጣይም በተለያዩ የአለም አገራት በሚገኙ አራት ቦታዎች ለእይታ እንደሚበቁ ተነግሯል፡፡
ከዚህ ቀደሞቹ  ከአፍሪካ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ኤግዚቢሽኖች በተለየ የአፍሪካ ስነ-ጥበብ፣ የድህረ ቅኝ-ግዛት ጉዳዮችን ማንጸባረቅ ብቻ ሳይሆን ውበትን አጉልቶ በማሳየት ጭምር ጥቅም ላይ ሊውሉ ይገባል በሚል እምነት የዘንድሮውን ኤግዚቢሽን እንዳዘጋጀ፣ ሞደርን አርት ሙዚየም አመልክቷል፡፡
‘ዘ ናይንቲ ናይን ሲሪየስ’  የተሰኘውን ጨምሮ የተለያዩ ስራዎቿን በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ ለእይታ ያበቃችው አይዳ ሙሉነህ፣ ከሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ በፊልም፣ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ሙያ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን፣ ስራዎቿን በተለያዩ ታላላቅ ኤግዚቢሽኖች ላይ ከማቅረብ ባለፈ፣ በርካታ አለማቀፍ ሽልማቶችን ለማግኘት የቻለች የፎቶግራፍ ባለሙያ ናት፡፡  
በአሁኑ ወቅት፣ ‘ደስታ ፎር አፍሪካ’ (DFA Creative Consulting plc.) የተባለና ትኩረቱን የፈጠራ ሥራዎች ላይ በማድረግ፤ ለአገር ውስጥና ለዓለም አቀፍ ገበያ የሚሆኑ የፈጠራ ሃሳቦችን የማማከር፣ ደረጃቸውን የጠበቁ ፎቶግራፎችን የማንሳትና ባህላዊ ዝግጅቶችን የማቀድ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ኩባንያ በማቋቋም፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የተለያዩ ስራዎችን በማከናወን ላይ ትገኛለች፡፡
የታላላቅ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን ታሪክ በሚተርከውና በቅርቡ ለህትመት እንደሚበቃ በሚጠበቀው ‘ተምሳሌት’ የተሰኘ መጽሃፍ ውስጥ የተካተቱት በርካታ ፎቶግራፎችም በአይዳ የተነሱ ናቸው፡፡
ነዋሪነቷ በኒውዮርክ የሆነው ኢትዮ-አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱም፣ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የስነጥበብ ትምህርቷን የተከታተለች በአለማቀፍ ደረጃ የምትጠቀስ ሰዓሊ ናት፡፡ የተለያዩ አለማቀፍ ሽልማቶችን የተቀበለች ሲሆን  የስዕል ስራዎቿም በከፍተኛ ዋጋ ተሸጠውላታል፡፡ ከእነዚህም መካከል፣ የዛሬ አራት ዓመት በታዋቂው አጫራች ድርጅት ሱዝቤይ አማካይነት፣ 1 ሚሊዮን 22 ሺህ  ዶላር (20 ሚሊዮን ብር ገደማ) የተሸጠላት ርዕስ አልባ ስዕሏ  ይጠቀሳል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን÷ በየመድረኩ ከሚሰማው የአክራሪነት ፍረጃና ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ እንቅስቃሴ ጋራ በተያያዘ የገጠሙትን የስም ማጥፋትና የማኅበሩን አገልግሎት የማሰናከል ወቅታዊ ተግዳሮቶች፣ ተቀራርቦ በግልጽ በመመካከርና በጸሎት መፍትሔ ለማስገኘት ሲያደርግ የቆየውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ፡፡
የማኅበሩ የሥራ አመራር ጉባኤ ከመጋቢት 27 - 28 ቀን 2006 ዓ.ም በአቡነ ጎርጎሬዎስ ት/ቤት አዳራሽ ባካሔደውና ከ46 የሀገር ውስጥና የውጭ ማእከላት የተውጣጡ 160 ያህል አመራሮች በተሳተፉበት የመንፈቅ ዓመት መደበኛ ስብሰባ በወቅታዊ ኹኔታዎች ላይ ባደረገው ግምገማ፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ ህልውናና በማኅበሩ አገልግሎት ቀጣይነት ላይ ተጋርጧል ያላቸውን ወቅታዊ ተግዳሮቶች በዝርዝር በማንሣት የመፍትሔ አቅጣጫ ማስቀመጡ ተጠቁሟል፡፡
የሥራ አመራር ጉባኤው ለማኅበሩ አስፈጻሚ አካል ባስቀመጠው የመፍትሔ አቅጣጫ፣ ማኅበሩ በቅ/ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደርያ ደንብ መሠረት ትውልዳዊ ተልእኮውን ለአባቶች በመታዘዝና በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በመወሰን የመፈጸም አሠራሩና ፍላጎቱ እንደጸና መኾኑንና ለወቅታዊ ተግዳሮቶቹ በግልጽ ተቀራርቦ ከመመካከርና ከጸሎት ውጭ በሌላ መንገድ የሚመጣ መፍትሔ ይኖራል ብሎ እንደማያምን አስታውቋል፡፡
የሥራ አመራር ጉባኤው በተዛባ አመለካከትና በሐሰተኛ ክሥ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባቶችና የመንግሥት አካላትን ግራ በማጋባትና በማሳሳት የማኅበሩን አገልግሎት ማስተጓጎል ዋነኛ አጀንዳ አድርገዋል ባላቸው ግለሰባዊና ቡድናዊ ቅስቀሳዎች ላይ በትኩረት መወያቱ ተነግሯል፡፡
መንግሥት ከሚያካሒደው የፀረ አክራሪነት ትግልና ከቤተ ክርስቲያኒቷ የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ አፈጻጸም ጋራ በማያያዝ የሚሰነዘሩበትን የስም ማጥፋት ዘመቻዎችና መሠረተ ቢስ ክሦች ከአባቶች፣ ከአስተዳደር ሓላፊዎች፣ ከሰንበት ት/ቤቶች፣ ከመንፈሳውያን ማኅበራትና ከመላው ምእመናን ጋራ ተቀራርቦ በመረዳዳትና በጸሎት ፍትሐ እግዚአብሔርን በመጠየቅ የመፍታት የወትሮ ጥረቱ ተጠናክሮ የሚቀጥልበትን አቅጣጫ ማስቀመጡንም ምንጮች ገልጸዋል፡፡
የማኅበሩ ዓላማና ፍላጎት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሐዋርያዊ ተልእኮ የሚነሣና ጥቅሙም ለቤተ ክርስቲያኒቱ በመኾኑ ከቤተ ክርስቲያኒቱና ከሀገሪቱ ህልውና የሚቀድም የተለየ የማኅበር (ቡድናዊ) ዓላማና ጥቅም እንደሌለም የሥራ አመራር ጉባኤው ያወጣው ውሳኔ ያመለክታል፡፡
አባላቱንና ተቋማዊ አሠራሩን በተመለከተ በማስረጃ ተደግፈው የሚቀርቡለትን ችግሮች ከመተዳደርያ ደንቡና ከውስጣዊ አሠራሩ አኳያ ያለማመንታት ለማረም ምንጊዜም ዝግጁ እንደኾነ የመከረው የሥራ አመራር ጉባኤው፥ ቤተ ክርስቲያናቸውን ከመከባከብ ባሻገር ለሀገራቸው ልማታዊ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ለማበርከት የሚበቃ አቅምና ሥነ ምግባር እንዳላቸው የሚያምንባቸውን ከ30ሺሕ መደበኛና ከግማሽ ሚልዮን በላይ ደጋፊ አባላት ያቀፈውን ይህን መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር በማበረታታት የድርሻውን እንዲወጣ ከማድረግ ይልቅ፣ በተለያዩ ክሦችና ውንጀላዎች ለማሸማቀቅ ያለዕረፍት የሚደረገው ሐሰተኛ ቅስቀሳና የክሥ ዘመቻ አግባብነት እንደሌለው ውጤትም እንደማያመጣ አስታውቋል፡፡    

የከባድ ሚዛን ቦክሰኞቹ ኢትዮጵያዊው ሳሚ ረታ እና ግብጻዊው አህመድ ሰኢድ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ሰላማዊ ግንኙነትን የማጠናከር አላማ ይዞ በሚዘጋጀውና በመጪው ግንቦት ወር መጨረሻ አዲስ አበባ ውስጥ በሚካሄደው የቦክስ ግጥሚያ አገራቸውን ወክለው እንደሚፋለሙ ተገለፀ፡፡
ኢትዮጵያዊው የከባድ ሚዛን ቦክሰኛ ሳሚ ረታ ባለፈው ሳምንት ለአናዶሉ ኤጀንሲ እንደተናገረው፣ ሁለቱ ቦክሰኞች ሰላማዊውን ፍልሚያ ለማካሄድ ተፈራርመው ቀን የቆረጡ ሲሆን  የአለም አቀፉ የቦክስ ፌዴሬሽንም ለውድድሩ እውቅና ሰጥቷል፡፡ ውድድሩን ያዘጋጀው ተቀማጭነቱ በአዲስ አበባ የሆነው ‘አፍሪካ ስፖርትስ ፕሮሞሽን’ የተባለ ድርጅት ሲሆን  የውድድሩ አላማም በሁለቱ አገራት መካከል ሰላማዊ ግንኙነትን ማጠናከር ነው፡፡ ውድድሩ፣ ‘አፍሪካውያን አንድ ህዝቦች ናቸው’ የሚል መልዕክት የሚያስተላልፍ ይሆናል ተብሏል፡፡ “ግጥሚያው የሁለቱን አገራት አንድነት የምናሳይበትንና ‘አለመተማመን ገደል ግባ!’ ብለን በጋራ የምናውጅበትን ዕድል ይፈጥራል” ብሏል ሳሚ ረታ፡፡ የአለም አቀፉ የቦክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚደንት ኦኔስሞ ኤ ንጎዊ በበኩላቸው፣ የውድድሩ መሰረታዊ አላማ በአፍሪካ አህጉር ሰላም እንዲሰፍን ማድረግ መሆኑን ጠቁመው፣ “በአፍሪካውያን  መካከል ህብረት መፍጠር” የሚለውን ይህን ታላቅ ሃሳብ ይዞ ለተነሳው ለሳሚ ረታ ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል፡፡
“ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ግድብ ለመስራት ውሳኔ ማሳለፏ አስደስቶኛል፡፡ አባይ ለሁሉም የሚበቃ የፈጣሪ ስጦታ ነው፡፡ ሁሉም አገራት በሰላማዊ ሁኔታ አብረው መኖር የሚችሉበትን እንዲሁም የፈጣሪን ስጦታ በትብብር መንፈስ የሚጋሩበትን መንገድ እንዲፈልጉ እንመክራለን” ብለዋል ንጎዊ፡፡
የቦክስ ግጥሚያው በናሽናል ኤርዌይስ ስፖንሰርነት በዲኤስ ቲቪ ሱፐር ስፖርት ቻናል በቀጥታ እንደሚሰራጭ የገለጸው ሳሚ፣ ግብጻዊው ተፋላሚው አህመድ ሰኢድም፣ በውድድሩ ለመሳተፍ በሙሉ ፈቃደኝነት ተስማምቶ ፊርማውን እንደማኖሩ፣ ቀኑን አክብሮ እንደሚመጣና እንደሚፋለሙም በእርግጠኛነት ተናግሯል፡፡
የውድድሩ ስፖንሰር የናሽናል ኤርዌይስ ባለቤት አቶ አበራ ለሚ በበኩላቸው፣ ኩባንያቸው የውድድሩን ሃሳብ ታላቅነት በመረዳትና በኢትዮጵያና በግብጽ መካከል ያለውን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በማጠናከር ረገድ የሚጫወተውን ሚና በማጤን፣ ግጥሚያውን ስፖንሰር ማድረጉን ለአናዶሉ ኤጀንሲ ተናግረዋል፡፡
የ32 አመቱ የከባድ ሚዛን ቦክሰኛ ሳሚ ረታ፣ ከዚህ በፊት ካደረጋቸው 21 የቦክስ ግጥሚያዎች፣ በ18ቱ ማሸነፉን ለኤጀንሲው ገልጿል፡፡

“ተጨባጩንና እውነተኛውን ነገር በጠበቃዬ በኩል ለፍ/ቤት አቅርቤያለሁ”

በተለይ “ገመና” በተሰኘው ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ ላይ የዶ/ር ምስክርን ገፀ-ባህሪ ተላብሶ በመጫወት እውቅናን ያተረፈው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ የ600 ሺህ ብር ክስ የተመሠረተበት ሲሆን አርቲስቱ ለተከሰሰበት ጉዳይ ምላሽ እንዲሰጥ ፍ/ቤቱ ለትላንትና ትዕዛዝ አስተላልፎ ነበር፡፡
ክሱ መመስረቱን ያልካደው አርቲስት ዳንኤል፤ ሆኖም “ክሱ መሰረተ ቢስና ከእውነት የራቀ መሆኑን በመግለፅ ተጨባጩን እውነታ አስፍሬ በጠበቆቼ በኩል ለፍ/ቤት ምላሽ ሰጥቻለሁ” ብሏል - ጉዳዩ በፍ/ቤት የተያዘ በመሆኑ ከዚህ በላይ ለመናገር እንደማይፈልግ በመግለፅ፡፡
አርቲስት ዳንኤልና ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ፤ “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ፊልም ወደ አማርኛ በመመለስ አብረው ለመስራት ውል ተፈራርመው የነበረ ሲሆን “አርቲስቱ በገባው ውል መሰረት ስራውንም አልሰራም ብሬንም አልመለሰም” በማለት ወ/ሮ ቤተልሄም የ662 ሺህ 120 ብር ክስ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 6ኛ ፍትሀ ብሔር ቢፒአር ችሎት መመስረታቸው  ታውቋል፡፡
አርቲስት ዳንኤል “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ፊልም ወደ አማርኛ በመመለስ ስምንት ያህል ትዕይንቶችን ከቀረፀ በኋላ አቋርጦ “የሴም ወርቅ” የተሰኘ ሌላ ፊልም መስራት የጀመረ ሲሆን በዚህ ወቅት ነበር ወ/ሮ ቤተልሔም እሱ የጀመረውን ፊልም “አብረን  እንስራ” የሚል ጥያቄ ያቀረቡለት- አርቲስቱ በቅርቡ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፡፡
አርቲስቱ የጀመረውን “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ ፊልም ከወ/ሮ ቤተልሔም ጋር አብረው ለመስራት ተስማምተው ከተዋዋሉ በኋላ ወደ ሥራው የገቡ ቢሆንም በኋላ ላይ “ወ/ሮዋ የስነ ምግባር ጉድለት ስላለባቸው አብሬያቸው መስራት አልቻልኩም” በሚል ዳንኤል ስራውን ያቆመ ሲሆን ወ/ሮ ቤተልሄም በበኩላቸው፤አርቲስቱ በውሉ መሰረት ፊልሙን በጊዜ ሰርቶ ባለማስረከቡ ብሩን እንዲመልስ መጠየቃቸውንና እሱም ብር አልወሰድኩም በማለቱ ግጭቱ እንደተካረረ መዘገቡ  ይታወሳል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የኢትዮፒካሊንክ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጆች ከወ/ሮ ቤተልሄም ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፣“የስም ማጥፋት ዘመቻ አካሂደውብኛል” ያለው አርቲስቱ፤በግለሰቧና በአዘጋጆቹ ላይ ክስ መመስረቱን ታህሳስ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ለንባብ በበቃው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ተናግሯል፡፡
ወ/ሮ ቤተልሔም የካቲት 7 ቀን 2006 ዓ.ም በአርቲስት ዳንኤል ላይ የ662ሺህ 120 ብር ክስ መመስረታቸውን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ ከሳሿ የቼክ ቁጥሮችን በማስረጃነት አያይዘው ለፍ/ቤቱ እንዳቀረቡ ገልፀዋል፡፡ ምንጮች እንደሚሉት፤ ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ ወደ ክስ ለመሄድ የተገደዱት ለፊልሙ መስሪያ ብለው ለአርቲስቱ የሰጡትን ገንዘብ እንዲመልስ ሲጠይቁት “ብር አልወሰድኩም” በማለቱ ነው፡፡ ፍ/ቤቱ አርቲስት ዳንኤል ለቀረበበት ክስ በትላንትናው እለት ምላሽ እንዲሰጥ  ትዕዛዝ አስተላልፎ የነበረ ሲሆን አርቲስቱም ምላሹን በጠበቆቹ በኩል ለፍ/ቤት ማስገባቱን ገልጿል። ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን ተመልክቶ ብይን ለመስጠት ለሚያዚያ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡