Administrator

Administrator

Saturday, 08 August 2015 09:20

የፀሐፍት ጥግ

(ስለጨለምተኝነት)
- ወጣት ጨለምተኛን እንደማየት አሳዛኝ
ነገር የለም፡፡
ማርክ ትዌይን
- ለጨለምተኛ ሃውልት ቆሞለት አይቼ
አላውቅም፡፡
ፖል ሃርቬይ
- ጨለምተኛ ማለት እውነትን ያለጊዜው
የሚናገር ሰው ነው፡፡
ሲራኖ ዲ በርግራክ
- ሙሉ በሙሉ ጨለምተኛ ነኝ ብዬ
አላስብም፡፡ ስለዚህ በሁሉም ፊልሞቼ
ውስጥ ተስፋን የምታዩ ይመስለኛል፡፡
ስፓይክ ሊ
- እኔ ራሴን እንደ ተስፈኛም ሆነ
እንደጨለምተኛ አልቆጥርም፡፡
ኒክ ቦስትሮም
- ጨርሶ ጨለምተኛ አይደለሁም፤ ነገር ግን
ተስፈኛም አልባልም፡፡
ናቴ ሎውማን
- ጨለምተኛ አንድም ጦርነት አሸንፎ
አያውቅም፡፡
አይዞንሃወር
- ዓለምን ስመለከት ጨለምተኛ ነኝ፤ ሰዎችን
ስመለከት ግን ተስፈኛ ነኝ፡፡
ካርል ሮጀርስ
- ጨለምተኝነት ወደ ደካማነት፣ ተስፈኝነት
ወደ ጥንካሬ ይመራል፡፡
ዊሊያም ጄምስ
- ተስፈኞችም ጨለምተኞችም
ለህብረተሰባችን የሚያበረክቱት አስተዋፅኦ
አለ፡፡ ተስፈኛ አውሮፕላንን ሲፈጥር፣
ጨለምተኛ ፓራሹትን ይፈጥራል፡፡
ጂ.ቢ.ስተርን
- ተስፈኛ አዲሱ ዓመት መጥባቱን ለማየት
እስከ እኩለ ሌሊት ሲጠብቅ፣ ጨለምተኛ
አሮጌው ዓመት መሰናበቱን ለማረጋገጥ
እስከ እኩለ ሌሊት ይጠብቃል፡፡
ቢል ቫውግን
- ጨለምተኝነቴ የጨለምተኞችን ሀቀኝነት
እስከመጠራጠር ድረስ ይዘልቃል፡፡
ኢድሞንድ ሮስታንድ
- ጨለምተኛ ማለት፤ ዕድል ስታንኳኳ
በኳኳታው ድምፅ የሚያማርር ሰው ነው፡፡
ኦስካር ዋይልድ
- የጨለምተኛነት መሰረቱ ፍርሃት ብቻ
ነው።
ኦስካር ዋይልድ
- ምንጊዜም ቢሆን ከጨለምተኛ ሰው
ላይ ገንዘብ ተበደሩ፤ ይከፍሉኛል ብሎ
አይጠብቅም፡፡
ያልታወቀ ደራሲ

‹‹በመዝባሪ ላይ አልደራደርም፤ እስከ መጨረሻው ከፊት ለፊት ነኝ››

    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአድባራቱን ሰፋፊ መሬቶችና የገቢ ማስገኛ ተቋማት እየመዘበሩ ራሳቸውን ያበለጸጉ የአስተዳደር ሓላፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ መመሪያ ሰጡ፡፡
የአስተዳደር ሓላፊዎቹ የአድባራቱን ሰፋፊ መሬቶችና የንግድ ተቋማት ያለጨረታ ከገበያ ዋጋ በታች ከ15 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ በመዋዋል የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥቅሞች አሳልፈው በመስጠት ራሳቸውን አበልጽገዋል- ተብሏል፡፡
ፓትርያርኩ መመሪያውን የሰጡት፣ ላለፉት ስምንት ወራት በሀገረ ስብከቱ አድባራትና አንዳንድ ገዳማት የመሬት፣ የሕንፃና የልዩ ልዩ ገቢ ማስገኛ ተቋማት ኪራይ ተመንን ሲያጣራ የቆየው ኮሚቴ ያዘጋጀው ጥናታዊ ሪፖርት ከጠቅላይ ጽ/ቤቱ የውሳኔ ሐሳብ ጋር ከትላንት በስቲያ ከቀረበላቸው በኋላ ነው፡፡
በፓትርያርኩ መመሪያ የተቋቋመው ኮሚቴው፣ በ51 አድባራት መሬት፣ ሕንፃና ሕንፃ ነክ ጉዳዮች ላይ ባካሔደው ጥናት የተጠቆሙት የመፍትሔ ሐሳቦችና በዋና ሥራ አስኪያጁ በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ሰብሳቢነት የሚመራው የአስተዳደር ጉባኤ የተስማማባቸው የመፍትሔ ሐሳቦች በሙሉ ተፈጻሚ እንዲኾኑ አቡነ ማትያስ ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡
በጥናቱ ሒደት የኮሚቴውን አባላት በጥቅም ለመደለል ከመሞከር ጀምሮ በማስፈራራትና ስም በማጥፋት የማጣራት ሥራውን ለማስተጓጐል ሲጥሩ የነበሩ ሐላፊዎች፣ በመፍትሔው አተገባበር ላይም ዕንቅፋት ሊፈጥሩ ይችላሉ ለሚለው ስጋት ፓትርያርኩ በሰጡት ምላሽ፤ ‹‹ወደ ኋላ ወደ ጎን የለም፤ ወደፊት ነው፤ በቤተ ክርስቲያን ሀብት ምዝበራ ከማንም ጋር አልደራደርም፤ ከጎኔ ኹኑ፤ እስከ መጨረሻው ከፊት ለፊት ነኝ›› ሲሉ በቁርጠኝነት ተናግረዋል፡፡
በጥናታዊ ሪፖርቱ እንደቀረበው፤ የገቢ ማስገኛ የንግድ ተቋማቱ፣ ከአዲስ አበባ የመሬት ገበያ አንጻር ሊታሰብ ከማይችልበት ዝቅተኛው በካሬ ሜትር 0.37 ሳንቲም፣ ከፍተኛው ብር 70 ያለጨረታ ከ15 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ የኪራይ ውል ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ይህም ጥቂት ሙሰኛ የደብር ሓላፊዎችና ግለሰብ ነጋዴዎች ሚልየነር እንዲኾኑበት ዕድል በመስጠት ቤተ ክርስቲያኒቱን የበይ ተመልካች እንዳደረጋት ተገልጧል፡፡
የአድባራት አለቆች፣ ጸሐፊዎች፣ ሒሳብ ሹሞችና የሰበካ ጉባኤ አባላት በተገኙበት በተካሔደው ማጣራት ለጥናት ቡድኑ መረጃ በመስጠታቸውና ጥያቄ በማንሣታቸው ከመመሪያ ውጭ ከሓላፊነታቸው የታገዱት፣ የአራዳ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር ዋና ተቆጣጣሪ መጋቤ ጥበብ ወርቁ  አየለና የደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን ዋና ሒሳብ ሹም ወ/ሮ መና የማነ ብርሃን ሥዩም ወደ ቀድሞ የሓላፊነታቸውና ቦታቸው እንዲመለሱ በአስተዳደር ጉባኤው ተወስኗል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሕግ አገልግሎት መምሪያ፤ ሙሰኛ ሓላፊዎችን ለሕግ ከማቅረብ በተጨማሪ  የገቢ ማስገኛ ተቋማቱ ለሦስተኛ ወገን እየተላለፉ የተሰጡበትን ውሎች በመሰረዝ የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥቅም የሚያስከብርና የሚያስቀድም ወጥ አሠራር እንዲዘረጋ ተወስኗል፤ ተቋማቱም በየአጥቢያው በተናጠል የሚተዳደሩበት አካሔድ ቀርቶ በማዕከል የሚመሩበት ሥርዐት እንደሚበጅ የተጠቆመ ሲኾን፤  ይህንንም የሚያስፈጽም ጽ/ቤትና ፓትርያርኩ የሚሰበስቡት ቦርድ እንደሚቋቋም ታውቋል፡፡
የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት በኾነው አዲስ አበባ፣ ጥናቱ ባልሸፈናቸው ሌሎች አድባራትና ገዳማትም እንዲቀጥል አቡነ ማትያስ ያዘዙ ሲኾን በመጪው ዓመት ጥቅምት በሚካሔደው 34ኛው ዓመታዊ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤም በአገር አቀፍ ደረጃ እንዲተገበር በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንዲወሰንበት እንደሚያደርጉም አስታውቀዋል፡፡

    አዲስ አመራር እንደሚመረጥ ይጠበቃል

      ሰማያዊ ፓርቲ የመጀመሪያውን ጠቅላላ ጉባኤ ነሐሴ 16 እና 17 የሚያካሂድ ሲሆን በዚህ ጉባኤ አዲስ መራር ይመረጣል ተብሎም ይጠበቃል፡፡ በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት ጠቅላላ ጉባኤ የሚደረገው በየ3 ዓመቱ መሆኑን የጠቀሱት የፓርቲው ብሄራዊ ም/ቤት ሰብሳቢ አቶ ሰይድ ኢብራሂም፤ ጉባኤው በሐምሌ መካሄድ የነበረበት ቢሆንም በአንዳንድ ምክንያቶች ምክር ቤቱ ለ3 ወር የማራዘም ስልጣኑን ተጠቅሞ እስከ ነሐሴ ማራዘሙን ገልፀዋል፡፡ በጉባኤው ላይ የሚሳተፉ አባላት ቁጥርና የጉባኤውን አካሄድ ለመወሰን ብሄራዊ ምክር ቤቱ በነገው እለት ስብሰባ እንደሚያደርግም ሰብሳቢው ተናግረዋል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውን እንዲያሳልጥ የተቋቋመው ኮሚቴምበእለቱ ሪፖርቱን ያቀርባል ብለዋል፡፡ በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት አንድ ፕሬዚዳንት ለሁለት የስልጣን ዘመን ብቻ መመረጥ እንደሚችል የጠቆሙት አቶ ሰይድ፤ በአሁኑ ወቅት ፓርቲውን የሚመሩት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለሁለተኛ ጊዜ ይወዳደሩ አይወዳደሩ እስካሁን እንዳላሳወቁ ተናግረዋል፡፡

ለዓመታት የአዕምሮ ሆስፒታል የቆየ አንድ ሰው ነበረ፡፡ ተሽሎት ከሆስፒታሉ ይውጣ ከተባለ በኋላ
ዶክተሩ እስቲ ለማንኛውም ቃለ - መጠይቅ ላድርግለት ብሎ ያስጠራውና፤
“እስቲ አንድ ነገር ንገረኝ፡፡ አሁን ከዚህ ሆስፒታል ብትወጣ ኑሮህን እንዴት አድርገህ ለመምራት ታስባለህ?” አለው፡፡ ሰውዬውም፤ “መቼም ተመልሼ ህይወት መጀመሬ በጣም ድንቅ ነገር ነው፡፡
ኑሮዬን ለመምራት የመጀመሪያ እርምጃዬ ዱሮ የሠራኋቸውን ስህተቶች አለመድገም ነው። የኒኩሊየር
ፊዚክስ ባለሙያ ነበርኩ፡፡ የኒኩሊየር መሣሪያ ጥናትና ምርምር ነበር አዕምሮዬ እንዲነካ ያደረገው፡፡
ከዚህ ብወጣ ወደ ንፁሁ ንድፈ - ሀሳብ ላይ ብቻ አተኩራለሁ፡፡ ያ ብዙ የማያስጨንቀኝ ስለሆነ
ሰላም አገኛለሁ”
የአዕምሮ ሐኪሙ፡-
“ድንቅ ነው!” አለ በመደሰት፡፡
“አለበለዚያ ደግሞ” አለና ቀጠለ ሰውዬው፤ “ላስተምርም እችላለሁ። የሳይንቲስት ትውልድ የማፍራት ኃላፊነት ያለብን ይመስለኛል፡፡ በዚያ ረገድ ላግዝ እችላለሁ፡፡” “በጣም ትልቅ ሀሳብ ነው” አለ የአዕምሮ ሀኪሙ፡፡ “ሌላው አማራጬ ደግሞ መፃፍ ነው፡፡ ህዝባችን የሳይንስ መፅሀፍ ዕጥረት አለበት፡፡ ወይም ደግሞ
በዚህ መልካም ተቋም ውስጥ ስላገኘሁት ልምድ ልፅፍም እችላለሁ፡፡” “ያማ በጣም የጠለቀ፣ ግሩም አማራጭ ነው” አለ ሀኪሙ፡፡ “በመጨረሻም” አለ የአዕምሮ ህመምተኛው፤
“በመጨረሻም፤ እነዚህ ሁሉ አማራጮች እምቢ ካሉኝ፣ በቃ የቡና ጀበና መሆኔን እቀጥላለሁ!” አለ፡፡
ሐኪሙ ጭንቅላቱን ይዞ፤
“በል እዚሁ ቁጭ በል!” አለው፡፡
*       *      *
ደህና ሄደን ከመቆልመም ይሰውረን፡፡ የጀመርነውን በአግባቡ ለመጨረስ ጥናቱንም ፅናቱንም ይስጠን! በሙስና ከመመንደግ፣ ቁልቁል ከማደግ ዲበ - ኩሉ ይጠብቀን! ከሸፍጠኛ ዳኛ፣ ከአባይ መስካሪ ያድነን! የመጪውን ዓመት ትምህርታችንን ይግለጥልን! ያለፈውን ዓመት ስህተታችንን እንዳንደግም ልብና ልቡና ይስጠን፡፡ ከውጪ ሸረኛ፣ ከውስጥ ቂመኛ ይጠብቀን፡፡ ሀገራችን “ደንጊያና ቅል ተላግቶ፣ ዜጋና ሹም ተሟግቶ አይሆንም” የማንልባት ሀገር መሆን ይኖርባታል፡፡ ሹም ሲበድል ዝም ብለን የማናይበት፣ ዜጋ መብቱን ሳያውቅ ሲቀር ምክንና ውጤቱን በወግ በወጉ የምናስረዳበት ሁኔታ እንዲኖር መጣር ይኖርብናል፡፡ “እናቱ ወንዝ የወረደችበትም እናቱ የሞተችበትም እኩል የሚያለቅሱበት” ሀገር መሆን የለባትም፡፡ ከቶውንም ሃይማኖታዊ አስተምህሮት ከፖለቲካዊ ጥቅም ፍለጋ ተለይተው የሚታዩበት ሀገር ታስፈልገናለች፡፡ ከሁሉም በላይ ዛሬ ሐሳዊ - ዲሞክራሲን (Pseudo - democracy) መዋጋት ግዴታ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ በአስመሳይነት በአደባባይ መደስኮርና ዕውነተኛው ዲሞክራሲ ለየቅል ናቸው! መንግሥት የአምስት ዓመቱን ዕቅድ አፈፃፀም ድክመትን በወጉ ገምግሞ ዓይነተኛ መፍትሄ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ የእከክልኝ ልከክልህን ዜማ ቅኝቱን በመሰረታዊ መልኩ መለወጥ ይኖርበታል፡፡
በተለይም ደግሞ በሂደቱ ውስጥ ዓይን እንደሚቆረቁር አሸዋ ሲያስቸግር የነበረውን ሙስና በቅጡ
መፈተሽ ይኖርበታል፡፡ ዛሬም የፍትህን፣ የሰብዓዊ መብቶችን፣  የትምህርት ሂደትን ጉዳይ በአፍዓዊ መልኩ ሳይሆን በልባዊ መልኩ መመርመር መሰረታዊ ነገር ነው፡፡ ይህ ካልሆነ “እያቃጠለ ከሚያጠግበኝ፣ እስኪቀዘቅዝ ይራበኝ” የሚለውን መጥቀስ ግድ ይሆናል፡፡ ከዚህም ይሰውረን!

 በታንዛኒያ ከተማ ዳሬሰላም 13  ክለቦችን በማሳተፍ ሲካሄድ የቆየው 48ኛው የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንሺፕ (ካጋሜ ካፕ) ትናንት በግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎች ቀጥሏል፡፡
ከግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎቹ በፊት በተደረጉት 26 ጨዋታዎች 74 ጎሎች ተቆጥረዋል፡፡ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.54 ጎሎች ማለት ነው፡፡
የኡጋንዳው ክለብ ካምፓላ ሲቲ የሱዳኑን አልሃሊ ሸንዲ 3ለ0 በማሸነፍ እንዲሁም ሌላው የኡጋንዳ ክለብ አዛም የታንዛኒያውን ያንግ አፍሪካንስ በመለያ ምት 5ለ3 አሸንፎ ለግማሽ ፍፃሜ ደርሰዋል፡፡ ሁለቱም ክለቦች በምድብ 3 ከአዳማ ከነማ ጋር የተደለደሉ ነበሩ፡፡ በግማሽ ፍፃሜ እርስበራስ ተገናኝተዋል፡፡ ሌሎቹ የግማሽ ፍፃሜ ተፋላሚዎች የሱዳኑ አል ካርቱም እና የኬንያው ጎሮማሃያ ናቸው፡፡ አልካርቱም በሩብ ፍፃሜ የሩዋንዳውን ኤፒአር 4ለ0 ሲረታ ጎሮማሃያ ደግሞ የደቡብ ሱዳኑን አል ማላይካ 2ለ1 በማሸነፍ ለግማሽ ፍፃሜው ደርሰዋል፡፡ ትናንት ሁሉም የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎች ተደርገዋል፡፡
ኢትዮጵያን በመወከል የተሳተፈው  አዳማ ከነማ በምድብ 3 ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች ተሸንፎ በጊዜ የተሰናበተው ምንም ነጥብ ሳያስመዘግብ በሰባት የግብ እዳ ነው፡፡  በምድብ 3 የመጀመርያ ጨዋታውን ከደቡብ ሱዳኑ ክለብ ማላይካ ጋር ባደረገበት ወቅት በ30ኛው ደቂቃ ታከለ አለማየሁ ባስቆጠረው ግብ  አዳማ ከነማ መምራት ቢችልም በመጨረሻ 2ለ1 ነበር የተሸነፈው፡፡  በሁለተኛው ጨዋታ ተገናኝቶ የነበረው ከኡጋንዳው ተወካይ ኬሲሲ ጋር ነበር፡፡  በ79ኛው ደቂቃ ያቆብ ፍስሃ በፈፀመው ፋውል ፍፁም ቅጣት ከተሰጠበት በኋላ የኬሲሲ አምበል  ጎሉን በማስቆጠሩ 1ለ0 ተሸንፏል፡፡ በምድብ 3 የመጨረሻ ጨዋታውን ከታንዛኒያ ክለብ አዛም ጋር አድርጎ 4ለ0 ከተሸነፈ በኋላ ከውድድሩ መሰናበቱ ይታወቃል፡፡ በሴካፋ የክለቦች ሻምፒዮና ካጋሜ ካፕ ታሪክ የኢትዮጵያ ክለቦች ውጤታማነት ቢያንስ ከአምስት የዞኑ አባል አገራት ከኬንያ፤ ኡጋንዳ፤ ታንዛኒያ፤ ሩዋንዳና ብሩንዲ ያነሰ ነው፡፡ በክለቦች ሻምፒዮናው ኢትዮጵያን የወከለ ክለብ ያስመዘገበው ትልቁ ውጤት ቅዱስ ጊዮርጊስ በ2010 እኤአ ላይ ለዋንጫ ጨዋታ የደረሰበት ብቻ ነው፡፡ በምስራቅ አፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮና ላይ እጅግ ውጤታማው ክለብ የታንዛኒያው ሲምባ ሲሆን ባገኛቸው ስድስት ዋንጫዎች ነው፡፡ የኬንያው ኤፍሲ ሊዮፓርድስ፤ የታንዛኒያው ያንግ አፍሪካንስ፤ የኬንያዎቹ ጎሮማሃያ እና ታስከር ኤፊሲ እኩል ለ5 ጊዜያት ዋንጫዎችን በመውሰድ በከፍተኛ ውጤት ሁለተኛ ደረጃን ተጋርተዋል፡፡ የሩዋንዳው ኤፒአርና የሱዳኑ አልሜሪክ እያንዳንዳቸው ሁለት ዋንጫዎችን ሲቀዳጁ፤ የኡጋንዳው ኬሲሲ፤ የሩዋንዳው አትራኮን፤ የኡጋንዳው ፖሊስ ኤፍሲ፤ የሩዋንዳው ራዮን ስፖርትስ፤ እንዲሁም የብሩንዲው ቪታሎ ኦ ቢያንስ አንድ ጊዜ የዋንጫው ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ በአገር ደረጃ ደግሞ የኬንያ ክለቦች 15 ጊዜ ሻምፒዮን በመሆን ሲመሩ፤የታንዛኒያ ክለቦች በ11 የዋንጫ ድሎች ይከተሏቸዋል፡፡ የኡጋንዳ ክለቦች 5 ጊዜ፤ የሩዋንዳ ክለቦች 4 ጊዜ ፤ የሱዳን ክለቦች 3 ጊዜ እንዲሁም አንድ የብሩንዲ ክለብ የዋንጫ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
በዓለም አቀፉ የእግርኳስ ፌደሬሽኖች ታሪክ እና አሃዛዊ መረጃ አሰባሳቢ ማህበር (IFFHS) መሰረት ባለፉት 10 ዓመታት ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች የደረጃ ዝርዝር እስከ 10ኛ እንድም ኢትዮጵያዊ ክለብ የለበትም፡፡ በደረጃ ሰንጠረዡ በዝተው የሚገኙት የኡጋንዳ፤ የኬንያ፤ የታንዛኒያና የብሩንዲ ክለቦች ናቸው፡፡ በአይኤፍኤችኤችኤስ መለኪያ መሰረት ባለፉት 10 ዓመታት ባስመዘገበው ውጤት አንደኛ ደረጃ የተሰጠው የታንዛኒያው ክለብ ሲምባ ነው፡፡ በመቀጠል ደረጃውን አከታትለው እስከ 4ኛ ደረጃ የያዙት የኡጋንዳ ክለቦች ኤስሲ ሲቪላ፤ካምፓላ ሲቲ ኬሲሲ እና ኤክስፕረስ ናቸው፡፡ የኬንያው ታስከር፤ የኡጋንዳው ዪአርኤ፤ የታንዛኒያዎቹ ያንግ አፍሪካንስና ሚትብዋ ሹገር፤ የኬንያው ማታሬ ዩናይትድ፤ የብሩንዲው ኡሊንዚ ስታርስ እና ሶኒ ሹገር እስከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡
የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች በአንፃሩ በህጉራዊ የክለብ ውድድሮች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ ብዙም ውጤታማ አይደሉም፡፡ የሱዳን ክለቦች አልሁላል፤ ኤልሜሪክ በቅርብ አመታት በሻምፒዮንስ ሊግ ያስመዘገቡት ስኬት ብቻ ለየት አድርጎ አውጥቷቸዋል፡፡የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በሚያወጣው የየአምስት ዓመቱ የአህጉራዊ ክለቦች የውጤት ደረጃ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ላይም የሱዳን ክለቦች በ33 ነጥብ 5ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ክለቦች በ4 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ አሁንም የሱዳን ክለቦች በ31 ነጥብ አምስተኛ ሲሆኑ፤ የኢትዮጵያ በ7 ነጥብ 17ኛ ናቸው፡፡

 ለ2008 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ለማለፍ የሚካሄደውን የብሄራዊ ሊግ ማጠቃለያ ውድድር የድሬዳዋ ከተማ እንደምታስተናግድ ተገለፀ፡፡ የብሄራዊ ሊግ ማጠቃለያ ውድድሩ ነሃሴ 17 ይጠናቀቃል የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን መግለጫ እንዳመለከተው በዋናነት በአብይ ኮሚቴ እንዲሁም ለውድድሩ በተመደቡ  24 ታዛቢዎችና አርቢትሮች እና ልዩ ልዩ አገልግሎት ሰጪዎችና  አስፈጻሚዎች በጽህፈት ቤት መመደባቸውን አስታውቋል፡፡
ውድድሩ በ2007 ዓ.ም ስራ ላይ በዋለው የብሄራዊ ሊግ ውድድር ደንብ መሰረት  እንደሚካሄድ እና ከደንቡ የወጣ የውድድር ማስፈጸሚያ ሰነድ ለእዚሁ ውድድር ሲባል ተዘጋጅቷል፡፡  የፌደሬሽኑ መግለጫ 24ቱ ተወዳዳሪ ክለቦች የምድብ እጣ ድልድላቸውን ሃምሌ 24 ቀን ካወቁ በኋላ፤ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳዳር ቡድን የመክፈቻ የነጥብ ጨዋታውን በእጣ ከሚደለደልለት ቡድን ጋር ሀምሌ 25 በማካሄድ እንደሚጀመር አመልክቷል፡፡
በብሄራዊ ሊግ ለመወዳደር ውል የገባ ተጨዋች የውል ጊዜው የሚያበቃው የውድድሩ መርሃ ግብር ሲጠናቀቅ እንደሆነም ፌዴሬሽኑ አስገንዝቧል፡፡
የስፖርታዊ ጨዋነት ተሸላሚው ቡድን የሚለየው በቢጫና ቀይ ካርድ፣ በፖዘቲቭ ጨዋታ፣ ለተጋጣሚ ክብር በመስጠት ፣ለዳኞች ክብር በመስጠት እንዲሁም በቡድን አባላትና ደጋፊዎች ስፖርታዊ ጨዋነት መመዘኛዎች መሰረት እንደሚሆን፣ በአጠቃላይ ውድድሩ ሻምፒዮን የሚሆነው ቡድን የዋንጫ እንዲሁም የ35 ወርቅ ሜዳሊያዎች ሽልማት እንደሚሆኑ ሁለተኛና ሶስተኛ የሚወጡ ቡድኖች ደግሞ እያንዳንዳቸው የ35 ብርና የነሃስ ሜዳሊያዎች ተሸላሚ ይሆናሉ የፌደሬሽኑ መግለጫ ገልጿል፡፡ ከየምድቡ አንደኛ በመውጣት ያለፉት 8 ቡድኖች ውድድሩ ሲጀመር ዋንጫ እንደሚሸለሙ፤ በዞን ተከፋፍሎ በተካሄደው ውድድር ከፍተኛ ግብ ያስቆጠረው ተጨዋች ተሸላሚ እንሚሆንና ከፍተኛ ግብ ያስቆጠሩት ተጨዋቾች ሁለት አና ከዚያ በላይ ከሆኑ ሽልማቱን እኩል እንደሚካፈሉ እንዲሁም በ24ቱ ቡድኖች ወድድር ከፍተኛ ግብ ለሚያስቆጥረው ተጨዋችም ሽልማት እንደሚበረከት በዝርዝር አሳውቋል፡፡በ24ቱ ቡድኖች ውድድር ኮከብ ግብ አግቢ፣ ተጨዋችና አሰልጣኝ በብሄራዊ ቴክኒክ ኮሚቴ አማካኝነት ተመርጦ እንደሚሸለም በተጨማሪ ያረጋገጠው ፌደሬሽኑ፤ የጥሎ ማለፍ ውድድሮች በ90 ደቂቃ ውስጥ ካልጠተናቀቁ አሸናፊዎቹ በመለያ ምቶች እንደሚለዩ እና በ24ቱ ቡድኖች ውድድር 1ኛ አና 2ኛ የሚወጡት ቡደኖች ወደ ፕሪሚየር ሊግ እንደሚያልፉም ገልጿል፡፡ በ24ቱ ቡድኖች ውድድር በአራት ምድቦች በአጠቃላይ የሚካሄዱት ጨዋታዎች ብዛት 68 ይሆናል፣የምድብ ጨዋታዎች በዛት 60 ሲሆን በሩብ ፍጻሜ 4 በግማሽ ፍጻሜ 2 እንዲሁም የደረጃ እና የዋንጫ ጨዋታዎች ይከናወናሉ ብሏል፡፡

 ዋና አሰልጣኝ ዮሃንስ ሳህሌ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ስኬታማነት የወዳጅነት ጨዋታ ያስፈልገኛል አሉ፡፡ ቡድናቸው ከመስከረም ወር በፊት ከጠንካራ ቡድን ጋር በመጋጠም አቋሙን መፈተሽ አለበት ብለዋል፡፡ ዋልያዎቹ  በመጭው 2008 ዓ.ም በጥቅምት ወር በአፍሪካ ዋንጫ፤ በቻን እና በዓለም ዋንጫ የማጣርያ ግጥሚያዎች ይኖሩታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ከሲሸልስ በ5ኛው የቻን ውድድር የመጨረሻ ዙር ማጣርያ ከብሩንዲ በዓለም ዋንጫ ቅድመ ማጣርያ ከስዋቶሜ ፕሪንስፒ በሚያደርጋቸው 3 ጨዋታዎች በጥቅምት ወር ይፈተናል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ዮሃንስ ከሶስቱ የማጣርያ ግጥሚያዎች በተለይ አስቀድሞ ከሲሸልስ ጋር  ከሜዳ ውጭ ለሚያደርጉት  የአፍሪካ ዋንጫ ሁለተኛ የምድብ ማጣርያ ጨዋታ ትኩረት አድርገዋል፡፡ ስለሆነም አቋማቸውን ለመፈተሽ በመስከረም ወር በፊት የወዳጅነት ጨዋታ እንደሚያስፈልጋቸው ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል በ2018 እኤአ ላይ ራሽያ ለምታስተናግደው 21ኛው የዓለም ዋንጫ የቅድመ ማጣርያ ድልድል ከሳምንት በፊት ወጥቷል፡፡ አፍሪካን የሚወክሉትን 5 ብሄራዊ ቡድኖች ለመለየት የሚደረገው ማጣርያ በሶስት ምእራፎች የተከፈለ ነው፡፡ ከአህጉሪቱ 53 ብሄራዊ ቡድኖች ኢትዮጵያ ከ28 እስከ 53 ባለው ደረጃ ስለተያዘች 3ቱን የማጣርያ ምእራፎች ማለፍ ይጠበቅባታል፡፡ በመጀመርያው ዙር የቅድመ ማጣርያ ምዕራፍ 26 ብሄራዊ ቡድኖች አንዷ ኢትዮጵያ ስትሆን የደርሶ መልስ ጨዋታዎቹ ወደ ሁለተኛው ዙር ማጣርያ የሚገቡትን 13 ቡድኖች ይፈጥራሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በዚህ የመጀመርያ ዙር ማጣርያ ለደርሶ መልስ ጨዋታ የተደለደለው ከስዋቶሜ እናፕሪንሲፒ ጋር ነው፡፡ የመጀመርያውን ጨዋታ ከሜዳ ውጭ  የመልስ ጨዋታው በሜዳ ላይ የሚደረግ ይሆናል፡፡ በመካከለኛው የአፍሪካ ዞን የምትገኘው ስዋቶሜናፕሪንሲፒ በፊፋ የእግር ኳስ ደረጃዋ 188ኛ ናት፡፡ በሁለተኛ ዙር የኢትዮጵያ ተጋጣሚ የምትሆነው ከመካከለኛው አፍሪካ ዞን የምትወከለው ኮንጎ ኪንሻሳ ናት ቀይ ሴይጣኖች በሚል ቅፅል ስም ትታወቃለች፡፡ በሁለተኛ ዙር ማጣርያ ቀጥታ የገቡት ብሄራዊ ቡድኖች ከ1 እስከ 27 ደረጃ ያላቸው ሲሆኑ በመጀመርያ ዙር ማርያ ካለፉት 13 ብሄራዊ ቡድኖች ጋር በዚህ ምእራፍ  አገራት የደርሶ መልስ ትንቅንቅ የሚያደርጉ ይሆናል፡፡ በሁለተኛ ዙር የ40 ብሄራዊ ቡድኖች ትንቅንቅ ጥለው ማለፍ የሚችሉት  ብሄራዊ ቡድኖች ደግሞ ወደ የመጨረሻው እና ሶስተኛው ዙር በሆነው የምድብ ማጣርያ ገብተው በአምስት ምድቦች ተከፍለው የዓለም ዋንጫ ቲኬታቸውን ለመቁረጥ ይፋለማሉ፡፡

 የሰላም ጓዶች አስደማሚ ጋብቻ
   ፕሬዜዳንት ባራክ ኦባማ ባለፈው ሐምሌ የማርያም ዕለት ከሰአት በኋላ   በአፍሪካ ህብረት ኔልሰን ማንዴላ  አዳራሽ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ በመላው አፍሪካ ከተሰማሩት የአሜሪካ የሰላም ጓዶች  ውስጥ ከፍተኛውን ቁጥር የያዙት ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙት  ናቸው ማለታቸው እውነታቸውን ነው፡፡ ከእነኝህ ወጣት አሜሪካዊያን  የሠላም ጓዶች  መካከል አንዱ የሥራ ባልደረባዬ ነው፡፡ ታዲያ የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማን  ንግግር ስሰማ፣ ይኸ የሠላም ጓድ  እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ ከአገሩ ልጅ ጋር  ያደረገው የጋብቻ ስነ ሰርአት ትዝ አለኝ፡፡
ይህ  ባልደረባችን  ባለፈው ሰኔ ወር አጋማሽ አንድ እሮብ ከሰአት በኋላ እያንዳንዳችን ጋ እየመጣ “ተነገ ወዲያ አርብ ሠርጌ ነው፤ ስለዚህ በ12፡30 ከኢድናሞል ወረድ ብሎ በሚገኘው--- ሬስቶራንት እንገናኝ፤ አለባበስ ቀለል ያለ ይሁን፤ሱፍና ክራቫት አስፈላጊ አይደለም” ብሎ ነገረን፡፡ እኛም ˝..ጥላኝ ሄደች በሀምሌ ጨለማ..˝ በሚባልበት የክረምት ወራት የሚደረግ  የፈረንጅ ሰርግ ላይ  ለመታደም   በሶሻል ኮሚቴአችን አማካኝነት መጠነኛ ስጦታ አዘጋጅተን የእራት ግብዣው ቦታ ተገኘን፡፡ ሙሽሮቹ እስኪመጡም ቢራችንን እየጠጣን ጠበቅናቸው፡፡
ወደ አመሻሹ ላይ ሙሽራው ሻሩናስና  ሙሽሪት ኤሪካ  እግብዣው ቦታ ሲደርሱ ደስታ በፊታቸው ላይ ይነበብ ነበር፤  ይፍነከነካሉ፤ያገኙትን ሁሉ መሳም ፤አብሮ ፎቶ መነሳት፤የሰርግ እለት ወሎአቸውን ማስረዳት፤በደረሱበት ጠረጴዛ ሁሉ መጠጥ ማስቀዳት፤ብቻ ምን አለፋችሁ ደስታቸው መጠን ያለፈው ሆነ፡፡ ሙሽሮቹ በተናጠል እያንዳንዱ ጠረጴዛ ላይ እየሄዱ  የሰርጋቸውን አዋዋል ይነግሩን ገቡ፡፡ የሙሽሮቹን  የሠርግ ቀን  ውሎ  እስቲ ላስቃኛችሁ፤
ሙሽሪትና ሙሽራው አዘውትረው በርገር ወደሚበሉበት ካፌ ሄደው ቁርስ ከበሉ በኋላ ዘወትር እንደሚያደርጉት ሁሉ ወደሚያውቁት ሊስትሮ ሄደው ጫማቸውን በማስጠረግ የሠርግ ቀናቸውን ጀመሩ
ወደ ውጪ ጉዳይ ሚ/ር  በመሄድ የጋብቻ ሰርተፊኬታቸውን  ለማግኘት  የሚያስችለውን  ወረቀት አገኙ
ወደ ጉለሌ ክ/ከተማ የወሳኝ ኩነቶችና የኗሪዎች አገልግሎት ጽ/ቤት ሄደው የጋብቻ ፊርማቸውን  በማኖር፣ የጋብቻ ሰርተፊኬታቸውን ተቀበሉ፤የቀለበት ስነሰርአታቸውንም በዛው አካሄዱ
የወረቀት ስራው ከተጠናቀቀ በኋላ ሙሽሮቹ ቀደም ሲል  በተደጋጋሚ  ወደተዝናኑበት  አንዲት መኪና ተከራይተውና ፎቶግራፍ የሚያነሳውን ጓደኛቸውን ይዘው  ወደ  እንጦጦ ተራራ አቀኑ፡፡ እንጦጦ ተራራ ላይ ከሚኖሩ  ሀጻናት ጋር  በተለይ ሙሽሪት ˝ እቴ እሜቴ የሎሚ ሽታ ˝ ን  ተጫወተች ፤ሙሽሮቹ እከብቶች ግጦሽ ሜዳ ላይ ተንሸራሸሩ፤ፎቶ ተነሱ፤ተሳሳሙ፤ታስሮ እንደተለቀቀ እምቦሳ ቧረቁ፤ አንድ ጎጆ ቤት ገብተው የሚወዱትን ጠላ ጠጡ፤ የእንጦጦ ህጻናት ˝መልካም ጋብቻ˝ በማለት እቅፍ አበባ አበረከቱላቸው
ከእንጦጦ መልስ እግረ መንገዳቸውን ሽሮ ሜዳ የአገር ልብስ መሸጫ ሱቅ ወዳለው  ጓደኛቸው  ጎራ ብለው ሰርጋቸውን እያከበሩ መሆናቸውን በመንገርና በማስደመም  ጓደኛቸው  ሱቅ ውስጥ ፎቶ ተነሱ፤ተያይዘውም በአቅራቢያው ወደሚገኘው ጠጅ ቤት ሄደው ጠጅ ጠጡ፤ ጠጅ ቤት ለነበሩት መሸተኞች ሙሽሮች መሆናቸውን በመግለጥ መሸተኛውን የሰርጋቸው ደስታ ተካፋይ አደረጉ፤ ፎቶም ከመሸተኛው ጋር ተነሱ፡፡
 ከዛም ሙሽራው በተደጋጋሚ ምሳ ወደሚበላበት ሬስቶራንት ሄደው በኢትዮጵያዊ ጉርሻ የታጀበ እንጀራ በወጥና ፒዛ በሉ
ወደ አዲስ አበባ መሀል ከተማ መስቀል አደባባይ ከመድረሳቸው በፊት አንድ በግ ተራ በመሄድ ከበግ ሻጮች፤ ገዢዎችና ከበጎቹ  ጋር ፎቶ ተነሱ
መስቀል አደባባይ እንደደረሱ አላፊ አግጋዳሚውን ሰብሰብ በማድረግ ጮክ ብለው  ˝ “ወዳጆቻችን ፤ዛሬ ሰርጋችን ነው!˝ ብለው ገለጻ ቢጤ አደረጉ፤ከዛም ሙሽሪት የያዘችውን እቅፍ አበባ ወደ ሰማይ በተነችው፤ የተሰበሰበው ጥቂት  ተመልካችም አበባውን እየተሻማ ተቀራመተው
ከዛ ወደ ቤታቸው በመሄድ እረፍት አድርገው እራት ወደተዘጋጀበት ሬስቶራንት አመሩ
እኛ ታዳሚዎች ዘመን የማይሽረውን ˝ ሙሽራዬን˝ እያዜምን ተቀበልናቸው፤ቁጥራችን ከ35 አይበልጥም ነበር
የምግብና መጠጥ መስተንግዶው ቀጠለ፤ከሁሉም አገሪቱ ማዕዘናት  ያሉ ባህላዊ  ጨዋታዎች ድምጻቸው  ከፍ  ብሎና ከቀደምት የእንግሊዝኛ ዘፈኖች ጋር ተቀላቅሎ   ተደመጡ፤እስክስታ ተመታ፤ዳንሱ ቀለጠ
 በመጨረሻ የኬክ መቁረሱ ሥነስርአት ተከናወነ፤ እሱንም ተከትሎ ከዚህ በታች የምታዩት የሙሽሮቹ ፎቶግራፍ በጥሩ ፍሬም ሆኖ  በስጦታ መልክ  ተበረከተላቸው፡፡ እኛ ስጦታውን ስናበረክት ከእኛ ቀድሞ ይህ  ምስልና  የሙሽሮቹ የሰርግ  ቀን ውሎ በፌስ ቡክና በኢንስታግራም ተለቆ ነበር ፡፡
 በሰርጉ ማግስት  ከሙሽራው ጋር ቆይታ አድርጌ ነበር፡፡
˝ሻሩናስ ፤ሰርግህን  አስመልክቶ አንድ ጽሁፍ ብጽፍ ፈቃደኝ ነህ?”
˝አዎ ግርማ ደስተኛ ነኝ ፤ሰርጋችንን ወደድከው?”
˝አዎ በጣም ወድጀዋለሁ፤ለእኛ  ወጣቶች እንደ ሞዴል ጋብቻ አድርጌ ስለአየሁት በሰርጋችሁ ላይ አንድ ጽሁፍ  ጋዜጦች ላይ አወጣ ይሆናል ˝
˝ግርማ በጣማ ደስተኝ ነኝ፤ የሰርጉን ፎቶዎች በሙሉ ሰርቨር ላይ እጭናቸዋለሁ ፤ በተጨማሪም  አንድ ጓደኛዬ ፖስት ያደረገውንም እልክልሃለሁ˝
˝በጣም ጥሩ፤ፎቶዎቹ ለጽሁፌ መነሻ  ይሆኑኛል˝
በመጨረሻም በሚቀጥለው ጥቅምት 2008 ላይ 23ተኛ አመቴን የማከብረውን፤ ከሽማግሌ መላክ እስከ ቅልቅል ድረስ ያለውን ኮተተ ብዙ የአበሻ ሰርግ ሁደት  እያሠብኩ፤
˝ሻሩናስ ፤አንድ ጥያቄ  ልጠይቅህ ከወላጆቻችሁና፤ ከዘመዶቻችሁ እርቃችሁ ሰርጋችሁን ለምን በኢትዮጵያ ምድር  ላይ  ለማድረግ  ወሰናችሁ?
˝ ግርማ፤ ለእኔና ለባለቤቴ ኤሪካ ኢትዮጵያ ልዩ ቦታ አላት፤ ስለሆነም  ሰርጋችንን  እዚሁ  በህይወታችን ውስጥ ትልቅ ስፍራ ካላቸው ወዳጆቻችን፤ ከህጻናት ጋር ፤የገጠሪቱ ኢትዮጵያን ስሜት የያዘ፤ አዘውትረን  የምንሄድባቸውን ቦታዎችና ጓደኞቻችንን  የሚያስታውስ ፤ ኢትዮጵያዊ  ስሜት ያለው   እንዲሆንልን  ስለፈለግን ነው˝ ብሎ መለሰልኝ!!
ወጣት ፍቅረኞች  እናንተስ? እኔ መቼም  ይህን ሰርግ ወድጄዋለሁ፤ ከተለመደው ኮተተ ብዙ  የአበሻ  ሰርግ ይልቅ ይኸ ቅልብጭ ያለ የሰላም ጓዶቹ  ሰርግ ይሻላል ባይ ነኝ፡፡ ምክንያቱም ሰርጉ ቀላል፤ አሳታፊና ወጪ ቆጣቢ በመሆኑ ነው፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ  ባለፈው የማሪያም ዕለት በንግግራቸው የጠቀሷቸው  የሰላም ጓዶች በአሜሪካና በኢትዮጵያ መካከል  ከንግድና  ኢንቨስትመት  ትስስሩ ጎን ለጎን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን በማጠናከር ላይ ናቸው፡፡ በላእላይ መዋቅር ደረጃ  በእምዬ ምኒልክ ጊዜ የተጀመረው  የኢትዮ-አሜሪካ መልካም ግንኙነት፣ በታህታይ መዋቅሩም በህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ሲጠናከር መሰረተ ሰፊና ስር የሰደደ ይሆናል፡፡
ሰለዚህ  ፕሬዚዳንት ኦባማ ሆይ፤ እባክዎትን ወደ ኢትዮጵያ የሚልኩልንን  የሰላም ጓዶች   የወንድና የሴቱን ቁጥር ባመጣጠነ መልኩ ከፍ ያድርጉልን፤ እኛ ከዚህ እያጋባን እንልካቸዋለን! 

የታሊባን ቃል አቀባይ፤“መሪያችን አልሞተም፣ አሁንም እየመራን ነው“ ብሏል
 
    የአፍጋኒስታን የደህንነት ባለስልጣናት፤ የታሊባኑ መሪ ሙላህ ሞሃመድ ኦማር ከሁለት አመታት በፊት መሞቱን አረጋግጠናል ሲሉ መናገራቸውንና የቡድኑ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ መሪያችን በህይወት አለ፤ አሁንም እየመራን ነው ሲሉ ማስተባበላቸውን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡
የአፍጋኒስታን ብሄራዊ የደህንነት ዳይሬክቶሬት ቃል አቀባይ አብዱል ሃሲብ ሳዲቅ እንዳሉት፣ ሙላህ ሞሃመድ ኦማር በጸና ታሞ በነበረበት በካራቺ ከተማ ውስጥ የሚገኝ ሆስፒታል በሚያዝያ ወር 2013 ህይወቱ እንዳለፈ አረጋግጧል፡፡
ሙላህ ሞሃመድ ኦማር ለመጨረሻ ጊዜ በአደባባይ የታየው እ.ኤ.አ በ2001 እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ግለሰቡ ሞቷል ተብሎ ሲነገር ይህ ለአራተኛ ጊዜ መሆኑንና አሜሪካም በዚህ ሳምንት የወጣውን መረጃ ትክክለኛ ነው ብላ መቀበሏን ገልጧል፡፡
የታሊባኑ መሪ ሙላህ ሞሃመድ ኦማር ልጅ ሙላህ ያቆብ፣ አባቱ ከአመታት በፊት እንደሞተ ማመኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ተቀማጭነቱ በፓኪስታን የሆነ አንድ አፍጋኒስታናዊ የታሊባን ከፍተኛ የጦር መሪም፣ ሙላህ ሞሃመድ ኦማር ከአመታት በፊት በተፈጥሯዊ ሞት ከዚህ አለም መለየቱን ለሮይተርስ መናገሩን ገልጧል፡፡
ታሊባንን የመምራት ሃላፊነቱን ልጅዬው ሙላህ ያቆብ እንደተረከበ እየተነገረ ሲሆን፣የታሊባን ቃል አቀባይ ቃሪ የሱፍ አህመዲ በበኩሉ፤መረጃው መሰረተ ቢስ ሃሜት ነው ሲል ማስተባበሉ ተዘግቧል።
እኔ እስከማውቀው ድረስ ሙላህ ሞሃመድ ኦማር አሁንም በህይወት አለ፣ቡድኑን የመምራት ሃላፊነቱንም በአግባቡ እየተወጣ ይገኛል ብሏል ቃል አቀባዩ፡፡

 የትሪፖሊ ፍርድ ቤት የጦር ወንጀል ፈጽሟል በሚል ክስ በተመሰረተበት የቀድሞው የሊቢያ ፕሬዚዳንት ሞኣመር ጋዳፊ ልጅ፣ ሳይፍ ጋዳፊ ላይ የሞት ፍርድ ውሳኔ ማስተላለፉን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ፍርድ ቤቱ በ2011 በተቀሰቀሰው የአረብ አብዮት የግድያ፣ የግርፋትና የፍንዳታ ተግባራትን በማቀጣጠል ጥፋተኛ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ባለው ሳይፍ ጋዳፊ ላይ በሌለበት የሞት ፍርድ ቢያስተላልፍም፣ ተከሳሹ ግን ድርጊቱን እንዳልፈጸመ መግለጹን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ከሳይፍ ጋዳፊ በተጨማሪ የቀድሞውን የሊቢያ የደህንነት ሃላፊ አብዱላህ አል ሴኑሲ ጨምሮ ሌሎች ስምንት ሊቢያውያንም በተመሳሳይ ክስ የሞት ፍርድ እንደተፈረደባቸው ዘገባው አስታውቋል፡፡
ከለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ፒኤችዲውን የተቀበለው ሳይፍ ጋዳፊ፤ በአሁኑ ወቅት በዚናታን ከተማ ውስጥ በሚገኝና ለትሪፖሊ መንግስት አሳልፌ አልሰጠውም ብሎ በተቃወመ ወታደር ቤት ውስጥ እንደሚገኝ ዘገባው አስታውሷል፡፡