Administrator

Administrator

    ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ የመፅሐፍ ንባብ ፕሮግራም ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር በነገው ዕለት ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ “ሰልፍ ሜዳ” በተሰኘው የደራሲ የግርማ ተስፋው መፅሀፍ ዙሪያ ውይይት ያካሂዳል፡፡ በወመዘክር አዳራሽ ለሚካሄደው ለዚህ ውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት አቶ ስለሺ ሀጎስ ሲሆኑ፤ የመፃሕፍት አፍቃሪያን በውይይቱ ላይ እንዲሳተፉ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ጋብዟል፡፡

Saturday, 12 December 2015 11:30

የኪነት ጥግ

(ስለ ልምምድ)
በልምምድ ወቅት ስህተቶችን መስራት አለብህ፡፡ ምክንያቱም እንደዚያ ነው የሚሆነውንና የማይሆነውን የምታውቀው፡፡
ክላርክ ፒተርስ
እውነት ብዙ ልምምድ አይፈልግም፡፡
ባርባራ ኪንግሶልቨር
ሦስት ሴት ልጆች አሉኝ፤ እናም ውጤቱ “ኪንግ ሊር”ን ያለ ልምምድ መተወን ሆነ፡፡
ፒተር ኢስቲኖቭ
በአንድ ወቅት በአራት ቀን ልምምድ ለአንድ ትወና መድረክ ላይ ወጥቼ ነበር፡፡
አና ፍሪል
እኔ የ6 ሳምንት የልምምድ ጊዜ ያስፈልገኛል፤ ሴቶች ደግሞ 9 ወራት ያስፈልጋቸዋል፤ ይሄንን ለመገንዘብ 15 ዓመት ፈጅቶብኛል፡፡
ዊሊያም ኸርት
ከመድረክ ይልቅ ፊልምን እመርጣለሁ። ሁልጊዜም ከትወናው በተሻለ ልምምዱን እወደዋለሁ፡፡
ብራድ ዶሪፍ
የልምምድ ሂደቱን ከልቤ እወደዋለሁ፡፡ እነዚያን በቀን 8 ሰዓት የልምምድ ጊዜያት! ተዋናዮችን በእጅጉ ነው የምወዳቸው፡፡
ፐርል ክሊጅ
ምንጊዜም በልምምድ ክፍል ውስጥ ስሆን ደስተኛ ነኝ፡፡ እዚያ ነው ሁልጊዜ ሙሉ አቅሜንና የፈጠራ ችሎታዬን የማገኘው፡፡
ሎውሪ ሜትካልፍ
አንድ ጊዜ ልምምድ ውስጥ ከገባህ በኋላ በክፍሉ ውስጥ ባለው ትርኢት ላይ ማተኮር አለብህ ብዬ አስባለሁ፡፡
ስኮት ኢሊስ
የሻወር ትዕይንት ከመስራት የበለጠ ገልጃጃ ነገር ምን አለ? የሻወር ትዕይንትን ለማለማ መድ፡፡
ኮቢ ስሙልደርስ
ቲያትርን መለማመድ  ለቃለ - ተውኔቱ ስጋ ማልበስ ነው፡፡ ተውኔትን ማሳተም ሂደቱን መገልበጥ ነው፡፡
ፒተር ሻፌር
በቲያትር ልምምድ ወቅት ትኩረቴን በሂደት ላይ ካለው ሥራ ሊያናጥበኝ ከሚችል ምንም  ዓይነት ንባብ ለመታቀብ እጥራለሁ፡፡
ሜርሴዲስ ማክካምብሪጅ

Saturday, 12 December 2015 11:28

የግጥም ጥግ

እዬዬ ማይገልፀው
ምን ይበል አባቷ
ምን ትበል እናቱ
ለወግ ያሰበችው ሲቀጠፍ በከንቱ
ምን ይላል ወገኔ
ጉንጬ በእምባ ሲርስ - አንጀቴ ሲታጠፍ
ኮትኩቼ ያበበው
መዐዛው ሚስበው
የማታ አበባዬ በአጭሩ ሲቀጠፍ
ያቺ ምስኪን እናት
የማታዋን ሳታውቅ በጠዋት ተነስታ
ከዛሬው ወጋገን የነገውን አይታ
ጨርሳ አትሸኘው
ለአይኗ እንኳ ሳስታ
በደንብ እንዳትስመው
ያንን ስርጉድ ጉንጩን
ብሉኝ ብሉኝ ሚለው
ሞልቶ-ትርፍ ፈገግታ
የጠዋት ፀሎቷ - ጅምር በረከቷ - በእንባዋ
 ሲታበስ
የፀበል ማቆርያ - የህመም
ብርታቷ - ሲሰበር ላይታፈስ
እንዴት አሟት ይሆን
ልቧ ውስጧ ሲሞት
ያልጠና አጥንቱ - ያልገራ ጅማቱ - ጎማ
ሲበትነው
ያልቦረቀች ነፍሱ - ጅምር ለጋነቱ - ሲቃ
ሲፈትነው
እህህ አይገልፀው
እዬዬ አይክሰው
እምባዋን ረጭታው -
ከመብሰክሰክ በቀር - ምን ታደርገዋች
አንዴ ፈሷል ነገር - ዳግመኛ አትወልደው -
በምን ታፍሰዋለች
(መታሰቢያነቱ ሰሞኑን በአዲስ አበባ ከትምህርት ቤት ሲመለሱ በመኪና አደጋ ህይወታቸውን ላጡት ህጻናት ይሁንልኝ፡፡)
(ከዘም ዛሚ ፌስቡክ)

Saturday, 12 December 2015 11:26

የዝነኞች ጥግ

 (ስለ ሀብት)
እውነተኛው ሀብት ወርቅ ወይም ብር ሳይሆን ጤና ነው፡፡
ማሃትማ ጋንዲ
ሀብት ህይወትን ሙሉ በሙሉ የማጣጣም አቅም ነው፡፡
ሔንሪ ዴቪድ ቶሪዮ
በቅጡ በሚመራ አገር ድህነት የሚያሳፍር ነገር ነው፡፡ በተበላሸ መንገድ በሚመራ አገር ሀብት የሚያሳፍር ነገር ነው፡፡
ኮንፍሺየስ
ሀብት የሰው የማሰብ አቅም ውጤት ነው፡፡
አየን ራንድ
ገንዘብ ጓደኞችን አይገዛም፤ የተሻለ መደብ ጠላት ግን ማግኘት ትችላለህ፡፡
ስፓይክ ሚሊጋን
ብልህ ሰው ገንዘብን በጭንቅላቱ እንጂ በልቡ ማኖር የለበትም፡፡
ጆናታን ስዊፍት
ገንዘብ የብልህ ሰው ሃይማኖት ነው፡፡
ዩሪፒደስ
ከሀብታም ሰዎች የምወድላቸው ብቸኛ ነገር ገንዘባቸውን ነው፡፡
ናንሲ አስቶር
ሀብታሞች በየቦታው አሉ፤ ነገር ግን ለአገራቸው ዕድገት አስተዋፅኦ አያደርጉም፡፡
ሂላሪ ክሊንተን
ባለፀጎችን ካልወደድክ በቀር ጨርሶ ሀብታም አትሆንም፡፡
ዳግላስ ኩፕላንድ
በመላው ዓለም ሀብታሞች ተወዳጅነት የላቸውም፡፡
ቪክቶር ፒንቹክ
ሀብት ለዓለም ከፍተኛ ጥቅሞችን ያስገኛል፡፡ ሀብታሞች ጀግኖች ናቸው፡፡
ፒ.ጄ.ኦ‘ሮዮርኬ
ገንዘብ እንደ ስድስተኛ ስሜት ነው - እሱ ሳይኖር ሌሎቹን አምስቱን መጠቀም አትችልም፡፡
ሶመርሴት ሟም
የገንዘብ ችግር የሀጢያቶች ሁሉ ሥር ነው፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው

      በሴቶችና በልጃገረዶች ላይ የሚፈፀሙ ጐጂ ባህላዊ ድርጊቶችን በተለይም የሴቶችን ግርዛት ለመከላከል አገሪቱ እያደረገች ላለው ጥረት ድጋፍ እያደረገ መሆኑን የአውሮፓ ህብረት አስታወቀ፡፡
በየዓመቱ ህዳር 30 ቀን የሚከበረውን የሰብአዊ መብት ቀን ምክንያት በማድረግ ህብረቱ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል በአዋሣ ዙሪያ ወረዳ፣ ጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለማስቀረት የተደረጉ ድጋፎችንና የማህበረሰብ አቀፍ ሥራዎችን ለጋዜጠኞች ባስጐበኘበት ወቅት በህብረቱ የሲቪል ማህበረሰብና የጾታ ጉዳዮች ፕሮግራም መሪ ስቴፋን ካሬት እንደተናገሩት፤ በወረዳዎቹ የሴት ልጅ ግርዛት፣ ያለዕድሜ ጋብቻ፣ ጠለፋንና የውርስ ጋብቻን ለማስቀረት አገሪቱ የምታደርገውን ጥረት ህብረቱ ሲደግፍ ቆይቷል፡፡
በክልሉ በተለይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ እናቶች፣ ህፃናትና ልጆችን መሠረታዊ ችግር በመቅረፍ ለነዋሪዎች የጤና እና የትምህርት እድል ለማስገኘት ለሚሰራው ሴንተር ኦፍ ኮንሰርን የተባለ ማዕከል ድጋፍ የሚያደርገው ህብረቱ፤ በእነዚሁ ወረዳዎች ውስጥ ለሚገኙና ቀድሞ በግርዛት ሥራ ላይ ለተሰማሩ 60 ሴቶች 1500 ብር መቋቋሚያ በመስጠት፣ ከጐጂ ልማዳዊ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ መደረጉም በዚሁ ወቅት ተገልጿል፡፡
ዞኑ በተለይም ከሴት ልጅ ግርዛትና ከውርስ ጋብቻ ጋር በተያያዘ በርካታ ችግሮች የነበሩበት ሥፍራ እንደነበር የገለፁት የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር አቶ አሰፋ ጌታነህ በበኩላቸው፤ የጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶቹ ሰለባ የሆኑ ሴቶችን መልሶ በማቋቋም ኑሮአቸውን ለማሻሻል ጥረት መደረጉን ጠቁመው፣ በወረዳው ሥር ባሉ ትምህርት ቤቶችና መንደሮች ማህበረሰቡን ለማስተማር ከፍተኛ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

 የተለያዩ የስፖርት መሥሪያ መሳሪያዎችን አምርቶ ለገበያ በማቅረብ የሚታወቀው የላይፍ ፊትነስ እናት ድርጅት ብራንዝዊክ ኮርፖሬሽን በዕድሜ ለገፉ ሰዎች ጠቃሚ የሆኑ የስፖርት መስሪያ ዕቃዎችን በማምረት የሚታወቀውን ሳይፈት የተባለ ድርጅት በመግዛት የድርጅቱ አካል ማድረጉን አስታወቀ፡፡
የላይፍ ፊትነስ ፕሬዚዳንት ሚስተር ክሪስ ላውሶን እንደገለፁት ላይፍ ፊትነስ ሳይፊትን መግዛቱ ቁጥራቸው በፍጥነት እያደገ ያለውን በዕድሜ የገፉ ወገኖችን ሊረዳ የሚችል ምርት ለማቅረብ ያስችለናል ብለዋል፡፡
ይህም ድርጅቱ ጡረተኞች እንዲሁም ልዩ እርዳታና እንክብካቤ የሚያሰፈልጋቸው ወገኖች ለሚገለገሉባቸው ቦታዎች፣ ለአረጋውያን መንከባከቢያ ተቋማት፣ ለማረሚያ ቤቶችና የተአድሶ ሥፍራዎች አስፈላጊ የሆኑ ምርቶችን የስፖርት መስሪያ ለማቅረብ እንደሚያስችላቸው ገልፀዋል፡፡
ላይፍ ፊትነስ ለጂም የሚሆኑ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ምርቶች፣ የመዝናኛ ጠረጴዛዎች እንዲሁም የተለያዩ ዕቃዎች አምርቶ ለገበያ በማቅረብ ቀዳሚ የሆነ ድርጅት ነው፡፡

   ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ባል ወደ ሩቅ አገር ሲሄድ መንገድ ላይ ይመሽበታል፡፡
ወደ አንድ ቤት ጎራ ብሎ፤
“የመሸበት መንገደኛ እባካችሁ አሳድሩኝ?” ሲል ይለምናል፡፡
አባወራውም፤
“ቤታችን የእግዚአብሔር ቤት ነው፡፡ ግባ፡፡ የበላነውን በልተህ፣ የጠጣነውን ጠጥተህ፤ መደብ ላይ እናነጥፍልህና ትተኛለህ፡፡” አለው፡፡
ባለቤቲቱም፤
“እኛም ወደናንተ አገር ብንመጣ ይሄንኑ እንደምታደርጉልን እናውቃለን፡፡ ተቀመጥ” አለችው፡፡ እንግዳው ገብቶ እየተቀመጠ፤ “እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ ብድር ከፋይ፣ ውለታ መላሽ እንዲያደርገን እመኛለሁ፡፡”
ውሃ አሙቀው እግሩን እንዲታጠብ አደረጉ፡፡ እራት ቀረበ፡፡ ከጎን ምድጃው ላይ ቡና ይቆላል፡፡ እራት እየተበላ፤
“ከእኛ ብዙ ርቀህ ለመሄድ አስበህ ነው?”
“ብዙም አይርቅም፡፡ ከእንግዲህ ግማሽ ቀን ቢያስጉዘኝ ነው”
“እንግዲያው ቡናህን ትጠጣና በጊዜ እንድትተኛ እናደርግሃለን፡፡ ቀኑን ሙሉ መንገድ መትቶህ ደግሞ ነገም ሌላ መንገድ ያደክምሃል፡፡” እራት አብቅቶ ቡና ቀረበ፡፡ ፈንዲሻ ተቆላ፤ ተበላና ወደ ተነጠፈለት መኝታ ሄደ፡፡
ጠዋት ቁርስ አብልተውት ሲወጣ ወደ ሴትዮዋ ጠጋ ብሎ፤
“እሜቴ አንድ ነገር ላስቸግርሽ?”
“ምን ልርዳህ?”
“ይሄ ማታ የቆሉትና ያበሉን ምን ነበር?”
“ፈንዲሻ፤ ፈንዲሻ ነው!”
“ገበያ ላይ ይገኛል?”
“ኧረ የትም ይገኛል!”
“እግዚአብሔር ይስጥልኝ” ብሎ አመስግኖ ተሰናበተ፡፡
ወደሚሄድበት ከተማ ደርሶ ሲመለስ ያን ፈንዲሻ እህሉን ገዝቶ ወደ ቤቱ አመራ፡፡
“ዛሬ ተዓምር የሆነ ነገር ይዠልሽ መጥቻለሁ” አላት ለሚስቱ
“ምን?”
“ፈንዲሻ የሚባል የሚፈካ እህል፡፡ ቡና ስታፈይ ትቆይውና እንበላለን”
ቡናው ከፈላ በኋላ ሚስትየው፣ የፈንዲሻውን በቆሎ ክዳን በሌላው ብረት ድስት አድርጋ ስታራግበው ከፊሉ በግራ፣ ከፊሉ፣ በቀኝ የቀረው ወደላይ እንደርችት መፈነጣጠር ጀመረ፡፡ ሚስት የቱን ትያዘው? አንዴ ወደቀኝ የሄደውን ልትይዝ ስትዘል፣ አንዴ ወደ ግራ የሄደውን ልትቀልብ ስትወራጭ፤ ባልም መላው ጠፍቶት ግራ እንደተጋባ ቆሞ፤
“አዬ ጉድ! አዬ ጉድ! ሳይቸግረኝ ዕብድ እህል ገዝቼ ሚስቴን አሳበድኳት!” አለ፡፡
*         *       *
ዕብድ እህል ገዝተን አገር እንዳናሳብድ መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ ዕብድ ዕቅድ አቅደን አገሬውን እንዳናሳብድ ተረጋግተን ማቀድ ይገባናል፡፡ ዕብድ ሲስተም ዘርግተን በየቀኑ እየተቋረጠ “ሲስተም የለም” እንዳንል ማስተዋል አለብን፡፡ ብቃት የሌለው የሰው ኃይል ቀጥረን ግራ ተጋብቶ ባለጉዳይ እንዳያሳብድ ከመነሻው በጥራት ላይ የተመሰረተ አሰራርና ሰራተኛ ማዘጋጀት ግድ መሆኑን መገንዘብ ዋና ነገር ነው! ጥናቶች ሁሉ ጥናት እያስፈለጋቸው ከመጣ፤ ድካማችን ሁሉ ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ ነው፡፡
“ቀድሞ ነበር እንጂ፣ መጥኖ መደቆስ
አሁን ምን ያደርጋል፣ ድስት ጥዶ ማልቀስ”
የሚለውን አገርኛ አነጋገር በቅጡ መረዳት፤ ምን ጊዜም ወቅታዊነት ያለው መሆኑን መገንዘብ ከአያሌ አባዜ ያድነናል!
ዕብድ የሲስተም እህል ባልተከደነ ብረት - ድስት እንደሚፈነዳዳው፣ ፈንዲሻ አላዋቂ ቆይውን እንደሚያደነባብር፣ ብልጣ ብልጥ ባለሙያም እንዳሻው እንደሚጮልልበት ማጤን አያዳግትም፡፡ ሙስናችን ለያዥ ለገራዥ ባስቸገረበት በአሁኑ ሰዓት፤ አንድ የጥንት ታሪካዊ ምሳሌ ማየት ደግ ነው!
አንድ መምህር አንድ ጥንታዊ ደብር እንደኃላፊ ይሾማሉ፡፡ አዲሱ ኃላፊ የማያስበሉና የማይሞዳሞዱ ናቸው! ቀድሞ በደብሩ ሹመኛ የነበሩትና በሙስና ይታሙ የነበሩት ሁሉ አኮረፉ፡፡ ስለዚህም ንጉሱ መጥተው አቤቱታ እናሰማ ሲሉ ጠየቁና ንጉሱ መጡ፡፡ እንዲህ ሲሉ ሹማምንቱ ከሰሱ፡-
“ንጉሥ ሆይ! ለመሆኑ ምን አጥፍተን ነው እንዲህ ያለ አህያ የሾሙብን?”
ንጉሡ፤ “እህ ምን ትላለህ? አዲሱ ተሿሚ?” አሉና ጠየቁት፡፡
አዲሱ ተሿሚም፤
“ይሁን ጃንሆይ! እኔስ አህያ ልሁን፡፡ ግን ጃንሆይ፤
እኔ አንድ አህያ ለስንት ጅብ እሆናለሁ?!” ሲል መለሰ፡፡
ንጉሱ፤ “ሥልጣንህ የፀና ይሁን፡፡ ነገሩ ገብቶኛል!” አሉና ወሰኑ፡፡ እንዲህ ያለ ንጉሥ ሊኖረን ይገባል፡፡ ከዚህ የምንገነዘበው ነገር እንግዲህ ስለመልካም አስተዳደርና ስለሙስና ታሪክ የሚያስተምር ሪኮርድም አለን እንደማለት ነው፡፡ ታሪካችንን በመረመርን ቁጥር ጥፋታችንን ፍንትው አድርጐ የማያሳይ መስተዋት አገኘን ማለት ነው፡፡
ስለነባሮቹ ጅቦች ይሄን ያህል ካልን፣ ስለአዳዲስ ጅቦችም የምናውቀውን እንል ዘንድ ወቅቱ ግድ ይለናል፡-
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ መንደር ውስጥ ሌብነትና ዘረፋ እጅግ እየናጠጠ ሲመጣ የሰፈሩ ሰው ሁሉ አውጫጪኝ ተቀመጠ! (በዚያ መንደር ተጠርጣሪ ሌቦች አቶ ለማ፣ አቶ ቢተውና አቶ ጀንበር ናቸው እየተባለ ይወራል፡፡)
ሰው በየፊናው እያጉተመተመ ድፍረቱን አጥቶ ሳለ፣ አንድ ባለቅኔ አዛውንት ተነሱና በወኔ፡-
“ጐበዝ!
ሌባው ለማ!
ቢተው ይተው!
ባይተው ግን፤ ጀንበር በሠረቀ ቁጥር፤ ህዝቡ የሚሰቃይበት፤ ከቶ አንድም ምክንያት አይኖርም!” ሲሉ ደመደሙ!
ህዝቡ ዋናውን ነቀርሳ ስለሚያውቅ፣ ግብረ - ገባዊ ባህሪውን ጥሶ “ዕውነትክን ነው! ይገባሃል!” ማለቱን ቀጠለ፡፡ ትልቁ ነጥብም እዚሁ ላይ ነው! ሌቦቻችንን እኛው እያወቅን አንሸሽማ! እቺ ባቄላ ያደረች እንፈሁ እንበል፡፡
የሀገራችንን ፖለቲካዊ - ኢኮኖሚ፣ ትላንትም፣ ዛሬም፣ ነገም፣ ውሉ የማይታወቅ ከማስመሰል ይልቅ፤ ፈር ቀዳጅ፣ አመርቂ፣ ዘላቂ፤ ሰው ለሰው አጠያያቂ፣ እንዲሆነ የቱን ብንገዛ፣ የቱን ብንሸጥ፣ የቱን ውሉን ብንሰርዝ፣ የቱን ከኃያላን ውጪ ብናደርግ… የሚለውን ሃሳብ ያለምንምና ያለ ማንም ተፅዕኖ ልንከውነው እንችል ይሆን ብሎ ከአገር ጋር መክሮ፣ ዘክሮ መራመድ የጥበብ መጀመሪያ ነው፡፡ ይህን ያሠመረና ሁሉን ያስተዋለ መንገድ መጓዝ፤ “ዕብድ እህል ገዝቼ ሚስቴን አሳበድኳት” ከማለት ያድነናል!!

   የግብጽ የመስኖ ሚኒስትር ሆሳም ሞጋዚ ኢትዮጵያ በመገንባት ላይ ያለችውን አወዛጋቢውን የታላቁ ህዳሴ ግድብ በተመለከተ  አለማቀፍ ሽምግልናን እንደአማራጭ ለመውሰድ ጊዜው ገና ነው ማለታቸውን አሃራም ኦንላይን የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘገበ፡፡
ግብጽ የግድቡ መሰራት ወደተፋሰሱ አገራት የሚደርሰውን የውሃ መጠን በከፍተኛ ሁኔታ ይቀንሰዋል በሚል ስጋቷን ስትገልጽ እንደቆየች ያስታወሰው ዘገባው፣ በግድቡ ዙሪያ ያሉ ችግሮችን በአለማቀፍ ሸምጋዮች መፍታትን እንደአማራጭ እንደማትወስድና አፍሪካውያን አደራዳሪዎች በጉዳዩ ጣልቃ እንዲገቡ እንደማትፈልግ ሚኒስትሩ መናገራቸውን ገልጧል፡፡
ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኡመር አልበሽር ታላቁ ህዳሴ እውን መሆኑ ተረጋግጧል፣ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተባብረው ሊሰሩ ይገባል ሲሉ በተናገሩ ማግስት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ሚኒስትሩ በቅርቡም ግድቡ በታችኛው የተፋሰሱ አገራት ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ በተመለከተ የሚደረጉ የቴክኒክ ጥናቶች ሳይጠናቀቁ የግድቡ ግንባታ መፋጠኑ እንዳሳሰባቸው መናገራቸውን አስታውሷል፡፡
ሚድል ኢስት ሞኒተር በበኩሉ ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዘገባ፣ ግብጽ የተባበሩት አረብ ኢሜሬትስን በጉዳዩ ጣልቃ በመግባት በግድቡ ዙሪያ የሚታዩ አለመግባባቶችን ለመፍታት ድጋፍ እንድታደርግ መጠየቋን አስነብቧል፡፡
የኢትዮጵያ፣ የግብጽና የሱዳን የውጭ ጉዳይና የመስኖ ሚኒስትሮች በግድቡ ዙሪያ በሚመክረው አስረኛው ዙር የጋራ ስብሰባ በሱዳን መዲና ካርቱም ከትናንት ጀምሮ በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ፡፡

• “መብራት ተቋርጦ ሶስት ህሙማን ሞተዋል” - የሆስፒታሉ ባለሙያ
• “መብራት የተቋረጠው ከሆስፒታሉ አቅም በላይ በሆነ ችግር ነው” - የሆስፒታሉ አስተዳደር


        በሀዋሣ ሪፈራል ሆስፒታል፤ መብራት በመቋረጡ ምክንያት፤ በፅኑ ህክምና ክፍል 3 ታማሚዎች እንደሞቱ፣ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮችን በመጥቀስ አዲስ አድማስ  ያወጣውን ዘገባ፣ ሆስፒታሉ ተቃወመ፡፡ ህሙማኑ መሞታቸውንና መብራት መቋረጡን ሆስፒታሉ ቢያምንም፤ ህሙማኑ የሞቱት በመብራት መቋረጥ ሳቢያ እንደሆነ የሚያረጋግጡ በቂ መረጃዎች በዘገባው አልቀረቡም፤ ሚዛናዊነትንም አያሟላም በማለት ቅሬታ አቅርቧል፡፡ ቅሬታዎቹ ብዙ ናቸው፡፡
የመብራት መቋረጥ ከሆስፒታሉ አቅም ውጪ የሆነ ክስተት እንደሆነ የሆስፒታሉ አስተዳደሩ ሲያስረዳ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ የኤሌክትሪክ መስመር በመጥፋቱ ምክንያት የተፈጠረ ክስተት መሆኑን የመብራት ኃይል ተቋም አረጋግጦልኛል ብሏል ለአዲስ አድማስ በፃፈው ማስተባበያ ደብዳቤ፡፡ በኤሌክትሪክ መቋረጥ የሚፈጠሩ ችግሮችን በጀኔሬተር ለማቃለል ከፍተኛ ርብርብ አድርጌአለሁ በማለት የሆስፒታሉ አስተዳደር ጽፏል፡፡ እነዚህ መረጃዎች በዘገባው አለመካተታቸውን ተችቷል፡፡
3 ህሙማን ሞተዋል የሚለው ዘገባ ስህተት ነው ሲል ሆስፒታሉ አስተባብሏል፡፡ ስህተቱንም ሲያስረዳ፤ ሁለቱ ህመምተኞች የሞቱት ህዳር 20 ቢሆንም አንድ ወላድ ህመምተኛ የሞተችው ህዳር 18 ቀን ነው ብሏል፡፡ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የሆስፒታሉ ባለሙያ ለአዲስ አድማስ በሰጡት መረጃ፤ በሁለቱም ቀናት መብራት ተቋርጦ ችግር እንደተፈጠረ አረጋግጠው፤ ከዚህም ጋር ተያይዞ ሦስት ህሙማን መሞታቸው እውነት ነው ብለዋል፡፡ በሁለቱም ቀናት መብራት መቋረጡንና በጀነሬተር ችግሩን ማቃለል አለመቻሉን በተመለከተ ጥያቄ ያቀረብንላቸው የሆስፒታሉ የህግ ክፍል ተወካይ፤ በደብዳቤ ከተፃፈው ምላሽ ውጭ ጥያቄዎችን ማንሳት አስፈላጊ አይደለም ብለዋል፡፡
የሆስፒታሉ አስተዳደር የፃፈው ደብዳቤ ግን ለእነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥ አልሆነም፡፡
ችግሩን ለማቃለል ርብርብ ማድረጉን፤ ታካሚዎቹ ህመም ፀንቶባቸው እንደነበር፣ ወላዷ እናት የሞተችው “በዋነኛነት” በመብራት መቋረጥ ሳይሆን በህመሟ መባባስ ምክንያት እንደሆነ ነው ደብዳቤው በደፈናው የሚገልፀው፡፡ በመብራት መቋረጡ ሳቢያ በህሙማን ላይ ጉዳት መድረስ አለመድረሱን በሚመለከት የተጠየቁት የህግ አገልግሎት ኃላፊ አቶ በቀለ በኩካ “በዘገባው ላይ በተገለፀው ዕለት መብራት መጥፋቱ የማይካድ ሃቅ ነው፤  በዚሁ ምክንያት የሰው ህይወት አልፏል ወይንስ አላለፈም በሚለው ጉዳይ ላይ ግን በማስተባበያ ደብዳቤው ላይ በተገለፀው መሠረት ብቻ ማረሚያ አውጡ” በማለት ለጥያቄያችን ምላሽ ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡
ባለፈው ሳምንት የሆስፒታሉ ተጠባባቂ ሜዲካል ዳይሬክተር ዶ/ር አብይ ሚካኤል፤ መረጃ እንዲሰጡን ጠይቀናቸው፤ “ምላሻችንን በኢሜይል እልካለሁ” ካሉን በኋላ፤ “ከሆስፒታሉ ሃኪሞች ጋር መነጋገር አለብኝ” በማለት ምላሽ ሳይሰጡን መቅረታቸው ይታወሳል፡፡    
ሆስፒታሉ፤ ሁሉም የጤና ባለሙያዎች ተጋግዘው የሚሰሩበትና ነርሶችም በኃላፊነት ከሃኪሞች ጋር የህክምና አገልግሎት በመስጠት የሚሳተፉበት አሰራር እንዳለ ደብዳቤው አክሎ ገልጿል፡፡  

    ኢትዮ ቴሌኮም፤ በ“አፍሪካ ቴሌኮም ሊደርሺፕ አዋርድ” በአራት ዘርፎች የአመቱ ምርጥ ተብሎ መሸለሙን አስታወቀ፡፡
የዓመቱ ምርጥ ቴሌኮም ኦፕሬተር፣ የአመቱ ዋና ስራ አስፈፃሚ፣ ለሰው ሀይል አስተዳደር ትኩረት የሰጠ ምርጥ ዋና ስራ አስፈፃሚና አለም አቀፍ ቀጣይነት ያለው ስራ አመራር  የተገበረ ተቋም በሚሉ ዘርፎች ከተለያዩ የአፍሪካ አገራት የቴሌኮም ተቋማት ጋር ተወዳድሮ በማሸነፍ፣ በ5ኛው የአፍሪካ የስራ አመራር ሽልማት ተሸላሚ መሆኑን ኩባንያው አስታውቋል፡፡
በሽልማት ፕሮግራሙ ላይ የተገኙት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ አንዷለም አድማሴ፤ ኩባንያው የሀገሪቱን ህዝቦች የቴክኖሎጂ ተቋዳሽ ለማድረግ መጠነ ሰፊ ፕሮጀክት ነድፎ ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጠዋል፡፡ ሽልማቱም አነሳሽና ለበለጠ ሰራ የሚያተጋ እንደሆነ ተናግረዋል፤ዋና ስራ አስፈፃሚው፡፡ ውድድሩን የመሩት ዳኞች አለማቀፍ እውቅና ካላቸው ኩባንያዎች የተውጣጡ ኤክስፐርቶች መሆናቸውም ታውቋል፡፡