Administrator

Administrator

ውዳሴ ዲያግኖስቲክ ሴንተር በየዓመቱ የሚያከናውነውና “ጳጉሜን ለጤና” የተሰኘው ነፃ የምርመራ አገልግሎት የፊታችን ማክሰኞ ይጀምራል፡፡
ማዕከሉ ከትናንት በስቲያ በሸራተን አዲስ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫና የፓናል ውይይት ላይ የማዕከሉ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ዳዊት ኃይሉ እንደተናገሩት፤ ማዕከሉ ያለበትን ማህበራዊ ኃላፊነት ለመወጣት ላለፉት ሰባት ዓመታት የሲቲስካን፣ ኤምአርአይ እና ሌሎች የተለያዩ የምርመራ አገልግሎቶችን ገንዘብ ከፍለው መታከም ለማይችሉ ህሙማን ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ከአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች እና ከአዲስ አበባ ከተማ የሚመጡና የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች በሀኪሞቻቸው ታዞላቸው በገንዘብ ማጣት ምክንያት ምርመራውን ለማግኘት ያልቻሉ ህሙማን፤ ከጳጉሜ 1-5/ 2008 ዓ.ም ድረስ በማዕከሉ በሚሰጠው ነፃ የምርመራ አገልግሎት ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
ማዕከሉ ላለፉት ሰባት ዓመታት በየዓመቱ በሚሰጠው በዚህ ነፃ የምርመራ አገልግሎት፣ ከ15ሺህ በላይ ህሙማን ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለፁት ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፤ በቀጣይም አገልግሎቱን በስፋት ለመስጠት ዕቅድ መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ በማዕከሉ ዓመቱን ሙሉ ገንዘብ ከፍለው አገልግሎቱን ማግኘት ለማይችሉ ወገኖች ከሚሰጠው ነፃ የምርመራ አገልግሎት በተጨማሪ “ጳጉሜን ለጤና” በሚል መሪ ቃል፣ በየዓመቱ በሚሰጠው ነፃ የምርመራ አገልግሎት ከ800-1000 ወገኖች ተጠቃሚ እንደሚሆኑም ገልጸዋል፡፡ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች በሃኪሞቻቸው ታዞላቸው በአቅም ማጣት፣ አገልግሎቱን ማግኘት ያልቻሉ ህሙማን በተጠቀሱት ቀናት ወደ ማዕከሉ በመሄድ፣ ምርመራውን በነፃ ማግኘት እንደሚችሉም አቶ ዳዊት ተናግረዋል፡፡
ማዕከሉ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ከመወጣት አንፃር በክፍለ ከተማው ለሚኖሩ ወገኖች ነፃ የአንቡላንስ አገልግሎትን ከመስጠቱም ሌላ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች የለሚያስፈልጋቸው የክፍለ ከተማው ነዋሪዎች መታወቂያቸውን ይዘው በመቅረብ፣ የ20 በመቶ ቅናሽ ለማግኘት እንደሚችሉ ጨምረው ገልፀዋል፡፡ 

   በርካታ ታላላቅ ዓለማቀፍ የሙዚቃ ሽልማቶችን በማስገባት ስኬታማ የሙዚቃ ጉዞውን የቀጠለው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ፤ በ2017 የዓለም የክብረወሰን መዝገብ በሁለት ክብረ ወሰኖች መመዘግቡን ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ዘ ዊክንድ በሚል ቅጽል ስሙ የሚታወቀው የ26 አመቱ ድምጻዊ፤ “ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” በሚለው የሙዚቃ አልበሙ ባለፈው የፈረንጆች አመት በ“ስፖቲፋይ” ድረገጽ ተጠቃሚዎች በብዛት በመታየቱና ሙዚቃዎቹ በቢልቦርድ የሙዚቃ ሰንጠረዥ ለረጅም ተከታታይ ሳምንታት በምርጥ አስር ዝርዝር ውስጥ በመቆየታቸው፣ በአለም የክብረ ወሰን መዝገብ ላይ በሁለት ክብረ ወሰኖች ስሙን ማስፈሩ ተገልጧል፡፡
“ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” የተሰኘው የአቤል የሙዚቃ አልበም ከታህሳስ 2014 እስከ ታህሳስ 2015 ባለው አንድ አመት ጊዜ ውስጥ በ60 ሚሊዮን የ“ስፖቲፋይ” ተጠቃሚዎች በመታየት ክብረ ወሰን ማስመዝገቡን የጠቆመው ተቋሙ፣ የድምጻዊው ዘፈኖች ከመጋቢት 2015 እስከ ጥር 2016 ባሉት ጊዚያት፣ ለ45 ተከታታይ ሳምንታት በቢልቦርድ የሙዚቃ ሰንጠረዥ ምርጥ አስር ደረጃ ውስጥ ተካትተው መቆየታቸውን ገልጧል፡፡

1- ኢህአዴግ ያለፉት 15 ዓመታት የተሃድሶ ጉዞውን ገምግሞ ሲያበቃ ያወጣው መግለጫ ግርታን ፈጥሯል፡፡ እርስዎስ የገዢውን ፓርቲ መግለጫ እንዴት አዩት?
ሀ) በህዝብ ተቃውሞ ከሚናጥ ፓርቲ የወጣ መግለጫ አይመስልም!
ለ) በስህተት ያለፈውን ዓመት መግለጫ ደግመውት እንዳይሆን!
ሐ)  ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ!!
መ) ኢህአዴግ ራሱን በራሱ በመሸወድ የሚደርስበት የለም!
ሠ) የሌላ አገር ፓርቲ ያወጣው መግለጫ ሳይሆን አይቀርም!
2- ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ፤ባለፈው ሳምንት የመኢአድ መሪዎችን በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዳወያይዋቸው ተዘግቧል፡፡ በኢህአዴግ የ25 ዓመት የሥልጣን ታሪክ፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችን በቤተ-መንግስቱ ጋብዞ ሲያነጋግር የአሁኑ የመጀመሪያው ነው ተብሏል፡፡ እርስዎ ዜናውን ሲሰሙ ምን አሉ?  
ሀ) እቺ አገር ተስፋ አላት!!
ለ) ግብዣ ነው ውይይት?
ሐ) ከውይይቱ የተገኘው ውጤት አልተነገረንም!!
መ) ግን እስከ ዛሬ ለምን ዘገዩ!?
ሠ) “የቱርክ ኢንቨስተሮችን ሲባሉ ከተቃዋሚዎች ጋር ተሞዳሞዱ” በሚል እንዳይገመገሙ ሰጋሁ!
3- በሪዮ ማራቶን 2ኛ በመውጣት ድል ያስመዘገበው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ፤ ለኦሮሞ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ያለውን የትግል አጋርነት ለማሳየት እጆቹን ወደ ላይ በማጣመር ተቃውሞውን ለዓለም ገልጧል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ አትሌቱ ወደ አገሩ ቢመለስ የተለየ ችግር እንደማይገጥመው አስታውቋል፡፡ እውነት ወደ አገሩ ቢመለስ  ችግር ሳይገጥመው በነጻነት የሚኖር ይመስልዎታል?
ሀ) ይሄን ለማወቅ ኢህአዴግን መሆን ይጠይቃል!
ለ) “አልበላሽምን ምን አመጣው?!” አለች ጦጢት!!
ሐ)መንግስት እንዳይምልለት ፕሮቶኮሉ አይፈቅድም!   
መ) ቆይ ግን ምን ፍለጋ ወደ አገሩ ይመለሳል!?
ሠ) ኢህአዴግ ገና አሁን ንግግር ተሳካለት!
4- በአማራና በኦሮምያ ክልሎች ህዝባዊ ተቃውሞ በተቀሰቀሰበት በአሁኑ ወቅት የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትር ቢሆኑ ምን ዓይነት የመፍትሄ እርምጃ ይወስዱ ነበር?
ሀ) እስካሁን በኦሮምያ ቢያንስ 4፣በአማራ 2 ህዝባዊ ውይይቶችን አደርጋለሁ!
ለ) በቀውጢ ሰዓት ጠ/ሚኒስትር መሆን አልፈልግም!
ሐ) ተቃውሞውን ተከትሎ የታሰሩ ዜጎችን በሙሉ እፈታለሁ!!
መ) ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር መደበኛ ውይይት እጀምራለሁ!
ሠ) “ከበሮ በሰው እጅ ሲያዩት ያምር፣ሲይዙት ያደናግር!; የሚለው ተረት ትዝ አለኝ!!
5- የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፤በህዝቡ ላይ ፍርሃት ላለመፍጠር በሚል በአተት የሞቱ ሰዎችን ቁጥር አንድም ያስተባብላል አሊያም ጨርሶ ከመናገር ራሱን ያቅባል፡፡ ይሄን የሚያደርገው ለምንድን ነው ብለው ያስባሉ?
ሀ) እንደ ኢህአዴግ የቁጥር ፎቢያ ይኖርበታል!!
ለ) ወረርሽኙ ሲቆም ለተረፍነው “ሰርፕራይዝ” ሊያደርገን ፈልጎ ነው!
ሐ) አተትም ፖለቲካ ሆናለች ማለት ነው!!
መ) የአገር ገጽታ እንዳይበላሽ ተብሎ ይሆን?
ሠ) ፍርኃት እኮ ህዝቡን የበለጠ እንዲጠነቀቅ ያተጋዋል!
(N.B- ከተሰጡት ምርጫዎች ውስጥ ለእርስዎ የሚስማማ ከሌለ፣
የራስዎትን ምርጫ (ረ) የማካተት መብትዎ የተጠበቀ ነው!!!)

   በኦሮሚያና በአማራ ክልል እየተካሄዱ ያሉ ተቃውሞዎች፣የተጠራቀመ የህዝብ ብሶት ፈንድቶ የታየባቸው ናቸው፡፡ አመፁ የህዝብ ብሶት የወለደው ምሬት ነው፡፡ የኢህአዴግ ሰርአት አንገሽግሾት የወጣ ነው፡፡ ለብዙ ጊዜ የነበረ በደልና ጭቆና፣ ትንሽ ወቅታዊ ምክንያት በመፈለግ ሲፈነዳ የታየበት ነው። ለምሳሌ በኦሮሚያ ማስተር ፕላኑ መነሻ ምክንያት ነው፡፡ መሠረታዊ መነሻ አይደለም፡፡ በአማራ ክልልም መሠረታዊ መነሻው የወልቃይት ጉዳይ አይደለም፡፡ እሱ መነሻ ምክንያት ነው እንጂ ዋና ምክንያቱ ጭቆና ነው፡፡ የተደራጀ አመራር ወይም ሃይል የሌለውም በዚህ የተነሣ ነው፡፡ ህዝብ ያለ መሪ ስሜቱን የገለፀበት አመፅ ነው፡፡
 ይሄን አመፅ የሚመራው ድርጅት ከሌለና ካልተደራጀ ዝም ብሎ ንብረት መውደምና የሠው ህይወት መጥፋት ብቻ ነው የሚያስከትለው፡፡ ምክንያቱም ከኢህአዴግ ተፈጥሮ አንፃር ስናየው፤ ለህዝብ ጥያቄ መልስ ከመስጠት ይልቅ የሃይል እርምጃ መውሰድ ነው የሚቀናው፡፡ ህዝቡ ደግሞ እየተነቃቃ ለውጥ እየፈለገ ሲሄድ፣ ዝም ብሎ ንብረት መውደምና ህይወት መጥፋት ይሆናል። መጨረሻም ለውጥ ላይኖረው ይችላል፡፡ ለውጥ የሚኖረው የተደራጀና መሪ ሲኖረው ብቻ ነው፡፡ ህዝብ የሚተማመንበት ሃገራዊ የፖለቲካ ድርጅት ሲኖር ነው መነሳሳቱ ለውጥ ሊያመጣ የሚችለው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ፓርቲዎች በተለያየ አቅጣጫ ተደራጅተው፣ እርስ በእርስ ከመናቆር በመላቀቅ፣ ለሃገሪቱ መድህን መሆን አለባቸው። የህዝብ ችግር የኛ ችግር ነው ብለው ህዝቡን ለመምራት አንድነት ፈጥረው፣ሃገሪቷን ከአደጋ ለመጠበቅ መንቀሳቀስ አለባቸው፡፡ ይህን ካደረጉ ህዝቡን ይዘው ከኢሕአዴግ ጋር የመደራደር አቅም ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ ወደ ድርድርና የፖለቲካ ውይይት እንዲገባ የማስገደድ ዕድል ያገኛሉ፡፡ ኢህአዴግም ከህዝቡ የተነሳው ተቃውሞ ሰፊ መሠረት ያለው መሆኑን አውቆ፣ ለድርድር ራሱን ሊያዘጋጅ ይችላል፡፡
ያለበለዚያ ኢህአዴግም እርምጃ እየወሰደ መቀጠሉ ስለማይቀር፣ዝም ብሎ መጠፋፋት ነው የሚሆነወ፡፡ ወደ እርስ በእርስ ግጭት ነው ሊያመራ የሚችለው፡፡፡ የህዝቡ የለውጥ ፍላጎት በሚገባ ካልተደራጀ፣ መጨረሻ ላይ ደግሞ እየተዳከመ ይሄዳል፡፡ ኢህአዴግ የህዝብን ሃሳብና ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ በህዝብ ላይ የሃይል እርምጃ መውሰድ መፍትሄ መሆን እንደማይችል መገንዘብ ይኖርበታል። ሃገሪቷንና ህዝቡን ከአደጋ የማዳን ሁኔታ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ስራ ነው የሚሆነው። አሁን ህዝቡን መምራት መቻል አለባቸው። የመደራደር አቅማቸውን ማሳደግ ይገባቸዋል፡፡ እነሱም አንድ ሆነው፣ሁሉንም የኢትዮጵያ ህዝብ በአንድነት እንዲቆም ማድረግ አለባቸው፡፡

    ችግሩ በውይይት ይፈታ ሲባል የምሁራን የቃላት ስንጠቃና የፖለቲከኞች ውይይት እንዳይሆን ነው። ችግሩ በዚህ አንቀፅና በዚህ ንዑስ አንቀፅ በሚል ሳይሆን ዕድት ያለ አዕምሮ ይዞ፣ በመሰብሰብ ሁሉንም አሳትፎ፣ ምን እናድርግ? ይህቺ ሀገራች ነች፤ለሀገራችን ለህዝባችን የሚበጀው የቱ ነው? ብሎ እንደ አዲስ ማሰብ ያስፈልጋል ባይ ነኝ፡፡ ይሄ ደግሞ የምሁራኑና የፖለቲከኞች ብቻ መሆን የለበትም። የሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ሀሳብ የሚወከልበት መድረክ መኖር አለበት፡፡ በተቻለ መጠን በተለይ በመንግስት በኩል በሰፊው ሊታሰብበት ይገባል።  የብልጣ ብልጦች ውይይት መሆን የለበትም። ለኢትዮጵያ ህዝብ እኛ ነን የምናውቅልህ ማለት አያስፈልግም፡፡ ሰፊው ህዝብ በሚገባ ይናገር፤እሱን እናዳምጠው፡፡ ይሄን ስናደርግ ደግሞ እየተቋሰልን እየተጋደልን መሆን የለበትም፡፡ በሁሉም በኩል ሰፊ ልብ ያስፈልጋል፡፡ በፅሞና ለመነጋገርም ጊዜ ያስፈልጋል፡፡ ታግሶ ነው መወያየት የሚያስፈልገው።

    በ97 ምርጫ ማግስት መንግስት በተቃዋሚዎች ላይ ከመጠን በላይ ኃይል መጠቀሙን በተመለከተ ያቀረበው ምክንያት ዘመናዊ የአድማ መበተኛ መሳሪያዎች የሉኝም የሚል ነበር፡፡ ዛሬም በዘመናዊ መንገድ አድማ መበተን አልቻለም። ለነገሩ በመጀመሪያ ደረጃ መበተንስ ያስፈልጋል ወይ? የሚለው መታየት አለበት፡፡ በእኔ እምነት ተቃውሞዎቹን እየበተነ ያለው የፖሊስ ሰራዊት አይመስለኝም፡፡ ወታደር ሲሰለጥን ግደል ሊባል ይችል ይሆናል፡፡ ፖሊስ ግን ሲሰለጥን ወንጀለኛን መግደል የወንጀሉን ምንጭ ለማጣራት ስለማይጠቅም ግደል አይባልም፡፡ ወንጀለኛ ከተገደለ ወንጀሉ አይታወቅም፡፡ ረበሹ የተባሉ ሰዎችን ከነሙሉ አካላቸው ይዞ ነው፣ ለምን ይህን አደረጋችሁ? በሚል የሚያጣራው፡፡ አሁን ግን ግንባርና ደረት እየመቱ ነው የሚገድሉት፡፡ ይሄ በምንም አይነት ሁኔታ ተቀባይነት የለውም፡፡
ሰዎች ረብሸው ጎማ አቃጥለው፣ ቤት ሰብረው ቢሄዱ በካሜራ አጣርቶ፣ እንደዚህ ሲያደርጉ ተይዘዋል ተብሎ ፍ/ቤት አቅርቦ ማስወሰን የሚቻል ነው፡፡ አሁን ግን ሽብር በመንዛትና በማስፈራራት አፈና እየተካሄደ ነው ያለው፡፡ ወላጆች፤ ልጆቻቸው መብታቸውን እንዳይጠይቁ፣ ቤታችሁ እሰሯቸውና ቀልቧቸው ነው እየተባለ ያለው፡፡ በአጠቃላይ እየተደረገ ያለውን ተቃውሞ መንግስት የሚያስተናግድበት መንገድ የመንግስት አይመስልም፡፡ ልጅ ቢያጠፋ ዝም ብሎ አይደበደብም፤ምንድን ነው ተብሎ ተጠይቆ ይመከራል፡፡ መንግስት ግን በዚህ መንገድ አይደለም ህዝብን እየያዘ ያለው፡፡
እንደኔ ሰላማዊ ተቃውሞዎቹ በኦሮሚያና በአማራ ክልል ብቻ ሳይሆን በብዙ የሀገሪቱ ክልሎች አሉ፡፡ ትግራይ ውስጥ ከምንግዜውም በላይ ሰው ተረብሾ ያለበትና በትክክለኛ መንገድ መተዳደር ያልቻሉበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በደቡብም ተመሳሳይ ነው። ግን ጎልተው እየወጡ ያሉት የኦሮሚያና የአማራ ክልል ናቸው፡፡ ከምንም በላይ የአማራ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር ነፍስ ዘርቶ፣ እግርና እጅ አውጥቶ እየተንቀሳቀሰ ነው ያለው። ይሄን እንግዲህ ኢህአዴግ የኔ ፍሬ ነው ሊል ይችል ይሆናል፡፡ ምክንያቱም የአማራ ብሄርተኝነት እፈልጋለሁ ሲል ነበር ተፈጠረለት። የአማራ ብሄርተኝነት ሲፈጠር ደግሞ የአማራ የሚባሉ ጥያቄዎችን ያመጣል፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በአግባቡ መመለስ አለበት ማለት ነው። የፈጠረው የአማራ ብሄርተኝነት የሚያመጣውን ጥያቄ መመለስ አለበት። እነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ ዝም ብሎ ከዚህም ከዚያም የሚነሱ አይደሉም፡፡ እነሱ እንደሚሉት፤ ሰው መሬት አስተዳደር ሄዶ ካርታ ስለተከለከለ፣ የኑሮ ውድነት ስላሰቃየው ወዘተ----የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ብቻ አይደለም፡፡ የነፃነት ጥያቄዎች ናቸው፡፡ የአዲስ አበባ ዙሪያ ማስተር ፕላን፣ ወለጋ ላለ ወጣት ይሄን ያህል ስሜት የሚሰጠው አይሆንም፡፡ አባይ አጠገብ ላለ የጎጃም ሰውም ጠረፍ ላይ ያለ መሬት ብዙም ሊያሳስበው አይችልም ነበር፤ ግን እነዚህ መነሻ ሰበቦች ናቸው፡፡
አፄ ኃይለሥላሴ በመጨረሻው ሰዓታቸው ላይ ጥያቄው የደሞዝ ይመስላቸውና ለወታደሩ ደሞዝ ይጨምራሉ፤እንደገና የነዳጅ ዋጋ ጥያቄ ይመስላቸውና የነዳጅ ዋጋ ያስተካክላሉ ግን በወቅቱ የነበሩት ጥያቄዎች እሳቸው ያሰቧቸው አልነበሩም፡፡ የነፃነትና መሰረታዊ የሆኑ የስርአት ለውጥ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ አሁንም ዋና ዋና የሚባሉትን ጥያቄዎች ከዚህ አንፃር መመልከት ያስፈልጋል እንጂ ዝም ብሎ በግምት መልስ በመስጠት ብቻ የሚገላገሉት አይደለም፡፡
ስልጣኑን የያዙት ሰዎች በባህሪያቸው የሚሰጣቸውን ምክረ ሀሳብ የሚቀበሉ አይደሉም፡፡ አይሰሙም አያነቡም፤ ቢሰሙም ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን ነው። እሱንም የሚሰሙት ያስተላለፉት መልዕክት በትክክል መነገሩን ለማጣራት ነው እንጂ ለማወቅ አይደለም፤ስለዚህ የመማር እድላቸው ሰፊ አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች እነሱ መስማት የሚፈልጉትን ብቻ ሳይሆን መስማት የማይፈልጉትንም ማድመጥ ይኖርባቸዋል፡፡ መፍትሄውን ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ እየተናገርን ነው፡፡ አዳምጠው ራሳቸውን ለለውጥ ዝግጁ የማያደርጉ ከሆነ፣ ሁኔታው ወደ አልሆነ አቅጣጫ ሊጓዝ ይችላል፡፡  እነሱም ክብር በሌለው ሁኔታ የሰሩት አንድም ሁለትም የሆነ ጥሩ ነገር ካለ ጠፍቶ ለውጥ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ስለዚህ ሁኔታው ወደዚያ እንዳያመራ ስርአት ያለው ሽግግር የሚፈጠርበትን ሁኔታ ማመቻቸት አለባቸው፡፡
በእጅጉ መማር ያለባቸው እነሱ ያላቸውን እውቀትና ኃይል ተጠቅመው፣ ጥሩ ነገር እንሰራለን ብለው የፈጠሩትን ስህተት፣ አሁን እነሱ ባላቸው የእውቀት ደረጃ ሊፈቱት አይችሉም፡፡ ስለዚህ ተጨማሪ እውቀትና አስተሳሰብ ማዳበር አለባቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች አዲስ አስተሳሰብና እውቀት ለመያዝ ዝግጁ እንዳልሆኑ የሰሞኑ መግለጫቸው ያመላክታል፡፡ መግለጫቸውን የሰማ ሰው፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ መሞታቸውን እርግጠኛ ይሆናል፡፡ አንድም እንኳ አዲስ መልዕክት የለውም፡፡ ከዚያ ሁሉ ገፅ መግለጫ አንድም የተጨበጠ መልዕክት አላገኘሁበትም፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነው፣ ይህን አይነቱን ውስብስብ ችግር ሊፈቱ አይችሉም። ስለዚህ ህዝቡ አመኔታ ሊጥልበት የሚችልበትን የመፍትሄ አቅጣጫ መከተል አለባቸው፡፡ ለዚህ ደግሞ ምሁራን የሚሰነዝሩትን የመፍትሄ ሃሳቦች በሚገባ ማዳመጥ አለባቸው፡፡  

ከአንድ የተረት ስብስብ መጽሀፍ የተገኘ ተረት የሚከተለውን ይመስላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በጣም ቁጠኛ የሆነ ልጅ ነበር፡፡ አባቱ የልጁን አመል ለመግራት አንድ ካርቶን ሙሉ ሚስማር ሰጠውና፤ “ቁጠኝነት ሲሰማህ አንድ አንድ ሚስማር እያወጣህ ከጣውላ በተሰራው ግድግዳ ላይ በመዶሻ ምታ” አለው፡፡
ልጁ የአባቱን ትዕዛዝ አክብሮ በመጀመሪው ቀን ሃያ አምስት ሚሥማር ግድግዳው ላይ ሲመታ ዋለ፡፡ ሃያ አምስት ጊዜ ተናዶ ነበር ማለት ነው፡፡ በሚቀጥለው ቀናት ግን ቁጣው እየቀነሰ ሄደ፡፡ ግድግዳ ላይ የሚመታቸው ሚስማሮች ቁጥር ቀስ በቀስ እየቀነሰ መጣ፡፡
በዚህም አንድ ግንዛቤ አገኘ፡፡ “ቁጣን መቆጣጠር ከመዶሻ ሥራ የቀለለኮ ነው” አለ፡፡ በመጨረሻው፤ ቁጣውን ሙሉ በሙሉ ተገላገለው፡፡ ወደ አባቱ ሄዶ፤ “አባዬ ቁጣ አቁሜያለሁ” አለው፡፡
አባትዬውም፤ “ለያንዳንዱ ሳትቆጣ ለዋልክበት ቀን አንድ አንድ ሚስማር ከግድግዳው ንቀል” አለው፡፡ ቀስ በቀስ ልጁ ሚስማሮቹን እየነቀለ ጨረሰና፤ “አባዬ ትዕዛዝህን ፈፅሜያለሁ፡፡ አንድም ሚስማር ግድግዳው ላይ የለም” አለው፡፡
አባት ልጁን ወደ ግድግዳው ወስዶ፤ ‹‹ጥሩ አድርገሃል ልጄ! ግን እስቲ ግድግዳው ላይ የቀሩትን ቀዳዳዎቹን ተመልከታቸው፡፡ ቀዳዳዎቹ አይጠፉም። በተቆጣህ ቁጥር አካባቢህ ላይ ቁስል ትተዋለህ፡፡ አንድን ሰው በጩቤ ወግተህ ጩቤውን ልትነቅልለት ትችላለህ፡፡ ቁስሉ ግን እዛው ነው። ጠበሳው አለ፡፡
ለቁጣህ ሺ ጊዜ ይቅርታ ልትጠይቅ ትችላለህ፡፡ ቁስሉ ግን እዚያው አለ። የቃልህ ቁጣ በአካል ላይ ጠባሳ እንደመተው ሁሌ ይኖራል፡፡ አስከፊነቱን ተገንዝበህ ከእንግዲህ አትድገመው!›› አለው፡፡
*   *   *
ንዴት፣ ቁጣ፣ ስሜታዊነትና ኃይል መጠቀም የሁልጊዜ ማሽነፍ ምልክቶች አይደሉም፡፡ ይልቁንም ጉጂነታቸው ያመዝናል፡፡ ኃይል ሚዛናዊ የአዕምሮ ቁጥጥርን ያዛባል፡፡ የድንገቴ ሁኔታን በቁጣና በኃይል ለመፍታት መሞክር ብዙ ሚስማር ግድግዳችን ላይ በመዶሻ እንድንመታ ያደርገናል፡፡ ሲበርድልን ደግሞ የሚተወው ጠባሳ አይጣል ነው! ጊዜያዊ መፍትሔ የዘላቂ ጠባሳ ወላጅ ነው፡፡ ሰላማዊ ውይይትን ከሁሉም ነገር አስቀድመን እንደ ጥሞና ገበታ መቁጠር ብልህነት ነው፡፡ ችግር መኖሩን ከመካድ፤ አምኖ መፍትሔ መሻት፣ የቀና አመራር ብርቱ እጅ ነው፡፡ የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል! ርኩቻ ለሀገርም፣ ለህዝብም ጤና አይደለም፡፡ ቸኩሎ እርምጃ መውሰድም ከጥቅሙ ጉዳቱ ይበልጣል፡፡ ‹‹ቁጣና ስሜታዊነት ከሩቅ ግብ አንፃር ሲታዩ ፀረ-ምርታማነት ናቸው፡፡ ሁልጊዜ ረጋ- ያልክና እሙናዊ ሁን፡፡ አንተ የረጋህ ሆነህ ባላንጣህ እንዲቆጣ ካደረግኸው፣ ጠቀሜታው ያንተ ነው! ባላንጣዎችህን ሚዛን አሳጣቸው፡፡ እነሱ ይሯሯጡ-ገመዱን ግን አንተ ያዝ!›› ይለናል ሮበርት ግሪን። ልብ ያለው ልብ ይበል ነው ነገሩ፡፡ ከተሳሳትን ማስተካከያውን እናብጅ- እንጂ ‹‹ካፈርኩ አይመልሰኝ›› አንበል፡፡ ‹‹አንጋጠው ቢተፉ ተመልሶ ባፉ›› ነው መጨረሻው!
“አትጣደፍ፡፡ ጥድፊያ  ራስህን ለመቆጣጠር እንዳትችል ያደርግሃል፡፡ ጊዜንም በቅጡ እንዳትጨብጥ ያስገድዱሃል፡፡ ሁሌ ታጋሽ ሁን፡፡ የመጨረሻው ቀን ያንተ ይሆናል፡፡ ትክክለኛዋን ቅፅበት ሰልላት፡፡ ወደ አሸናፊ ኃይል ትቀየር ዘንድ ጊዜን የማሽተት አቅምህ ወሳኝ ነው፡፡ ጊዜህ ካልበሰለ አፈግፍግ፡፡ ከበሰለ ግን አትዘግይ፤ ጥርቅም አድርገህ ምታ” ይለናል ከላይ የጠቀስነው ደራሲ፡፡
በሀገራችን ጉዳይ ያገባናል የሚሉና በውይይት የሚያምኑ፣ ችግሮችን ለመፍታት አቅም ይኖራቸዋል፡፡ ሀገራችን ልበ - ብሩሃን ሰዎችን ትሻለች፡፡ ሆደ - ሰፊና ከስሜታዊነት ለመታቀብ ብቃቱ ያላቸውን ብልህ ሰዎች ትፈልጋለች። ችግሮቻችን በርካታና ሥር የሰደዱ እንደመሆናቸው  ሁሉ፣ የአንድ ሰው ሳይሆን የብዙዎችን ትከሻ፣ የብዙዎቹን ርብርቦሽ፣ የብዙዎችን አዕምሮ - ለአዕምሮ መናበብ የግድ ይሻሉ፡፡ አንድ ድርጅት፣ አንድ ማህበር፣ አንድ ተቋም ብቻ የሚፈታቸው አይደሉም፡፡ ‹‹ብቻውን የሚሮጥ የሚቀድመው የለ፣ ብቻውን የሚሟገት የሚረታው የለ›› የሚለው ተረት፤ ሌሎችን የማያሳትፍ አመራር ፋይዳው ትንሽ መሆኑን ነው የሚጠቁመን!!

Monday, 29 August 2016 10:21

ዳግማዊ ኦሮማይ

ኢህአዴግ ሕገ መንግሥት አርቅቆ ቢነሣም ሕገ መንግሥታዊነትን አላሰፈነም
          የሕዝብ ብሶት ሲያይል ሽንገላና ጊዜያዊ መፍትሔዎች ቀልቡን አይስቡትም
          በሥርዓቱ በመሾምና ንብረት በማግበስበስ መካከል እምብዛም ልዩነት የለም
                    ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ
   ለበዓሉ ግርማ ሞት ምክንያት የኾነው፣ ‹‹ኦሮማይ›› በሚል ርእስ የጻፈው መጽሐፍ እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡ እንደ እርሱ አተረጓጎም፣ ኦሮማይ ማለት አለቀ፣ ተፈጸመ፣ ሰዓቱ ደረሰ የሚል አንድምታ ያለው ቃል ነው፡፡ የበዓሉ ትረካ የደርግን ሥርዓተ መንግሥት ማብቂያ የሚጠቁም ሲኾን፣ ኒኮሎ ማኪያቬሊ የዛሬ አምስት መቶ ዓመት፣ ‹‹ስለ ልዑላኑ ማውራት ከአንገት ያሳጥራል›› እንዳለው የበዓሉም መጨረሻ በዚኹ መንገድ ተጠናቋል፡፡
የዚህ መጣጥፍ ዋና ዓላማ፣ በዓሉ፣ ‹‹ኦሮማይ›› በሚለው መጽሐፉ የደርግ ሥርዓት እያበቃለት መኾኑን እንደጠቆመው፣ እኔም በአኹኑ ወቅት በአገራችን እየተከሠተ ያለው ቀውስ፣ የኢሕአዴግ የፖለቲካ ሥርዓት ወደ ማብቂያው እየተጓዘ መኾኑን እንደሚያመለክት ለማሳየት ነው፡፡ ለመጣጥፌ ‹‹ኦሮማይ›› የሚለውን የበዓሉን ቃል በመዋስና የእርሱን ትረካ እንደ ‹‹ቀዳማዊ ኦሮማይ›› በመውሰድ፣ አኹን ኢሕአዴግ ያለበትን የፖለቲካና የሥርዓት ቀውስ ‹‹ዳግማዊ ኦሮማይ›› ብዬዋለኹ፡፡ እዚኽ ላይ ቀዳማዊም ኾነ ዳግማዊ ኦሮማይ የአንድን ሥርዓት የፍጻሜ ደውል የሚያስተጋቡ መኾናቸውን ልብ ይሏል፡፡
ኢሕአዴግ የሚመራውን ሥርዓት ከኦሮማይ ኹኔታ ጋር አዛምዶ ለማየት የሚያስችሉ በርካታ መገለጫዎች ቢኖሩም፣ ለዚኽ ጽሑፌ የሚከተሉትን ሦስት ነጥቦች እንደ ማሳያ አቀርባለኹ፡፡  
አገር በጄ
በዚኽ ነጥብ የማነሣው ዋነኛ ርእሰ ጉዳይ፣ ከኢሕአዴግ በፊት የነበሩት የፖለቲካ ሥርዓቶች የነበረባቸውን ግድፈቶች በማስወገድ፣ ለሕዝቦች ነጻነት እና ለጠንካራ አገራዊ አንድነት ዋስትና በሚል መርሕ የተመሠረተው ፌዴራላዊ የፖለቲካ ሥርዓት መከተል የሚገባውን ፈር ለቆ፤ ከዚኽ በፊት ‹‹አገር በጄ›› ብለው እንደተነሡት ነገሥታት ኢሕአዴግም፣ ያንኑ የጠቅላይነት ሥርዓት በፓርቲ የበላይነት እንደተካው ለማሳየት ነው፡፡
ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ አሰባስበው በአሰናዱትና፣ ‹‹Kasa and Kasa›› በሚል ርእስ በታተመው መጽሐፋቸው፣ ስለ ዘመነ መሳፍንት አስደናቂና ፈር ቀዳጅ የታሪክ እይታ ያላቸውን ነጥቦች አቅርበዋል፡፡ እንደ ፕሮፌሰሩ አቀራረብ፣ ዐፄ ቴዎድሮስ ቀደም ሲል ከነበረው የአገዛዝ ሥርዓት የተለየና አዲስ ሥርዓት መሥርተዋል። ይህንኑም አዲስ ሥርዓት፣ ‹‹አገር በጄ›› የሚል ስያሜ ሰጥተው ካብራሩት ሦስት ምሁራን (ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ፣ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴና ብላቴን ጌታ ማኅተመ ሥላሴ ወልደ መስቀል) መነሻ ሐሳብ በመውሰድ የራሳቸውን ትንተና አቅርበዋል፡፡
ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ በዚኹ ትንታኔአቸው፣ ዐፄ ቴዎድሮስ ‹‹አገር በጄ›› ብለው መሳፍንቱንና መኳንንቱን እንዲኹም ከፍተኛ ማዕርግ ያላቸውን ባላባቶች ወደ ጎን በመገፍተር በምትካቸው ራሳቸው በመረጧቸውና ዝቅተኛ የሹመት ደረጃ ባላቸው ምስለኔዎች ማስተዳደር እንደ ጀመሩ አብራርተዋል፡፡ እንግዲኽ ይህ በዐፄ ቴዎድሮስ የተወጠነው የ‹‹አገር በጄ›› መርሕ ነው፣ ከዐፄ ቴዎድሮስ ጀምሮ እስከ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ድረስ ተጠናክሮ የቀጠለው፡፡ ይህ መርሕ በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ይበልጥ ተጠናክሮ፣ ‹‹ጠቅል›› የሚል ስያሜ በመያዝ ሙሉ ለሙሉ ጠቅላይ አሐዳዊ ሥርዓት ኾነ፤ ደርግም ቢኾን ይህን አሐዳዊ ሥርዓት በሶሻሊስት ሥርዓት መርሕ አስቀጠለው፡፡
በደርግ ውድቀት ዋዜማ የኢሕአዴግ አዲስ ሕገ መንግሥት ተረቆ አገሪቷ፣ ወደ አገር በጃችን (ፌደራላዊ) ሥርዓት መሸጋገሯን ይደነግጋል፡፡ ይህንንም የፌደራል ሥርዓት ተግባራዊ ለማድረግ አገሪቱ በተለያዩ የክልል መንግሥታት ተዋቀረች፡፡ ይኸው፣ ሕዝቦችን የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤት የሚያደርግ ነው በሚል መርሕ የተመሠረተው አዲሱ ፌዴራላዊ ሥርዓት ጥቂት መንገድ ከተጓዘ በኋላ በሒደት፣ አገር በጃችን ቀርቶ አገር በፓርቲዬ መኾን ጀመረ፡፡
በዚኽ የ‹‹አገር በጄ›› መርሕ፣ አንድ ገዢ ፓርቲ ፍጹም የበላይነት ከተቀናጀ በኋላ የፈለገውንና የተመቸውን የክልሎች ግዛትና ሀብት፣ ‘የፓርቲዬና እኔ ወክዬዋለኹ የሚለው ሕዝብ ንብረት ነው’ ብሎ በተስፋፊነት ቢራመድ የሚያስገርም አይኾንም፡፡ የገዢው ፓርቲ የበላይነት ሥር ከሰደደ በኋላ የሕዝቦች ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብት በእጅጉ እየተገደበ ሔዷል፡፡ በየክልሉ የሚነሡ የማንነት ጥያቄዎች፣ በኢንቨስትመንት ስም የሚካሔደው የመሬት ወረራ፣ ‘ራሳቸውን የማስተዳደር አቅም የላቸውም’ በሚል ሰበብ የሕዝቦችን ሉዓላዊነትና የራሳቸውን ክልል በራሳቸው የማስተዳደር መብት የመጣስ ችግሮች፤ በአኹኑ ወቅት አስከፊ ደረጃ ላይ ደርሰዋል፡፡
አገር በጄ በሚለው ፅንሰ ሐሳብ፣ ነገሥታቱ በተበታተነ መልኩ በተለያዩ መሳፍንት ይተዳደሩ የነበሩ ግዛቶችን አዋሕደው አገራዊ አንድነትን አጠናክረዋል። ይህን በሚያደርጉበት ጊዜ ግን፣ ለአገር አንድነት የነበራቸውን ትልቅ ግምትና ቦታ ያኽል፤ ለሕዝቦች ነጻነት፣ ማንነትና መብት መጠበቅም ተገቢውን ትኩረት አልሰጡትም ነበር፡፡ ኢሕአዴግ በበኩሉ፣ ሕገ መንግሥት ቀርፆ ፌዴራላዊ ሥርዓት ሲመሠርት፣ የግዛት አንድነት ብቻ ሳይኾን የሕዝቦች ነጻነትም ለአንድ አገር ህልውና አስፈላጊ ነው፤ በሚል መርሕ ከአሐዳዊ አገዛዝ ወደ ፌዴራላዊ አገዛዝ ማለትም ከ‹‹አገር በጄ›› ወደ ‹‹አገር በጃችን›› ለማሸጋገር በማለም ነበር፡፡
የዚኽም ሽግግር ዓላማ፣ የአገሪቱን አንድነት አስጠብቆ ለዜጎች መብትንና ነጻነትን የሚያጎናጽፍ የፌደራል ሥርዓትን በሕገ መንግሥት ለመመሥረትና ሕገ መንግሥታዊነትን ለማስፈን ነበር፡፡ ይህ ዓላማም ኢትዮጵያ፣ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች አገር መኾኗን በመገንዘብ የአገሪቷን አንድነት ለማስጠበቅና የሕዝቦችን መብት ለማስከበር ነበር፡፡
ነገር ግን፣ የኢሕአዴግን አገዛዝ ስንመለከት፣ አገር በጄ ወይም አገር በፓርቲዬ የሚለው አካሔድ፣ የአገሪቱን የአንድነት ጉዞም ኾነ የሕዝቦችን የነጻነትና የመብት ፈለግ አልተከተለም፡፡ ይልቁንም የተወሰኑ ወገኖችን ጥቅምና የበላይነት ማእከል በማድረግ፣ ነገሥታቱ ያስጠበቁትን የአገር አንድነት በማፋለስና በፌዴራሊዝሙ አስከብረዋለሁ ያለውን የአገር አንድነትም ኾነ የሕዝቦች መብትና ነጻነት በመጋፋትና በመፈታተን አዝማሪው እንዳለው ‹‹...ኹለተኛ ጥፋት›› ኾኗል፡፡
ኢ-ዴሞክራሲያዊነት
የኢሕአዴግ የፖለቲካ ሥርዓት ሲጀምር፣ ሕገ መንግሥት በወረቀት ላይ አርቅቆ በአንድ በኩል፣ ከአሐዳዊ ወደ ፌደራላዊ ሥርዓት ሽግግር ሲደነግግ በሌላ በኩል ደግሞ፤ ከግለሰባዊ አገዛዝ፤ የሥልጣን ክፍፍልን መሠረት ወደ አደረገ ዴሞክራሲያዊ ጎዳና ለመግባት የሚያስችል መንገድ ከፍቶ ነበር፡፡ እዚኽ ላይ ቁልፍ ጉዳይ የሚኾነው፣ በሕገ መንግሥቱ ውስጥ የተደነገጉ ሠናይ ትልሞች አኹን ባለንበት የፖለቲካ ምዕራፍ በምን ደረጃ ላይ እንዳለ ስንጠይቅ ነው፡፡
ይህን ጥያቄ ይዘን፣ የኢሕአዴግን የ21 ዓመት የሕገ መንግሥት ጉዞ ስንገመግመው፣ ሥርዓቱ ሕገ መንግሥት አርቅቆ ቢነሣም ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓተ ወግን ሊጎናጸፍ ግን አልቻለም፡፡ ይኸውም ኢሕአዴግ፣ ሕዝቦችን ለሉዓላዊ የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤት ከማብቃት ይልቅ በጥቂት ሰዎች እንዲከማች ያደረገ፤ ሕገ መንግሥትን ማጽደቅ እንጂ ሕገ መንግሥታዊነትን ያላሰፈነና በኹሉም መልኩ የበላይነት የተጎናጸፈ ሥርዓት መኾኑ ነው፡፡ ለዚኽም እውነታ የሚከተሉትን ነጥቦች በማሳያነት ማቅረብ ይቻላል፡፡
አንደኛ፣ ማንኛውም ዴሞክራሲ በመሠረቱ የፖለቲካ ሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር ያስገድዳል፡፡ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ምኅዳር በምናይበት ጊዜ፣ ሥርዓቱ፣ ‹‹የፖለቲካ ሥልጣንን ለሕግ አውጭው፣ ለሕግ አስፈጻሚውና ለሕግ ተርጓሚው ያከፋፈለና የመንግሥት ሥልጣንን የገደበ ነው፤›› ቢባልም፤ የሕግ አስፈጻሚው ክፍል በአንድ በኩል ፌዴራሊዝሙን በሌላ በኩል ደግሞ፣ በሕግ አውጪውና በሕግ ተርጓሚው ላይ ትልቅ ጫና በማሳረፍ ሥልጣናቸውን በእጅጉ ገድቦታል፡፡ በመኾኑም የሕግ አስፈጻሚው ተቋም ራሱን እያፋፋና እያጠናከረ በአንፃሩ ሌሎቹን የመንግሥት ተቋማት እያሽመደመደ ሔዷል፡፡
ኹለተኛ፣ ከአገራችንም ኾነ ከሌላው አገር ታሪክ እንደምንረዳው፣ ሕግ ለነጻነት ትልቅ ዋልታ ነው፡፡ በመኾኑም የአንድን አገር ፍትሕም ኾነ ነጻነት ለማስከበር የፍትሕ ተቋማት በነጻነትና በገለልተኛነት መንቀሳቀስ መቻል አለባቸው፡፡ ኾኖም በአገራችን የፍትሕ ተቋማት የራሳቸው ልዕልና ኖሯቸው የሚንቀሳቀሱ አይደሉም፡፡ የራሳቸውን ልዕልና ያላስከበሩ ተቋማት ደግሞ የዜጎችን ነጻነት ያስከብራሉ ለማለት አይቻልም፡፡ በዚኽም የተነሳ የሕግ የበላይነት ሳይኾን የፖለቲካ ፍላጎት የበላይነት ትልቁን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ሕግ ባለሥልጣናትን መቆጣጠር ሲገባው በተቃራኒው ባለሥልጣናት ሕግን እንዳሻቸው ለመቆጣጠር አስችሏቸዋል፡፡ በመኾኑም አገሪቱን የሚያስተዳድሩ መሪዎች የሕግ ማህቀፍ ሳይጣልባቸው በዘፈቀደ ሕግ እያወጡ ለፖለቲካ መሣርያነት እንዲጠቀሙበት ኾኗል፡፡
ሦስተኛ፣ ማንኛውም ሕገ መንግሥት በዜጎችና በመንግሥት መካከል የሚገኝ የውል ሰነድ ነው፡፡ ይኹንና የውል ፍጥጥሙን፣ በብሔርና በመንግሥት መካከል ያደረገው የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ግን፣ ለዜግነት ተገቢውን ቦታና ዋጋ አልሰጠም፡፡ በመኾኑም ብሔር የሚለው እሳቤ ጎልቶ ሲቀርብ፣ ዜጋ የሚለውን እሳቤ አኮስሶታል፡፡ ይህን የዜጋ እሳቤ ማኮሰሱ ሦስት ዐበይት ችግሮችን ፈጥሯል፡፡
አንደኛው፣ ዜጎች በብሔራቸው ከተመደበላቸው ክልል ውጭ ተንቀሳቅሰው መኖር እንዳይችሉ አድርጓቸዋል፡፡ ኹለተኛው፣ ከተለያዩ ብሔሮች የሚወለዱትንና ራሳቸውን ከብሔር ማህቀፍ ያወጡ ዜጎችን ብሔር አልባ እንዲኾኑ አድርጓቸዋል፡፡ ሦስተኛው፣ መጽሐፍ ቅዱስ እስራኤሎችን፣ ‹‹የተመረጡ ሕዝቦች›› እንደሚላቸው ኹሉ፣ በእኛ አገር የፖለቲካ ሒደትም በአገሪቷ ውስጥ ካሉ ብሔሮች መካከል ‘የተመረጠ ብሔርና ሕዝብ’ በሚል መድልዎ ይካሔዳል፡፡
ሥርዓቱ ፍጹም የበላይነትን ያሰፈነ ለመኾኑ አራተኛው ማሳያ፣ በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ የዴሞክራሲ ግብ የሚሠምረው፣ በአገሪቱ ውስጥ የሚተገበሩ ፖሊሲዎችን ከማርቀቅ ጀምሮ እስከ አፈጻጸም ያለው ሒደት፣ ኅብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ ሲከናወን ነው፡፡ በዚኽ ረገድ ኢሕአዴግ የሚያወጣቸው ፖሊሲዎች፥ ኅብረተሰቡን ያሳተፉ፣ የሕዝቡን አስተያየት ያካተቱና የሕዝቡን ይኹንታ አግኝተው የሚተገበሩ አይደሉም፡፡ ይልቁንም የምናወጣቸው ፖሊሲዎችና የምናስፈጽማቸው ተግባራት፣ ትክክለኛውን አቅጣጫ የተከተሉ ናቸው ብለው ስለሚያምኑ የተለያዩ ሐሳቦችና አመለካከቶች በግልጽና በሐቅ እንዲንሸራሸሩ ቦታ አይሰጡም፡፡ ይህ ፍጹም ርግጠኝነት ለዴሞክራሲ ማበብ ትልቅ መሰናክል እንደሚኾን መረዳት ተስኗቸዋል። ይህም ሕዝቦች በነጻነት ሐሳባቸውን የሚያቀርቡበት መድረክና የሚደመጡበት ተቋም (የብዙኃን መገናኛ) በአገሪቷ ውስጥ እንዳይኖር ምክንያት ኾኗል፡፡
ሙሰኝነት
በአማርኛ፣ ‹‹ሙስና›› በእንግሊዝኛ፣ ‹‹Corruption›› የሚባለው ስያሜ በጣም ሰፊና በተለያዩ የታሪክ ዘመናት የራሱ የኾነ ይዘት፣ ቅርፅና ትርጉም እየያዘ የመጣ ፅንሰ ሐሳብ ነው፡፡ ‹‹ሙስና›› ለሚለው ቃል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ የሚከተለውን ፍች ሰጥተዋል፡፡ ሙስና ማለት ‹ጥፉነት›፣ ‹ጥፋት›፣ ‹መፍረስ›፣ ‹መበስበስ›፣ ‹መከራ›፣ ‹መቅሠፍት›… ወዘተ ማለት ነው፡፡ እንዲኹም ‹‹ሙሱን (Agent)›› ‹የማሰነ›፣ ‹ጥፉ›፣ ‹መጥፎ›፣ ‹ብልሹ›፣ ‹ግም›፣ ‹ድፍር› …ወዘተ. ማለት ነው፡፡ እንደ እንግሊዝኛው ኦክስፎርድ መዝገበ ቃላት ፍች ደግሞ፣ ‹‹Corruption›› ማለት በዋናነት ‹መበስበስ›፣ ‹መቆርቆዝ›፣ ‹መበታተን›፣ ‹መዝቀጥ›… ወዘተ ሲኾን፣ ከእነዚህ ገለጻዎች የምናገኘው ምስል፥ ‹‹መበከል›› እና ‹‹ከተፈጥሯዊ ማንነት መውጣትን›› ነው፡፡
ልብ ብለን መገንዘብ የሚኖርብን ነገር ቢኖር፣ የአማርኛውም ኾነ የእንግሊዝኛው ትርጓሜ በሐሳብ ደረጃ ተቀራራቢነትና ተያያዥነት እንዳላቸው ነው። በተጨማሪም የአማርኛውም ኾነ የእንግሊዝኛው ፍቺ፣ አኹን በዘመናችን ካለው እሳቤ ጥልቀትና ስፋት ያለው ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህንንም የምንልበት ዐቢይ ምክንያት፣ ዘመናዊው አተያይ ሙስናን፣ ከኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ውጭ የማያይ፤ በግለሰብና በማኅበረሰብ ጥቅም መካከል የሚገኝ ሽኩቻ ብቻ አድርጎ ስለሚያቀርብ ነው፡፡
በአገራችን ያለውን የሙስና ደረጃና ኹኔታ በሚገባ ለማየት ግን የጥንቱንና ዘመናዊውን አተረጓጎምና አተያይ በድምር መውሰድ ይኖርብናል፡፡ እኔም ከፈላስፎች ጥቂት ብሂላትን በመውሰድ፣ ኹለቱንም አተያዮችና አተረጓጎሞች በጥቂቱም ቢኾን ማየቱ ጠቀሜታ ይኖረዋል፤ እላለኹ፡፡ የአራት ፈላስፎችን ሐሳብ አጠር አድርገን እንመልከት፡-
አርስቶትል፡-
እንደ ጥንታዊው የግሪክ ፈላስፋ አርስቶትል አስተምህሮ፣ የአንድን የፖለቲካ ማኅበር እንደ ሰንሰለት የሚያያይዘው ተቀዳሚ ዕሴት ፍትሕ ነው፡፡ ያለ ፍትሕ ማንኛውም ማኅበረሰብ በሰላምና በጸጋ ሊኖር አይችልም። ሙስና፣ ይህን ወሳኝ የሞራልና የሕግ ዕሴትና አውታር ስለሚያበትከውና ስለሚያመክነው ለማኅበረሰቡ ህልውና ትልቅ አደጋ ነው፡፡
ሲሰሮ፡-
ለሲሰሮ፣ የሙስና ተቀዳሚ መሠረቱ፣ ማኅበረሰቡን ለማስተዳደር ሓላፊነት የተቀበሉ ሰዎች በፍቅረ ንዋይ እየተነዱ ከዋናው ተግባራቸው መውጣታቸው ነው። ለዚኽ ፈላስፋ፣ ሙስና፣ ሰፋ ያለ የሞራል፣ የሕግና የፖለቲካ ብልሹነትን የሚጠቁም ጉዳይ ነው፡፡
ቅዱስ ኦገስቲን፡-
እንደ ቅዱስ ኦገስቲን አባባል፣ የሰውነት ክፍሎቻችን የየራሳቸው የሥራ ድርሻ እንዳላቸው ኹሉ፤ በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ የሚኖሩ ተቋማትም የየራሳቸው የሥራ ድርሻ አላቸው፡፡ እንደ እርሳቸውም እሳቤ፣ የሰው ልጅ አንድ አካሉ ሲታመም መላው ሰውነቱ እንደሚታወክ ኹሉ፤ ሙስናም፣ በአንደኛው የማኅበረሰብ አካል ከታየ ሌሎቹንም ክፍሎች እንደሚበክል ይናገራሉ፡፡
ኒኮሎ ማኪያቬሊ፡-   
እንደ ማኪያቬሊ አገላለጽ፣ የጥንት ሮማውያን ወታደራዊ ድል ከተጎናጸፉ በኋላ ግዙፍ ግዛተ ዐፄ/ኢምፓየር/ ገነቡ፡፡ በዚኽም ብዙ ሀብት እና ትልቅ የፖለቲካ ኃይል ማግኘት ቻሉ፡፡ ኾኖም ግን ያገኙት ሀብት እና ምቾት የተንደላቀቀ አኗኗር እንዲያገኙ ቢያስችላቸውም፣ ከንዋይ ጋር ተያይዞ ከሚመጣው የሞራል ዝቅጠት ሊያመልጡ አልቻሉም፡፡ ማኪያቬሊ፣ ይህን የታሪክ እውነታ ዋቢ በማድረግ ስለ ሙስና የጻፈውን በኹለት ነጥቦች አሳጥሬ ላቅርብ፡፡
ሀ/ ሙስና፣ ከምቾት እና ከቅምጥል ኑሮ የሚነሣ የሥነ ምግባር እና የዲስፕሊን ጉድለት ነው፡፡
ለ/ የግል ጥቅም ከማኅበረሰብ ጥቅም የበላይነት ይዞ ሲገኝ፣ ‹‹የእኔ…›› የሚለው የራስ ወዳድነት መንፈስ ከሪፐብሊኩ ፍላጎት እና መንፈስ ጋር ሲጋጭ ነው፡፡
በአገራችን ያለው የኢሕአዴግ ሥርዓት በሙስና የተዘፈቀ በመኾኑ ሳቢያ፣ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ከተሟሉ መገለጫዎቻቸው ጋር ተሸክሞ እንደሚገኝ አምናለኹ፡፡ የኢሕአዴግ ሥርዓት በአስከፊ ሙስና ውስጥ እንዲዘፈቅ በምክንያትነት ከሚጠቀሱ ነጥቦች መካከል የሚከተሉት ዋነኞቹ ናቸው፡፡
አንደኛው ምክንያት፣ መንግሥቱም ኾነ ዜጎች፣ በአገሪቱ የፖለቲካና የኢኮኖሚ መዋቅሮች የየራሳቸው ሓላፊነትና ድርሻ ሊኖራቸው ሲገባ፣ ይህ ካለመኾኑ የመነጨ ነው፡፡ ሥርዓቱ፣ እኒኽ ዜጎች በመንግሥት የተለያዩ መዋቅሮች ተገቢው ሓላፊነትና ድርሻ እንዳይኖራቸው በማድረግ ራሱ የፖሊሲ አውጪ፣ ራሱ አስፈጻሚና ራሱ ዋነኛ የኢኮኖሚው ተዋናይ ኾኗል፡፡
ከዚኽ ጎን ለጎን ሳይጠየቅ የማይታለፈው ደግሞ፣ ሥርዓቱ በሕዝብና በግለሰብ መብት መካከል ያለውን ልዩነት ማየት የተሳነው መኾኑ ነው፡፡ አንድ ግለሰብ፣ ፍትሕ ላይ የተመሠረተ፣ የማይሻርና የማይገሰስ መብት አለው፡፡ በመኾኑም ብዙኃኑን ይጠቅማል በሚል እሳቤ የግለሰቡን የማይገሰስ መብት መጣስ ፍትሐዊ አይደለም። በዚኽ ሥርዓት ግን የማኅበረሰቡን ወይም የብዙኃኑን ጥቅም ለማስከበር በሚል ሰበብ የግለሰቡ መብትና ህልውና ሲጨፈልቅ ይታያል፡፡ ይህም በዋነኛነት የግለሰቡ ጉዳት ፖለቲካዊ ኪሳራ አያመጣብኝም ከሚል እሳቤ የመነጨ ነው፡፡
ይህም መንግሥት ለግለሰቡና ለሲቪል ማኅበረሰቡ መላወሻ የማይሰጥ፣ አንድ ወጥ መንግሥታዊ ሥርዓት እንዲኾን አድርጎታል፡፡ እነዚኽ የሥርዓቱ ባሕርያትም፣ መንግሥት በኹሉም የአገሪቱ ሀብትና ንብረት ላይ እጁን እንዲዘረጋ፣ የመንግሥት የአስተዳደር ሕጎች በትክክል እንዳይተገበሩ፣ የአሠራር ብልሹነት እንዲስፋፋ፤ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት በማባከን ሥርዓቱ የሙስና መናኸሪያ እንዲኾን አድርጎታል፡፡
ከላይ የጠቀስናቸውን ፈላስፎች ሐሳብ አጠቃለን ስናየው፣ ሙስና የሚከተሉትን አሉታዊ ተጽዕኖዎች እና ውጤቶች ያስከትላል፡፡ እነርሱም፡- ኢፍትሐዊነት፣ የግል ጥቅም አሳዳጅነት፣ ሥርዓተ ብልሹነት፣ አድልዎና የሞራል ዝቅጠት ናቸው፡፡
በአገራችንም ያለው የኢሕአዴግ ሥርዓት፣ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ከተሟሉ መገለጫዎቻቸው ጋር የተሸከመ እንደኾነ ስለምናምን፣ ሥርዓቱ ደግሞ እንዴት ወደ እነዚኽ አስከፊ የሙስና ኹኔታዎች እንደገባ በሚከተሉት ነጥቦች ማሳየት ይቻላል፡፡
አንደኛ፡- የኢሕአዴግን የፖለቲካ ሥርዓት ስንመለከት፣ በይዘቱ በጣም ሰፊና ትልቅ መንግሥት ነው፡፡ ይህም አንዱ፣ በመንግሥትና በሲቪል ማኅበረሰብ መካከል ልዩነት እና ወሰን መኖሩን የማይቀበል ሲኾን፤ በሌላ በኩል ደግሞ፣ በሕዝብና በግለሰብ መካከል ያለውን መሠረታዊ ልዩነት በመናድ አንድ ወጥ የኾነ የጠቅላይ አገዛዝ መንግሥት የዘረጋ ኃይል ነው፡፡ ይህ ደግሞ፣ በኹሉም የአገሪቷ ንብረት ላይ በበላይነት እጁን እንዲከትና የብክነት እክሎችና የትግበራ እንከኖች ብሎም የሙስና መናኸሪያ እንዲሆን አድርጎታል፡፡     
ለሥርዓቱ በሙስና መዘፈቅ ኹለተኛው ምክንያት፣ ከፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል፣ በብቃት ላይ የተመሠረተ ውድድር፣ ከጤናማ የኢኮኖሚ ፉክክር፣ ከሕጋዊ የሀብት ምንጭ… ወዘተ አኳያ ትልቅ ክፍተት ያለበት ሥርዓት መኾኑ ነው፡፡ በእኔ ግምት ይህ ክፍተት ካለማወቅ የመነጨ ሳይኾን፣ ኾነ ተብሎ የፖለቲካ ሥልጣን ከጨበጡት ሹመኞች ጋር የብሔር ትስስር ያላቸውንና የእኛ የሚሏቸውን ወገኖች ለመጥቀም በማሰብ የተደረገ ነው፡፡ በዚኽ መልኩ ፍትሐዊነት በጎደለው በአንድ አገር የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ፣ እነዚህ ዕሴቶች በሚጓደሉበት ወቅት ደግሞ፣ አኹን በአገራችን እንደምናስተውለው፣ የአገሪቷ ሀብት የጥቂት ቡድኖች መጠቀሚያና ችሎታን መሠረት ያላደረገ ኢፍትሐዊ ውድድር ተጠቃሚ እንዲኾኑ አስችሏቸዋል፡፡
በአጠቃላይ በኢሕአዴግ ሥርዓት ውስጥ ያለውን የሙስና ደረጃ ስናየው፣ ሌቪ የተባለው የጥንታዊ ሮማ የታሪክ ምሁር ስለ ሙስና ያለውን ያስታውሰናል። ሌቪ እንደሚለው፣ ‹‹ሙስና የተንሰራፋበት ሥርዓት ዝም ብለው ቢተዉት ሥርዓቱን ማፍረሱ አይቀርም፡፡ በአንፃሩ ደግሞ፣ የተስፋፋውን ሙስና ለመግታት ሙከራ ቢደረግም እንኳ ሥርዓቱ መፍረሱ አይቀርም፡፡››
ከላይ ያነሣናቸው የአገር በጄ፣ የኢ-ዴሞክራሲና የሙስና መንሰራፋት ችግሮች፣ አኹን ሥርዓቱ ለአጋጠመው ሕዝባዊ ተቃውሞና ዐመፅ መንሥኤዎች ናቸው፡፡
ወደ ኦሮማይ ጎዳና
ሌኒን፣ በ1920 (እ.ኤ.አ)፣ አንድ አገር ዐብዮታዊ ኹኔታ ውስጥ ስትገባ የሚከተሉትን አራት ክሥተቶች እንደ ምልክት እናያለን ብሎ ነበር፡፡ እኔም ሥርዓቱ ወደ ዳግማዊ ኦሮማይ ድባብ እየገባ ነው፣ ብዬ ስለማምን የሌኒንን አራት መገለጫዎች አንሥቼ የራሴን አተያይ ለማቅረብ እሞክራለኹ።
1ኛ/ ለዐብዮቱ ጠላት የኾኑ መደቦች በመካከላቸው ባለው ውስጣዊ ትግል ምክንያት ወደ ውዥምብርና ክፍፍል ያመራሉ፡፡ ይህ ውስጣዊ ውዥምብር ደግሞ ለድክመት ይዳርጋቸዋል፡፡ በመኾኑም ድሮ በሚተገብሩት መንገድ ሥርዓታቸውን ማስቀጠል አይችሉም፡፡  
2ኛ/ ከሥርዓቱ ተጠቃሚነት አልፎ ተቀባይነትና አመኔታ ያለው የንኡስ ከበርቴ መደብ፣ በሕዝቡ ዘንድ ማንነቱ በሚገባ ታውቆና በሕዝቡ ፊት ተጋልጦ፣ በጥቂቱም ቢኾን የነበረውን ሕዝባዊ ቅቡልነት ሙሉ ለሙሉ ያጣል፡፡
3ኛ/ ዐብዮተኞቹ ከቡርዣው መደብ ጋር የሚያደርጉትን ቁርጠኛ ትንቅንቅ ሰፊው የሠራተኛው መደብ መደገፍ ይጀምራል፡፡
4ኛ/ የገዢው መደብ ሠራዊት እርስ በርስ መከፋፈል፣ መፈረካከስና ማመፅ ይጀምራል፡፡
እንደሚታወቀው እነዚህ ነጥቦች፣ የሩስያ ዐብዮት መሪ የዛሬ መቶ ዓመት ለዐብዮት መፈጠር አመልካች ክሥተቶች ናቸው በሚል የጠቀሳቸው ናቸው፡፡ በመኾኑም ሌኒን ያለውን በንባቡ ( ቃል በቃል) በመውሰድ፣ ዛሬ አገሪቷ ያለችበትን ኹኔታ ለመግለጽ ሳይኾን፣ ከእነዚህ ነጥቦች መካከል የተወሰኑት አኹን ባለው የአገራችን የፖለቲካ ኹኔታ ላይ እንዴት እንደሚስተዋሉ ቀጥሎ እንመለከታለን፡፡
ሀ/ ‹‹በድሮው መንገድ ሥርዓቱ መቀጠል ሲሳነው››
በፍትሕ፣ በዴሞክራሲና በመብት ዙሪያ የተነሡ ጥያቄዎች፣ ሥርዓቱ እስከ ዛሬ በሚያስተዳደረው መንገድ ሊፈቱ እንደማይችሉ ሕዝቡ ርግጠኛ ኾኗል፡፡ በመኾኑም እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ የሚቻለው የሥርዓት ለውጥ ሲመጣ ብቻ እንደ ኾነ ሕዝቡ ተገንዝቧል፡፡ ሌኒንም፣ እንደ ድሮው ሥርዓቱ መቀጠል አይችልም፤ በሚልበት ጊዜ፣ በሕዝቡ ለተነሡት ኹለንተናዊ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት የሚቻለው፣ በድሮው መንገድ ሳይኾን አዲስ የሥርዓት መንገድ መከተል እንደሚያስፈልግ ሕዝቡ ሲያምን እንደኾነ መናገሩ ነው፡፡  
ለ/ ‹‹የሕዝብ ቅቡልነት ማጣት››
ለአንድ ሥርዓት የቅቡልነት ጥያቄ ቁልፍ ጉዳይ ነው፤ ቅቡልነቱም በተለያየ መንገድ ሊመጣ ይችላል፤ መንገዶቹም፡- ባህላዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ ሕገ መንግሥታዊ… ወዘተ ሊኾኑ ይችላሉ፡፡ የአንድ ሥርዓት ዕድሜ፣ ቀጣይነት ወይም ዘላቂነት የሚወሰነው፣ ከሕዝብ ከሚያገኘው ቅቡልነት የተነሣ ነው፡፡
አገዛዙ የሕዝብ ቅቡልነትን ሲያጣ በመሣሪያ ኃይል ሥርዓቱን ማስቀጠል ይፈልጋል፡፡ አኹንም በአገራችን እያየን ያለነው የሕዝብን ጥያቄ በመሣሪያ ለመግታት የሚደረግን ጥረት ነው፡፡ ነገር ግን፣ ይህ የኃይል አካሔድ እንደማያዛልቅ የታወቀ ነው፡፡ በዚኽ ረገድ ፈረንሳዮች አንድ ትምህርታዊ  አባባል አላቸው፡፡ ይህም ‹‹መሣሪያን ብዙ ነገር ያደርጉበታል፤ ኾኖም ለብዙ ጊዜ አይቀመጡበትም›› የሚል ነው፡፡
ሐ/ ‹‹የሕዝብ ቁርጠኝነት››  
የሕዝብ ብሶት ከፍተኛ ደረጃ በደረሰ ጊዜ ሽንገላና ጊዜያዊ መፍትሔዎች ቀልቡን አይስቡትም፡፡ ቀደም ሲል፣ ሕዝቡ፣ መንግሥት ወይም የአስፈጻሚ አካላት ሕገ መንግሥቱን ቢያስከብሩ ችግራችን በሒደት ሊፈታ ይችላል የሚል ተስፋ ነበረው፡፡ አኹን ግን ያለው የፖለቲካ ሥርዓት ሕገ መንግሥቱን መሠረት አድርጎ የሕዝቡን ጥያቄ ለማስተናገድም ኾነ መፍትሔ ለመስጠት ከማይችልበት ደረጃ ላይ መድረሱን ከመረዳት አልፎ፣ ሥርዓቱ ሕገ መንግሥቱን ለመተግበር የሚያስችል ባሕርይና ፈቃድ እንደሌለው ተገንዝቧል፡፡ በዚኽ ምክንያት በተነሣሣው ሕዝባዊ ዐመፅ፣ መንግሥት በብቸኛነት በሚቆጣጠረው የብዙኃን መገናኛ የተለያየ ምክንያት ቢያቀርብም ሕዝቡ ልቡንም ጆሮውንም ሳይሰጠው የተቃውሞ እንቅስቃሴውን ቀጥሏል፡፡
ማጠቃለያ  
እንደ ኢትዮጵያ የተለያዩ ማኅበረሰቦች ባሉበት አገር፣ የሚዘረጋው የፌዴራል ሥርዓት ቢያንስ የሚከተሉትን ኹለት ወሳኝ ጉዳዮች ማሟላት እንደሚገባቸው በዘርፉ ለበርካታ ዓመታት ጥናትና ምርምር ያደረገው አረንድ ሊፕሐርት ይገልጻል፡፡ እነርሱም፡-
አንደኛ፡- በአገሪቷ ውስጥ ባሉት ማኅበረሰቦች መካከል ፍትሐዊ የሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር ያስፈልጋል፡፡ ሁለተኛ፡- በአገሪቷ ውስጥ ያሉት ማኅበረሰቦች፣ ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብት መጎናጸፍ ይኖርባቸዋል፡፡ ሊፕሐርት፣ የሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር ያስፈልጋል፣ ሲል ኹሉም ማኅበረሰቦች ውሳኔ በመስጠት ሒደት ላይ ቀጥተኛና ተገቢውን የተሳትፎ ሚና ሊኖራቸው ይገባል ማለቱ ነው፡፡
ኹሉም ማኅበረሰቦች ራሳቸውን በራሳቸው ያስተዳድሩ ማለትም፣ የራሳቸውን ቋንቋ፣ ባህል፣ ሥልጣኔ፣ ሃይማኖት… ወዘተ እንዲያሳድጉና በአገሪቷ ላይ የሚኖራቸውን የጋራ የባለቤትነት ስሜት እንዲያጎለብቱ እንዲያስችላቸው ነው። ከእነዚኽ ኹለት ነጥቦች አኳያ የኢሕአዴግን መንግሥት አመራር ስናየው፣ ፌዴራላዊ ሥርዓትን በመተግበር በባህልና በትምህርት መስኮች ማኅበረሰቦች ያላቸውን ማንነት እንዲያስጠብቁ ቢሞክርም፣ ጅማሮው እየዋለ ሲያድር መልሶ የማኅበረሰቦችን ማንነት ወደ መጨፍለቅ፣ እኔ የሰየምኩኽን ማንነት መላበስ አለብኽ፣ ወደሚል ዓምባገነናዊ አካሔድ ተለውጧል፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፣ በፖለቲካ ሥርዓቱ ውስጥ የሕዝቦችን ዴሞክራሲ መብት በጉልበት በመገደብ ፍትሐዊ የሥልጣን ውክልና እንዳይኖራቸው እስከ ማድረግም ደርሷል። እንደሚታወቀው ዴሞክራሲ፣ ለኹሉም እኩል የኾነ መንገድ ትከፍታለች፡፡ ኾኖም በአንድ ጉዳይ ላይ ‹‹የመድልዎ›› ስሜት ይታይበታል፡፡ ይህም ዴሞክራሲ በተፈጥሮዋ ግቧን ለማሳካት በዋናነት የቁጥርን መርሕ መከተሏ ነው፡፡ በኢሕአዴግ ሥርዓት ግን፣ ዴሞክራሲ፣ ይህን መርሕ ተከትላ ለሕዝቦች የሥልጣን ውክልናና ትክክለኛውን ምላሽ እንዳትሰጥ በጉልበት ተገድባለች፡፡ ለዚኽም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከፍተኛ የመቀመጫ ቁጥር ያላቸው ሕዝቦች ወደ ኋላ ተገፍተው፣ ከእነርሱ በእጅጉ ያነሰ የመቀመጫ ቁጥር ያላቸው ሕዝቦች በመንግሥት ሥልጣን ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ይዘዋል፡፡ ይህን ሕዝቦች ባላቸው የመቀመጫ ቁጥር ውክልና መሠረት ተገቢውን ሥልጣን አለማግኘታቸው እንደ ማሳያ መውሰድ ይቻላል፡፡
በእነዚህ ኹለት መሠረታዊ ችግሮች ሳቢያ፣ በአኹኑ ወቅት የኢሕአዴግ ሥርዓት ፍትሐዊ የሥልጣን ክፍፍልን ለመተግበርም ኾነ ሙሉ ለሙሉ አስጠብቄዋለኹ በሚለው የሕዝቦች የማንነት ጥያቄ ዙሪያ ለሚነሡ ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ መስጠት ተስኖታል፡፡ ከሁሉም በላይ የሚያስገርመው፣ ትላንት የነበሩት ሥርዓቶች የሕዝቦችን ማንነት አላከበሩም፤ እያለ ሲወነጅል የነበረው መንግሥት፣ አኹን ካለፈው በከፋ መልኩ ለማኅበረሰቡ ባይተዋር የኾነ ማንነት እየለጠፈ ባለኽበት እርጋ ማለቱ ነው፡፡
አኹን የተነሣው ጥያቄ፣ በዴሞክራሲ ዕጦት አካባቢና አብረው የሚሔዱት የሕግ የበላይነት፣ ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል እንዲኹም፣ በሰብአዊ መብት ረገጣ ጉዳዮች ላይ ነው፡፡ አንዳንድ ምሁራን፣ ከአኹን በኋላ ኢሕአዴግ ሕገ መንግሥቱን ማክበር ቢጀምር ነገሮች ይስተካከላሉ፤ የሚል አቋም ይዘው እየተሟገቱ ነው፡፡ እንደ እኔ አስተሳሰብ፣ በአንድ በኩል፣ ኢሕአዴግ ሥልጣን ላይ ለመቆየት ባለው ፍላጎትና ዴሞክራሲ ራሷ እንዲተገበርላት በምትፈልገው መካከል ትልቅ ቅራኔ ስላለ፣ ሥርዓቱ፣ ሕገ መንግሥቱን በሥራ ላይ ያውላል ብሎ መመኘቱ ትልቅ ስሕተት ነው የሚኾነው። በሌላ በኩል፣ ዴሞክራሲ በሌለበት ቦታ የመናገርና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ብሎም ኹሉም ወገኖች የሚደመጡበትና ሐሳባቸውን የሚገልጹበት መድረክ ሊኖር አይችልም፡፡
አንዳንድ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን በብዙኃን መገናኛ እየቀረቡ፣ ‹‹አኹን የተፈጠረው ችግር በውይይት ይፈታ፤ ሕዝቡም ሐሳቡን በግልጽ ተወያይቶ መፍታት ይኖርበታል›› ሲሉ ይሰማሉ፡፡
የእኒኽን ምሁራን ሐሳብ ስሰማ የሚገርመኝ ነገር ቢኖር፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የተነሣውን ችግር ቀርቶ፣ የሐሳብ መፈተሻና የነጻ ውይይት መዲና ሊኾን በሚገባውና ዛሬ የዶ/ር አድማሱ ጸጋዬ በኾነው ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሐሳብን በነጻነት መግለጽ እንደማይቻል እየታወቀ፣ ምሁራኑ ራሳቸውም ሐሳባቸውን በነጻነት የማንሸራሸር መብታቸውን ተገፈው ባሉበት ወቅት፣ ‹‹ሕዝቡ በነጻ ውይይት ችግሩን ይፍታ›› ማለታቸው ነው፡፡
ሙስና ለአንድ የፖለቲካ ሥርዓት ኢፍትሐዊነት ማሳያ ነው፡፡ የመንግሥት የአስተዳደርና የአገልግሎት ተቋማት በሕጉ መሠረት ለዜጎች ፍትሐዊ አገልግሎት የሚሰጡና ኹሉንም ዜጎች በእኩልነት የሚያስተናግዱ አይደሉም፡፡ የአገሪቱን የልማትና የንግድ ሥራዎች በበላይነት የሚመሩት የመንግሥት ተቋማትም በአገሪቱ ሕግ መሠረት በዘርፉ ለተሰማሩ ዜጎችም ኾነ የግል ድርጅቶች ከአድልዎ የጸዳ ፍትሐዊ አገልግሎት የሚሰጡ አይደሉም፡፡ በዚኽም ምክንያት በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በኮንስትራክሽንና መሰል የአገሪቱ ወሳኝ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ጥቂቶች ብቸኛ ተጠቃሚ ኾነዋል፡፡
ይህም በሥርዓቱ ውስጥ የሕግና የፖለቲካ አይነኬ ሕዋሶችን ፈጥሯል፡፡ እነዚህ ሕዋሶች ሥርዓቱ የሕግ የበላይነትን በመጣስ የፈጠራቸው ከመኾኑ አኳያ፣ የእነዚኽ ሕዋሶች ህልውና እስከ ቀጠለ ድረስ ሙስናን ለመቆጣጠር የሚያስችል ርምጃ ለመውሰድ አይቻልም፡፡ በኢሕአዴግ ሥርዓት በመሾምና ንብረት በማግበስበስ መካከል እምብዛም ልዩነት የለም፡፡ በመኾኑም አንድ ሰው ተሾመ ማለት ከበረ እንደ ማለት ነው፡፡ ይህ ችግር በአገሪቷ ውስጥ በዜጎች መካከል ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍልና ነጻ የኢኮኖሚ ውድድር እንዳይኖር ከማድረጉም በላይ አገሪቷን ወደማትወጣው አዘቅት ውስጥ ጨምሯታል፡፡
በመሆኑም ከላይ ያነሣናቸው የፌዴራሊዝም፣ የዴሞክራሲና የሙስና ችግሮች ባለው የኢሕአዴግ ሥርዓት መፍትሔ የሚያገኙት፣ ቀደም ብሎ እንደዚኽ ዓይነት ጥያቄዎችን የሚያስተናግድና የሚፈታ አሠራርና ተቋም ቢኖር ነበር፡፡ ኾኖም ይህ በሌለበትና ሕዝቡ ውስብስብና አስቸጋሪ ጥያቄ ባነሣበት በዚኽ ወቅት፣ አገዛዙ ሥርዓቱን ለማዳን የሚያስችል መፍትሔ ይዞ ይቀርባል ብሎ ማመን በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ከእነዚኽ መፍትሔ አልባ ችግሮች ተነሥቼ፣ ኢሕአዴግ ወደ ‹‹ኦሮማይ ቀጣና›› እየገባ ነው ብዬ አምናለኹ፡፡
መጣጥፌን የምደመድመው፣ ከደበበ ሰይፉ፣ ‹‹ለራስ የተጻፈ ደብዳቤ›› ግጥም፣ በአኹኑ ወቅት እየተከሠተ ያለውን የፖለቲካ ቀውስ ያሳያል ብዬ ያመንኩበትን ስንኞች በማቅረብ ነው፡፡
---- በእሱ ውድቀት እናንተ እርካብ ብትመቱ
በብሶቱ ብትፈይዱ
በመክሊቱ ብትነግዱ፤…
ይህ ፍጹም ባድማ፣ ይህ ፍጹም ድቅድቅ ጨለማ
እሚበራ እንዳይመስላችሁ በእናንተ የይስሙላ ቁራጭ ሻማ፡፡
ግን መጋረጃው ያልተነሣ ተውኔት፣
ያልተፈታ ዕንቆቅልሽ፣ አለውና ጨለማ
           ነፋስ - እሳት ገሞራን፣ ሊታቀፍ ይችላልና ጠፍ ባድማ
ዐይን ያለው ይይ!
ልብ ያለው ያስተውል!
ጆሮ ያለው ይስማ!
********   **********
ከአዘጋጁ፡- ጽሁፉ የጸሃፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ  መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

       አምናና ዘንድሮ፣ ከፍተኛ እርዳታ ካገኙ ሦስት አገራት አንዷ ኢትዮጵያ ናት።
       ለረሃቡ 1.4 ቢ ዶላር (30 ቢ. ብር) እርዳታ ተገኝቷል። ግማሹ ከአሜሪካ! (የዩኤን መረጃ)፡፡
       3ቱ ትልልቅ ለጋሾች፣ የአሜሪካ፣ የእንግሊዝና የጀርመን መንግስታት ናቸው።
       ረሃብ የሚከሰተው፣ የእህል ምርት ምን ያህል ሲቀንስ ነው?
       በ1966 ዓ.ም፣ የእህል ምርት 13 ሚ. ኩንታል ቀንሶ ነበር። በ77ም እንዲሁ
            (የዓለም ባንክመረጃ)፡፡
       በ2007 ዓ.ም? ረሃብ የተከሰተው፣ የእህል ምርት በ5ሚ ኩንታል ስለቀነሰ ነው።                    (ስታትስቲክስ ኤጀንሲ)።

    አዴግ ሰሞኑን ያወጣውን ረዥም መግለጫ ሰምታችኋል? ከመግለጫው ውስጥ ጥቂት ዓረፍተ ነገሮችን በመመልከት፣ የአገራችን ፖለቲካ ምን እንደሚመስል መታዘብ እንችላለን። እንደተለመደው፣ እንደወትሮው፣ ተቃዋሚም፣ ደጋፊም እንደሚያደርገው፣ ለፕሮፓጋንዳ እስከጠቀመ ድረስ፣ ፍሬ እና ገለባውን እያደበላለቁ የመንጎድ ፖለቲካ፣ የአገራችን ባህል ነው፡፡  
በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ኃይለኛ ድርቅ መከሰቱን ይጠቅሳል መግለጫው። ከዚያስ? “ትርጉም ያለው እርዳታ” ባናገኝም፤ የረሃብ አደጋውን በራሳችን አቅም መቋቋም ችለናል ብሏል ኢህአዴግ፡፡ የአገሪቱ ኢኮኖሚ ስለተሻሻለ የረሃብ አደጋው እጅግ የከፋ ጥፋት እንዳላደረሰም ተናግሯል፡፡
እስቲ፣ እውነተኛውን መረጃ … እውነተኛውን ፍሬ ከገለባው ለመለየት እንሞክር፡፡ አዎ፣ የአምናው ድርቅ፣ ባለፉት 50 ዓመታት ከተከሰቱት የዝናብ እጥረት አደጋዎች ሁሉ የከፋ እንደሆነ አለማቀፍ የሙያ ተቋማት ገልፀዋል።  በዚሁ ድርቅ ሳቢያ ብዙ ሰው በረሃብ አለማለቁም፣ ደግ ነገር ነው፡፡ “ትርጉም ያለው እርዳታ አላገኘንም” የሚለው የኢህአዴግ አባባል ግን፣ ፍሬ የሌለው ገለባ ነው። ደግሞም ያስተዛዝባል። ዘንድሮ፣ ከሶሪያ በመቀጠል፣ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የነፍስ አድን እርዳታ አግኝታለች፡፡ ይሄ፣ ትርጉም የለውም?
በደፈናው ሳይሆን፣ በቁጥር ቁልጭ ብሎ ይታያልኮ። ኢትዮጵያ፣ ባለፉት ሃያ ወራት ብቻ 1.4 ቢሊዮን ዶላር (30 ቢ. ብር) ነፍስ አድን እርዳታ እንዳገኘች የዩኤን መረጃ ይገልፃል፡፡
ይሄ ቀላል እርዳታ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ እስከዛሬ ካገኘችው የረሃብ እርዳታ ሁሉ ይበልጣል፡፡ ያው፣ እንደሌላው ጊዜ፣ ዋናዋዎቹ ለጋሾች፣ የአሜሪካና የአውሮፓ መንግስታት ናቸው - በተለይም የአሜሪካ መንግስት፡፡ ከጠቅላላው እርዳታ ውስጥ፣ ግማሹ ከአሜሪካ መንግሥት የተሰጠ ነው - 684 ሚሊዮን ዶላር (15 ቢሊዮን ብር ገደማ)፡፡
ከአሜሪካ በመቀጠልስ?
በአውሮፓ ህብረት በኩልና በተናጠል በሚሰጡት እርዳታ፣ የእንግሊዝና የጀርመን መንግስታት ይጠቀሳሉ። እያንዳንዳቸው ከ140 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለረሃቡ ለግሰዋል፡፡
እነዚህን እውነታዎች መካድ፣ ያስተዛዝባል፡፡ ምስጋና ቢስ መሆን ምን ጥቅም አለው? በእርግጥ፣ “እርዳታ መገኘቱ በቂ ነው” ማለት አይደለም፡፡
እርዳታው በጊዜ ካልደረሰና በወጉ ካልተሰራጨ፣ ብዙ ጥፋት ይከሰታል፡፡ የእርዳታ እህል ደግሞ፣ ቶሎ አይደርስም፡፡ እናም፣ መንግስት ቀደም ብሎ፣ እህል ገዝቶ ማምጣቱ ጥሩ ነው፡፡ ወጪውን በእርዳታ ያካክሳል፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፡፡ መንግስት፣ በየመስኩ ሲዝረከረክና ችግሮች ሲያባብስ እንደምናየው፣ የእርዳታ ስርጭት ላይ ቢዝረከረክ ኖሮ ብዙ ጥፋት በደረሰ ነበር። ይህ አለመሆኑ መልካም ነው። ምን ለማለት ነው? ከፍተኛ እርዳታ መገኘቱን መካድ ሳያስፈልገው፣ “እኔም አደጋውን ለመቋቋም ጥሬያለሁ” ማለት ይችል ነበር፡፡ ፍሬውን ከገለባው መለየት ከጀመርን? “የአገሪቱ ኢኮኖሚ ስለተሻሻለ፣ የረሃብ አደጋው የከፋ አደጋ አላደረሰም” የሚለውን አባባል ደግ እንይ፡፡ የእህል ምርት አድጓል ማለት ነው፡፡ እንዴት ነው ነገሩ? የእህል ምርት ካላደገማ በረሃብ እናልቃለን፡፡ በሃያ ዓመት ውስጥኮ፣ የአገሪቱ የህዝብ ቁጥር በእጥፍ ጨምሯል፡፡ የእህል ምርት ካላደገ፣ በእርዳታም መዳን አይቻልም፡፡ ይልቅስ፣ ዋናው ጥያቄ፣ “የእህል ምርት በምን ያህል መጠንና በምን ያህል ፍጥነት አደገ?” የሚል ነው፡፡
የእህል ምርትን ከህዝብ ብዛት ጋር ማገናዘብ እንችላልን፡፡ ከ1950 ዓ.ም ጀምሮ፣ ንጉሱ እስከወረዱበት ድረስ የተመረተውን የእህል ምርት እንመልክት፡፡
የዓለም ባንክ መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ያኔ በየዓመቱ በአማካይ፣ ለአንድ ሰው 180 ኪሎ እህል ይመረት ነበር፡፡ ለሃያ ዓመታት፣ እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ፣ እንዲህ ነበር የቀጠለው፡፡ ንጉሱ እስከወረዱበት ዓመት ድረስ ማለት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ግን፣ ማሽቆልቆል ጀመረ። በደርግ ዘመን፣ አመታዊው የእህል ምርት፣ ለአንድ ሰው ከ140 ኪሎ ግራም በታች ነበር ይላል መረጃው፡፡ በኢህአዴግ ዘመንም ቶሎ አልተሻሻለም፡፡ የእህል ምርት በንጉሱ ዘመን ወደነበረበት ደረጃ የተሻሻለው፣ በ2002 ዓ.ም ነው፡፡
ምን ማለት ነው? “የእህል ምርት አድጓል” ተብሎ ሲነገር፤ “አገሬው አለፈለት፤ በለፀገ፤ ተትረፈረፈ” ማለት አይደለም፡፡ “ከ35 ዓመታት በፊት ወደነበረበት የምርት ደረጃ ተሻሽሏል” እንደማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ያው፣ … እንደያኔው፣ ዛሬም ድህነት ውስጥ ነን፡፡ እንደያኔው ዛሬም፣ ለድርቅ እና ለረሃብ በጣም ቅርብ ነን፡፡ አፋፍ ላይ ነን ከታች ገደል፣ ከላይ ናዳ፡፡

· ሳንፈራረጅ በውይይት ችግሮቻችንን መፍታት አለብን
· ጥያቄዎች ሳይወሳሰቡ በጊዜ መፈታት አለባቸው
· ህዝብ መተንፈሻ ሲያጣ አደባባይ ይወጣል

“ኢትዮጵያዊነት ላይ ስራ አልተሰራም”
ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ (የኢኮኖሚ ባለሙያ)

ህገ መንግስቱ በሚፈቅደው መሰረት የህዝብ ድምፅ    መሰማት አለበት፡፡ የህዝብ ድምፅ በሚሰማበት ጊዜ በተለይ ህዝብ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ሲፈልግ ለመንግስት ማሳወቅ ያስፈልጋል። ይሄ በሰለጠኑ ሀገራትም የሚደረግ ነው፡፡ መንግስት አስፈላጊውን ጥበቃ እንዲያደርግ ነው ይህ የሚሆነው፡፡ እኛ ሀገር አሁን ባለው ሁኔታ መንግስት ራሱ እንደሚናገረው የሙስና መስፋፋት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ በተለይ ወጣቱ የስራ እድል አለማግኘቱ፣ መንግስት ከዩኒቨርስቲ ተመርቆ ለሚወጣው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር የተማረ ኃይል የስራ እድል አለመፍጠሩ ----- በሀገሪቱ ካሉ ወቅታዊ ችግሮች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
በሌላ በኩል በዋናነት በህገ መንግስቱ አንቀፅ 39 ላይ የተጠቀሰው የማንነት ጉዳይ እየተስፋፋ ሄዶ የት ነው የሚደርሰው የሚለው አሳሳቢ ነው። ህገ መንግስቱ የማንነት ጥያቄን እስከፈቀደ ድረስ መንግስትም ማክበር አለበት፡፡ ግን እኔ እንደማስበው ከሆነ፣ እኛም በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሆነን ካነሳናቸው ጥያቄዎች መካከል የመሬትና የብሔር ብሔረሰቦች ጉዳይ ዋነኞቹ ነበሩ፡፡ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ብሔር ብሔረሰቦች ቋንቋቸው ባህላቸው ተከብሮላቸዋል፡፡ ግን ይሄ ከተረጋገጠ በኋላ “ኢትዮጵያዊነት” የሚለው ላይ ስራ አልተሰራም፡፡ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ነን የሚለውን በተለይ አዲሱ ትውልድ እንዲያወቀው የማድረጉ ጉዳይ ብዙ ትኩረት አልተሰጠውም፡፡ ሌላው የሰብአዊ መብት አከባበር ጉዳይ ነው፡፡ ትልቁ የመንግስት ስራ ያለው ወረዳዎች አካባቢ ነው፡፡ የመሬት፣ የፍትህ፣ የፀጥታ የመሳሰሉ ጉዳዮች በቀጥታ ከህዝቡ ጋር በሚገናኙት በነዚህ የወረዳ አመራሮች እጅ ነው ያለው፡፡ እነዚህ ሰዎች ብቃት ያላቸው መሆን አለባቸው፡፡ መንግስት ልማቱን የሚያቀነባብሩትና ከህዝቡ ጋር በቀጥታ የሚገናኙት ወረዳዎችና ዞኖች መሆናቸውን በመገንዘብ፣ በከፍተኛ ደረጃ ብቃት ያላቸው ሰዎች መመደብ አለበት፡፡ ከማንም በላይ እነዚህ ሰዎች ህዝቡን አዳምጠው ምላሽ የሚሰጡ መሆን አለባቸው፡፡ በክልል ወረዳ ድንበሮች አካባቢ ያለ ግንኙነትና የልማት ሁኔታዎችን ብቃት ያላቸው ሰዎችን በመመደብ መስራት ያስፈልጋል፡፡
ራሳቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም፤ በኦሮሚያ በደረሰው ጉዳይና ባጋጠመው ችግር ይቅርታ መጠየቃቸው በራሱ መንግስት ህዝቡን እያዳመጠ ነው እንድል ያደርገኛል፡፡ ከዚያም አልፎ በመግለጫዎች የህዝብን ጥያቄ እያዳመጠ መሆኑን ለመገንዘብ ያስችላሉ፡፡ የአዲስ አበባ ፊንፊኔ ዙሪያ ማስተር ፕላን እንዲቆም ማድረጉ ሌላው ትልቁ ነገር ነው፡፡
ከህዝቡ የሚነሱ ጥያቄዎች ብዙ አይነት ናቸው፡፡ አንዳንዱ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡ ቅማንት፣ ወልቃይት የመሳሰሉት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች ህገ መንግስቱን መሰረት በማድረግ በቀላሉ መፈታት የሚችሉ ይመስለኛል፡፡ በመንግስት ደረጃ ደግሞ በከፍተኛ ስልጣን ላይ ያሉት ጥያቄው ቢገባቸውም፣ በቀዬው ያሉት ባለስልጣናት ግንዛቤው ይኖራቸው ይሆን የሚለው ሌላው ጥያቄ ነው፡፡ በመልካም አስተዳደርና በሙስና ጉዳይ ላይ ዋና ተዋናይ ሊሆኑ የሚችሉት መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና ነፃ ፕሬስ ናቸው፡፡ ነፃ ፕሬስ በተለይ የምርመራ ጋዜጠኝነትን ተግባራዊ አድርጎ፣ እንዲህ ያሉ ንቅዘቶችን መርምሮ ማውጣት አለበት። በተለይ ሙስና ላይ ብዙ ሊሰሩ ይገባል፡፡ ግን ይሄን ለማድረግ አሁን ያሉት ነፃ ሚዲያዎች አቅም ተፈጥሮላቸዋል ወይ የሚለው የኔም ጥያቄ ነው፡፡ በሽግግሩ ጊዜ ወደ 90 ጋዜጦች ነበሩ፡፡ እነዚህ ጋዜጦች ሁሉንም ነገር በድፍረት ያወጡ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ እያነሱ መጥተው አሁን ያለበት ደረጃ ደርሷል፡፡ አሁን እንደምናየው ቅዳሜና እሁድ የሚወጡ ጋዜጦች፤ በማተሚያ ቤት ችግር ለረቡዕ ነው እየደረሱ ያሉት። መንግስት ይሄን የሚዲያ ዘርፍ ማነቆዎች መፍታት ይገባዋል፡፡
ህዝብ የታመቀ ችግር ሲመጣ ነው ሰላማዊ ሰልፍ የሚወጣው፡፡ መተንፈሻ ሲያጣ አደባባይ ይወጣል። እነዚህ ነገሮች ወደ ንብረት ውድመትና የህይወት ጥፋት እንዳይሄዱ ጥንቃቄ ይሻል፡፡ ምናልባትም እንደ ደቡብ ሱዳን፣ በአራት ወገን ጦርነት ውስጥ እንዳለችው ሱዳን (ኮርዶፋን፣ ዳርፉር፣ አቢዬ፣ ብሉ ናይል-----ጦርነት ላይ ናቸው)፣ ሶማሊያ ወዘተ-- እንዳንሆን ከወዲሁ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ እንዲህ ያሉ ተቃውዎችም ሲነሱ የሀገሪቱን ሉአላዊነት ሳይፈታተኑ መንግስት ማስተካከል ያለበትን ነገር ቢያስተካክል፤ መቀየር ያለበት ነገር ቢቀይር፤ የተቃውሞ ኃይሎችም ራሳቸውን አደራጅተው፣ ህዝቡን አሳምነው የመንግስትን ስልጣን በሰላማዊ ምርጫ የሚይዙበት አካሄድ ነው መከተል ያለባቸው፡፡ አሁን በሀገሪቱ ያሉት ፓርቲዎች 90 ቦታ የተከፋፈሉ፣ አንድ አጀንዳ ይዘው መውጣት ያልቻሉ ናቸው፡፡  የ97 ምርጫ ጊዜ የቅንጅት ኃይሎች፣ በፓርላማው 172 ያህል ወንበር ነበር ያገኙት። የእነሱ ወደ ፓርላማ አለመግባት የኢትዮጵያን ዲሞክራሲ ክፉኛ የጎዳው ይመስለኛል፡፡ ያኔ ህዝቡ መርጧቸው ፓርላማ አለመግባታቸው፣ብዙዎችን ተስፋ አስቆርጧል፡፡ አሁን ህዝቡ አደባባይ ወጥቶ የሚናገረው ስለከፋውና ስለቸገረው ነው፡፡
በአረብ ሀገራት በእነ ቱኒዚያ፣ ግብፅ፣ ሊቢያ በመሳሰሉት ሲካሄድ የነበረው አመፅ በሶሻል ሚዲያ ብቻ አልነበረም የተመራው፡፡ እርግጥ ነው ሶሻል ሚዲያ አገልግሎት ነበረው፡፡ ዋናው ግን የሙስሊም ወንድማማቾች ህብረት የሚባሉ ከ50 ዓመታት በላይ ሲደራጁ የቆዩ ኃይላት ነበሩ አመፁን በባለቤትነት የመሩት፡፡ እኛ ሀገር ዋናው ችግር ሀገር ሳይፈርስ ፀጥታ ሳይደፈርስ፣ የህዝብ ህይወት ሳያልፍ፣ ንብረት ሳይጠፋ ሰላማዊ የመንግስት ስልጣን ሽግግር ማድረግ ይቻላል ወይ የሚለው ነው። ተቃዋሚዎች ይሄን ለመፍጠር አስበው መደራጀት ያስፈልጋቸዋል። ምናልባት የቅንጅት ምሳሌ ጥሩ ሊሆን ይችላል፡፡ ግን ህዝቡ ብቻ የሚንቀሳቀስ ከሆነ የትም አያደርስም፤ ሀገር ነው የሚያፈርሰው። መንግስት ደግሞ የሀገሪቱንና የህዝቡን ፀጥታ ማስከበር አለበት፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ከመደረጉ በፊት ለመንግስት ማሳወቅ ያስፈልጋል፡፡ መንግስትም እንዲህ ያሉ ሰልፎችን መፍቀድ አለበት። ምክንያቱም በሌላ መድረክ ሊሰማ የማይችለውን የህዝብ ቅሬታዎች የሚሰማበት መድረክ ይሆናል፡፡
እነ ሂውማን ራይትስ ዎች፣ እነ አምነስቲ ኢንተርናሽናልም የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሪፖርቶችን የሚያወጡት በስልክና በመሳሰሉት በሚያገኙት መረጃ ላይ ተመስርተው ነው፡፡
ምናልባት እነዚህ ድርጅቶች ሀገር ውስጥ ገብተው የሚከናወኑ ነገሮችን ተመልክተው፣ የሰብአዊ መብቶች መጓደልን ሪፖርት ቢያደርጉ መንግስትን ይጠቅመዋል እንጂ አይጎዳውም፡፡ አሁን በውጭ ሆነው የሚያቀርቡት ሪፖርት ችግሩን እያባባሰው ያለ ይመስለኛል፡፡ በሌላ በኩል በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ብዙ ቅሬታ እንዳላቸው ያስታውቃሉ፡፡
መንግስት እነዚህ ሰዎችን በመቅረብ ሀገራቸውን የሚያገለግሉበትን ነገር ማመቻቸት አለበት፡፡ ጥያቄያቸው ላይ መነጋገር ያስፈልጋል፡፡ በዜግነታቸው የሚገባውን ክብር ሰጥቶ መንግስት ማነጋገር አለበት፡፡   

==================================

“በውይይት ችግሮቻችንን መፍታት አለብን”
ፕ/ር አህመድ ዘካሪያ (የዓለም እርቀ ሰላም ግብረ ሰናይ ድርጅት አመራር)

እኛ እንደ ሀገር ሽማግሌዎች የማረጋጋት ስራ ነው በዋናነት መስራት ያለብን፡፡ መፍትሄውን የሚያወያዩ አካላት ናቸው የሚያስቀምጡት፡፡ እንደ ሀገር ሽማግሌ፣ የህግም የፖለቲካም ስልጣን ስለሌለን የሞራል ጫና የማሳረፍ ሚና ነው የሚኖረን። እኛ ሰላም እንዲሰፍን፣ የተጋጩ እንዲታረቁ ነው የምንጠይቀው፡፡
ጦርነትን አንፈልግም፡፡ የሀሳብ ግጭት ከሆነ በጠረጴዛ ዙሪያ ይፈታል፡፡ ደም መፋሰስ ለዚህች ሀገር አይበጅም፡፡ ህገ መንግስቱን አይቶ እንደገና ማስተካከል የሚያስፈልገው ነገር ካለም ማስተካከል ይገባል፡፡  
አሁን ያለው ጥያቄ ከአስተዳደር ጉዳይ ጋር የሚያያዝ ይመስላል፡፡ ጥያቄውን ህገ-መንግስቱን መሰረት አድርጎ መፍታት ያሻል፡፡ የሰለጠኑት ሀገራትም የራሳቸው ችግር አለባቸው፤የመፍትሄ አሰጣጣቸው ነው ከኛ የሚለየው፡፡ የሰው ልጅ ትልቁ ከፈጣሪ ያገኘው ችሮታ የማስተዋል፣ የማመዛዘንና የመፍረድ ኃይልን ነው፡፡ ፈጣሪ እኒህን ከሰጠን የመፍትሄ ምንጮች መሆን አለብን፡፡ ህዝቡን በነዚህ ባህሪዎች ውስጥ እንዲገባ ማድረግ አለብን። ያለበለዚያ እቺ ሀገር ለማንም የማትሆን አገር ትሆናለች፡፡
አሁን ትልቁ ጦርነታችን ረሀብ ነው፤በየጊዜው እየመጣ የሚፈታተነን፡፡ ግን እሱንም ማሸነፍ ያቃተን ይመስላል፡፡ አንዳንዴ ረሀብን ማሸነፍ ስላቃተን ይሆን የምንጣላው ብዬ አስባለሁ። እንደ ኢትዮጵያዊነታችን አንድ የሆንን ህዝቦች፣ እርስ በእርስ የምንናቆርበት ምክንያት አይገባኝም፡፡ ለኢኮኖሚ በሽታው መድኃኒት ብንፈልግለትና ትንሽ ችግር ባያጣላን ጥሩ ነው፡፡ እኔ መንግስት፤ ህዝብ ለማለት አልፈልግም፡፡ ምክንያቱም መንግስትም ህዝብ ነው፡፡ ከኛው ነው የመጡት፡፡ ሳንፈራረጅ በውይይት፣ በንግግር ችግሮቻችንን መፍታት አለብን፡፡

======================================

“ህገ መንግስቱ ለህዝብ እንጂ፣ህዝብ ለህገ መንግስቱ አይደለም የተሰራው”

አቶ ክቡር ገና

ጥያቄውን ያነሳው አካል በግልፅ ባይወጣም ጥያቄ ተነስቷል፡፡ ጥያቄዎቹ የአንድ አካል ብቻ ሳይሆኑ በብዙ ሰዎች የሚንሸራሸሩም ሆነዋል። ስለዚህ መልስ አሰጣጥ ላይ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ አንደኛ በህዝቡ የተነሱትን ችግሮች መሰረታዊ ምክንያት ሳይሆን ከላይ የሚታዩትን ብቻ ለመቅረፍ ከተጣረ ችግሩ ለጊዜው ጋብ ይላል እንጂ አይጠፋም። በአጠቃላይ አሁን የተነሱ ጥያቄዎች ከጊዜ በኋላ ሊነሱ እንደሚችሉ ይታወቁ የነበሩ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በሁለት አይነት መንገድ መመለስ ይቻላል፡- በኃይልና  በፖለቲካዊ መፍትሄ፡፡ የኃይል አማራጭ ምን ያህል ምላሽ ይሰጣል የሚለው አጠያያቂ ነው። ፖለቲካዊ መፍትሄ ይሰጥ ከተባለ ግን ረጅም ጊዜ ቢወስድም፣ ቁጭ ብሎ መነጋገርና መደራደር ያስፈልጋል፡፡ ለአንድ ጥያቄ አንድ መልስ በሚል ብቻ ሊታለፍ የሚችል ችግር አይደለም፡፡ መጀመሪያ መሰረታዊ ችግሩን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ጥያቄው ከጠያቂዎች ሲመጣ በትክክለኛ መንገድ ስላልመጣ፣በትክክል ላልመጣ ጥያቄ በትክክል ምላሽ ላይሰጥበት ይችላል፡፡ ነገር ግን አንዳንዴ መንግስትም ጥያቄው ባይመጣም፣ጥያቄውን ራሱ ፈጥሮ መመለስ አለበት።
ጥያቄዎቹን በአጠቃላይ ስናያቸው ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል፣ የአመራር ሁኔታ፣ የአገልግሎት አሰጣጥ ፍትሃዊነት፣የሙስና ችግርን በሙሉ የሚያካትቱ ነው የሚመስሉት፡፡ ጎንደር የተነሳውን ጥያቄ ስንመለከት፣ ከግዛት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በጊዜ ምላሽ መስጠት ያስፈልጋል። ሳይወሳሰቡ በጊዜ መፈታት አለባቸው፡፡ ትክክለኛ ምላሽም ማግኘት አለባቸው፡፡ እንደኔ እነዚህ ብቻ አይመስሉኝም ምክንያቶቹ፡፡ ህዝቡ የመተንፈሻ መድረክ ማጣቱ አንዱ ምክንያት ይመስለኛል። የኢትዮጵያ ህዝብ በየ5 ዓመቱ አንዴ ድምፁን እንዲሰጥ ብቻ ነው በምርጫ የሚጠየቀው፡፡ ከዚያ በኋላ መነጋገሪያ መድረክ የለም፡፡ ለምሳሌ አሁን ፓርላማውን ስናይ፣መቶ በመቶ አንድ አካል ሆኖ ሃሳብ እንደተፈለገው እንዳይንሸራሸር አድርጓል። ምላሽ የማያገኙ ነገር ግን በየጊዜው የሚነሱ ጥያቄዎችም አሉ፡፡ ግን ብዙ ጊዜ የሚደረገው መልዕክቱን ትቶ መልዕክተኛውን መደብደብ ነው። እነዚህ ነገሮች ሲደማመሩ ነው ህዝቡ እንዲህ ያለ እርምጃ የሚወስደው፡፡
እንዲህ ያለውን ችግር ያስተናገዱ በርካታ የዓለም ሀገራት አሉ፡፡ በእንዲህ ያለው ችግርም የጠፉ ሀገራት አሉ፡፡ ዩጎዝላቪያ የምትባለው ሀገር ልክ እንዲሁ በዘር በብሄር ተለያይታ፣ኋላ ላይ በ1980 ከሀገራት ዝርዝር ጠፍታለች፡፡ ከዚህ እኛም መማር አለብን፡፡ ህገ-መንግስቱ ለህዝብ እንጂ ህዝብ ለህገ-መንግስቱ አይደለም የተሰራው፡፡ ስለዚህ ጥያቄዎቹ በሙሉ በፍርሃት ሳይሆን በግልፅ መውጣት አለባቸው፡፡ የችግሩ ፈቺ የተባለው አካልም ከህዝቡ ሳይጠብቅ ራሱ ጥያቄዎቹን ፈጥሮ ለመፍታት መንቀሳቀስ አለበት፡፡ ችግሩ ሊፈታ የሚችለው ሁሉም በእኩል ለችግሩ መፍትሄ ለማምጣት ሲረባረብ ብቻ ነው፡፡