Administrator

Administrator

ከ50 ሺህ በላይ ሰዎች የአገሪቱ ዜጎች ለመሆን አመልክተዋል
      ተቀማጭነቱ በቪየና የሆነው ኤሮስፔስ ኢንተርናሽናል ሪሰርች ሴንተር የጀመረውን አዲስ ፕሮጀክት የሚያስፈጽመው የጠፈር ተመራማሪዎች ቡድን፤ በጠፈር ላይ አስጋሪዳ የተባለች አዲስ አገር ሊመሰርት ማቀዱ ተገለጸ፡፡
የእቅዱ ባለቤቶች የሆኑት ሳይንቲስቶች፤አገሪቱ የሆነ ጊዜ ላይ በተመድ እውቅና እንደሚሰጣት ተስፋ አለን ቢሉም፣ አንዳንድ ባለሙያዎች ግን በጠፈር ላይ የሚቀርብን የአንዲት አገር ብሄራዊ ሉአላዊነት ጥያቄ የሚከለክሉ አለማቀፍ ህጎችን ጠቅሰው፣የእቅዱን ተፈጻሚነት ተጠራጥረውታል፡፡
የአገሪቱ ዜጎች መሆን የሚፈልጉ ሰዎች በድረ-ገጽ አማካይነት ለፕሮጀክቱ ጽህፈት ቤት ማመልከቻ በማቅረብ መስፈርቱን ካሟሉ፣ ዜግነትና ፓስፖርት ይሰጣቸዋል ብለዋል፤ የፕሮጀክቱ አባልና በአውሮፓ የጠፈር ምርምር ማዕከል ለ15 አመታት ያገለገሉት ሌና ዲ ዋይን፡፡ ሳይንቲስቶቹ በጠፈር ላይ ሊመሰርቷት ላሰቧትና አዲስ የንግድና የሳይንስ ምርምር አማራጭ ትሆናለች ለሚሏት አገር አስጋሪዳ የሚል ስም ያወጡላት ሲሆን በአንድ አፈታሪክ ውስጥ በሰማይ ላይ ትገኛለች ተብሎ ከሚነገርላት አስጋሪዳ የተባለች አገር የተወሰደ ነው ተብሏል፡፡
ለአዲሲቱ አገር ብሄራዊ መዝሙርና ሰንደቅ አላማ ለማውጣት ውድድር እየተደረገ ነው ያለው ዘገባው፤ እስካሁን ድረስ ከ50 ሺህ በላይ ሰዎች በድረ-ገጽ አማካይነት የአገሪቱ ዜጋ መሆን እንፈልጋለን በማለት ለፕሮጀክቱ ባለቤቶች ማመልከታቸውንም አስታውቋል፡፡

 በዶ/ር ጃራ ሰማ የተፃፈውና ‹‹ከሱስ የነፃ ትውልድ የመፍጠር ጥበብ›› የተሰኘ መፅሀፍ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ  በመወዘክር  አዳራሽ ይመረቃል። መፅሃፉ በኦሮምኛና በአማርኛ የተሰናዳ ሲሆን በዋናት ለሱሰኝነት ሊዳርጉ ስለሚችሉ ዋና ዋና ምክንያቶች፣ ሱስንና ሱሰኝነትን እንዴት መከላከል እንደሚቻል፣ ከሱሰኝነት መላቀቅ ስለሚቻልባቸው መንገዶች፣ ሱስ ሊያስይዙ ስለሚችሉ ነገነሮችና በአጠቃላይ ከሱሰኝነት ነፃ ሆኖ የሚኖርበትን መንገድ የሚያመላክትና የሚተነትን እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በአማርኛ የተዘጋጀው መፅሀፍ፤ በአራት ምዕራፎች ተከፋፍሎ፣ በ156 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ100 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡

 ባለቤቶቹ ሌላ ባለ 5 ኮ ከብ ሆቴል ግ ንባታ ጀምረዋል
                   
        በእኛ አገር ክረምት አብቅቶ መስከረም ሲጠባ፣ ሜዳውና ጋራ ሸንተረሩ በአደይ አበባ ተውቦ ልብን በሐሴት ይሞላል፡፡ በአውሮፓም ተመሳሳይ ክስተት ይፈጠራል፡፡ ክረምቱ እንደወጣ አገር ምድሩ ጎልደን ቱሊፕ (Golden Tulip) በተሰኘች በጣም በምታምር ወርቃማ አበባ ይሸፈናል፡፡ በዚህች ወርቃማ አበባ የተሰየመው ባለ 5 ኮከቡ “ጎልደን ቱሊፕ” ሆቴል፤ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ 1 ኪ.ሜ ያህል ርቀት ላይ፣ ከቦሌ መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት፣ ከአትሌት ብርሃኔ አደሬ የገበያ ማዕከል (ሞል) ገባ ብሎ ይገኛል፡፡
ባለ 5 ፎቁ “ጎልደን ቱሊፕ አዲስ አበባ” ሆቴል፣ የቦታ ጥበት ቢኖርበትም ባለቤቶቹ ዓለም አቀፍ ደረጃውን እንዲጠብቅ ተጨንቀው ነው የሰሩት። ገና ወደ ሆቴሉ ሲገቡ ሎቢው ቀልብን ይስባል። ከበሩ በስተቀኝ የተለያዩ ጣፋጭ ኬኮች፣ ትኩስ ዳቦ፣ እንዲሁም ሻይ ቡና የሚያዙበት ወይም ገዝተው ይዘው የሚሄዱበት “ግራብ ኤንድ ጎ”  (Grab & Go) ያገኛሉ፡፡ ከፊት ለፊቱ 24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጠው “ስፓይሲ ሬስቶራንት” አለ። በስተግራ የእንግዶች ማረፊያ ሶፋዎች በወግ በወጉ ተደርድረዋል፡፡
አነስተኛ የቦርድ ስብሰባዎችና ከዚያ ከፍ ያሉ እንዲሁም ለሰርግ እስከ 200 ሰዎች ማስተናገድ የሚችሉ አራት አዳራሾች ያሉት ከሎቢው በላይና ከ1ኛው ፎቅ በታች ባለው ወለል ላይ ነው፡፡  የስብሰባ አዳራሾቹ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የተገጠመላቸው ሲሆን ቪዲዮ ኮንፈረንስ ማካሄድ የሚያስችሉ፣ የአየር ሙቀትና ቅዝቃዜ መቆጣጠሪያ (ኤሲ) ያላቸው ናቸው፡፡ የቦታ ችግር ስላለበት የውጭ እንግዶች አያስተናግድም እንጂ አልጋ የያዙ እንግዶች የሚጠቀሙበት ደረጃውን የጠበቀ፣ ዘመናዊ ጂምናዚየም ምድር ቤት አለ፡፡ ሆቴሉ 4 የመጠጥና ምግብ አገልግሎት የሚሰጥባቸው ስፍራዎች አሉት፡፡ ሰፊ ስፖርት ባርም አለው፡፡ ሌመን ባርና ብቻቸውን መጨዋወት የፈለጉ ሰዎች የሚስተናገዱበት ሃቫና (ቪአይፒ) ባር የሚገኙት እዚሁ ፎቅ ላይ ነው፡፡
ሆቴሉ ሥራ የጀመረው በሐምሌ 2007 ዓ.ም ሲሆን ለግንባታውና ለውስጥ ቁሳቁሶቹ 180 ሚሊዮን ብር መፍጀቱን፣ ለ189 ቋሚና ለ15 ተለማማጅ ሰራተኞች የሥራ ዕድል መፍጠሩን፣ የጎልደን ቱሊፕ ፕሮጀክት ኃላፊና ወኪል አቶ ታምራት በላይ ገልጸዋል፡፡ የሆቴሉ ማኔጅመንት የሚመራው በዓለም አቀፉ ብራንድ በ“ጎልደን ቱሊፕ” ነው፡፡
አቶ ታምራት ወኪል ሆነው ሆቴሉን ያሰሩት እንጂ የገንዘብና የእውቀት ምንጩ፣ በደርግ ጊዜ የስኮላርሺፕ ዕድል አግኝተው ወደ ቻይና የሄዱት ወንድማቸው የአቶ አስቻለው በላይ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ በዚህ ደረጃ ያሉ ሌሎች ዓለም አቀፍ ሆቴሎች ያላቸውን ነገሮች አገር ውስጥ ካሉ ሙያተኞች ይበልጥ ሀሳብ በማመንጨት፣ ግብዐቶችን በማቅረብ ከፍተኛ እገዛ ማድረጋቸውን ወንድማቸው ገልፀዋል፡፡    
“ጎልደን ቱሊፕ” በ1960ዎቹ በ6 የግል ሆቴል ባለቤቶች፣ በሆላንድ ኔዘርላንድስ መመሥረቱን የጠቀሱት አቶ ታምራት፣ እ.ኤ.አ በ2009 የ“Starwood Capital” አባል ከሆነ በኋላ የ“Luver Hotels Group” ሽርክና ውስጥ ገብቶ፣ በአውሮፓ 2ኛው ታላቅ የሆቴል ግሩፕ መሆኑን፣ በዓለም ደግሞ 8ኛ ደረጃ መያዙን ተናግረዋል፡፡ በ2015 ግዙፉ የቻይናው ኩባንያ “Jin Jiang International” የሉቨር ሆቴል ግሩፕን መግዛቱን የገለጹት አቶ ታምራት፤ ኩባንያው በመላው ዓለም ከ3ሺ በላይ ሆቴሎች እንደሚያስተዳድር ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ይህ ኩባንያ በአውሮፓ የሆቴሎች ኢንዱስትሪ ውስጥ በ2ኛ ደረጃ እንደሚገኝ፣ በ51 አገሮች ውስጥ 1100 ሆቴሎች እንዳሉትና ደረጃውም በዓለም ላይ ከምርጦቹ 5 ብራንዶች አንዱ መሆኑን አስረድተዋል።
“ጎልደን ቱሊፕ አዲስ አበባ ሆቴል” 90 የመኝታ ክፍሎች ሲኖሩት፣ በየፎቁ 18 አልጋዎች አሉት፡፡ ሦስት ደረጃ ያላቸው የመኝታ ክፍሎች እንዳሉት የጠቀሱት አቶ ታምራት፤ 70 ክፍሎች ደሉክስ፣ 15 ክፍሎች ኤክስኩቲቭና 5 የዲፕሎማቲክ ሱትስ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ አምስቱ የዲፕሎማቲክ ክፍሎች የአገር መሪዎች፣ ዲፕሎማቶች፣ የአገር ተወካዮች፣ የቢዝነስ መሪዎች፣ … ያሉ ታዋቂና ጥበቃ የሚደረግላቸው ሰዎች የሚያርፉባቸው ሲሆኑ ሳሎን (መሰብሰቢያ)፣ መኝታ ቤት፣ መታጠቢያና መጸዳጃ ክፍሎች አሏቸው፡፡ የመሰብሰቢያ ክፍሉ ሰፊ ነው፡፡ ሶፋ፣ ቲቪ፣ ስልክ፣ ኤሲ፣ ለስብሰባ አስፈላጊ የሆኑ ቁሶች፣ … ያካትታል፡፡ ቲቪው እንግዳው ክፍሉን ሲይዝ፤ “ዌልካም” ይለዋል፡፡ ክፍሉን ሲለቅ ደግሞ፤ “ይህን ያህል ተጠቅመሃል፣ ይህን ያህል ሂሳብ ትከፍላለህ” ይለዋል፡፡ መኝታ ክፍሉ ሰፊ ነው፡፡ ቲቪ፣ ስልክ፣ ፍሪጅ፣ ካዝና፣ ወዘተ … አሉት፡፡ መታጠቢያ ክፍሉ ገንዳና የቁም መታጠቢያ አለው። ገንዳ ያላቸው 5ቱ ክፍሎች ብቻ ናቸው፡፡ ሽንት ቤቱ አውቶማቲክ ነው። ቁልፎቹን ሲጫኑ ከፍና ዝቅ ይላሉ፡፡ መኝታ ክፍሉ 3 ስልኮች ሲኖሩት፣ አንዱ መታጠቢያ ክፍል ውስጥ ነው፡፡
ኤክስኩቲቭና ደሉክስ ክፍሎች በስፋትና በአገልግሎት በአብዛኛው ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ሁሉም ክፍሎች ሁለት ክፍል (መኝታና መታጠቢያ) አንድ ቲቪ፣ ሁለት ስልኮች (መኝታና መታጠቢያ ክፍል) ፍሪጅ (ሚኒ ባር)፣ ካዝና፣ አየር መቆጣጠሪያ፣ የቁም መታጠቢያ፣ ቡናና ሻይ ማፍያ ---- አሏቸው፡፡
ግንባታው ሲጀመር የተሰጣቸው ፈቃድ ባለ 4 ኮከብ ሆቴል እንዲሰሩ ነበር - አቶ ታምራት እንደሚሉት፡፡ በተሰጣቸው ፈቃድ መሰረት፣ ባላቸው ጠባብ ቦታ ባለ 4 ኮከብ ደረጃ ለማሟላት ተጨንቀውና ተጠብበው ሰሩ፡፡ ለትላልቅ ሆቴሎች ደረጃ ሲሰጥ የባለ 5 ኮከብ ደረጃ መመዘኛውን አሟልተው ስለተገኙ፣ የባህልና ቱሪዝም ሚ/ር ደረጃውን እንደሰጣቸው ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን በቦታ ጥበት የተነሳ ሁሉንም አገልግሎቶች እንዳላሟሉ አቶ ታምራት ያምናሉ፡፡ አቶ ታምራት፤ “ጎልደን ቱሊፕ” ሲሰራ የእውቀት፣ የአቅርቦት፣ የዲዛይን ካልሆነ በስተቀር ከገንዘብ ጀምሮ ምንም ዓይነት ችግር እንዳላጋጠማቸው ይናገራሉ፡፡ አሁን ወደ ሆቴል ኢንዱስትሪው ዘልቀው ገብተዋል፡፡ በሊዝ ባገኙት 5 ሺህ ካ.ሜ ቦታ ላይ ከአሁኑ ሆቴል በ5 ደቂቃ የእግር ጉዞ ርቀት ላይ፣ ሌላ ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ግንባታ መጀመራቸውን ገልፀዋል፤ አቶ ታምራት፡፡
“ጎልደን ቱሊፕ”ን ሲገነቡ ከቀረጥ ነፃ ዕድል ስለተሰጣቸው በአግባቡ ተጠቅመውበታል። ማዕከላዊ ሲስተም ያለው የአየር ማመጣጠኛ፣ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች፣ ለሆቴል አገልግሎት የሚሆኑ ቁሳቁሶች፣ …ያለ ቀረጥ አስገብተዋል፡፡ “በዕድሉ ባንጠቀም ኖሮ በራሳችን አቅም ይህን ሆቴል ለመገንባት በጣም ይከብደን ነበር፡፡ ስለተደረገልን እገዛ በጣም አመሰግናለሁ” ብለዋል፤ አቶ ታምራት፡፡

- የ2016 የስነ-ጽሁፍ አሸናፊው ቦብ ዳይላን፤ በሽልማት ስነ ስርዓቱ ላይ ላይገኝ ይችላል

ባለፈው ሳምንት ታዋቂውን ድምጻዊና የዘፈን ግጥም ደራሲ ቦብ ዳይላንን የ2016 የኖቤል የስነ-ጽሁፍ ተሸላሚ አድርጎ እንደመረጠው ያስታወቀው የኖቤል አካዳሚ፤ ለግለሰቡ ሽልማቱን ስለምሰጥበት ሁኔታ ላሳውቀው ለቀናት ባፈላልገውም ላገኘው ባለመቻሌ ታክቶኝ ትቼዋለሁ ማለቱን ዘ ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
አካዳሚው ሽልማቱን ለቦብ ዳይላን ስለሚያበረክትበትና በመጪው ህዳር ወር ላይ ስለሚከናወነው ፕሮግራም መረጃ ለመስጠት በማሰብ ድምጻዊውን ለቀናት አፈላልጎ እንዳጣውና ተስፋ ቆርጦ ፍለጋውን እንደተወው አስታውቋል፡፡
የአካዳሚው ጸሃፊ ሳራ ዳንጁስ፤ ቢቸግራቸው ወደ አንድ የቦብ ዳይላን የቅርብ ሰው ስልክ በመደወልና ኢ-ሜይል በማድረግ መረጃ መስጠታቸውንና ምላሽ ማግኘታቸውን ጠቅሰው፣ከዚህ በኋላ ግን እሱን መፈለግ እንደታከታቸው ተናግረዋል፡፡ ቦብ ዳይላን በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ መገኘት ካልፈለገ የራሱ ምርጫ ነው ብለዋል- ጸሃፊዋ፡፡  
ቦብ ዳይላን ለታላቁ የኖቤል ሽልማት መመረጡን በተመለከተ እስካሁን ድረስ በይፋ ምንም ነገር ትንፍሽ አለማለቱ ብዙዎችን ሲያነጋግር መሰንበቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ድምጻዊው በ2000 ዓ.ም ለኦስካር ሽልማት ተመርጦ በነበረበት ወቅትም በሽልማት ስነ ስርዓቱ ላይ ሳይገኝ መቅረቱን በማስታወስ፣ በዘንድሮው የኖቤል ሽልማት ስነ ስርዓት ላይም ላይገኝ እንደሚችል አመልክቷል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የቻይና ንጉስ፤ አማካሪ የሚሆነው ሁነኛ ሰው ይፈልግና አንድ አዋቂ ሊቅ አለና ወደ እሱ እንዲሄዱ፣ እንዲያሳምኑትና እንዲያመጡት ብልህ ባለሟሎችን ይልካቸዋል፡፡
ያ አዋቂ ሰው በአንድ ኃይቅ ዳርቻ ነው የሚኖረው፡፡ የንጉሡ ባለሟሎች ወደ አዋቂው ሰፈር ሄዱ፡፡ አዋቂውን ሰው አገኙትና፤ “እንደምነህ ወዳጃችን? ከንጉሡ መልዕክት ይዘን የመጣን ባለሟሎች ነን” አሉት፡፡
ሊቁ አዋቂ፤
“ምን ጉዳይ ገጥሟችሁ ወደኔ ዘንድ መጣችሁ?” ሲል ጠየቀ፡፡
ባለሟሎቹም፤
“ንጉሥ አስተዋይ፣ ታጋሽ፣ አርቆ አሳቢ፣ ዕውቀት የማይጠግብ ፈላስፋ ሰው ይፈልጋሉ፡፡ የመረጡትም አንተን ነው፡፡ ለዚህ ነው ወደ አንተ ዘንድ የመጣን” አሉት፡፡  
ሊቁ አዋቂም፤
“መምጣታችሁስ ደህና፡፡ ግን አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ፡፡”
ባለሟሎቹ፤
“መልካም ጥያቄህን ሰንዝር” አሉት
ሊቁ፤ “ጥያቄዬ፣ ንጉሡ ትክክለኛ አማካሪያቸው፣ እኔ መሆኑን በምን አወቁ? ዕውቀታቸው ትክክል ከሆነስ ለምን ለአማካሪነት አሰቡኝ?”
ባለሟሎቹ፤
“ነገሩ አልገባህም ማለት ነው፡፡ ንጉሡ የሚያምኑት ደመ - ነብሳቸውን ነው፡፡ ቀልባቸው የወደደውን! ያ ደግሞ አንተ ነህ፤ አለቀ” አሉት፡፡
ሊቁም፤ “ንጉሡ ቤተ መንግስት ውስጥ አንድ ከወርቅ የተሰራ ኤሊ አለ አይደለም?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
“አዎን” አሉት፤ ስለ ኤሊው በማወቁ እየተገረሙ፡፡ ከዚያም አጠገባቸው እጭቃ ላይ የሚሄድ አንድ የውሃ-ኤሊ አሳያቸውና፤
‹‹ይሄን ኤሊ ተመልከቱ፡፡ ይሄ ኤሊ ንጉሡ ዘንድ ካለው የወርቅ ኤሊ ጋር ቦታ ትለዋወጣለህ ወይ? ተብሎ ቢጠየቅ ምን የሚል ይመስላችኋል?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
ባለሟሎቹም፤
‹‹እምቢ የሚል ይመስለናል›› አሉት፡፡ ሊቁም፤ ‹‹በወርቅ ተለብጦ ጠረጴዛ ላይ ከመቀመጥ እዚሁ ሰፈሩ ውስጥ በሕይወት መኖሩን መረጠ፡፡ እንግዲህ የእኔም መልስ እንደዚያው ነው፡፡ እዚሁ ያለሁበት መሬት ላይ መኖርን እመርጣለሁ፤ በሉና ለንጉሡ ንገሩልኝ›› ብሎ አሰናበታቸው፡፡
*     *     *
ትክክለኛ ቦታቸውን የሚያውቁ ሰዎች ብልሆች ናቸው፡፡ ትክክለኛ ሰዎችን ለመምረጥና በትክክለኛ ቦታ ለማስቀመጥ የሚችሉ ሰዎችም እጅግ ብልሆች ናቸው፡፡ የራሳቸውን አቅምና ብቃት በአግባቡ መዝነው፡፡ “ይህ ቦታ ለእኔ አይሆንም፡፡ አልመጥነውም›› ለማለት የሚችሉ ሰዎች ራሳቸውንም፣ የሥራ ባልደረቦቻቸውንም፤ ህብረተሰብንም ከስህተት ያድናል፡፡
ዛሬ የህዝብ ጥያቄዎች ሰላም፣ ዲሞክራሲ፣ የህግ የበላይነትና የጉዳዩ ባለቤት መሆን ነው፡፡ በሀገራችን የመልካም አስተዳደርን ጉዳይ ስናነሳም አንዱ ችግራችን በሥራ መደቡ ላይ የተቀመጡ ሰዎች ወይ ብቃት ሲያንሳቸው፤ ወይ ቅንነት ሲያንሳቸው ወይ ደግሞ የማይችሉትን የሚችሉ መስለው ለመታየት፣ ያልሆነ ምስል ፈጥረው ሲገኙና ሥራን ሲበድሉ ነው፡፡ ከቶውንም የመልካም አስተዳደር ችግሩ እየተባባሰ ሲሄድ እኒሁ ሰዎች ስለ መልካም አስተዳደር መጉደል ጮክ ብለው እያወሩ መፍትሄ ሳያገኝ ሥር-የሰደደ በሽታ ሆኖ ቆይቷል። They shout at most against the vices they themselves are guilty of እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ፡፡ ጅራፍ እራሱ ገርፎ እራሱ ይጮህ እንደማለት ነው፡፡
ሁለተኛው ችግራችን ሙስና እና ሙስናን ለመሸፈን የሚደረግ ኃይለኛ የአስተዳደራዊና የተላላኪዎች መረብ መዘርጋት ነው፡፡ እከክልኝ ልከክልህ፣ ሸፍነኝ ልሸፍንህ ነው፡፡ በሀገራችን ስለ ሙስና ሲነገር እጅግ ብዙ ጊዜው ነው፡፡ ከመባባሱ በስተቀር ሁነኛ ለውጥ አልመጣም። ሙሰኞቹም ከዕለት ዕለት እየናጠጡ፣ የ‹‹አይደረስብንም” መተማመን እያበጁ፣ “በማን ይነካናል” ኩራት እየተደገጉ ይኖራሉ፡፡ ጉዳዮችን አጥርቶ ፍትሀዊ መፍትሄ የሚሰጥ በመጥፋቱ ነገሮች እየተጓተቱ ወደ ጤነኛ ዕድገት ከመሄድ ይልቅ አድሮ ጥሬ ወደ መሆን ያመራሉ፡፡ ኃላፊነት የመውሰድና የተጠያቂነትን መርህ አለመቀበል ወይም ተቀብሎ በሥራ ላይ አለማዋል፣ በስልጣን መባለግን ማስከተሉ መቼም አሌ የሚባል ነገር አይደለም፡፡ ሥልጣንን ለግል ጥቅም ማዋል አንዴ ከተጀመረ የሱስ ያህል የማይላቀቁት ጠንቅ ነው፡፡ “ከጅብ ጅማት የተሰራ ክራር ቅኝቱ ልብላው ልብላው ነው” የሚባለውን ተረት ልብ ይሏል። ከሁሉም የሚከፋው ደግሞ የመረጃ ማጥፋት ተግባር ነው፡፡ ብልሹ አሰራር ባለበት ቦታ የሰነዶች በቦታቸው አለመገኘት አይንቅም፡፡ ያን ብልሹ አሰራር በጥንቃቄ ፈትሾ፣ የውስጥ ቦርቧሪን ማግኘት ግድ ይሆናል፡፡ የውስጥ ቦርቧሪ እያለ መልካም አስተዳደርን መመኘት ምኞት ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ ወደ ራስ ማየትና ውስጥን መመርመር ትክክለኛውን የጥፋት ቦታ፣ ትክክለኛውን ቀዳዳ ለማግኘትና አፋጣኝና ቁርጠኛ መፍትሄ ወደ መፈለግ እንዲኬድ ያደርጋል፡፡ የምንሰጠው መፍትሄም የ“ከአንገት በላይ” መሆን የለበትም፡፡ በሥልጣን የባለገ መውረድ ካለበት መውረድ አለበት! ወለም ዘለም አያዋጣም፡፡ ከአንጀት ካለቀሱ እንባ አይገድም፣ ይሏልና፡፡ የችግርን ዕውነተኛ ገፅታ ካገኘን፣ የችግሩን ፈጣሪ ክፍሎችን ለይቶ ማውጣት አዳጋች አይሆንም፡፡ ምነው ቢሉ፤ “አይጢቱ ከሌለች ጉድጓዱ ኬት መጣ?” ብሎ መጠየቅ የአባት ነውና!

    የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ለሁለት “ሴት ቶፕ ቦክስ” አምራቾች፣ ለሦስት የግል ቴሌቪዥንና ለሦስት የኤፍ ኤም ሬዲዮ ብሮድካስተር ድርጅቶች ፈቃድ ሰጠ፡፡  
ባለፈው ረቡዕ በሸራተን አዲስ በተከናወነው የፊርማ ሥነ-ሥርዓት፣ “ሴት ቶፕ ቦክስ” ለማምረት ከባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ከአቶ ዘርዓይ አስገዶም ጋር የተፈራረሙት ጣና ኮሙኒኬሽን ኃ.የተ. የግ.ማ እና ብረታ ብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ሃይቴክ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ናቸው፡፡
የግል የቴሌቪዥን ብሮድካስት ፈቃድ የተሰጣቸው ሦስት ድርጅቶች፡- ፋና ብሮድካስት ኮርፖሬሽን፣ ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልና አርኪ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ ኃ.ተ. የግ.ማ ናቸው፡፡ የግል ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ብሮድካስቲንግ ፈቃድ የተሰጣቸው ሦስት ድርጅቶች ደግሞ ኤዲስቴለር ትሬዲንግ ኃ.የተ.የግ.ማ (አሐዱ 94.3)፣ አርኪ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስና ዋን ላቭ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ ኃ.የተ. የግ.ማ (ሉሲ 107.8) ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ናቸው፡፡ በዕለቱ የተሰጠው ሦስት የኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ፈቃድ፣ አሁን በአዲስ አበባና አካባቢያዋ አገልግሎት እየሰጡ ያሉትን ሰባት ጣቢያዎች ጋር ቁጥር ወደ 10 እንደሚያደርሰው ታውቋል፡፡
“ሴት ቶፕ ቦክስ” ማለት አሁን ያለው አናሎግ የቴሌቪዥን ስርጭት ወደ ዲጂታል ሲቀየር ስርጭቱን መቀበል የሚያስችል በቴሌቪዥን አናት ላይ የሚደረግ መሳሪያ ወይም በቴሌቪዥኑ ላይ የሚገጠም አንቴና ነው፡፡ መሳሪያው በዘጠኝ ወር ውስጥ ለአገልግሎት ይደርሳል ተብሏል፡፡ አቶ ዘርዓይ አስገዶም ንግግር ካደረጉ በኋላ የዕለቱ የክብር እንግዳ በምክትል ጠቅላይ ሚ/ር ማዕረግ የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል  ንግግር አድርገዋል፡፡ በዚሁ ወቅት አቶ ታደሰ ካሳ፤ “ሴት ቶፕ ቦክስ” አምራቾችን፣ አቶ ወልዱ ይመስል፤ የቴሌቪዥን ብሮድካስተሮችን እንዲሁም አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ፤ የኤፍ ኤም ሬዲዮ ብሮድካስተሮችን በመወከል የተሰማቸውን ተናግረዋል፡፡

“የሰመጉን ሪፖርት አንቀበልም አላልንም”
   ባለፈው ጥቅምት 5 ቀን 2009 ዓ.ም ታትሞ በወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ከሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ) ዋና ዳይሬክተር አቶ ብፅአተ ተረፈ ጋር በተደረገው ቃለ ምልልስ፤ ‹‹ከፕሬዚዳንቱ ፅ/ቤት ሁለተኛ ሪፖርታችሁን ወደ ፅ/ቤታችን እንዳትልኩ ተብለናል›› ሲሉ የተናገሩት የፕሬዚዳንቱን ፅ/ቤት ስም የሚያጠፋና ፈፅሞ ያልተባለ ነገር ነው፤ አንድም ቀን ሪፖርታችሁን አንቀበልም ብለናቸው አናውቅም፤ ልንልም የምንችልበት ምክንያት የለንም፡፡ የፕሬዚንዳንቱ ፅ/ቤት ሁሉንም የሃገሪቱን ዜጎችና ተቋማት በእኩልነት የሚያገለግል ተቋም ነው፡፡
አቶ አለምነህ ረጋሳ  የፕሬዚዳንቱ የፅ/ቤት የፕሮቶኮልና ኮሚኒኬሽን ተጠባባቂ ዳይሬክተር፡፡

   በቴሌኮም ማስፋፋትና በኔትወርክ ዝርጋታ ስራ የተሰማራው ህዋዌ፤ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ለ‹‹መሰረት በጎ አድራጎት›› ድርጅት የትምህርት መሳሪያ ድጋፍ አደረገ፡፡  ድርጅቱ 4500 ደብተሮችን፣ 1500 እርሳሶችን፣ 1500 እስክርቢቶዎችንና ላጲሶችን ለግሷል፡፡ በርክክብ ስነስርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የድርጅቱ መስራችና ዳይሬክተር ወ/ሮ መሰረት አዛገ ህዋዌ ስላደረገላቸው ድጋፍ አመስግነው፣ ድጋፉ  ‹‹አንድ እሽግ ለአንድ ልጅ›› በሚል የሚያካሂዱትን የትምህርት ቁሳቁሶች አቅም ለሌላቸው የማከፋፈል ፕሮጄክት፣ በእጅጉ እንደሚያግዛቸው ተናግረዋል፡፡ በዕለቱ ከህዋዌ ያገኙት ድጋፍ በገንዘብ ሲተመን ከ50 ሺህ ብር በላይ እንደሆነ የገለፁት ወ/ሮ መሰረት፤ ድጋፉ ሌሎችም ድርጅቶች ማህበራዊ ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ መነቃቃትን ይፈጥራል ብለዋል፡፡
ከድጋፉ ጎን ለጎን መሰረት በጎ አድራጎት ድርጅት የተመሰረተበትን አምስተኛ ዓመት ያከበረ ሲሆን በአምስት አመት ጉዞው ያከናወናቸውን፣ ያሳካቸውንና ያለፋቸውን ፈተናዎች በዘጋቢ ፊልም ለታዳሚዎቹ አቅርቧል፡፡ የህዋዌ ተወካዮችም ድጋፋቸውን እንደሚቀጥሉ በዕለቱ ቃል ገብተዋል፡፡ በመሰረት በጎ አድራጎት ድርጅት ጽ/ቤት በተካሄደው በዚህ ፕሮግራም ላይ ድርጅቱ አምባሳደር አርቲስት ሩታ መንግስተአብና አርቲስት ግሩም ኤርሚያስ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር

      የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ዛይድ ራድ አል ሁሴን በመጪው የአሜሪካ ምርጫ ሪፐብሊካንን በመወከል ለፕሬዚዳንትነት በመወዳደር ላይ የሚገኙት አነጋጋሪው ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ አሸንፈው ከተመረጡ አለማችን የከፋ አደጋ ላይ ትወድቃለች ማለታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
አስፈሪና አሸባሪ አመለካከቶችን የሚያራምዱት ትራምፕ፤ ይህን አቋማቸውን የማይቀይሩና በምርጫው የሚያሸንፉ ከሆነ ለአለማችን ትልቅ ስጋት መሆናቸው አይቀሬ ነው ያሉት ዛይድ፣ በተለይም ትራምፕ ግርፋትን ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው ማለታቸውንና በተጋላጭ ማህበረሰቦች ላይ ያላቸውን አሉታዊ አመለካከት ክፉኛ ተችተውታል፡፡
በየትኛውም አገር በሚካሄድ ማንኛውም አይነት የፖለቲካ ቅስቀሳ ጣልቃ የመግባት ፍላጎት እንደሌላቸው የገለጹት ዛይድ፣ ግርፋትን በሚያስፋፋና ተጋላጭ ማህበረሰቦችን የሰብአዊ መብቶቻቸው ተጠቃሚ እንዳይሆኑ በሚያደርግ መልኩ የሚቋጭ ምርጫ ሲያጋጥም ግን ዝም ማለት ተገቢ አይደለም ብለዋል፤ባለፈው ረቡዕ ጄኔቫ በሚገኘው የተመድ ዋና ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፡፡
ዛይድ በቅርቡ በሄግ ባደረጉት ንግግር ዘረኝነት የተጠናወታቸው አደገኛ ሰው ናቸው ሲሉ የትራምፕንና የሚከተሉትን ፖሊሲ በይፋ ተችተው እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሩስያ አምባሳደር በበኩላቸው፤ አንድ የተመድ ከፍተኛ የስራ ሃላፊ የውጭ አገራትን መሪዎችና መንግስታትን መተቸት አይጠበቅበትም ሲሉ የኮሚሽነር ዛይድን ንግግር መቃወማቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

     ባለፈው ሃምሌ ወር ከተቃጣበትና ከከሸፈው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር በተያያዘ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ዜጎቹን ማሰሩን የቀጠለው የቱርክ መንግስት ባለፈው ማክሰኞም ተጨማሪ 125 የፖሊስ መኮንኖችን ማሰሩን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የፖሊስ መኮንኖቹ እንዲታሰሩ የተወሰነባቸው ባይሎክ የተሰኘውንና በመፈንቅለ መንግስቱ ጠንሳሽ የሆነው ቡድን ደጋፊዎች የሚጠቀሙበትን የአጭር የጽሁፍ መልዕክት ማስተላለፊያ የሞባይል አፕሊኬሽን ሲጠቀሙ ተገኝተዋል በሚል መሆኑን ዘገባው ገልጧል፡፡
የመንግስት ሃይሎች ማክሰኞ ዕለት በመዲናዋ ኢስታንቡል የፖሊስ መኮንኖችንን በቁጥጥር ስር ማዋላቸውን  የጠቆመው ዘገባው፣ ከታሰሩት መካከልም 30 ያህሉ ምክትል የፖሊስ አዛዦች እንደሆኑ ገልጧል፡፡
የአገሪቱን የፍትህ ሚኒስትር ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው ባለፉት ወራት ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር ንክኪ አላቸው በሚል የተጠረጠሩ 32 ሺህ ያህል የወታደራዊ ሃይል መኮንኖች፣ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ዳኞች፣ መምህራንና ሌሎች ባለሙያዎች ታስረዋል፡፡