Administrator

Administrator

· በዓለም ላይ ከ15ሺ በላይ አባላት፣ከ400 በላይ ክለቦች አሉት
· በርካታ ቱሪስቶች የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውን መሰረዛቸው ቱሪዝምን ጎድቶታል
· ኢቦላ ባልተከሰተበት ሁኔታ ጎብኚዎች ወደ ኢትዮጵያ እንዳይጓዙ ተከልክለው ነበር
· ኤርታአሌ አሁንም አደገኛ ቀጣና በሚል ለጉብኝት ከተከለከሉ ሥፍራዎች አንዱ ነው
· በእስራኤል የሮኬትና የሚሳኤል ተኩስ እያለ፣ብዙ ቱሪስቶች አገሪቱን ይጎበኛሉ

ስካል ዓለም አቀፍ ቱሪዝም ክለብ ከ40 ዓመት በፊት በጃንሆይ ዘመን በኢትዮጵያ ውስጥ ተቋቁሞ የነበረ ቢሆንም መንግስት ሲለወጥ ክለቡም እንቅስቃሴውን አቁሟል፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ምሽት ካዛንቺስ በሚገኘው ጁፒተር ሆቴል የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ታደሰ፣ የአሜሪካው ስካል ቱሪዝም ክለብ አባል ሚስተር ስቴፈን ቢ ሪቻርድ እንዲሁም የአስጎብኚ ድርጅቶች ማህበር ኃላፊዎችና እንግዶች በተገኙበት በይፋ ተከፍቷል፡፡ ክለቡ ከ40 ዓመት በፊት ተከፍቶ ለምን ስራ አልቀጠለም? ድርጅቱን በአሁን ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ለምን መክፈት አስፈለገ፣ በቀጣይስ ምን ለማከናወን አቅዷል በሚሉትና ተያያዥ ዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ የስካል አዲስ አበባ አስተባባሪ፣የ “ግራንድ ሆሊዴይ ኢትዮጵያ” አስጎብኚ ድርጅት ባለቤትና የኢትዮጵያ የአስጎብኚ ድርጅቶች ማህበር የቦርድ አባል ከሆኑት ከአቶ ደሳለ ምትኩ ጋር ተከታዩን ቆይታ አድርጋለች::

እስቲ ስካል ዓለም አቀፍ የቱሪዝም ክለብ ምን እንደሆነ ይንገሩኝ ?
ስካል በቱሪዝም ዙሪያ ማለትም፡- በሆቴል በመስተንግዶ፣ በአስጎብኚነት፣ በመኪና ኪራይና በአጠቃላይ በቱሪዝም ዘርፍ የተሰማሩ የቱሪዝም መሪዎችና ባለቤቶች ማህበር ነው፡፡ የተመሰረተው በ1934 እ.ኤ.አ ሲሆን በዓለም ላይ ከ85 አገራት በላይ ይንቀሳቀሳል፡፡ ዋና መቀመጫውም ስፔይን ውስጥ ነው፡፡
ዛሬ ስካል ዓለም አቀፍ የቱሪዝም ክለብ በኢትዮጵያ ተመስርቷል፡፡ እስከ አሁን እንዴት ዘገየ?
ከ40 ዓመት በፊት በንጉሱ ጊዜ ተቋቁሞ ነበር፤ ነገር ግን ወዲያው የመንግስት ለውጥ ሲመጣ ቀረ። አሁን ከ40 ዓመት በኋላ በጣም በከፍተኛ ጥረት፣ በተለይ ላለፉት አራት አመታት ከስካል ዩኤስኤ እና ከስካል ናይሮቢ ጋር በመተባበር ሊመሰረት ችሏል፡፡
የስካል አዲስ አበባ ዋና ባለድርሻ አካላት እነማን ናቸው?
በዋናነት የጉዞ ወኪሎች፣ የሆቴል ባለቤቶችና ማናጀሮች፣ አስጎብኚ ድርጅቶች፣ በቱሪዝም ላይ የሚሰሩ እንደ ኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ያሉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ በመስተንግዶ ላይ የሚሰሩ ባለሀብቶችና ስራ አስኪያጆች ባለድርሻ አካላት ናቸው፡፡
ክለቡን በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ማቋቋም ለምን አስፈለገ?
ክለቡን በአሁኑ ሰዓት አገራችን ላይ ለማቋቋም የመረጥንበት ዋነኛ ምክንያት አንደኛ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በአሁኑ ወቅት የተፈጠረውን አለመረጋጋት በተመለከተ በተለያዩ ዓለማትና የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቶች እየወጣ ያለው መመሪያ የተጋነነና ከእውነታው ጋር የማይገናኝ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ለጉብኝት አስጊና ምቾቷን ያጣች አገር አድርገው በመሳል፣ ዜጎቻቸው ወደዚች አገር ድርሽ እንዳይሉ እያደረጉ ነው፡፡ እየወጡ ያሉት የጉዞ ማስጠንቀቂያዎችና ክልከላዎች፣ በአብዛኛው እጅግ የተጋነኑ ናቸው። ምንም እንኳን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቢታወጅም አሁንም ሁሉም ነገር ተረጋግቶ ነው ያለው፤ ሁሉም ስራውን እየሰራ ይገባል፤ ቱሪስቶችም እየጎበኙ ነው፡፡ ይህ በሆነበት ሁኔታ ብዙ ኤምባሲዎች፣ የውጭ አገር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮችና ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች የሚያወሩት ለቱሪዝም እንቅፋት እየፈጠረ ይገኛል፡፡
ይህንን የተዛባ አመለካከት መቶ በመቶ እንኳን ባይሆን በተወሰነ መልኩ ለማሻሻልና ገፅታችንን ለመመለስ፣ “ስካል አለም አቀፍ አዲስ አበባ”ን በአሁን ወቅት ማቋቋማችን ትልቅ አስተዋፅኦ ያደርግልናል ብለን በማመን ነው ወቅቱን የመረጥነው፡፡ ይህ የተጋነነ አሉታዊ መረጃ እየተናፈሰ ባለበት ወቅት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ያለውን የቱሪዝም ክለብ በአገራችን ማቋቋማችን ብዥታውን በተወሰነ መልኩም ቢሆን ያጠራዋል ብለን አምነንበታል፡፡ ስካል በዓለም አቀፍ ደረጃ ከ15 ሺህ በላይ አባላት አሉት፡፡ ይህ ዜና ቢያንስ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ላሉ 15 ሺህ ሰዎች ይደርሳል ማለት ነው፡፡ ይሄ ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ስለዚህ በዓለም ላይ ኢትዮጵያ በጥሩ ጎኑ ትነሳለች፤ የቱሪዝሙም ችግር ቀስ በቀስ እያገገመ ይመጣል ማለት ነው፡፡ ስካል በዓለም ላይ ከ400 በላይ ክለቦች አሉት፡፡
 ከአራት ዓመት በፊት ቱሪስቶች አፋር ኤርታአሌ ላይ ጥቃት ደርሶባቸው ከሞቱ በኋላ ቦታው በቱሪስቶች ከማይጎበኙ አደገኛ ቦታዎች አንዱ ሆኖ በካርታ ላይ ቀይ ተቀብቷል፡፡ ነገር ግን ከዚያ በኋላ በርካታ ቱሪስቶች እየጎበኙት እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህንን የቱሪስት መስህብ ከ”አደገኛ ቀጣና” ለማውጣት እንደ አስጎብኚዎች ማህበር ምን ጥረት አደረጋችሁ?
የውጭ አገር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮች በአብዛኛው የጉዞ ማስጠንቀቂያዎችን ሲያወጡ፣ በተለይ አፍሪካ ውስጥ ከሆነ፣ ሁሌም የአደጋ ቀጠና አድርገው ነው የሚያስቡት፡፡ ሌላው ቀርቶ የኢቦላ ወረርሽኝ በአንዳንድ የአፍሪካ አገሮች በተለይም በምዕራብ አፍሪካ በተከሰተ ጊዜ ምንም ኢቦላ ባልተከሰተበት ሁኔታ ጎብኚዎች ወደ ኢትዮጵያም ጭምር እንዳይጓዙ ማስጠንቀቂያዎችና ክልከላዎች ሲደረጉ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው። ኢቦላ በወቅቱ ከአፍሪካ ይልቅ በአውሮፓ ውስጥ ነበር የተከሰተው፡፡ ይህ ለአፍሪካ ያላቸውን የተዛባ አመለካከት የሚያሳይ ነው፡፡ በአፍሪካ ላይ አንድ ትንሽ ነገር ሲከሰት ተሯሩጠው ሪፖርት የሚያደርጉትን ያህል፣ ሁኔታው ሲሻሻልና ወደ ቀድሞ ሁኔታው ሲመለስ ለማስተካከል ግድ የላቸውም ወይም አይፈልጉም፡፡ እንዳልሺው ኤርታአሌ ላይ የተከሰተው ነገር ሶስት ወይም አራት  አመት ሆኖታል፤ ነገሩ በተከሰተ በጥቂት ጊዜ ውስጥ የፀጥታው ሁኔታ ተስተካክሎ፣ ለጎብኚዎች ክፍት ከሆነ ከሁለት አመት በላይ ሆኖታል፡፡ እኛ እንኳን በድርጅታችን በኩል በርካታ ቁጥር ያላቸው ጎብኚዎችን ወደ ቦታው  ልከናል፡፡ አሁን እኔና አንቺ እያወራን ባለንበት ሰዓት እንኳን በእኛ ድርጅት በኩል ሄደው፣ኤርታአሌን የሚጎበኙ ብዙ ቱሪስቶች አሉ፡፡ ቦታው በጥሩ የፀጥታ ሁኔታ ላይ ከመሆኑም በላይ እንደዚያ ቦታ የሚያስደንቅ መስህብም የለም፡፡ እንዳልኩሽ አንድ ጊዜ የጉዞ ማስጠንቀቂያ ከወጣ በኋላ ይረሳል፤መልሰው ወቅታዊ ሁኔታውን ለዜጎቻቸው አይገልፁላቸውም፡፡
በኢትዮጵያ በኩል ይህንን ጉዳይ በየጊዜው የማስታወሱ ስራ የማን ነው?
እኛ ሁሌም ጥረት እናደርጋለን፡፡ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅትም ሆነ የአስጎብኚ ድርጅቶች ማህበር እንዲሁም አስጎብኚ ድርጅቶች በየግላቸው ጥረት ያደርጋሉ፡፡ ነገር ግን የውጭ አገር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ትኩረት አይሰጡትም። ይህን ትኩረት የሚነፍጉት ደግሞ አፍሪካ ላይ በመሆኑ ነው፡፡
በአገሪቱ በተፈጠረው አለመረጋጋትና በተለይ በኢሬቻ በዓል ላይ ኢትዮጵያዊያን ህይወታቸውን ማጣታቸውን ተከትሎ በርካታ ቱሪስቶች የጉብኝት ፕሮግራማቸውን እየሰረዙ መሆኑ ይነገራል፡፡  ስካል ዓለም አቀፍ የቱሪዝም ክለብ በአዲስ አበባ መመስረቱ፣ ‹‹ሀይ ሲዝን›› ተብለው በሚታወቁት የታህሳስና ጥር ወራት ቱሪስቶች ሀሳባቸውን ቀይረው ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ የሚያደርገው አስተዋጽኦ ይኖራል ብለው ያምናሉ?
ችግሩ የተከሰተው በጣም መጥፎ ወቅት ላይ ነው፡፡ ወገኖቻችንም ህይወታቸውን ማጣታቸው እጅግ በጣም ያሳዝናል፡፡ ነገር ግን እንዲህ አይነት ችግሮች ሲከሰቱ ቶሎ ለመርሳት ያስችግራል። እኛ እንደ ኢትዮጵያ አስጎብኚዎች ማህበር፣ ለ“ሀይ ሲዝኑ” ቱሪስቶች መጥተው እንዲጎበኙ ጥረት እያደረግን ነው፡፡ ችግሩ ተከስቷል ወይ አዎ፤ ይህን መካድ አንችልም፤ ነገር ግን አሁን ሁሉም ተረጋግቶ ወደነበረበት ተመልሷል፡፡ ይህንን ደግሞ ለተለያዩ ኤምባሲዎች ጋዜጣዊ መግለጫዎችን በመላክ፣ ያለውን ትክክለኛ ወቅታዊ የአገሪቱን ሁኔታ ለዓለም ለማሳየት እየሞከርን ነው፡፡ ስካል አለም አቀፍ አዲስ አበባ በእዚህ አገር መመስረቱም፣ የጥረታችን አንዱ አካል ነው፡፡ በሌላ በኩል ችግሩ ሲከሰትም ሆነ ከተከሰተም በኋላ እዚህ መጥተው ጎብኝተው የተመለሱ ቱሪስቶች የነበራቸውን ቆይታ ለአገራቸው እንዲገልፁ፣ ሁሉም ነገር ወደ ቀድሞ ሁኔታው መመለሱን እንዲመሰክሩ እያደረግን እንገኛለን፡፡
ጥረታችን እንዳለ ሆኖ “ሀይ ሲዝን” ከመቅረቡ አንፃር ብዙ ነገሮችን ወደ ነበሩበት ለመመለስ ሊከብደን ይችላል፡፡ ብዙ የጉብኝት ፕሮግራሞች ተሰርዘዋል፡፡ የተወሰኑ ጎብኚዎች ሊመጡ ይችላሉ። ይህ ለየአገሩ እንዳለው አመለካከት የሚወሰን ነው። ለምሳሌ እስራኤልን ብንወስድ፣ በየቀኑ የሮኬትና የተለያየ ሚሳኤል ተኩስ እያለ፣ በርካታ ቱሪስት አገሪቱን ይጎበኛል፡፡ በሌላው አገር ቱሪስት እየሞተ እንኳን አሁንም ቱሪስት ወደዚያው ያመራል፡፡ እኛ አገር ከስንት ጊዜ አንዴ ነው ይሄ ነገር የተከሰተው። ባይከሰት መልካም ነበር፡፡ ከተከሰተ በኋላ ነገሮች ወደ ቀድሞ ሁኔታቸው ሲመለሱም ግን የሚሰማን የለም፡፡ ይሄንን ሁኔታ ወደነበረበት ለመመለስ ጥምረት ይፈልጋል፡፡ በጋራ በመስራት አገራችንን ወደ ቀድሞ ገፅታዋ ለመመለስ እንጥራለን፡፡
“የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ብዥታን ፈጥሯል” የሚል አስተያየት ከአስጎብኚ ድርጅቶች ይደመጣል። እርስዎ ይሄን አስተያየት ይጋሩታል?
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በተመለከተ የሚመለከተው አካል ለውጭ አገር ዲፕሎማቶች፣ ኤምባሲዎችና አለም አቀፍ ድርጅቶች ግልፅ በሆነ መልኩ ጎብኚዎቹን እንደማይነካ፣ ይበልጥ የጎብኚዎችንም ሆነ የአገሪቱን ደህንነት ለመጠበቅ የወጣ መሆኑን ገልፆ በጥብቅ ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ፈረንሳይ ውስጥ አለ፤ ቱርክ ውስጥ አለ፤ነገር ግን በርካታ ቱሪስቶች ይሄዳሉ፡፡ እስካሁንም በነዚህና በሌሎች አገሮች በርካታ ቱሪስቶች እየሞቱ እንደሆነ ይነገራል። በአገራችን ለጉብኝት መጥቶ ጥቃት የደረሰበት አንድም ቱሪስት የለም፡፡ ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ብዥታ ላለባቸው ወገኖች፣ያለ ማቋረጥ መግለፅ ተገቢ ነው፡፡ ይህ ሲሆን ቱሪዝም ወደ ቀድሞው ቦታው ይመለሳል፡፡ በነገራችን ላይ እንደ ቱሪዝም የሰውን ህይወት የሚለውጥ ዘርፍ የለም፡፡ የሆቴል አስተናጋጅ፣ ጀልባና በቅሎ አከራይ፣ ቱር ጋይድ፣ ቤተ-ክርስቲያንና ገዳማት፣ መስጊድና መሰል ተቋማትና ግለሰቦችን ህይወት ቱሪዝም ይይዛል፡፡ አገራችን ላይ አንድም ቱሪስት ሳይሞት፣ በጨለምተኝነት አፍሪካ ውስጥ ስለተገኘን ብቻ እንዲህ አይነት የከረረ ማስጠንቀቂያና የጉዞ ክልከላ የሚያደርጉ አካላት ኃላፊነት እንደጎደላቸው ይሰማኛል፡፡
ብዙ ቱሪስቶች የሚመጡባት ጀርመን ቻንስለር የሆኑት አንጌላ መርከል አገራችንን ጎብኝተው ከተመለሱ በኋላ በርካታ የጀርመን ቱሪስቶች የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውን መሰረዛቸው ይነገራል፡፡ በዚህ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
እንግዲህ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን እውነተኛ ነገር ለማረጋገጥ እዚህ አገር ከተገኙት የጀርመን መሪ በላይ ማንም ምስክር ሊሆን የሚችል አይመስለኝም፡፡ መጥተው በሰላም ጉዳያቸውን ፈፅመው ተመልሰዋል፡፡ እርሳቸውም ለብዙ ጎብኝዎች ምስክርና ማረጋገጫ መሆን ነበረባቸው። ግን የሆነው በተቃራኒው ነው፡፡ ተስፋ መቁረጥ ግን የለብንም፤ መንግስትም ሆነ እኛ በቱሪዝሙ ዘርፍ ያለነው በውጭ አገር በሚገኙ ኤምባሲዎቻችንና እዚህ አገር ባሉ የየአገራቱ ኤምባሲዎች አማካኝነት ተገቢውን ጥረት በማድረግ ወደቀደመ ገፅታችን መመለስ አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው፡፡ እርግጠኛ ነኝ የኢትዮጵያ መንግስትም ይህንን እያደረገ ነው። አገራት መቶ በመቶ እንኳን ማስጠንቀቂያውን ባይቀንሱት ቢያንስ ደረጃውን ቢቀንሱት መልካም ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
ስካል አዲስ አበባ ወደፊት ምን ለመስራት አቅዷል?
 አሁን ተመስርቷል፡፡ ለሁሉም የስካል አባል አገራት መመስረቱን አሳውቀናል፤ ብዙ ሽፋን ያገኛል። በዓለም አቀፍ ሚዲያዎችም ጭምር ማለት ነው፡፡ ሚያዚያ ላይ እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ ክለቡ የሚያዘጋጀው ጉባኤ አለ፤ ከ80 በላይ የስካል ክለብ አባላት ይሳተፋሉ፡፡ እግረ መንገዳቸውንም አገሪቷንና ያለችበትን ሁኔታ አይተው ይሄዳሉ፤ በቀጣይ የኢትዮጵያን ቱሪዝም ለማሻሻል በርካታ ስራዎችን ስካል ይሰራል ብለን እናምናለን፡፡
እስቲ ስለ አስጎብኚ ድርጅትዎ ደግሞ አጠር አድርገው ይንገሩኝ?
ድርጅታችን “ግራንድ ሆሊዴይስ ኢትዮጵያ” ይባላል፤ የተመሰረተው ከ13 ዓመት በፊት ነው፡፡ ከተለያዩ አገራት የተለያዩ ጎብኚዎችን በማምጣት፣በከፍተኛ መስተንግዶ አስጎብኝተን፣ የአገራችንን መልካም ገፅታ አሳይተን እንመልሳለን። ሁሉም እንግዶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ናቸው ብለን ስለምናምን፣ ለእንግዶቻችን ትኩረት እንሰጣለን፡፡ በዓመት ከ500 በላይ እንግዶች ተቀብለን የምናስተናግድ ሲሆን ከ15 በላይ ቋሚ ሰራተኞች አሉን፡፡ እንደየወቅቱ ሁኔታ ብዙ ጊዜያዊ ሰራተኞችንም እንቀጥራለን፡፡ ለምሳሌ ብዙ ቱርጋይዶችን፣ ሹፌሮችን፣ ምግብ አብሳዮችን እንቀጥራለን፡፡ በሁሉም የኢትዮጵያ አቅጣጫዎች ያሉ የቱሪስት ቦታዎችን እናስጎበኛለን፡፡  
የጉብኝት ፕሮግራማቸውን የሰረዙ ቱሪስቶች አልገጠሟችሁም?
ብዙ የተሰረዙ ፕሮግራሞች አሉ፡፡ በቁጥር ለማስቀመጥ ብቸገርም ከተለያዩ አገራት በርካታ ስረዛዎች አጋጥመውኛል፡- ከቤልጂየም፣ ከአሜሪካ ከፊንላንድና ከሌሎችም አገራት የጉብኝት ፕሮግራሞች ተሰርዘዋል፡፡       

በአገሪቱ ለተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ ምሁራን፣ፖለቲከኞች፣ ዕውቅ ግለሰቦችና የአገር ሽማግሌዎች የመፍትሄ ሃሳብ የሚሉትን መሰንዘራቸውን ቀጥለዋል፡፡ ሃሳባቸው
ጆሮ አግኝቷል ወይ ለሚለው እርግጠኛ መልስ መስጠት አይቻልም፡፡ ውጤቱን በሂደት የምናየው ይሆናል፡፡ አንድ ነገር ግን በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፡፡ የመፍትሄ
ሃሳቦቹ ቀውሱ እልባት እስኪያገኝ ድረስ መቀጠል አለባቸው፡፡ መንግስት በአዲሱ ዓመት ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ መስጠት በመጀመር፣ሰላምና መረጋጋት ያሰፍናል ብለን
ተስፋ እናደርጋለን፡፡ ችግሮችን በውይይት የመፍታት ባህላችንም በሂደት እንደሚጎለብት እምነታችን ጽኑ ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ለዛሬ
የፖለቲከኞችን እንዲሁም ጋዜጠኞችን አስተያየት አጠናቅሯል፡፡
የዚህ ውይይት ዓላማ፣በአገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ችግሮች ዙሪያ ሃሳቦችን በማንሸራሸር መፍትሄ ማፈላለግና መጠቆም ነው፡፡ በአገራችን ለተከሰተው የፖለቲካ ቀውስ
መፍትሄ የሚሆን ሃሳብ ወይም አስተያየት አለን ለምትሉ ወገኖች መድረኩ ክፍት ነው፡፡


“የአገዛዙ ሆደ ሰፊነት ወሳኝነት አለው”
አቤል ዓለማየሁ - (ጋዜጠኛ)

በአሁን ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ፖለቲካዊ ሁኔታ ድብርት የዋጠው ነው ብዬ አስባለሁ። የማይናገሩና ዝም እንዲሉ የተደረጉ ብዙኃን ስላሉ፣ ነገሮች ሁሉ ሰላም እንደሆኑ ማሰብ ተገቢ አይደለም። ኃይልና ፍርሃት የመናገር ነፃነትን ሲገፉ፣ ዴሞክራሲ ተስፋዋ ይዳፈናል።
መንግሥት በአገራችን የተፈጠሩት ፖለቲካዊ ቀውሶችና ግጭቶች ከሥር መሠረታቸው እንዲወገዱ ከልብ የመነጨ ቁርጠኝነት ካለው፣ የጉዳዩ ባለቤት የሆነውን ሕዝብ ቀርቦ በጥልቀት ማነጋገር አለበት። ለዚህ የሚረዱም ስልጡን የአገራዊ ውይይት መድረኮች ያስፈልጋሉ። ማግለል፣ አሉታዊ ስያሜዎች እየሰጡ መግፋትና የተወሰኑ የራስ ሰዎችን ብቻ ለውይይት አምጥቶ፣ተወዳድሶ መለያየት ፋይዳ ቢስ ነው፡፡ ‹‹አገሬን›› ብለው በየአደባባዩ የሚሞግቱ ጥቂት ሰዎችን መግፋት ሳይሆን ወደ ውይይት ጠረጴዛው ማምጣት ይገባል። በየእስር ቤቱ ያሉ፣ በየድረ ገጹና በውጪ ሚዲያዎች ላይ አፍ አስከፋች ሙግት የሚያቀርቡ በውጪ የሚኖሩ በርካታ ምሁራንም ከውይይት ጠረጴዛው አንድ ጫፍ ላይ ቦታ ሰጥቶ ማነጋገር ተገቢ ነው፡፡
ለውይይት የሚረዱ ፈንጣቂ ሀሳቦችን በማንሸራሸሩ በኩል መገናኛ ብዙሐን የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ ነው። በአሁን ሰዓት ነፃ ፕሬስ ተዳፍኗል። ያሉት የኅትመት ውጤቶች ቁጥር ከአንድ ጣት አንጓ የሚበልጥ አይደለም። ሚዲያው ጠፍቶ ይቅርና ኖሮ እንኳን ሀሳባቸውን በነፃነት የሚያንሸራሽሩ ምሁራንና ልሒቃንን ማግኘት አስቸጋሪ ነው። በአዲስ አበባ ከምናገኛቸው ብቁ ጋዜጠኞች ይልቅ ናይሮቢና ዋሽንግተን ላይ ተሰደው የከተሙ ጋዜጠኞች ቁጥር ይልቃል። መንግሥት ከራሱ በሚጀምር ተነሳሽነት ፕሬስ እንዲያብብ ጠንካራ ሥራ ማከናወን አለበት። ያለ ሀሳብ፣ ያለ ውይይት፣ ያለ ሙግት፣ ያለ ትችት ያሉብንን ቁልል አገራዊ ችግሮች ንደን ልናቃልል አንችልም። ለዚህ ደግሞ የአገዛዙ ሆደ ሰፊነት ወሳኝነት አለው። ሀሳብ በውስጥ ሲታመቅ በቅርቡ በተለያዩ ክልሎች እንደተፈጠረው ዓይነት ለግጭት መንስዔ ስለሚሆን፣ ሀሳብ ማብላያ መድረኮች ሊኖሩ ይገባል።
አገራችን ያለባት የአይዲዮሎጂ ችግር ይሁን፣ የሥርዓተ መንግሥት ቅርዕ መፋለስ፤በውይይት ለውጥ ማምጣት ይቻላል። ውይይት ማመቻቸት መሰልጠን ነው። ሕዝቡ የሚመጥነው የአስተዳደር ሥርዓት ግንባታ እንዲኖርም ትልቅ ሚና ይጫወታል። ብዙዎች ‹‹በአፋጣኝ የሽግግር መንግሥት ሊቋቋም ይገባል›› ሲሉ እሰማለሁ። በሀሳቡ ላይ ቅራኔ ባይኖረኝም ተቃዋሚ ጎራው ለማስገደድና ለመደራደር የሚያበቃ አቅም ሳይገነባ፣ ኢሕአዴግ. ጥያቄውን ይቀበላል ብሎ ማሰቡ ፍጹም የዋህነት ይመስለኛል።


=================================

“ሁሉን አቀፍ ውይይት ያስፈልጋል”

አቶ ይድነቃቸው ከበደ (የሰማያዊ ፓርቲ ብሔራዊ ምክር ቤት ሰብሳቢ)


በአገራችን የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ህዝብ በአገዛዙ ሥርዓት ላይ በከፋ ደረጃ ቅሬታ እንዳለው የሚያመላክት ነው፡፡ ገዢዉ መንግሥት በአገራችን የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ፣ ከዚህ ቀደም እንደሚያደርገው ሸፋፍኖ ለማለፍ ያልተቻለው ከመሆኑም በላይ፣ ተቃውሞ መኖሩን አምኖ ተቀብሎአል፡፡ ነገር ግን የተቃውሞው ምክንያት አገዛዙ እንደሚለው፤ “የኢኮኖሚ እድገት ያመጣው የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ነው፡፡” ለማለት በግሌ እቸገራለሁ፡፡ እኔ ለህዝባዊ የተቃውሞ እንቅስቀሴው ትክክለኛው ምክንያት፣ህዝባዊ ቅቡልነት ያለው የመንግሥት አስተዳደር እጦት ያመጣው ነው! ብዬ አምናለሁ፡፡ በመሆኑም ዋናው ምክንያት ለህዝብ የቆመ፣ ከህዝብ የተመረጠ የመንግሥት አስተዳደር መሻት እንደሆነ በግሌ ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ የኑሮ ሸክሙ የከበደው፣የእለት እንጀራ ከስንት አንዴ በእድል የሚመገብ ህዝብ በበዛበት አገር፣ የኢኮኖሚ እድገት ያመጣው ጥያቄ ነው፤ ማለት ግራ ያጋባል። ዛሬ ላይ ከጫፍ እስከ ጫፍ የተነሳው ተቃውሞ እዚህ ደረጃ ከመድረሱ በፊት፣የተረጋጋ የፖለቲካ ሽግግር በማድረግ፣ የዜጎች ጥያቄ እንዲመለስ በተለያየ መልኩ ጥረት ሲደረግ ነበር፡፡ ለሚደረጉ ጥረቶች ሁሉ በአገዛዙ በኩል ይሰጥ የነበረው ምላሽ ተገቢ ባለመሆኑ ችግሩ  ሊከሰት ችሎአል፡፡ ይህም እንደሚሆን ይጠበቅ ነበር፡፡
ዛሬ ማን ምን መስማትና ማየት እንዳለበት በአዋጅ የሚደነገግበት ደረጃ ላይ ተደርሷል።  ህዝባዊ ተቃውሞ መኖሩን አምኖ የተቃውሞ ምክንያቱ ደግሞ “የኢኮኖሚ እድገት ያመጣው የመልካም አስተዳደር ጥያቄ” ነው፡፡ በማለት ያመነ መንግስት፣ በአስቸኳይ አዋጅ አማካኝነት ምላሽ ለመስጠት መሞከሩ አስገራሚ ያደርገዋል፡፡ የአገዛዙ ስርዓት አሁንም ቢሆን እየሄደበት ያለው መንገድ ነገሮችን ይበልጥ የሚያወሳስብ እንጂ ወደ-መፍትሔ የሚያመራ አይደለም፡፡ የመንግሥት ምላሽ ከህዝቡ ጥያቄ ጋር ፈጽሞ የሚገናኝ አይደለም፡፡ ነገሩን ይበልጥ አስገራሚ የሚያደርገው ችግሩን ለመፍታት ጥረት እያደረግሁ ነው የሚለው መንግሥት፣ እንደ መፍትሔ የተጠቀመው የዜጎች መሰረታዊ መብት በአዋጅ መገደብ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ በፍፁም ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ ሊሆን አይችልም ፡፡
አሁን በአገራችን የሚታየው ችግር ከስርዓት አቅም በላይ ነው፡፡ “ላልተካደ ጉዳይ” ማስረጃ ማቅረብ በህግ አስገዳጅ አይደለም እንደሚባለው፣ገዢው መንግሥት ተቃውሞውን ለመቋቋም ከመደበኛ ህግ አልፎ የተለየ አዋጅ ለማውጣት ተገድዷል።   ይህም የችግሩን አሳሳቢነት አመላካች ነው፡፡ ለችግሩ መፍትሔ የሚገኘው ግን በችግሩ ዙሪያ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በቅድሚያ የጋራ ግንዛቤ ሲኖራቸው ብቻ ነው፡፡ ለዚህም እንዲረዳ ሁሉን አቀፍ ውይይት ሊካሄድ ይገባል፡፡ መፍትሔው ህዝብ ላነሳው መሰረታዊ ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ መሆን አለበት፡፡ ይህ እንዲሆን ሁሉን አሳታፊ ውይይት በአስቸኳይ መካሄድ አለበት፡፡ አሁን ሥልጣን ይዞ የሚገኘው አካል ከማንም በላይ ለዚህ ጉዳይ ተባባሪ ሊሆን ይገባል፡፡ በተለይ ዘላቂ የሆነ መፍትሔ ለማምጣት እንዲረዳ፣ በአገር ውስጥና ከአገር ውጪ የሚገኙ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን፣ የሰብአዊና የዲሞክራሲ መብት ተሟጋቾች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣በትጥቅ ትግል ተሳታፊ የሆኑ (የተኩስ አቁም ስምምነት በማድረግ)፣ምሁራን፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የህዝብ እንደራሴዎችና ሌሎች የሚመለከታቸው በሙሉ የሚገኙበት አስቸኳይ የመፍትሔ ሃሳብ የሚመነጭበትና ስምምነት ላይ የሚደረስበት ውይይት  መካሄድ አለበት፡፡ የውይይቱ ቅድመ ሁኔታና የመወያያ ነጥቦች እንዲሁም ተዛማች ነገሮች የዚሁ አካል ሊሆን ይገባል የሚል የግል አስተያየት አለኝ፡፡
(ይህ አስተያየት በግል የቀረበ እንጂ የፓርቲ አቋም የሚመለከት አይደለም)

=================================


“በሃሳብ የበላይነት መታመን አለበት”  ኤልያስ ገብሩ - (ጋዜጠኛ)

መንግስትና ህዝብ የሚገናኙባቸው መንገዶች መታፈናቸው ነው ችግር የፈጠረው፡፡ ቀደም ሲል ተቃዋሚዎች ፓርላማ ገብተው ይብዛም ይነስም የህዝቡን ድምፅ ያስተጋቡ ነበር፡፡ ከ1997 ዓ.ም በፊት ሚዲያዎችም በርካታ ነበሩ፡፡ ከዚያም በኋላ በምክንያታዊነት መንግስትን የሚተቹ ሚዲያዎች በጥቂቱም ቢሆን ተፈጥረው ነበር፡፡ እነዚህ ሁሉ ዛሬ የሉም፡፡ የፀረ ሽብር አዋጁ ሲወጣ፤ ጋዜጠኞች ሲሰደዱ፣ ፖለቲከኞችም በሽብር ሲከሰሱ … ብዙ ድምጾች ተዳፍነዋል፡፡ ሚዲያዎች በጅምላ የተከሠሡበት አጋጣሚ የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡ ራሱን ለምርጫ ሲያዘጋጅ የነበረው ትልቁ “አንድነት” ፓርቲም እንዲበተን ተደርጓል፡፡ ጠንከር ያሉ ሚዲያዎችና የህዝብ ውክልናን በጥቂቱም ቢሆን ያገኙ ፓርቲዎች እንዲህ ሲሆኑ ህዝብ በራሱ ለመተንፈስ ወደ አደባባይ ወጥቷል፡፡ ሰው ሃሳቡን የሚገልፀው ከተፈጥሮ የተቸረው ስጦታም ስለሆነ ጭምር ነው፡፡
ህዝብ በጨዋነት ነበር ጥያቄዎቹን ሲያቀርብ የነበረው፡፡ ግን የመንግስት ምላሽ ይሄን የሚመጥን አልነበረም፡፡ ኢህአዴግ ስብሰባዎችን ሲያዘጋጅ የነበረው ራሱን በሚጠቅመው መንገድ ብቻ ነው። ስብሰባዎቹ ላይ የተለየ ሃሳብ ያንፀባረቀ ብዙ ችግር ይደርስበታል፡፡ እኔ በአጠቃላይ ይሄ ችግር ህገ መንግስት ያለ ማክበር ውጤት ነው እላለሁ። ኢህአዴግ የራሱን ጥቅም ብቻ ሳይሆን የሰፊውን ህዝብ ጥቅም ባስከበረ መልኩ መንቀሳቀስ አለበት። ከ25 አመት በኋላም ዲሞክራሲ ገና ሂደት ነው ልንባል አይገባንም፡፡
አሁን ጉዳዩ ከቁጥጥር ውጭ ስለወጣ ነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የታወጀው፡፡ ይህ አዋጅ ውጤት ያመጣል አያመጣም የሚለው በሂደት የሚታይ ነው የሚሆነው፡፡ እንደኔ ግን በዚህ ሁኔታ አልነበረም አዋጁ መታወጅ ያለበት፡፡ ኢህአዴግ በቅጡ ህገ መንግስቱን ማክበር አለበት፡፡ ህገ መንግስቱ ከተከበረ የሃሣብ የበላይነት ያብባል፡፡ በሃሳብ የበላይነት መታመን አለበት፡፡ ሰው በሰላማዊ መንገድ ነው ወደ አደባባይ እየወጣ የነበረው፡፡ ይህ ሰላማዊነቱ ሊከበርለት ይገባል፡፡ ሚዲዎች በሙሉ ነፃ መሆን አለባቸው፡፡


=============================


“ህዝብ የሚተማመንበት ሁኔታ መፈጠር አለበት”
ነብዩ ኃይሉ (የቀድሞ የ”አዲስ ፕሬስ” ዋና አዘጋጅ)


የችግሮች ሁሉ መነሻ ምክንያት የኢህአዴግ ሁሉን ነገር የመቆጣጠር ባህሪ ነው፡፡ እስከ 1997 ዓ.ም ድረስ አንፃራዊ በሚባል መልኩ የፕሬስ፣ የሲቪክ ተቋማት … የፖለቲካ ፓርቲዎች የተሻለ እንቅስቃሴ ያደርጉ ነበር፡፡ በአብዛኛው በ97 ተፈጥሮ የነበረውን መነሳሳት ለማዳከም ሲባል ብዙ ነገሮች ተዘጉ፤ ብዙ አፋኝ ህጎች ወጡ፡፡ የሽብርተኝነት አዋጁ፣ የፕሬስ ህጉ፣ የፓርቲዎች የምዝገባ አዋጅ የመሳሰሉት ወጥተው በፊት ነፃ የሚመስሉ ነገሮች በሙሉ ታፍነዋል፡፡ በሌላ በኩል የመልካም አስተዳደር ጉድለት፣ የህዝብን ጥያቄ በአግባቡ ያለመመለስ ችግር ተፈጥሯል፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች መፍትሄ አግኝተው ሊስተካከሉ የሚችሉበት ዕድልም በገዳቢ አዋጆች የተዘጋ ሆነ፡፡ ለምሳሌ በዚህ ረገድ የሲቪክ ተቋማትና የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲሁም የሚዲያዎች ሚና ቀላል አይሆንም ነበር፡፡ ህብረተሰቡ እነዚህ መንገዶች ሲዘጉ ቅሬታውን የሚያቀርብበት አማራጭ አጥቶ በራሱ መንገድ ለማቅረብ ተገደደ፡፡ ይሄው ነው በሀገሪቱ የተከሰተው፡፡  
አሁን ችግሩ ተባብሶ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እስከማወጅ ተደርሷል፡፡ እርግጥ ነው ችግሩ አስቸኳይ አዋጅ ሊያሳውጅም ላያሳውጅም ይችላል። ይሄን የሚገመግሙት ቦታው ላይ ያሉ ሰዎች ናቸው። በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ የተቀመጡት አብዛኞቹ ገደቦች በፊትም ነበሩ ብዬ አስባለሁ፡፡ ለምሳሌ ፓርቲዎች ለረጅም ጊዜ ስብሰባና ሰልፍ ሲጠይቁ ተፈቅዶላቸው አያውቅም፡፡ አሁን ይሄ አዲስ እገዳ አይደለም፡፡
በግሌ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ለችግሩ መፍትሄ ይሆናል የሚል እምነት የለኝም፡፡ መፍትሄው የተፈጠሩ ችግሮችን አጥርቶ፣ የጥፋቱ መንስኤ ናቸው የተባሉ የመንግስት ባለስልጣናትንም ሆነ ሌሎችን ማጣራትና ለህግ ማቅረብ ቢቻል ጥሩ ነው፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን የሚያሰፉ እርምጃዎችም መወሰድ አለባቸው፡፡ ህዝብን በሚገባ ሊያደራጁ የሚችሉ በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች እንደገና ሊመሰረቱ ይገባል፡፡ አሁን ያሉት ህዝብን ይወክላሉ ብዬ አላምንም፡፡ ምክንያቱም እውቀቱና ፍላጎቱ ያላቸው ግለሰቦች ከመድረኩ በተለያየ መንገድ ተገፍተው ወጥተዋል፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የጠቀሱት የምርጫ ስርአት ቢሻሻልም ብዙ ነገሮችን ማስተካከል የሚቻል ይመስለኛል፡፡ ኢህአዴግ እንደ አንድ ባለድርሻ ሆኖ ምሁራንን፣ የሲቪክ ተቋማትን ያካተቱ ውይይቶች ቢደረጉ ጥሩ ነው። ለጠፋው የሰው ህይወትና በማይመለከታቸው ሁኔታ ንብረታቸው ለወደመ ሁሉ ካሳ የሚከፈልበት ሁኔታ መመቻቸት ይኖርበታል፡፡ የማይተካ የሰው ህይወትም ያለፈበት ስለሆነ እርቅ ወርዶ፣ ህዝብ የሚተማመንበት ሁኔታ መፈጠር አለበት፡፡

በመጪው ሳምንት ሪፖርቱን ለፓርላማ ያቀርባል
   ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ላይ የደረሰውን የእሳት አደጋ ተከትሎ የ22 ታራሚዎች ህይወት ማለፉ የሚታወስ ሲሆን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ቃጠሎውን በተመለከተ ያደረገውን የምርመራ ሪፖርት በመጪው ሳምንት ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ያቀርባል ተብሏል፡፡
አደጋው የደረሰ ሰሞን በስፍራው ተገኝተው ሁኔታውን የተመለከቱት የኮሚሽኑ ከፍተኛ አመራሮች፤ የእሳቱን መንስኤና የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ ኮሚሽኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ አጣርቶ የምርመራ ውጤቱን ይፋ እንደሚያደርግ መግለፃቸው ይታወሳል፡፡  የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ አባዲ፤ ምርመራውና ማጣራቱ ተጠናቆ ሪፖርቱ መዘጋጀቱን ጠቁመው፤ በመጪው ሳምንት ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት እንደሚቀርብ ገልፀዋል፡፡
በማረሚያ ቤቱ ላይ የደረሰውን የእሳት አደጋ ተከትሎ በወቅቱ 2 ታራሚዎች በጥይት፣ ቀሪዎቹ በቃጠሎው ህይወታቸው ማለፉ መገለፁ የሚታወስ ነው፡፡ ባለፈው ዓመት ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሌላ በጎንደርና ደብረ ታቦር ወህኒ ቤቶችም በደረሰው የቃጠሎ አደጋ የታራሚዎች ህይወት ማለፉ አይዘነጋም፡፡  

ባለፈው ዓመት ግንቦት ወር ላይ በዳንግላ ከተማ የቀድሞ ፍቅረኛው ላይ የአሲድ ጥቃት የፈፀመው ሰለሞን በላይ፤ የ18 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት፡፡ የአማራ ክልል የዳንግላ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በትናንትናው ዕለት በዋለው ችሎት ተጎጂዋ መሰረት ንጉሴ በአካል ተገኝታ የጥቃቷን መጠን አስረድታለች፡፡ ምንም እንኳ ጥፋተኛው የፈፀመው ጥቃት በሞትና በእድሜ ልክ እስራት የሚያስቀጣ ቢሆንም ድርጊቱን መፈፀሙን በማመኑና ከዚህ ቀደም የወንጀል ሪከርድ የሌለበት በመሆኑ፣ ፍ/ቤቱ በ18 ዓመት ፅኑ እስራት እንደቀጣው የዳንግላ ከተማ ሴቶች፣ ህፃናትና ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጽ/ቤት ሀላፊ ወ/ሮ አዛሉ ናደው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
‹‹ጥፋተኛው ወንጀሉን ከፈፀመበት ዕለት አንስቶ በቁጥጥር ስር የዋለ ሲሆን እኛም በጉዳዩ ላይ ጥብቅ ክትትል ስናደርግ ነበር›› ያሉት ሀላፊዋ፤ ምንም እንኳ በሞትና በእድሜ ልክ እስራት የሚያስቀጣ ወንጀል ቢፈፅምም ፍ/ቤቱ አንዳንድ ነገሮችን ከግምት አስገብቶ የ18 ዓመት እስር መፍረዱ ሌሎችን የሚያስተምር ተገቢ ቅጣት ነው ብለዋል፡፡ ወጣቷ ተጎጂ አሁንም በከፍተኛ ስቃይ ላይ መሆኗን የገለፁት ሀላፊዋ፤ ወቅታዊው የፀጥታ ችግር ትኩረታቸውን ስቦት እንጂ ከዳንግላ ከተማ አስተዳደር፣ ከክልሉና ከባለሀብቶች ጋር በመተባበር ልጅቷ አስቸኳይ የውጭ ህክምና የምታገኝበትን መንገድ ለማፈላለግ እንተጋ ነበር ብለዋል፡፡
ወጣት መሰረት ንጉሴ አዲስ አበባ በሚገኙ በጎ ፈቃደኛ ግለሰቦች ድጋፍ ላለፉት አምስት ወራት የቀለብ፣ የህክምናና የቤት ኪራይ ወጪ ተሸፍኖላት፣ መጠነኛ ህክምና ብታደርግም ጤናዋ መሻሻል ባለመቻሉ ወደ ውጭ አገር ሄዳ ለመታከም እስከ 1 ሚ.ብር መጠየቋን ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡
ባለፈው ጥቅምት 3 ቀን 2009 ዓ.ም በአዜማን ሆቴል የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ተዘጋጅቶላት የነበረ ሲሆን በዚህ ዝግጅት ከ200 ሺህ ብር የበለጠ ባለመገኘቱ በአስቸኳይ ወደ ውጭ ሄዳ ለመታከም እንዳልቻለች ገልፃ፤ አሁንም የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲደርስላት ጥሪ አቅርባለች፡፡
ፍርድ ቤቱ በወንጀለኛው ላይ የሰጠውን ፍርድ በተመለከተ ለአዲስ አድማስ አስተያየቷን የሰጠችው ተጎጂዋ፤ ‹‹በእርግጥ ሞት ወይም የእድሜ ልክ እስራት ይፈረድበት ብለሽ ይግባኝ ጠይቂ ተብዬ ነበር፤ 18 ዓመት ከህሊና ፀፀት ጋር በቂ ነው ብዬ ትቼዋለሁ›› በዋና የምግብ አብሳይነት (Chef) እየሰራች ራሷንና ወላጅ የሌላቸውን ታናናሽ እህቶቿን ታሳድግ እንደነበር ያስታወሰችው መሰረት፤ አሁን በደረሰባት ጉዳት እህቶቿ ያለ ረዳት መቅረታቸውን ጠቅሳ፤ ይህም ሌላ ህመም እንደሆነባት ተናግራለች፡፡

   ሰማያዊ ፓርቲ በአዲስ አበባ፣ በኦሮሚያና በአማራ ክልል አመራሮቼ፣ አባላትና ደጋፊዎቼ እየታሰሩብኝ ነው አለ፡፡ የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሰለሞን ተሰማ፤ በአዲስ አበባ ከታሰሩት አመራሮች መካከል የፓርቲው ብሄራዊ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ይድነቃቸው ከበደ ሚኒሊክ ሆስፒታል የታመመ አባል ለመጠየቅ በሄዱበት ለእስር መዳረጋቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ከስራ አስፈፃሚዎች መካከል አቶ አበበ አካሉ፣ የፓርቲው የሴቶች ጉዳይ ኃላፊ ወ/ሪት ብሌን መስፍን፣ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት መርከቡ ሀይሌ፣ እያስቤድ ተስፋዬ፣ አቶ አወቀ ተዘራና የፓርቲው የቀድሞ የህግ ጉዳይ ኃላፊ አቶ አዲሱ ጌታነህ እንደሚገኙበት ገልፀው፣ ከአዲስ አበባ ውጭ ከዋግህምራ ዞን ሰቆጣ ከተማ አቶ አበበ አየለና ሞገስ አበጀ የተባሉ አባላትም ታስረውብናል ብለዋል፡፡
ከአርሲ ዞን ደግሞ አቶ አበራ ታደሰ፣ አቶ ጀዋሮ ገልገሎ የታሰሩ ሲሆን ከደብረብርሃን አቶ አስራት እሸቴ፣ ከባህርዳርና አካባቢው አቶ በላይነህና አቶ ማሩ መታሰራቸውን ገልፀዋል፡፡
“አቶ በላይነህና አቶ ማሩ የተባሉት አባሎቻችን ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት ቢታሰሩም እስካሁን ፍ/ቤት የመቅረብ መብታቸውን ተነፍገዋል” ያሉት አቶ ሰለሞን ሌሎቹ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኋላ ለእስር መዳረጋቸውንና እስካሁን ፍ/ቤት አለመቅረባቸውን ጨምረው ገልፀዋል፡ ከአመራሮች፣ ከስራ አስፈፃሚዎችና አባላት በተጨማሪም የፓርቲው ደጋፊ የሆኑ፣ አርቲስቶች፣ መፅሀፍ አሳታሚዎችና የህትመት ውጤቶችን የሚያሰራጩ ግለሰቦች ለእስር ተዳርገውብናል ያሉት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው፤ ለምሳሌ ደጋፊያችን አትሌት ግርማ ገርባባ ስፔን ለውድድር ሄዶ እንደተመለሰ ባልታወቀ ምክንያት ታስሯል ብለዋል፡፡
‹‹በአሁኑ ወቅት አፈሳው፣ ወከባውና እንግልቱ በፓርቲያችን አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ላይ ተጠናክሮ ቀጥሏል” ያሉት ኃላፊው በምን ምክንያት እንደታሰሩ ለማወቅ የሚጠይቅም መልስ የሚሰጥም አካል የለም›› ሲሉ አማርረዋል፡፡ “አንድ ሰው ፍ/ቤት ቀርቦ የክስ ቻርጅ ሲደርሰው ቢያንስ ያጠፋው ይታወቃል ያሉት አቶ ሰለሞን፤ ‹‹አመራሮቻችን ከሶስት ሳምንት በላይ ቢታሰሩም ፍ/ቤት አለመቅረባቸው የህገ - መንግስቱን አንቀፅ 29 በእጅጉ ይቃረናል ብለዋል፡፡
‹‹መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ምክንያት በማድረግ የሚያደርሰውን የመብት ጥሰት እንዲያቆምና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም የህገ መንግስቱን መርሆዎች እንዲከተል እንጠይቃለን›› ያሉት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው፤ የፓርቲው አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች በያሉበት ቦታ ፍ/ቤት ቀርበው የተከሰሱበትን ምክንያት እንዲያውቁ፣ መብታቸው እንዲከበር፣ እንዲፈቱና ወደ ስራቸው እንዲመለሱ እንጠይቃለን›› ብለዋል፡፡ 

በሩሲያ የሚነገር አንድ ተረት አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የውሃ ክፍል ኃላፊ ሁለት የበታች ሰራተኞቻቸውን ይጠሩና፤
“ያስጠራኋችሁ አንድ አጣዳፊ ሥራ ስላለ ነው” ይላሉ፡፡
“ምንድን ነው ጌታዬ? እኛ ሥራውን ለመፈፀም ዝግጁ ነን” ይላሉ ሠራተኞቹ፡፡
አለቅየውም፤
“በጣም ጥሩ፡፡ ነገ ሹፌራችን ወደሚያሳያችሁ ቦታ ትሄዱና አንዳችሁ ቦዩን ትቆፍራላችሁ፡፡ አንዳችሁ ደግሞ ቧምቧ ትቀብራላችሁ፡፡ ሥራው ረዥም ርቀት ላይ የሚሰራ ስለሆነ ማለዳ ወፍ ሲንጫጫ ሄዳችሁ ነው ስራውን መጀመር ያለባችሁ” ሲሉ ትዕዛዝ ያስተላልፋሉ፡፡”
ሰራተኞቹ፤
“በሚገባ እንፈፅማለን” ብለው ወደየክፍላቸው ይሄዳሉ፡፡
በነጋታው ጠዋት ግን ቧምቧ እንዲቀብር የታዘዘው ሰራተኛ፤ ሹፌር ከቤት ሊወስደው ሲሄድ፣
“ዛሬ አሞኛል ሥራውን ልሰራ አልችልም” ብሎ ከነቧንቧው ቤቱ ይቀራል፡፡
ቦዩን እንዲቆፍር የታዘዘው ሠራተኛ ግን ወደተባለው ቦታ ሄዶ መቆፈር ይጀምራል። ሆኖም አቆፋፈሩ ያስገርማል፡፡ የተወሰነ ርቀት ይቆፍርና መልሶ አፈሩን እየመለሰ ይደፍነዋል፡፡ እንዲህ እያደረገ ቀኑን ሙሉ ሲቆፍርና ሲደፍን ውሎ የተባለውን ርቀት ጨርሶ ወደመሥሪያ ቤቱ ይመለሳል፡፡
አለቃው፤
“እህስ ጨረሳችሁ ወይ?” ሲሉት
“አዎ ጌታዬ፤ እኔ የተባለውን ርቀት ቆፍሬ ጨርሼ መጥቻለሁ”
“ባልደረባህስ የታለ?”
“እሱ ቧምቧውን እንደያዘ አሞኛል ብሎ ቤቱ ቀርቷል፡፡ እኔ ግን የታዘዝኩትን ቦይ ቆፍሬ መልሼ አፈሩን በሚገባ ደፍኜ ኃላፊነቴን ተወጥቼ ተመልሻለሁ ጌታዬ” አለ፡፡
*   *   *
የምንሰራው ሥራ ዓላማ ሳንገነዘብ ኃላፊነት መወጣትም ሆነ ከተጠያቂነት እድናለሁ ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ “እንስራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” የሚባለው ተረት ዓይነት ነው፡፡ አንድም በሥራ መለገም፣ አንድም ዓላማ ቢስ ሥራ መስራት፤ ከተጠያቂነት አያድኑም፡፡ ባለቧንቧው ይታመም አይታመም ማንም እርግጠኛ አይደለም፡፡ ቧንቧውን ቢያንስ ለሥራ ባልደረባው አለመስጠቱ ግን ፍፁም ከተጠያቂነት አያድነውም፡፡ ቆፋሪው ቧንቧውን ይዞ ለመሄድ አልሞከረም፡፡ በመቆፈር ያፈሰሰው ላብ ቢያሳዝንም መልሶ በመድፈኑ ቢያንስ ለጅልነቱ ዋጋ ይከፍላል፡፡
ዋናው ነገር ግን ሥራው ሳይሠራ ቀርቷል፡፡ በዚህ ዓይነት የባከነ ጊዜ፣ ጉልበት፣ ቧንቧው ሊሰጥ ይችል የነበረው አገልግሎት፤ ምን ያህል ጉዳት እንደሚያደርስ ለመገመት አያዳግትም፡፡ በሀገራችን ሁሌ እንደ ችግር ከሚነሱ ጉዳዮች አንዱ ብክነት ነው፡፡
አንድ ብክነት አለ ሲባል በተያያዥነት የሚነሱ እንደ ሠንሠለት የተሳሰሩ አያሌ ተመላካች ነገሮች እንደሚኖሩ አንዘንጋ፡፡ በቡድን የሚሠሩ ሥራዎች አንድ ሰው ሲጎድል ወይም ኃላፊነቱን ሲያጎል ቀጥ ይላሉ፡፡ የሥራ ፍሰት ምሉዕነት (System flow) ይዛባል፡፡ አንደኛው የሥራ ክፍል ኃላፊነቱን ሲወጣ ሌላኛው ክፍል ሥራውን ካልሠራ፣ የመሥሪያ ቤቱ ድፍን የሥራ ሂደት ሽባ እስከመሆን ሊደርስ ይችላል። የአመራር ደካማነት፣ የቁጥጥር ማነስ፣ የአልምጥ ሠራተኞች መብዛት፣ ስህተትን አንዱ ባንዱ ላይ መላከክ (Blame-Shifting)፣ የራሴን ከተወጣሁ ምን ቸገረኝ ማለት፤ ነገርን ከሥሩ አለማየት፣ ችግሮችን በወቅቱ አለመፍታት፣ ወገናዊነትን አለማስወገድ፣ ተቋማዊ ጥንካሬን ማጣት ወዘተ የተለፋበት ሥራ፣ የተደከመው ድካም ፍሬ እንዳያፈራ ያደርጋል፡፡ ይህ በፈንታው የሀገርን ሀብት ለብክነት ይዳርጋል፡፡ ዕድገትን ያቀጭጫል፡፡ ህዝብ ትክክለኛ አገልግሎት እንዳያገኝ ያደርጋል፡፡ በዚህ ላይ ነጋ ጠባ የምንወተወተው የናጠጠው ሙስና ሲጨመር፣ ምን ያህል የኢኮኖሚ ዝቅጠት ውስጥ እንደሚከተን ማስላት ነው፡፡
ለመልካም ሠራተኞች ምን ያህል የሞራል ድቀት እንደሚያመጣ ማስተዋል ነው። ልብ መባል ያለበት ድክመቶችና ጥፋቶች የበታች ሠራተኞች ላይ ብቻ የሚታዩ ክስተቶች አድርጎ መቁጠር ስህተት መሆኑ ነው፡፡ በከፍተኛ ደረጃ ላይ ያሉ የበላይ ኃላፊዎችም፣ በማን አለብኝነትም ሆነ በዕውቀትና ልምድ ማነስ ጥፋት ይፈፅማሉ። በሥልጣን ይባልጋሉ፡፡ ሙስና ውስጥ ይዘፈቃሉ፡፡ ሆነ ብለው ሥራ የሚያጓትቱና ተገልጋይን ህዝብ የሚያጉላሉም ይኖራሉ፡፡ መፈተሽ አለባቸው፡፡ ‹‹ወዳጄ፤ ለመሆኑ ብሣና ይሸብታል ወይ?›› ብሎ ቢጠይቀው፤ ‹‹ለዛፍ ሁሉ ያስተማረ ማን ሆነና ነው?›› አለው፤ የሚለው ተረት የሚጠቁመን ይሄንኑ ነው!


 በመካከለኛው የጣሊያን አካባቢ የምትገኘው ካልዳሪ ዲ ኦርቶና የተባለቺው ከተማ፣ እግር የጣለው ሰው ሁሉ እንዳሻው እየጠለቀ ሌት ተቀን በነጻ የሚጠጣው የወይን ፏፏቴ ሰርታ ከሰሞኑ በአገልግሎት ላይ ማዋሏ ተነግሯል፡፡
ወደ አንድ ታዋቂ የጣሊያን የእምነት መዳረሻ በሚወስድ መንገድ ላይ ወደምትገኘው ወደዚህች ከተማ ጎራ ያለ ሰው፤ባደረሰው ሰዓት ሁሉ አምስት ሳንቲም ሳያወጣ ከጣፋጩ ቀይ ወይን እየጠለቀ መጠጣት ይችላል ብሏል፤ ሜትሮ ሰሞኑን ባወጣው ዘገባ፡፡ ከተማዋ ወይን በነጻ ማቅረብ የጀመረቺው አንድ የጣሊያን የወይን እርሻ ኩባንያና መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት፣ የእምነት መዳረሻውን አካባቢ ጠብቆ ለማቆየት በጀመሩት የጋራ ፕሮጀክት አማካይነት ነው ተብሏል፡፡
አካባቢው በየአመቱ በሺህዎች የሚቆጠሩ የእምነት መንገደኞች የሚያልፉበት ነው ያለው ዘገባው፤ ጣሊያን ከዚህ ቀደምም እ.ኤ.አ በ1990ዎቹ አካባቢ ተመሳሳይ የነጻ የወይን ፏፏቴ በመክፈት አገልግሎት እንዲሰጥ አድርጋ እንደነበር አስታውሷል።

 “ኦባማ የፈየደው ነገር የለም፤ ድምጼን የምሰጠው ለትራምፕ ነው”

       የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ወንድም የሆኑት ማሊክ ኦባማ፤ የሪፐብሊካኑ ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካን ዳግም ታላቅ አገር ሊያደርጋት ይችላል ማለታቸውን ኒውዮርክ ፖስት ዘግቧል፡፡
የአሜሪካና የኬንያ ዜግነት ያላቸው ማሊክ ኦባማ፤ከወራት በፊትም፣ “ወንድሜ ባራክ ኦባማ ለአሜሪካውያንም ሆነ ለኬንያውያን ቤተሰቦቻችን ፋይዳ ያለው ነገር አልሰራም፤ ስለዚህም በቀጣዩ ምርጫ ድምጼን የምሰጠው ለዶናልድ ትራምፕ ነው” ማለታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ ከተፎካካሪያቸው ሄላሪ ክሊንተን ጋር ባደረጉት የመጨረሻ ዙር የምርጫ ክርክር ላይ እንዲገኙላቸው ከጋበዟቸው የክብር እንግዶቻቸው አንዱ እኒሁ የኦባማ ወንድም ማሊክ ኦባማ እንደነበሩ ታውቋል፡፡

 ሰሜን ኮርያ፤ የአሜሪካ መንግስት የኒውክሌር ሃይል ደህንነቷን አደጋ ላይ የሚጥል እንቅስቃሴ የሚያደርግ ከሆነ አስቀድማ በመከላከል ላይ ያተኮረ የኒውክሌር ጥቃት ልትፈጽም እንደምትልች አንድ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን ማስጠንቀቃቸውን ኤንቢሲ ኒውስ ዘግቧል፡፡
አሜሪካ አገራችንንና መሪያችንን ለማጥቃት ያለሙ የኒውክሌር መሳሪያዎችን በድንበራችን አካባቢ አደራጅታለች፤ የምትፈጽምብንን ጥቃት ለመመከት ወደ ኋላ አንልም ብለዋል፤ሊ ዮንግ ፒል የተባሉት የሰሜን ኮርያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለስልጣን፡፡
ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሚደረጉባት ተጨማሪ ማዕቀቦችም ሆኑ የአሜሪካ ጫና ሰሜን ኮርያን የጦር መሳሪያ አቅሟን ከማጠናከር በፍጹም አይገታትም ሲሉም አስታውቀዋል፤ ባለስልጣኑ። ሰሜን ኮርያ በዚህ አመት ብቻ ለአምስት ጊዜያት ያህል የኒውክሌር ሙከራ ማድረጓን ያስታወሰው ዘገባው፤አገሪቱ በቀጣይም ሌሎች ሙከራዎችን ልታደርግ እንደምትችል ባለስልጣኑ ማስታወቃቸውንም ገልጧል፡፡ አለማቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ተቋም፤ ሰሜን ኮርያ እያስፋፋችው ያለውን የኒውክሌር ፕሮግራም እጅግ አሳሳቢ ሲል እንደተቸውም አስታውሷል፡፡

 - ከ370 ሺህ በላይ ስደተኞች ወደ አገራቸው ተመልሰዋል

      በአፍጋኒስታን በተደረገው ጦርነት ባለፉት 9 ወራት ብቻ ከ2 ሺህ 600 በላይ ሰዎች መሞታቸውንና ከ5 ሺህ 200 በላይ የሚሆኑትም የመቁስል አደጋ እንደደረሰባቸው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስታወቀ፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍጋኒስታን ድጋፍ ልኡክ ረቡዕ ዕለት ባወጣው ሪፖርት እንዳለው፣ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በጦርነቶች ሳቢያ 639 የአገሪቱ ህጻናት ለሞት ተዳርገዋል፤ 1 ሺህ 822 ያህሉም የከፋ የመቁሰል አደጋ ደርሶባቸዋል። ድርጅቱ ከ61 በመቶ በላይ ለሚሆነው ሰብዓዊ ጥፋት ተጠያቂ ያደረገው የመንግስቱን ተፋላሚ ቡድን ታሊባንን ሲሆን፣ ሁለቱ የአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች በዜጎች ላይ ጥፋት ከሚያስከትሉ ተግባራት እንዲቆጠቡ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡ ባለፉት ሰባት አመታት በአገሪቱ በተደረጉ ጦርነቶች ከ25 ሺህ በላይ ሰዎች መሞታቸውንና ከ45 ሺህ በላይ መቁሰላቸውን ሪፖርቱ አስታውሷል፡፡
በተያያዘ ዜናም ባለፉት 9 ወራት ብቻ በጎረቤት ፓኪስታን የስደት ኑሮን ሲገፉ የነበሩ ከ370 ሺህ በላይ አፍጋኒስታናውያን ስደተኞች ወደ አገራቸው መመለሳቸውን በመጠቆም፣ በፓኪስታን ከ2.5 ሚሊዮን በላይ አፍጋኒስታናውያን ስደተኞች እንደሚገኙም ተመድ ማስታወቁን ቪኦኤ ዘግቧል፡፡
ባለፈው ሳምንት ብቻ 52 ሺህ የሚሆኑ አፍጋኒስታናውያን ድንበር አቋርጠው ወደ አገራቸው መግባታቸውን ዘገባው ጠቅሶ፣ በሳምንት ይሄን ያህል ቁጥር ያለው ስደተኛ ወደ አገሩ ሲገባ ባለፉት 7 አመታት ይሄ የመጀመሪያው ነው ብሏል፡፡