Administrator

Administrator

የጸረ-ትራምፕ ተቃውሞው ከ27 በላይ ከተሞችን አዳርሷል
    በዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሪፐብሊካኑን ወክለው የተወዳደሩት ዶናልድ ትራምፕ ማሸነፋቸውን የሚገልጸው የምርጫ ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ባለፈው ረቡዕ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ተባብሶ መቀጠሉ እየተዘገበ ነው፡፡
የትራምፕን በምርጫ ማሸነፍ በመቃወም ወደ አደባባይ የወጡ ተቃዋሚዎች በአስር ሺህዎች እንደሚቆጠሩ የዘገበው ሲኤንኤን፤ ረቡዕ ዕለት የተጀመረው ተቃውሞ ወደ በርካታ የአገሪቱ አካባቢዎች መዛመቱንና እስከ ሃሙስ ድረስም ከ25 በላይ በሚሆኑ የአገሪቱ ከተሞች ተቃውሞ መደረጉን ጠቁሟል፡፡
ተቃዋሚዎቹ ትራምፕ ስልጣን መያዛቸው አግባብ አለመሆኑንና አገር የመምራት ብቃት እንደሌላቸው በመግለጽ፣ ፎቶግራፋቸውን ከማቃጠልና በተለያዩ ተቋማት ላይ ጥፋት ከማድረስ አልፈው በአንዳንድ የአገሪቱ አካባቢዎችም የምርጫ ውጤቱ እንዲሰረዝና ሄላሪ ክሊንተን ስልጣን እንዲይዙ እስከመጠየቅ መዝለቃቸውን ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘግቧል፡፡
ረቡዕ የጀመረው ተቃውሞ ሃሙስም ወደ ዴንቨር፣ ሚኒያፖሊስ፣ ፖርትላንድ፣ ኦክላንድና ሌሎች የአሜሪካ ከተሞች መስፋፋቱን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ በፖርትላንድ 4 ሺህ ያህል ተቃዋሚዎች አደባባይ በመውጣት በፖሊስ መኮንኖችና በመደብሮች ላይ ጥቃት መፈጸማቸውንና ፖሊስም ከ29 በላይ ሰዎችን ማሰሩን ገልጧል፡፡
በዴንቨርም 3 ሺህ ያህል አሜሪካውያን ተቃውሞ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ አሜሪካውያን በቀጣይም ተቃውሟቸውን ለመቀጠልና የትራምፕን አሸናፊነት እንደማይቀበሉ የሚገልጹ ድርጊቶችን ለመፈጸም እያቀዱ ነው ሲል ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘግቧል፡፡
በዋሽንግተን ሰፋ ያለ ተቃውሞ ለማድረግ ታስቦ በፌስቡክ የተከፈተው ዘመቻ እስከ ሃሙስ ተሲያት ድረስ፣ 30 ሺህ አባላትን ማፍራቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ተቃውሞውን የሚደግፉ የቡድኑ አባላት ቁጥር በየሰዓቱ በሺህዎች እያደገ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
አሜሪካ በትራምፕ አሸናፊነት በተከፉ ተቃዋሚዎች ብትጥለቀለቅም፣ በምርጫ ቅስቀሳው ወቅት አንዳቸው ሌላኛቸውን ሲያብጠለጥሉና ሲወነጅሉ የከረሙት ተመራጩ ዶናልድ ትራምፕና ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግን፣ ሃሙስ በዋይት ሃውስ ተገናኝተው ልዩነትን ያሸነፈ ውይይት አድርገዋል ተብሏል፡፡
ኦባማና ትራምፕ 90 ደቂቃ በፈጀው ውይይታቸው፤ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በሚደረግበት ሁኔታና በሌሎች ብሄራዊና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዎች ዙሪያ መምከራቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡


     አዴፓ በሃገሪቱ አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ እንዲፈጠር ለተቃዋሚዎች፣ ለምሁራንና ለህዝቡ ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን በሚቀጥሉት 6 ወራት ይህን ውጥን እውን ለማድረግ በትጋት እንደሚሰራም አስታውቋል፡፡
‹‹ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ መፍጠር የወቅቱ ቀዳሚና አንገብጋቢ ጥያቄ ነው›› በሚል ፓርቲው ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ፤ ኢዴፓ የራሱን ጠቅላላ ጉባኤ ለማዘጋጀት ኮሚቴ አቋቁሞ እየተንቀሣቀሰ መሆኑን በመግለፅ ህዝቡ ድጋፉን እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ ‹‹ህዝቡ ባልተደራጀና ባልተቀናጀ ሁኔታ በሃይልና በነውጥ ጭምር እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የሚፈለገውን ለውጥ ሊያመጣ አይችልም›› ያለው ፓርቲው፤ ከዚህ ስጋት በመነሣት ኢዴፓ  ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ምሁራን የህዝቡን ትግል በአግባቡ የሚመራ ጠንካራ ፓርቲ ለመፍጠር ተግተው መስራት አለባቸው ብሏል፡፡
ቀጣዮቹን 6 ወራት በመጠቀምም ፓርቲው ተጠናክሮ ሊመጣ የሚያስችለውን ጥረት ሁሉ እያደረገ መሆኑን በመግለፅ፤ የጉዳዩ ባለቤት የሆነው ህዝብ፣ መንግስትና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ድጋፍ እንዲያደርጉለት ጠይቋል፡፡
መንግስት አንድ ጠንካራ ፓርቲ እንዲፈጠር ተገቢውን ድጋፍ ሊያደርግ ይገባል ያለው ኢዴፓ፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጣዊ ድክመታቸውን በሃቅ በመገምገምና፣ ራሳቸውን በጥራት በማጠናከር፣ ከእርስ በእርስ መጠላለፍና መነቋቆር ወጥተው አንድ መሆን አለባቸው ብሏል፡፡
‹‹ኢዴፓ በዚህ አጀንዳ እውን መሆን የሚሠጠው ትኩረት ከፍተኛ ነው›› ያለው መግለጫው፤ የፓርቲን ደንብና መመሪያ እንዲሁም ፕሮግራም ከማሻሻል ጀምሮ የፓርቲውን ስያሜ እስከመቀየርና የተናጥል ህልውናውን እስከ ማክሰም የሚደርስ እርምጃ ለመውሠድ ዝግጁ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ ይህን የሚያደርገውም አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ በመፍጠር መሆኑን የጠቀሰው ኢዴፓ፤ የሃገሪቱ ምሁራንም ዳር ቆመው ከመታዘብና ከመተቸት ፓርቲዎችን በእውቀታቸውና በገንዘባቸው እንዲደግፉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በሃገሪቱ የተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ ረግቦ እውነተኛ የብዙሃን ፓርቲ ስርአት የሚፈጠርበት ሁኔታ እንደሚኖር ፓርቲው ያለውን ተስፋ በመግለጫው አመላክቷል፡፡

• 42 ሺህ ተሳታፊዎች
 • የቻይናዋ ኦሎምፒክ ሻምፒዮን ዢን ዋንና የደቡብ አፍሪካው ማራቶን ሯጭ ሄነሪክ ራማላ
 እንግዶች ናቸው
   • 6ሺ በቀይ መነሻ 36ሺ በአረንጓዴ መነሻ
      • 500 አትሌቶች፤ 250 ቱሪስት ሯጮች፤ 20 አምባሳደሮች፤30 የአካል ጉዳተኞች፤ 500 የበጎ
         ፍቃድ አገልጋዮች እንዲሁም 30 አርቲስቶች
          • ባለፈው ዓመት ከ750 ውጭ ቱሪስት ሯጮች 1.803 ሚ ዶላር የኢኮኖሚ አስተዋፅኦ

    በቀጣይ ሳምንት መነሻ እና መድረሻውን በመስቀል አደባባይ  አድርጎ በሚካሄደው 16ኛው ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 42 ሺህ ስፖርኞች ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡ የታላቁ ሩጫ ዲያሬክተር ለዝግጅት ክፍላችን በላኩት መግለጫ እንዳስታወቁት ‹‹መስቀል አደባባይ ትልቁ ምልክታችን ነው፡፡ ውድድሩን በዚህ እንድናደርግ ስለተፈቀደልን ትልቅ ደስታ ይሰማናል፡፡ ከስራችን ውስጥ አንዱና ዋንኛው የአገራችንን ገፅታ መገንባት ነው›› ብለዋል፡፡ የ 10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው መነሻው በመስቀል አደባባይ ሆኖ በስታዬም፤ በሜክሲኮ፤ በአፍሪካ ህብረት አደባባይ፤ ሳር ቤት፤ ቄራ፤ ጎተራ ማሳለጫ፤ ላንቻ፤ መሳለሚያ በማድረግ በመስቀል አደባባይ ይፈፀማል፡፡
በ2008 እኤአ በቤጂንግ ኦሎምፒክ በ3ሺ መሰናል የኦሎምፒክ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችውና በቻይና የናይኪ ክለብ ፕሬዝዳንት የሆነችው የቻይናዋ አትሌት ዢን ዋን እና ታዋቂው የረጅም ርቀት፤ የማራቶን ሯጭ የሀጎነው የደቡብ አፍሪካው ሄንድሪክ ራማላ በክብር እንግድነት የሚገኙ ሲሆን ታዋቂው የደቡብ አፍሪካ የብሮድካት ኩባንያ ሱፕር ስፖርት የ52 ደቂቃዎች ስርጭት እንደሚሰራ ታውቋል፡፡
የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በሁለት ምድብ በተካፋፈለ አዲስ አሯሯጥ መደረጉ ልዩ ያደርገዋል፡፡ የመጀመርያዎቹ በቀይ መነሻ የሚሮጡትና ከ1 ሰአት ባነሰ ጊዜ ውስጥ 10 ኪሎ ሜትሩን የሚጨርሱ ሲሆን ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አዘጋጆች በደረሰን መረጃ በዚሁ ምድብ ለመሮጥ የተመዘገቡት ብዛታቸው 6000 ነው።  በሌላ በኩል በሁለተኛው ምድብ በአረንጓዴ መነሻ ለመሮጥ 36ሺ ተሳታፊዎች መመዝገባቸውን ያመለከቱት አዘጋጆቹ፤ በዚህ ምድብ ውድድሩን ለመጨረስ ከ1 ሰአት በላይ ጊዜ የሚወስድባቸውና በፌስቲቫል መልኩ የተለያዩ ትርኢቶችን እያሳዩና እየተዝናኑ የሚሮጡ እንደሚገኙበት ገልፀዋል፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ቢሮ ለስፖርት አድማስ በላከው መግለጫ እንደተጠቆመው ዘንድሮ በውድድሩ ላይ 500 አትሌቶች በዋናው ውድድር ተሳታፊ ሲሆኑ ከ300ሺ ብር በላይ ለሽልማት መዘጋጀቱ ታውቋል፡፡ በአጠቃላይ በ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው ከሚሳተፉት 42ሺ ተሳታፊዎች መካከል 15ሺ ያህሉ በግል፤ 24ሺ በተለያዩ ድርጅቶች፤ 600 በሞባይል ባንኪንግ ለተሳትፎ መመዝገባቸውን የጠቀሰው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መረጃ፤ 20 የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች፤ 30 የአካል ጉዳተኞች፤ 500 የበጎ ፍቃድ አገልጋዮች እንዲሁም 30 አርቲስቶች ‹‹ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ›› የሚለውን ዓላማ በማንገብ ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫውን ለሶስት አመታት አብይ ስፖንሰር የሆነው ቶታል ኢትዮጵያ ሲሆን ከ15 በላይ የተለያዩ ስፖንሰሮችን ያሰባሰበ ውድድር እንደሆነም ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል በ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው  ከውጭ አገር የሚመጡት ተሳታፊዎች ብዛት 250 ሲሆኑ ለመጀመርያ ጊዜ የቻይና ስፖርተኞችም እንደሚገኙ  ታውቋል፡፡ ዘንድሮ የውጭ አገር ተሳታፊዎች ብዛት የቀነሰው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መውጣቱን ተከትሎ የብዙ አገራት ኤምባሲዎች ለዜጎቻቸው በሰጡት ማስጠንቀቂያ ተሳትፏቸውን ለመሰረዝ በመወሰናቸው ነው፡፡
ይሁንና የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድር በቱሪዝም ገቢ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ የላቀ አስተዋፅኦ እንዳለው  በሊድስ ቢኬትዩኒቨርስቲ የተሰራው አንድ ጥናት ማረጋገጡን ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ በዩኒቨርስቲው ለካርኒጄ ሪሰርች ኢንስትቲዩት The Economic Impact of International Tourists attending the 2015 Great Ethiopian Run በሚል ርእስ በዶክተር ኢያን ሪቻርድስ የተሰራው ጥናት እንዳመለከተው ባለፈው ዓመት በ15ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድር 750 የውጭ አገር ዜጎች ተሳትፈው በተለያዩ ወጭዎች እና ለበጎ አድራጎት በሰጡት መዋጮ ከ1.803 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ አስተዋፅኦ አድርገዋል። በጥናታዊ ሪፖርቱ ላይ በዝርዝር እንደተገለፀው 750ዎቹ ቱሪስት ሯጮች ለሆቴል፤ ለአየር ትኬት በተለያዩ ሁኔታዎች በድምሩ 803ሺ ዶላወጭ ሲያደርጉ ከመካከላቸው 38 በመቶ ያህሉ በበጎ ፍቃድ የገቢ ማሰባሰብ እንቅስቃሴ በመሳተፍ 1 ሚሊዮን ዶላር አዋጥተው ለተለያዩ የእርዳታ ድርጅቶች እንዲበረከት አድርገዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የ2009 የፕላን ኢንተርናሽናል የልጆች ውድድር የዛሬ ሳምንት በወጣቶችአካዳሚ እንደሚካሄድም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የልጆች ውድድሩ በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር ዋዜማ ሲካሄድ  በሶስት የእድሜ መደቦች ከ11 ዓመት በታች፤ ከ8 አመት በታ እና ከ5 ዓመት በታች ተካፍሎ ሲደረግ ከ4500 በላይ ህፃናና ታዳጊዎችን በማሳተፍ እንደሆነ ታውቋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ መሀንዲስ፣ አንድ የፊዚክስ ባለሙያ እና አንድ ጠበቃ አንድ ቦታ ተቀምጠው ቃለ መጠይቅ እየጠበቁ ነበር፡፡ ቃለ-መጠይቁ ለአንድ መሥሪያ ቤት በዋና ኃላፊነት ለመቀጠር ነበር፡፡
በመጀመሪያ ቃለ-መጠይቁ የተደረገለት ለመሐንዲሱ ነበር፡፡
‹‹ሥራዎ ምንድነው?›› ተብሎ ተጠየቀ፡፡
‹‹መሐንዲስ ነኝ›› አለ፡፡
‹‹የት የት ሠርተሃል በሙያህ?››
ብዙ ቦታዎችን ጠቀሰ፡፡
በመጨረሻም፤
‹‹ሁለት ሲደመር ሁለት ስንት ነው?›› ተብሎ ተጠየቀ፡፡
መሀንዲሱ ይቅርታ ጠይቆ ወጣ፡፡ የተለያዩ መለካቶችን አደረገ፡፡ አያሌ ስሌቶችን ሠራ፡፡ ከዚያም ወደ ቃለ መጠይቁ ክፍል ተመለሰና፤
‹‹ሁለት ሲደምር ሁለት አራት ነው!›› ሲል መለሰ፤ ፍርጥም ብሎ፡፡
ሁለተኛው ተጠያቂ የፊዚክስ ባለሙያው ሆነ፡፡
‹‹ሥራዎ ምንድን ነው?›› ተብሎ ተጠየቀ
‹‹የፊዚክስ ባለሙያ!››
‹‹ምን ምን ይሠሩበታል?››
‹‹ልዩ ልዩ የሳይንስ ምርምሮችን አደርጋለሁ››
‹‹መልካም፤ ሁለት ሲደመር ሁለት ስንት ነው?››
የፊዚክሱ ባለሙያ ይቅርታ ጠይቆ ለማሰብ ወጣ፡፡ ወደ ቤተ መፃህፍት ሄደ፡፡ ተገቢውን ምርምር አደረገ፡፡ ከዩናይትድ ስቴት ደረጃ ምደባ ጽሕፈት ቤት ጋር ተመካከረ፡፡ ብዙ የሂሳብ ስሌት ሠራ፡፡ በመጨረሻም፤
‹‹ሁለት ሲደመር ሁለት አራት ነው!›› ሲል አወጀ፡፡
የመጨረሻው ቃለ መጠይቅ ተደራጊ ጠበቃው ነበር፡፡
‹‹ሥራዎት? ተባለ፡፡
‹‹ህጋዊ ጠበቃ››
‹‹ምን ምን ሠርተውበታል?››
‹‹የቤት ጉዳይ፤ የጋብቻና ፍቺ፣ የሙስና፣ የአስተዳደር ክርክር፣ የንግድ ጉዳይ፣ የውርስ ጉዳይ፣ የመኪና ሽያጭ ክርክር፣ በአጠቃላይ የማሕበራዊ ጭቅጭቆችንና ንብረታቸው የተዘረፈባቸውን ሰዎች ፍትሃዊ ጥያቄዎች ጉዳይ ስከራከር ኖሬያለሁ፡፡››
መልካም የመጨረሻው ጥያቄ የሚከተለው ነው፡፡
‹‹ሁለት ሲደመር ሁለት ስንት ነው?››
ጠበቃው ክፍሉ ውስጥ እየተንጎራደደ ማሰብ ጀመረ፡፡ ሰው በአካባቢው መኖር አለመኖሩን አረጋገጠ፡፡ የተተከለ የሚሥጥር ማዳመጫ ስልክ ይኖር እንደሆነ ኖሩን አጣራ፡፡ ከዚያም በሹክሹክታ እንዲህ አለ፡-
‹‹ሁለት ሲደመር ሁለት ስንት እንዲሆን ትፈልጋላችሁ? እንደራደር!›› አለ፡፡
*    *    *
ጊዜና ዘመን ሲበላሽ፣ ሙስናም ጣራ ሲነካ፤ ተራው የሂሳብ ስሌት እንኳ መደራደርን ይጠይቃል። አንዳንዶች እንደሚሉት፤ ወደፊት ሰላምታም የገንዘብ ድርድር ሳያስጠይቅ አይቀርም፡፡ እያደር ሰብዕናም ቦታ ያጣል፡፡ የሁሉም ነገር መፈክር ‹‹ገንዘብ! ገንዘብ! ገንዘብ!›› ብቻ ይሆናል፡፡ እንደ ‹‹ሁለት ሲደመር ሁለት›› ሂሳብ፣ ላይ ላዩን ቀላል የሚመስለው ነገር ሁሉ ከሥሩ የሚጎተት ገንዘብ አለ፡፡ ይሄ የገንዘብ ጥያቄ፣ በሰጪና ተቀባይ መካከል የሚያልቅ ብቻ አይደለም፡፡ በየመንግስት ቢሮው የገንዘብ ጥያቄ አለ፡፡ በየግል ድርጅቱ የገንዘብ ጥያቄ መዓት ነው፡፡ በመንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የገንዘብ ጥያቄ በሽ-በሽ ነው! በየተቋማቱ ገንዘብ የማይገባበት ጨዋታ የለም፡፡ ባንኩ፣ ኢንሹራንሱ፣ ስንት ህዝብ ይታደጋሉ ሲባሉ፤ የዚያው የገንዘብ ውስጠ- ወይራ አካላት ናቸው፡፡ ስለተደረሰባቸው ጥቂት ባለገንዘቦች ሲወራ፤ ያደፈጡ ዋና ዋና በዝባዦች ያመልጡና ከስዕሉ ይሠወራሉ፡፡ ዝቅተኛውና መካከለኛው ተበዝባዥ እቤት የሚልበት ቦታ ሳይኖር በየጎጆው እያለቀሰ ይኖራል፡፡ የተገመቱና የሚጠረጠሩ መዝባሪዎች በቶሎ እርምጃ ስለማይወሰድባቸው፣ ይብሱን ሲፋፉና የልብ-ልብ ሲሰማቸው ማየት የዕለት ጉዳይ ይሆናል፡፡ የነገም ሌላ ቀን ነው (Gone with the Wind ) መጽሐፍ አንደኛው ገፀ-ባህሪ ሬት በትለር፡-
‹‹አገር ስትለማ ቀስ በቀስ መበልፀግ ይቻላል፡፡
አገር ስትጠፋ ግን በፍጥነት መበልፀግ ይቻላል››
ይለናል፡፡ ስለዚህ ለመዝባሪዎች የአገር መጥፋት የፈጣን ብልፅግና ዕድል ነው እንደማለት ነው። ሙስናን በሥር-ነቀል መንገድ ማጥፋት የግድ የሚሆነው፣ አገርን ማዳን ግድ ስለሆነ ነው፡፡ እንጂ ጥቂት ግለሰቦች ሲናጥጡ ማየት ስለሚያስቀና አይደለም፡፡
የመዝባሪዎች አለመኖር የሰላም ዋስትና ነው፡፡ ሰላም የዲሞክራሲ፤ የፍትሕ፣ የእኩልነት፣ የሉዓላዊነት ዋስትና ነው፡፡ የምርጫም ዋስትና ነው፡፡ የአሜሪካን ምርጫ ስናይ በመጀመሪያ በህሊናችን የሚመጣው የሰላሙ ድባብ ነው፡፡ የምርጫ ሳጥን አይገለብጥም፡፡ ቆጠራ አይሳሳትም፡፡ ቂም- በቀል የለም፡፡ ልቅ የሆነ የፖለቲካ ክርክር ግን አለ!! ተሰዳድበውም፣ ተማምተውም፣ ተሸረዳደውም፤ ተካሰውም… በመጨረሻው ወሳኙ የህዝቡ ድምፅ መሆኑን አምነው፤ ‹‹በመመረጥህ እንኳን ደስ አለህ››… ‹‹ጥንካሬሽን አደንቃለሁ!›› ሲባባሉ ስናይ ትምህርት ልንወስድ ይገባናል፡፡ የተመረጠው ማንም ይሁን ማን፤ እንዲት አሜሪካ አለች፡፡ በወጉ መስተዳደር ያለባት! የህዝቡን ድምፅ አክብሮ፣ ህዝቡን የሚመራ ፕሬዚዳንት የተመረጠባት! ኃያል አገር ናት ብሎ ህዝቡ የሚያምንባት! እንደ ፖለቲካ ሰዎች አባባል፤ ‹‹የአሜሪካ ህዝብ፤ አሜሪካ ውቂያኖስ አቋርጣ ነፃነትንና ዲሞክራሲን ለማስከበር ስትሄድ የሚደግፍ ህዝብ ነው፡፡ ነገር ግን ወደ ምርጫ ሳጥን ለመሄድ መንገድ ማቋረጥ ወገቤን ይላል፤ ይከብደዋል!›› ያም ሆኖ እንደ ምንም መንገድ አቋርጦ ለመሄድ የቻለው ክፍለ-ህዝብ ድምፅ ይሰጣል፡፡ ድምፁም ይከበራል፡፡ ዋናው ቁም ነገር፤ ለአገር ጥሩ ሥራ ለመሥራት መኖር ያለበት ቁርጠኝነት፣ መከፈል ያለበት መስዋዕትነት መኖሩን ማስተዋል ነው፡፡ ሼክስፒር፤ ‹‹መልካም መልካሙን ሥራ! ሠይጣን ይፈር!›› (Do good and shame the devil!)
የሚለንን ከቀልባችን ሆነን ካሰብንበት፣ ታላቅ አገር- አድን መርህ የሚሆነው ለዚህ ነው!!

አንድ የኢራኖች ተረት የሚከተለውን ይላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ብዙ ጫጩት የምትፈለፍል አንዲት ዶሮ ነበረች፡፡ የዶሮዋ ባለቤት አንድ ቀን፣ “የምትወልጂውን ጫጩት እንድትነግሪኝ እፈልጋለሁ” አላት፡፡
ዶሮዋም፤
“ምኑን ነው ስለ ጫጩቱ ማወቅ የፈለግኸው?” ብላ ግልፅ እንዲያደርግላት ጠየቀችው፡፡
ባለቤትየውም፤
“ወንድ ይሁን ሴት? ለእርባታ የሚሆን ወይስ የማይሆን? መልኩስ ምን ይመስላል?” ብሎ አብራራላት፡፡
ዶሮዋም፤
“ይሄንን ሁሉ እኔ አላውቅም፡፡ የታቀፍኩት ዕንቁላል በቀኑና በራሱ ጊዜ መፈልፈሉን ብቻ ነው የማውቀው”
ባለቤትየው፤
“እኔ የምፈልገውን ዓይነት ጫጩት ካልሰጠሺኝ እስከ ዛሬ ከእኔ ጋር መኖርሽ ከንቱ ነው ማለት ነው፡፡ አሁንም አታዋጪኝም፡፡ ብታስቢበት ይሻላል” አላት፡፡
ዶሮይቱም፤
“የጠየቅኸኝ እጅግ ከባድ ጥያቄ ነው፡፡ ጫጩት እያፈራሁልህ ማመስገን ሲገባህ ገና የሚወለዱትን ካላወቅሽ ብለህ ውለታዬን ሁሉ ያለ ዋጋ ማስቀረትህ አሳዝኖኛል”
ባለቤትየው፤
“እስከ ዛሬ የወለድሻቸውስ ወዴት ሄዱ?”
ዶሮይቱ፤
“እሱን መመለስ ያለበት፤ ትላንትና እራሱ ነው”
ባለቤትየው፤
“ወደፊት ስለምትወልጂያቸው አዳዲስ ጫጩቶችሽ ምንም ማወቅ አልችልም ማለት ነው በቃ?”
ዶሮይቱ፤
“ለማለት የምችለው አንድ ነገር ብቻ ነው”
ባለቤትየው በጥድፊያ፤
“ምን? እባክሽ ንገሪኝ?” አላት፡፡
ዶሮዋም፤
“ስለአሮጌዎቹ ጫጩቶች ትላንት እንደነገረን ሁሉ፤ ስለ አዲሶቹ ጫጩቶች ደግሞ ነገ ይነግረናል”
ብላ መለሰችለት፡፡
*    *    *
በአንድ ሀገር ላይ የሚደረግ ለውጥ በአንድ ጀምበር የሚገኝ አይደለም፡፡ ቀስ በቀስ እና በሂደት የሚሆን ነገር ነው፡፡ ለውጥ አጓጊ የመሆኑን ያህል በጥድፊያ ካልሆነ ብለን ሱሪ በአንገት ብናደርገው “የቸኮለች አፍሳ ለቀመች” የሚባለው ተረት ይመጣል፡፡ “አትሩጥ አንጋጥ” ማለት ያስኬዳል፡፡ “ለውጥ የእረፍትን ያህል እፎይታን ይሰጣል” ይላሉ አበው፡፡ አዋቂዎች፤ “a change is as equal to rest” እንዲሉ በፈረንጅኛው፡፡ ለውጥ አስተሳሰባችንን መቀየር ይሻል፡፡ በጎታች አስተሳሰብ ከተያዝን የለውጥንም መምጣት የኋሊት እንጎትተዋለን፡፡ ለረዥም ጊዜ ስንጠይቀው የነበረው “ትክክለኛው ሰው በትክክለኛው ቦታ ይቀመጥ” (The right man at the right place) ጊዜውን ጠብቆ እየመጣ ይመስላል፡፡ የሰሞኑ ሹም ሽር ይሄን ያመላክታል ብለን እንገምታለን። ቢያንስ ብሔረሰባዊ ምደባን ብዙም ያማከለ አለመሆኑ ደግ ነው! ሆኖም አብረን ማየት ያለብን መሰረታዊ ጉዳዮች አሉ፡፡ አንደኛው፤ በአንድ መስሪያ ቤት ውስጥ ሲሰራበት የነበረው የቆየ ልማድ፣ ለአዲሱ ሹም እንቅፋት እንዳይሆንበት ምን ማሻሻያ ሊደረግ ይችላል? የሚለው ነው፡፡ ጎታች ባህል አዲሱንም ኃይል የመጎተት አቅም ሊኖረው እንደሚችል አለመዘንጋት ነው፡፡ የሚያሰራ ሁኔታ መኖር አለበት እንደማለት ነው፡፡ ሁለተኛው፤ ከዚህ ቀደም ገዢ መሬት ሆኖ የቆየውን፤ ፖለቲካውን ቀዳሚ፣ ሙያተኝነትን ተከታይ አድርገን እናይበት የነበረውን የአስተሳሰብ መነፅር መቀየር እንደሚገባን ማስተዋል ነው፡፡ አለበለዚያ “አዲስ ወይን በአሮጌ ጋን” እንደሚባለው ይሆንብናልና ነው፡፡ በምንም ዓይነት ሙያተኝነት (professionalism) ቀዳሚ መሆን አለበት!! ሶስተኛው፤ ገና የቀስ በቀስ ለውጥ (evolution) ላይ እንጂ አብዮታዊ ለውጥ ውስጥ (revolution) እንዳይደለን ማጤን ነው፡፡
የያዝነው ለጥያቄዎች ሙያዊ ምላሽ የምንሰጥበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ያም በሙያዊ ተሐድሶ (Technocratic reform) ነው፡፡ አዝጋሚ ይሁን እንጂ በንቃት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ለውጥ የጥንቱ ሌኒን፤ “አንድን ህዝብ ከአሥር ዓመት የፖለቲካ ትምህርት ይልቅ፤ የአንድ ዓመት እንቅስቃሴ የተሻለ ንቃት ይሰጠዋል።” የሚለውን አለመርሳት ነው፡፡ ይኸው ሊቅ፤ ‹‹ታላቅ ለውጥ የሚመጣው ፓርቲው ራሱን ሲቀጣ ወይም ሲያስወግድ (The party purges itself)” ነው ይለናል፡፡ ለሚካሄደው አዎንታዊ ሁኔታ አዎንታዊ አመለካከት መኖር ገንቢ ነው፡፡ ዜጎች፣ የሲቪል ማህበራትና ቡድኖች፤ ተቺና ጠያቂ የመሆናቸውን ያህል የሚያምኑበትን የመደገፍ ባህልም ሊኖራቸው ይገባል፡፡ እንደ ሙሽራይቱ፤ ሁሌ ‹‹ካልታዘልኩ አላምንም›› እያሉ መጓዝ ላያዋጣ እንደሚችል መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ሀገራችን የምሁራን ሀብታም ሆና ሳለ፣ የሚያሠራ ሁኔታ በመጥፋቱ ዕውቀት በየሥርቻው ተቀርቅሮ፣ በየፊፋው ተንሸራቶ፤ ወይም አንድያውን ተገልሎ የከረመበት ሁኔታ መኖሩ ፀሀይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡ ለዛሬ አዎንታውያን ‹‹ለሁሉም ጊዜ አለው›› የሚለው ብሂል መልካም ተስፋ ነው፡፡ በዚያም ብቻ አያልቅም፡፡ ከበደ ሚካኤልን ማዳመጥ ደግ ነው፡-
‹‹ለሁሉም ጊዜ አለው፣ ብሏል ሰለሞን
እጠይቀው ነበር፤ በተገናኘን፤
ሞት እራሱ እሚሞት ምን ጊዜ እንደሆነ››
ድህነትን ጨርሶ ለመገላገል ገና ብዙ ጊዜ ይጠይቃል፡፡ የፖለቲካ ጣጣችን ከባህል ነገረ-ሥራችን ተሠናሥሎ፤ ካልተሻሻለ ውሃ-ወቀጣ ይሆንብናል! ጥረት፣ ማስተዋል፣ ጥበብ ነው የሚያሳድገን፡፡ አለበለዚያ፤ ነገን መጠራጠርም ግድ ይሆናል፡-
ነገ
‹‹ነገ፤ እባክህ አትምጣ እኔው እመጣለሁ
ደሞ፣ ዛሬ ብዬ፣ እሞኝብሃለሁ….››
የሚለውን ያገራችንን ገጣሚ ረቂቅ መልዕክት እንድናስብ እንገደዳለን! ዞሮ ዞሮ፤ ‹‹የወደቀ ሁሉ ጨዋ ነው›› ከሚል የአስተሳሰብ እሥረኛነት ነፃ መሆን የዕድገታችን መሽከርክሪት ነው! ‹‹የወደቀ ዛፍ ምሣር ይበዛበታልም›› የሚለው ተረት፤ ጨካኝ ላልሆነ ትውልድ እንደማይሠራ ማስተዋል ግድ ሆኗል!!
በመጨረሻ ማስተዋል ያለብን ትልቅ ቁም ነገር፤ አዳዲስ ሹማምንት አገኘን ማለት ወደ ፒራሚዱ ታህታይ መዋቅር ካልወረዱ አደጋ መሆኑን፤ ለውጥ አዳጊ እንጂ ያለቀ ጉዳይ አለመሆኑን፤ ነገ ገና ውጤቱን የምናውቀውን ጉዳይ ዛሬ ካልዳኘን ብለን አለመወራጨቱ፤ መገንዘብ ዋና ነገር መሆኑን ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የለውጥን ሀሳብ በአዎንታዊ መንገድ ማሰብና አሉታዊ ነገሮችን ማስወገድ ትልቅ ኃይል አለው! ሼክስፒር፤ ‹‹Do good and shame the devil›› ያለው ይሄንን ነው፡፡ ‹‹መልካም ሥራና ሠይጣን ይፈር! ጉድ ይሁን!›› እንደ ማለት ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ አዲስ ነገር የተፈጠረበት ጊዜ ነው ስንል በሚዲያ ከልኬቱ በላይ አናጋንነው፡፡ ሥራውን ሳናይ አናናፋው! ሆኖም አዲስ መንፈስ መፈጠሩን በርቱዕና ሀቀኛ መንፈስ ለሚያየው እንደ ዕድገት መሆኑን እናስብ! ኢትዮጵያ ብዙ ልጆች አሏት!
ብቁ ንቁ፡፡ አራማጅ፡፡ ተራማጅ፡፡ ለውጥ ፈጣሪ! ይህን እሳቤ የያዘ ሰው፤
‹‹ልጄ፤ አዲስ ፀጉር አበቀልኩ›› አለ፤ አባት፡፡
‹‹እዛው ቆዳህ ላይ?›› አና ጠየቀ ልጁ፡፡ ‹‹አዎ ልጄ፤ ባታውቀው ነው እንጂ፣ ቆዳዬ‘ኮ ሠፊ ነው!!” አለ አባት። ያልተለየ ያልተፈተሸ … ማንም ልብ ያላለው ቦታ አለኝ ማለታቸው ነው! ኢትዮጵያ ሰፊ ናት፡፡ አዋቂዎቻችን ብዙ ናቸው፡፡ ሆኖም አያያዝ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ያልተጠቀምንበትን ኃይል እንጠቀምበት፡፡ ሁሉም ሊያግዛቸው ይገባል!! መማር የዕውቀት ፍፃሜ አይደለም፡፡ ተግባር ፈተና ነው፡፡ በፈተናው ማደግም፣ መለወጥም ይቻላል። ለማንኛውም ቀና አስተሳሰብን የመሰለ ነገር የለም!

ትርፉ በ152 በመቶ አድጓል፤ የባለአክስዮኖች የትርፍ ድርሻ 39.5 በመቶ ደርሷል
    ብርሃን ኢንተርናሽናል ባንክ በተጠናቀቀው የ2015/16 የበጀት አመት ከትርፍ ግብር በፊት 349.8 ሚሊዮን ብር ማትረፉን ባንኩ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታወቀ፡፡
ብርሃን ኢንተርናሽናል ባንክ በበጀት አመቱ ያስመዘገበው ትርፍ ባለፈው አመት ከነበረው የ152 በመቶ ብልጫ እንዳለው የጠቆመው የባንኩ መግለጫ፣ የባንኩ ባለአክስዮኖች የትርፍ ድርሻ መጠንም ባለፈው አመት ከነበረበት 20.3 በመቶ ወደ 39.5 በመቶ ማደጉን ገልጧል፡፡
ባንኩ በተጠናቀቀው የበጀት አመት አሰራሩንና ቅልጥፍናውን በማሳደግና ከደንበኞቹ ጋር ይበልጥ ተቀራርቦ በመስራት  ውጤታማ ስኬት ማስመዝገቡንና ተቀማጭ ገንዘቡም ባለፈው አመት ከነበረበት የ72.6 በመቶ እድገት በማሳየት 5.3 ቢሊዮን ብር መድረሱንም መግለጫው አስታውቋል።
ባንኩ በበጀት አመቱ የሰበሰበው የውጭ ምንዛሬ ካለፈው አመት የ88 በመቶ ብልጫ በማሳየት 130.9 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱን፣ አጠቃላይ የብድር ክምችቱም 3.8 ቢሊዮን ብር መድረሱን፣ አጠቃላይ ሃብቱ ካለፈው የበጀት አመት የ3 ቢሊዮን ብር ጭማሪ በማሳየት 7.2 ቢሊዮን ብር መድረሱን፣ የተከፈለ ካፒታሉ 730.6 ሚሊዮን ብር መድረሱን እንዲሁም ጠቅላላ ካፒታሉ ወደ 1.1 ቢሊዮን ብር ማደጉን መግለጫው አብራርቷል፡፡
ብርሃን ኢንተርናሽናል ባንክ በአመቱ 33 አዳዲስ ቅርንጫፎችን በመክፈት አጠቃላይ የቅርንጫፎቹን ቁጥር 105 ማድረሱን የጠቆመው መግለጫው፣ የባንኩ ደንበኞች ቁጥር በበጀት አመቱ መጨረሻ 195 ሺህ 412 መድረሱንም የባንኩ መግለጫ አክሎ አስታውቋል፡፡

 የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋማት ገምጋሚ በጥራት በማሰልጠን በስራ አፈፃፀማቸው የመረጣቸውን ማሰልጠኛ ተቋማት ሸለመ ከአዲስ አበባ ዮዮ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በጥራት አሰልጥኖ ብቁ ሾፌሮችን እያወጣ ነው ለተባለውና ከአዲስ አበባ ተቋማት 1ኛ የወጣው ዮዮ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም የዋንጫ እና የሰርተፍኬት ሽልማት አግኝቷል፡፡
ጥቅምት 17 ቀን 2009 በተደረገው በዚህ የሽልማት ስነ ስርአት ላይ በክልል ያሉ ሌሎች የማሰልጠኛ ተቋማትም መሸለማቸው ታውቋል፡፡
2003 ዓ.ም የተመሰረተው ዮዮ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም በሁሉም የመንጃ ፍቃድ የስልጠና ዘርፎች ላይ ስልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

በመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ላሉ ከ1 ሺህ በላይ አረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን በነገው ዕለት በአለምገነት ቆርቆሮ ፋብሪካ ባለቤቶች የምሳ ግብዣ ያደርጋል፡፡
በምሳ ግብዣው ላይ ሁሉም ህብረተሰብ እንዲታደም የተጋበዘ ሲሆን በዝግጅቱ ላይ የሃይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው በሺህ የሚቆጠሩ እንግዶች ይገኛሉ ተብሏል፡፡
ማዕከሉ በአሁን ወቅት ከመንግስት ባገኘው 30ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ለአረጋውያን ምቹ የሆነ መኖሪያ ተገንብቶ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡
ከአረጋውያንና አዕምሮ ህሙማኑ ጋር በማዕከሉ በመገኘት ልደት፣ ሰርግ፣ ኒካ፣ ቀለበት፣ መልስ፣ ሰዲቃ፣ የሙት መታሰቢያ፣ ምርቃት እና ሌሎች ዝግጅቶች ማድረግና አረጋውያኑን መመገብ እንደሚቻልም ማዕከሉ አስታውቋል፡፡ 

መነሻ
ባለፈው ሳምንት በወጣው “ቁምነገር” መጽሄት ላይ የጸሀፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ ቃለመጠይቅ ታትሞ ነበር፡፡ በሁለት ክፍል ያሳተማቸው ግጥሞች ላይ የተሰነዘሩ ትችቶች አሉ ወይ? ብሎ ጋዜጠኛው ላቀረበለት ጥያቄ እንዲህ ሲል መለሰ፡
‹‹ፊት ለፊት መጥቶ የነገረኝ ሰው የለም፡፡ አንድ ግን ዶ/ር በድሉ የሚባል ሰው በጋዜጣ ላይ ትችት ጽፎ ነበር፡፡ በኋላ ራሱ ይቅርታ ጠይቋል፡፡ እንዴት ነው የተቸኸው ሲባል፣ በየ 100 ገጹ አንዱን ግጥም አንብቤ ነው የምተቸው አለ፡፡ ይሄ ምን አይነት ንቀት ነው፡፡ በፍጹም እንዲህ አይደረግም፡፡ ትልቅ ስህተት ነው፡፡ ደራሲው የጻፈበትን ርእዮተ አለምስ አይተኸዋል ወይ ሲባል፣ ‹ይሄ ምን ርእዮተ አለም አለው› አለ፡፡ ሰዎች ናቸው ይህን የሚነግሩኝ፡፡ የኔ ግጥም እኮ የተጻፈው በሶሻሊስት ርእዮተ አለም ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ ‹ይሄን ርእዮተ አለም ሳታውቅ እንዴት ጻፍክ?› አሉት፡፡ ከዚያ፣ ‹ይቅርታ፣ እኔ ይህንን አላወቅኩም ነበር አለ፡፡ በድሉ ጥሩ ገጣሚ ነው፡፡ ስራዎቹንም አንብቤለታለሁ፡፡ ቢሆንም ግን የኔን ግጥም ለመተቸት ብቃቱ ያለው አይመስለኝም። . . . እንዲያውም በእሱ ላይ የሆነ ልጅ መልስ ጽፎ ነበር፡፡ ግን “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ወስዶ ሲሰጣቸው አይታተምም ብለው ከለከሉት፡፡ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ቢታተም ኖሮ መከራከሪያ ነጥብ ይሆን ነበር፡፡ ለውይይት በር ይከፍታል፡፡ ግን እምቢ አሉት፡፡›› (ቁምነገር፣ ቅጽ 15፣ ቁጥር 270፡፡)
በዚህ አንቀጽ ከሰፈረው የጋሽ አያልነህ ንግግር ያለው እውነት አንድ ብቻ ነው፤ የእኔ ስም፡፡ ግራ ተጋባሁ፡፡ የእጅ ስልኬን አነሳሁና ጋሽ አያልነህ ዘንድ ደወልኩ፤ ስልኩ ተይዟል፡፡ ቆይቼ ደወልኩ፤ ይጠራል፡፡ አላነሳውም፡፡ ከአንድ ሰአት በሁዋላ ደወልኩ፡፡ ስልኩ ተዘግቷል፡፡ ሲከፈት እንዲነገረኝ አንድን ጨቁኜ ዘጋሁት፡፡ ይህ የሆነው ቅዳሜ ነው፡፡ እሁድ አልፎ ሰኞ መጣ፤ ስልኩ አልተከፈተም፡፡ ሰኞ እለት የ”ቁም ነገር” መጽሄት አዘጋጅ ዘንድ ደወልኩ፡፡ የሰፈረው መረጃ ሀሰት መሆኑን ስነግረው፣ ‹‹እንዴት ሊሆን ይቻላል? ጋሼ አያልነህ አይዋሽም፤ ትልቅ ሰው ነው፡፡›› አለኝ፡፡ አያይዞም፣ እንደሚያናግረውና ማስተባበያ ካለው እንደሚያትመው ገልጸልኝ፡፡ እራሴን ተጠራጠርኩት፡፡ የጋሽ አያልነህ ግጥሞች የታተሙ ሰሞን ሚዩዚክ ሜይዴይ በሚያዘጋጀው ሂሳዊ ውይይት ላይ፣ ለውይይት መነሻ የሚሆን ሀሳብ፣ እራሱ ጋሽ አያልነህ ባለበት እንዳቀረብኩ ትዝ ይለኛል፡፡ በጋዜጣ ግን በፍጹም አልጻፍኩም፡፡ ምን አልባት ለውይይት ያቀረብኩትን አትመውት ይሆን? በወቅቱ የሚዩዚክ ሜይዴይ አስተባባሪ የነበረው በፍቃዱ አባይ ስለነበር በእጅ ስልኩ ላይ ደወልኩ። ሁኔታውን በዝርዝር ገለጥኩለት፡፡ ለዚያ ውይይት ያቀረብኩት መነሻ ሀሳብ በየትኛውም ጋዜጣ እንዳልታተመ ገለጠልኝ፡፡ አያይዤም፣ ‹‹ለመሆኑ በውይይቱ ላይ ይቅርታ ጠይቄው ነበር እንዴ?›› ስል ጠየኩት፡፡ ‹‹በጭራሽ! እንዲያውም መጨረሻ  ላይ እኮ እራሱ ጋሽ አያልነህ፣ ‹ስሜታዊ ሆኜ በድሉን ያስቀየምኩት ይመስለኛል፤ ይቅርታ ልጠይቅ ብሎ› ይቅርታ የጠየቀው እሱ ነው፤ ካስፈለገ እኮ ሙሉ ውይይቱ በምስል መቅጃ ተቀድቷል፡፡›› አለኝ። “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ አዘጋጅ ዘንድ ደወልኩ፤ ‹‹በእኔ ስም ጋሽ አያልነህ ግጥሞች ላይ የታተመ ሂስ አለ እንዴ?›› ጠየቅኩ፡፡ ‹‹ኧረ በጭራሽ›› መለሰልኝ፡፡ ‹‹እሺ የሆነ ልጅ መልስ አምጥቶ ለምን አናትምም አላችሁ?›› ደግሜ ጠየቅኩ፡፡ ‹‹እንዴ! መጀመሪያ አንተ ካልጻፍክ መልስ እንዴት ይመጣል?›› በጥያቄ መለሰልኝ፡፡ ‹‹እሺ መልስም አይሁን፣ ስለ ጋሽ አያልነህ ግጥሞች፣ የተጻፈ፤ የእኔን ስም የሚጠቅስ ጽሁፍ መጥቶላችሁ ነበር?›› ደግሜ ጠየቅኩ፡፡ ‹‹ኧረ በፍጹም!››፡፡
ማክሰኞ ጠዋት የስልኬ የመልእክት ማሳበቂያ ድምጽ ጮኸ፡፡ ከፍቼ ሳነበው፣ ‹ጋሽ አያልነህ ስልኩን ከፍቷል፤ አሁን ብትደውል ታገኘዋለህ ይላል›፡፡ ደወልኩለት፡፡ ተነሳ፡፡
‹‹ሀሎ ጋሽ አያልነህ››
‹‹ማን ልበል?››
‹‹በድሉ ነኝ፡፡››
‹‹አያልነህ መኪና እየነዳ ነው፤ ‹ከደቂቃዎች በኋላ እደውልልሀለሁ› እያለህ ነው፡፡››
‹‹ጥሩ፡፡ በቁምነገር መጽሄት ላይ እኔን ጠቅሶ የተናገረውን እንዳነበብኩትና ስለዚያ ጉዳይ ላነጋግረው እንደምፈልግ ንገርልኝ፡፡››
‹‹እነግረዋለሁ፡፡ ይደውልልሀል፡፡››
አንድ ሰአት. . . ሁለት ሰአት አለፈ፤ አልተደወለም። እኔ ደወልኩ፡፡ መጥራት እንደጀመረ ጥሪው ተጨናገፈ፡፡ ደግሜ ደወልኩ፤ አሁንም ተጨናገፈ፡፡ ከዚያ በኋላ ያለው ምርጫ ሁለት ነው፡፡ አንድ፣ ንቆ መተው፡፡ ሁለት፣ እሾህን በሾህ እንዲሉ፣ የሚዲያውን ሁከት በሚዲያ ማጥራት፡፡ እኔ ሁለተኛውን መረጥኩ፡፡ ንቆ መተው፣ ይሉኝታ . . . የሚባሉት እሴቶች፣ በመቻቻልና በመከባበር አብሮ ለመኖር ትልቅ ዋጋ ቢኖራቸውም፣ ያለ ቦታቸው ሲገቡና ደፋር ሆን ብሎ ሲጠቀምባቸው የሀሰትን፣ የበደልንና የእስስታዊነትን ጡንጫ ያደነድናሉ፡፡ በተለይ እንደ ጋሽ አያልነህ አይነት በእድሜ አንጋፋና ታዋቂ ሰው በርካታ ወጣቶች ላይ ሊያሳድር የሚችለው ተጽእኖ ቀላል ስላልሆነ፣ እንዲህ አይነቱን ‹ጅብ ወለደ› ንቆ መተው፣ በተለይ እንደኔ ግማሽ እድሜውን መምህር ሆኖ ለኖረ፣ ሀላፊነትን ያለመወጣትም ጭምር ነው፡፡  
በጋሽ አያልነህ ንግግር ላይ መልስ ለመስጠት ከወሰንኩ በኋላ፣ ጽሁፌ ምን አይነት መሆን፣ ምን ምን ጉዳዮች መያዝ አለበት? ብዬ እራሴን ጠየቅኩ። በ‹‹እንዲህ ብለሀል!  . . . እንዲህ አላልኩም!››  ብቻ የታጀለ ፍሬ ከርስኪ እንዲሆን አልፈለግኩም፡፡ ጋሽ አያልነህ ‹‹ . . እንዲህ አለ አሉ›› ብሎ የጠቃቀሳቸውን ሀሳቦች፣ ከ‹‹አለ አሉ›› የሀሜት ግርግም አውጥቼ፣ ከእውቀትና እውነት መስክ ላግጣቸው ወደድኩ፡፡
ለምን ይዋሻል!?
ጋሽ አያልነህ፣ በጸሀፊነት የማውቀህ የመጀመሪያ ዲግሪ የቋንቋና ስነጽሁፍ ተማሪ ከነበርኩበት፣ ከ1980ዎቹ መጀመሪያ አንስቶ ነው፡፡ በእሳት ሲነድ፣ ትግላችን፣ ሻጥር በየፈርጁ፣ የመንታ እናት. . . ወዘተ. በመሳሰሉት አብዮታዊ ተውኔቶቹ አውቅሀለሁ፡፡  
ጋሽ አያልነህ ትዋሻለህ፡፡ ‹‹. . ዶ/ር በድሉ የሚባል ሰው በጋዜጣ ላይ ትችት ጽፎ ነበር፡፡›› አልክ፤ እኔ በየትኛውም ጋዜጣ ትችት አልጻፍኩም፤ ጋዜጣውን አምጣና ሞግተኝ፡፡ በአንድ ውይይት ላይ ለውይይት የሚሆን የመነሻ ሀሳብ በቃል አቅርቤያለሁ፡፡  ‹‹በኋላ ራሱ ይቅርታ ጠይቋል፡፡›› አልክ፤ እኔ አንተን ይቅርታ አልጠየቅኩም፡፡ ይቅርታ ያልጠየቅሁ ይቅርታን ስለምጸየፍ ወይም የተሸናፊነትና የአሽናፊነት መግለጫ አድርጌው አይደለም፡፡ ባጠፋ እንኳን አንተን ታላቄን፣ ታናሼንም ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡ አንተ ግን ይቅርታ መጠየቅን የተሸናፊነት መገለጫ አድርገህ ትመለከተዋለህ፡፡ ይህን ያስባለኝ፣ አዳራሽ ሙሉ ሰው በተሰበሰበበት፣ ውሉ ዝግጅቱ በምስል መቅጃ በተቀዳበት ዝግጅት መጨረሻ ይቅርታ የጠየከኝ አንተ ሆነህ ሳለ ገለበጥከው፡፡ ምነው እኔ አጥፍቼ በሆነና ይቅርታ በጠየቅኩህ (በነገራችን ላይ ዘንግተኸው ከሆነ ሚዩዚክ ሜይዴይ የተቀረጸው ፊልም አለ)፡፡ ጋሼ በጣም ያዘንኩት በአንተ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በሰው ልጅ ላይ ያለኝን እምነት የፈተነብኝ፣ ‹‹ፊት ለፊት መጥቶ የነገረኝ ሰው የለም፡፡. . . . . ሰዎች ናቸው ይህን የሚነግሩኝ፡፡›› ያልከውን ሳነብ ነው፡፡ ምነው ጋሼ! አዳራሽ ሙሉ ሰው ፊት፣ መድረክ ላይ ተቀምጠን፣ ወጣት በፍቃዱ አባይ ውይይታችንን እየመራው፣ የግጥሞችህን ጉድፎች ያልኩትን ፊት ለፊት አልነገርኩህም?  
ጋሼ አንድ ጸሀፊ ለቤተሰቡ፣ ለወገኑ፣ ሲልቅም ለሰው ልጆች ክብር ሊኖረው ይገባል፡፡ ለዚህ ሁሉ መሰረቱ ግን ራስን ማክበር ነው፡፡ የጸሀፊው የራስ ክብር ደግሞ መሰረቱ እውነትን በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ (ህይወቱን የሚያስከፍለው ቢሆን እንኳን) ለመመስከር ያለው ቆራጥነት ነው፡፡ ራስህን ለእውነትና ፍትህ ስታስገዛ፣ ለማህበረሰብህ እውነትና ፍትህን ትመግበዋለህ፡፡ ከዚህ አንጻር ለራስህ ክብር የለህም ብልህ ቅር ይልህ ይሆን? ለራስህ ክብር ቢኖርህ እንደምን እንዲህ ያለ የሀሰት ቅሌት ውስጥ አያልነህን ትጨምረዋለህ? ‹‹እንዴት ነው የተቸኸው ሲባል፣ በየ 100 ገጹ አንዱን ግጥም አንብቤ ነው የምተቸው አለ፡፡ ይሄ ምን አይነት ንቀት ነው፡፡ በፍጹም እንዲህ አይደረግም፡፡ ትልቅ ስህተት ነው። ደራሲው የጻፈበትን ርእዮተ አለምስ አይተኸዋል ወይ ሲባል፣ ‹ይሄ ምን ርእዮተ አለም አለው› አለ፡፡ የኔ ግጥም እኮ የተጻፈው በሶሻሊስት ርእዮተ አለም ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ ‹ይሄን ርእዮተ አለም ሳታውቅ እንዴት ጻፍክ?› አሉት፡፡ ከዚያ፣ ‹ይቅርታ፣ እኔ ይህንን አላወቅኩም ነበር አለ።››  በየ100 ገጹ አንድ ግጥም ብወስድማ፣ 1156 ገጽ ካለው አንዱ መጽሀፍህ ውስጥ 11 ግጥሞች ብቻ ነበር የሚሆነው፡፡ እኔ ግን ሌላው ቀርቶ ጋሼ፣ በዘጠኝ ቀን የእስር ቤት ቆይታህ (ከግንቦት 28 ቀን 1996 እስከ ሰኔ 7 ቀን 1969) የጻፍካቸውን ወደ 22 የሚጠጉ ግጥሞች ገምግሜ፣ ‹‹አንድ ጓድ ለሌላው ጓድ የጻፋቸው ደብዳቤዎች ይመስላሉ፤አንተ ራስህ በመግቢያህ ውስጥ ስለ ግጥም ያስቀመጥካቸውን ባህርያት አያሟሉም.›› ብዬህ ነበር፡፡
ሌላው የተሟገትንበት ነጥብ፣‹ ‹በድሉ ሶሻሊዝምን አያውቅም፤ የተማረው አሜሪካ ስለሆነ ሶሻሊዝምን ይጠላል፡፡›› ስትል፣ የተማርኩት አሜሪካ ሳይሆን ኖርዌይ መሆኑን አስተካክዬህ፣ ስለ ሶሻሊስት ሪያሊዝም ስነጥበባዊ ፍልስፍና ተነጋግረን ነበር፡፡ አሁንም ደግሜ ልንገርህ ጋሼ፣ በየዘመኑ የተጻፉ ስነጽሁፎችን ለመገምገም በየዘመኑ መኖር አያሻም፤ እንዲያ ቢሆን ለሀምሌትና ኦቴሎ የሼክስፒር ዘመነኛ ሀያሲ ከየት አባታችን እናመጣ ነበር! ስለ የዘመኑ ስነጥበባዊ ፍልስፍና እና ስለየ ስራዎቹ ባህርያት ማወቅ፣ በንባብ የመተንተንን አቅም ማዳበር ለአንድ ሀያሲ በቂው ነው፡፡ በነገራችን ላይ ጋሼ፣ ሶሻሊዝምን እንዳንተ በቅርብ ባይሆንም፣ በመኖርም አውቀዋለሁ፡፡ ገና በ11 አመቴ፣ በጠዋት የኪራይ ወተት ሳመጣ፣ ከደጃችን ላይ ክብ ሰርቶ የከበበውን ሰው፣ ግራ ቀኝ ሰርስሬ ስገባ፣ ቀይ ሽብር የጣለውን የጎረቤታችንን የእንሰሳት ሀኪሙን የዶ/ር መክብብ ተሰማን ሬሳ ስመለከት፣ከእጄ ካመለጠው የወተት ሽጉጥ (የቢራ ጠርሙስ ሽጉጥ ይባል ነበር) የፈሰሰው ወተት አፈሩ ላይ ከረጋው ደም ጋር ሲደባለቅ የፈጠረው ህብረ ቀለም ዛሬም ደምቆ ይታየኛል፡፡ ‹‹ሁሉም ለአብዮታዊት እናት ሀገር ዘብ ይቁም!›› ብላችሁ ባወጃችሁት የብሄራዊ ውትድርና አገልግሎት፣ ገና 18 አመት ልደፍን መንፈቅ ሲቀረኝ ከትምህርት ቤት ታፍሼ፣ የሁለት አመት ከመንፈቅ ግዳጄን ተወጥቻለሁ፡፡ እና ጋሼ እንዳንተ ባልንቦጫረቅበትም፣ እንደ አንድ የዘመነ ደርግ ወጣት ሶሻሊዝምን በመኖርም በመጠኑ አውቀዋለሁ፡፡
‹‹እንዲያውም በእሱ ላይ የሆነ ልጅ መልስ ጽፎ ነበር፡፡ ግን “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ወስዶ ሲሰጣቸው አይታተምም ብለው ከለከሉት፡፡ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ቢታተም ኖሮ መከራከሪያ ነጥብ ይሆን ነበር፡፡ ለውይይት በር ይከፍታል። ግን እምቢ አሉት፡፡›› ላልከውም ተደራቢ ውሸትና (ካፈርኩ አይመልሰኝ) መሆኑን የጋዜጣው አዘጋጆች አረጋግጠውልኛል፤ እና ጋሼ ግን ለምን? እንዳንተ ያለ አንጋፋ፣ የኢትዮጵያን ደራስያን ማህበርን በምክትል ሊቀመንበርነት የሚመራ፣ ብዙ ወጣቶች በአርአያነት ቀና ብለው የሚመለከቱት ሰው ለምን ይዋሻል? አንድ የሰውን ልጅ እታደጋለሁ የሚል ደራሲ፤ እንደምን ከዚህ አይነቱ ውሸት ጋር አደባባይ መቆም ይቻለዋል?
የደራሲው እውነት ወዴት አለች!?
የደራሲ እውነት የግሉ እውነት ብቻ አይደለም፤ እንዲያውም ማህበራዊና ሰብአዊ እውነቱ ነው ጸሀፊን በማህበሰቡ ውስጥ የመሪነት ሚና የሚያጎናጽፈው፡፡ በዚህ ረገድ አኔና አንተ በዘመናችን እንደ አቤ ጉበኛና በአሉ ግርማ ያሉ ስለ ሰው ልጅ እውነት መስዋእት የሆኑ ደራስያን እናውቃለንና ታድለናል። ለሰው ልጅ እውነት ለመቆም የሚውተረተር ነፍስ ካለንም ድጋፍ ልናደርገው እንችላለን፡፡ ጋሼ መቼም አደባባይ ቆመን እንድንነጋገር መርጠሀልና እስቲ ስለዚህ አይነቱ የደራሲ እውነት እንነጋገር፡፡ ከአንተ ዘንድ ይህች የደራሲው ማህበራዊና ሰብአው እውነት አለችን? እኔ አታውቃትም ብዬ እማኝ ጠቅሼ እሞግትሀለሁ። እማኝ የምጠቅሰው አንተኑ ነው፤ ተግባርና አንደበትክን፡፡
ባለፈው ሳምንት በዚያው በ”ቁምነገር” መጽሄት ላይ እንዲህ ብለሀል፤ ‹‹ዛሬ የኢትዮጵያ ኪነጥበብ ህዝብ እየመራ አይደለም፡፡ በመሰረቱ ኪነጥበብ ህዝብን መምራት አለበት፡፡›› ልክ ብለሀል ጋሼ፤ እኔም በዚህ ነጥብ እስማማለሁ፡፡ ስለዚህ ሁላችንም እንደ አቅማችን የምንኖርበት ማህበረሰብ መንገዱን ያስተውልበት ዘንድ ጭላንጭል ለመፈንጠቅ እንሞክራለን፡፡ የሚገርመው ግን ይህ አባባልህ ከሰበካነት አልፎ የደራሲ ነፍስህ ግብር አለመሆኑ ነው፡፡ ‹‹እኔ በደርግ ውስጥ የነበርኩ ሰው ነኝ። በእዚያ ውስጥ እያለሁ ምን እጽፍ ነበር? በአንድ በኩል ለእንጀራ የሚሆን ስራ ትሰራለህ፡፡›› ትላለህ፣ እዚያው ቃለመጠይቅ ውስጥ፡፡ ‹‹ለእንጀራ›› ማለት ምን ማለት ነው ጋሼ? በደርግ ዘመን ወጣቶች ላመኑበት፣ ለሀገርና ማህበረሰብ ይበጃል ላሉት እውነት መስዋእት ሲሆኑ፣ ደራስያን ባመኑበት እውነት ፍቅር ተነድፈው ሲጠፉ፣ አንተ ለእለት እንጀራ ትጽፍ ነበር! እስቲ ልጠይቅህ፤ ትግላችንን፣ የመንታ እናትን፣ ሻጥር በየፈርጁን፣ እሳት ሲነድን . . . .  ጽፈህ የበላኸው እንጀራ ምን ምን ይላል? ይህን የምጠይቅህ ለምን አብዮቱን በብእርህ አፋፋምክ፣ ደገፍክ ብዬ አይደለም፡፡ ብዙዎች በደርግ ዘመን ስለ አብዮቱ ጽፈዋል፡፡ ‹ሶሻሊዝም የሀገራችንን ህዝቦች ለዲሞክራሲና ለብልጽግና ያበቃል፤ በህዝቦች መካከል እኩልነትን ያሰፍናል› ብለው ከልብ አምነው እንጂ፣ለእለት ጉርስ ብለው ግን አይደለም። ባለቅኔውንና ጸሀፌ ተውኔቱን ደበበ ሰይፉን ታውቀዋለህ፡፡ ለሶሻሊዝም የነበረው እምነት መቼም ከሀይማኖት የላቀ ነበር፡፡ ‹መስከረም›፣ ‹በስሙ ሰየማት›፣ ‹ትዝታ ከበሮ›ን የመሳሰሉት ግጥሞቹ፣ደበበ ሶሻሊዝምን ምን ያህል ከልቡ ያምንበት እንደነበር ከማሳየታቸውም በላይ፣ እውነቱና ምናቡ  ተቃቅፈው ያዘመሩትን ቅኔ ምጥቀት ይመሰክራሉ። ደበበ ከደርግ መውደቅና ከሶሻሊዝም ቀብር በኋላ፣ የኖረውን ኑሮና መጨረሻውን የምታውቅ ይመስለኛል፡፡ በአሉንም ከእኔ በተሻለ ታውቀዋለህ። ጋሼ እንዲህ ያለችው እውነት አንተ ዘንድ የለችም፡፡ ትላንት እውነቴና እምነቴ ነው ብለህ፣ ‹እሳት ሲነድን› ያንቀለቀልክለትን አብዮት፣ ዛሬ እንጀራ ገዶኝ ነው ማለት፣ በዚህኛው ዘመንም ማኛ ለማነጎት ምጣድ ከማስማት የዘለለ ፋይዳ የለውም፡፡


የፌስ ቡክ ተከታዮቹ ከ1 ሚሊዮን በላይ ሆነዋል

ቃና ቴሌቪዠን የተመልካቾቹን የመዝናኛ አማራጭ ለማጎልበት ሁለት አዳዲስ ዝግጅቶችን (አንድ ወጥ እና አንድ በአማርኛ የተመለሰ) ማቅረብ መጀመሩን ገለጸ፡፡
በአሁኑ ጊዜ ጣቢያው በየሳምንቱ የ30 ሰዓት አዳዲስና ያልታዩ ዝግጅቶችን ለተመልካቹ እንደሚያቀርብ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ሰሞኑን 5ኛ ክፍሉ የተሰራጨው የ #ምንድን ዝግጅት፣ የተለያዩ ወቅታዊ ማሕበረሰብ ተኮር ርዕሶችን እያነሳ ከተለያዩ ምልከታዎች አንጻር የሚያወያይ ሲሆን በዚህም የተመልካቾችን ተሳትፎና ጤናማ ውይይቶች ያበረታታል ተብሏል። አዲስ የተጀመረው “ልጅቷ” የተባለው የኮሎምቢያ ድራማ፤ በእውነተኛ ክስተቶች ላይ የተመረኮዘ ሲሆን የጦርነትን አስከፊ ገጽታ ያሳያል፡፡ ታሪኩ አንዲት ሴት በሽምቅ ተዋጊዎች ተመልምላ የጦርነትን አስከፊ ገፅታ በአፍላ እድሜዋ እንድትኖረው ስትገደድና ከብዙ ዓመት በኋላ አምልጣ አዲስ ኑሮ ለመጀመር ስትሞክር፣ ከሕብረተሰብ ጋር ለመቀላቀል፣ ነፃነትዋን ለመልመድና ቤተሰብዋን ለመጋፈጥ የሚደርስባትን ውጣ ውረድ ያስቃኛል፡፡ ድራማው ከፍተኛ አድናቆትን ያገኘ ሲሆን በቅርቡ ኔትፍሊክስ በተባለው ታዋቂ የፊልም አቅራቢና አከፋፋይ ተገዝቶ፣ በብዙ አገሮች እየታየ ይገኛል ብሏል - ቃና በመግለጫው፡፡
በተመልካቾች ዘንድ ተወዳጅነትን ያተረፈውን ጥቁር ፍቅር የተሰኘ ድራማ የሚተካ ቅጣት የተባለ ወደ አማርኛ የተመለሰ የቱርክ ድራማ በቅርቡ ማቅረብ እንደሚጀምር ጠቁሞ ቅጣት በይዘቱ ልክ እንደ ጥቁር ፍቅር በተለያዩ አገሮች ዝና እና ሽልማት ተቀዳጅቷል ተብሏል፡፡
ጣቢያው የተመልካቾቹን ዕይታ ለማበልፀግና ፍላጎታቸውን ለመገንዘብ፣ በየጊዜው የተለያዩ ጥናቶችና ዳሰሳዎች እንደሚያካሂድ ጠቁሞ ግኝቶችንም በሚያቀርባቸው ዝግጅቶች ላይ እንዲንፀባረቁ ይደረጋል ብሏል፡፡
በስርጭት ላይ በቆየበት የስድስት ወር ጊዜያት ውስጥ ጥሩ አቀባበል ማግኘቱን የጠቀሰው ቃና.፤ የፌስ ቡክ ተከታዮቹ ከ1 ሚሊዮን በላይ መድረሳቸውን አስታውቋል፡፡ በቅርቡ በቤል ካሽ የተካሄደ በ 5000 ሰዎች ላይ የተደረገ አገር አቀፍ የስልክ መጠይቅ፤ ከሶስት ተጠያቂዎች ውስጥ አንዱ የቃና ቴሌቪዥን ዝግጅቶችን ከሰኞ እስከ አርብ በየቀኑ እንደሚያዩ አመልክቷል፡፡
“ቃና ቴሌቪዥን በሕብረተሰቡ ዘንድ ያለው አቀባበል አበረታችና ከጠበቅነው በላይ ነው። ወደፊትም  የመዝናኛ አማራጭ የሆኑ አዝናኝና አሳታፊ ዝግጅቶችን ለማቅረብ የተመልካቾቻችንን ፍላጎት ማጥናት እንቀጥላለን” ብለዋል፤ የቃና ቴሌቪዥን የኮሙኒኬሽን እና ማርኬቲንግ ዳይሬክተር፡፡  
ቃና ቴሌቪዥንና የዝግጅት አጋሩ ቢ ሚዲያ በቅርቡ ይፋ የሚሆኑ ተጨማሪ ወጥ ስራዎችን እያዘጋጁ እንደሚገኙም ለማወቅ ተችሏል፡፡