Administrator

Administrator

 ሙሴቪኒ በበኩላቸው፤ ሚስቶቻቸውን የሚደበድቡ ወንዶችን አውግዘዋል

     የኡጋንዳ ርዕሰ መዲና ካምፓላ የካቶሊክ ሊቀ ጳጳስ ኪዚቶ ሉዋንግዋ፤የአገሪቱ ሴቶች በወንዶች ላይ ድብደባ መፈጸማቸውን እንዲያቆሙ መጠየቃቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ሚፒንጊ በተባለቺው የአገሪቱ አውራጃ ከሚቀርቡ አስር የቤት ውስጥ ጥቃት አቤቱታዎች መካከል ግማሹ፣ በሚስቶቻቸው የተደበደቡ ባሎች ጉዳይ መሆኑን የአገሪቱ ፖሊስ ሪፖርት ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ነው ጳጳሱ፣”ሴቶች ወንዶችን መደብደብ ያቁሙ” ሲሉ መልዕክት ያስተላለፉት ብሏል - ዴይሊ ሞኒተር፡፡ ጳጳሱ አክለውም፣”ወንዶች የቤተሰብ መሪ (ሃላፊ) እንደሆኑ አምነው መቀበል አለባቸው፤ ባሎቻቸውን መውደድና ማክበርም ይጠበቅባቸዋል” ሲሉ መናገራቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በአንጻሩ የዩጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩሪ ሙሴቬኒ ጾታዊ ጥቃትን ለመከላከል የሚያስችል አዲስ ዘመቻ መጀመራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤መንግስታቸው ሚስቶቻቸውን የሚደበድቡ ባሎችን እንደሚያወግዝ ማስታወቃቸውን አመልክቷል፡፡

 - ከ500 በላይ በሚሆኑ ኩባንያዎች የባለቤትነት ድርሻ አላቸው
       - ኦባማ ባለቤታቸው ለፕሬዚዳንትነት እንደማትወዳደር አስታወቁ

      ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሙሉ ትኩረታቸውን አገር በመምራት ስራቸው ላይ ለማድረግና የጥቅም ግጭት ስጋትን ለማስወገድ በማሰብ፣ ወደ ዋይት ሃውስ ሲገቡ የንግድ ስራቸውን ሙሉ ለሙሉ እንደሚያቆሙ ባለፈው ረቡዕ ማስታወቃቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
“ሙሉ ትኩረቴን አገሪቱን ለመምራትና አሜሪካን እንደገና ታላቅ አገር ለማድረግ ስል ግዙፉን የቢዝነስ ስራዬን ሙሉ ለሙሉ አቋርጣለሁ፡፡ እርግጥ ነው ፕሬዚዳንት ሆኜ ቢዝነስ እንዳልሰራ የሚከለክለኝ ህግ የለም፤ነገር ግን  በንግድ ስራዬና በስልጣኔ መካከል የጥቅም ግጭት እንዳይኖር ማድረግ እንዳለብኝ ይሰማኛል” ብለዋል፤ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ በትዊተር ገጻቸው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፡፡
አገር የመምራቱ ተልዕኮ የበለጠ ዋጋ አለው ያሉት ትራምፕ፣ ከተሰማሩባቸው በርካታ የቢዝነስ መስኮች ሙሉ ለሙሉ መውጣት የሚያስችሏቸው ህጋዊ ሰነዶች እየተዘጋጁ እንደሚገኙና ጉዳዩን በተመለከተ በቅርቡ ይፋዊ መግለጫ እንደሚሰጡም ተናግረዋል፡፡ ትራምፕ ከዚህ ቀደምም የቢዝነስ ስራቸውን የመምራት ሃላፊነቱን ለሶስቱ ልጆቻቸው ዶናልድ ጄአር፣ ኤሪክ እና ኢቫንካ እንደሚያስረክቡ ተናግረው እንደነበር ዘገባው አስታውሷል፡፡ ዶናልድ ትራምፕ ከሚታወቁበት ትርፋማ የሪልእስቴት ኢንቨስትመንታቸው በተጨማሪ፣ በአሜሪካና በተለያዩ የአለማችን አገራት በአያሌ የንግድ ዘርፎች ውስጥ የተሰማሩ ሲሆን ከ500 በላይ በሚሆኑ ታላላቅ ኩባንያዎችም የባለቤትነት ድርሻ እንዳላቸውም ይታወቃል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ በዲሞክራቷ ዕጩ ሄላሪ ክሊንተን ሽንፈት የተናደዱ አሜሪካውያን ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ ከአራት አመታት በኋላ በሚደረገው ምርጫ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ በፕሬዚዳንትነት እንዲወዳደሩ ዘመቻ መጀመራቸው የሚታወስ ሲሆን ባለቤታቸው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግን ሚሼል ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት እንደማይወዳደሩ አስታውቀዋል፡፡ ኦባማ ከሮሊንግ ስቶን መጽሄት አዘጋጅ ጃን ዌነር ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ፣ ባለቤታቸው ሚሼል ፖለቲከኛ የመሆን ፍላጎት እንደሌላቸው በመጥቀስ፣ በፍጹም ለፕሬዚዳንትነት አትወዳደርም ማለታቸውን አሶሼትድ ፕሬስ መጽሄቱን ጠቅሶ ባለፈው ረቡዕ ዘግቧል፡፡

 በሰከንድ 130 ኳድሪሊዮን ስሌቶችን የመስራት አቅም አለው ተብሏል
       የጃፓን ኮምፒውተር ሳይንስ ባለሙያዎች በዓለማችን በፍጥነቱ አቻ አይገኝለትም የተባለውንና በአንድ ሰከንድ 130 ኳድሪሊዮን ስሌቶችን የመስራት አቅም ያለውን እጅግ ፈጣን ኮምፒውተር ለመስራት ማቀዳቸው ተዘግቧል፡፡
139 ሚሊዮን ፓውንድ ወጪ ይደረግበታል የተባለውና ስራው በመጪው የፈረንጆች አመት 2017 ይጀመራል ተብሎ የሚጠበቀው ይህ ፈጣን ኮምፒውተር፤አገሪቱ ያለ አሽከርካሪ የሚንቀሳቀሱ መኪኖችንና ሮቦቶችን በአዲስ ፈር ቀዳጅ ፈጠራ ለመስራት የያዘቺውን ዕቅድ የሚያግዝ ነው መባሉን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ናሽናል ኢንስቲቲዩት ኦፍ አድቫንስድ ኢንደስትሪያል ሳይንስ ኤንድ ቴክኖሎጂ በአገሪቱ ተቋም የሚተገበረው የፈጣን ኮምፒውተር ፕሮጀክቱ፣ የጃፓን መንግስት አገሪቱን ብቃት ያላቸው ማሽነሪዎችን በማምረት ረገድ አለማቀፍ መሪነቱን ከያዙት ደቡብ ኮርያና ቻይና ጋር ተወዳዳሪ ለማድረግ የያዘው እቅድ አካል መሆኑንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የጃፓኑ ኮምፒውተር በስራ ላይ ሲውል በአሁኑ ወቅት የአለማችን ፈጣን ኮምፒውተር የሆነውን የቻይናውን “ሰንዌይ ቲያሁላይት” በመተካት የቀዳሚነቱን ስፍራ ይይዛል ተብሏል፡፡

 500 ሺ ያህል ህዝብ በጦርነት አገሩን ጥሎ ተሰዷል
       የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በእርስ በእርስ ግጭት ከምትታመሰዋ የማእከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ አጠቃላይ የህዝብ ቁጥር ግማሽ ያህሉን የሚሸፍነውና ከ2 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው የአገሪቱ ህዝብ የሰብአዊ እርዳታ እንደሚያስፈልገው አስታወቀ፡፡ አገሪቱን ከ3 አመታት በፊት ከገባችበት የእርስ በእርስ ግጭት ለማውጣትና ወደ መረጋጋት ለመመለስ የሚደረገው ጥረት የተሻለ ለውጥ ቢመዘገብበትም፣ ባለፈው መስከረም ወር በተፋላሚ ሃይሎች መካከል ዳግም ግጭት መቀስቀሱን ተከትሎ የሰብዓዊ ቀውሱ መባባሱንና የእርዳታ ፍላጎቱ መጨመሩን የተመድ የሰብዓዊ ጉዳይ ትብብር ቢሮ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ በአገሪቱ በሚንቀሳቀሱ የሰብዓዊ ድርጅቶች ላይ ሳይቀር ጥቃት እየተፈጸመ መሆኑ፣ ለዜጎች እርዳታ እንዳይደርስ እንቅፋት ጥሯል ያለው ዘገባው፤ የአገሪቱን የ2017 የሰብአዊ እርዳታ ፍላጎት ለማሟላት 400 ሚሊዮን ዶላር  ገንዘብ እንደሚያስፈልግ መገለጹንም ጠቁሟል፡፡
በአገሪቱ ለሶስት አመታት በዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ 400 ሺህ ያህል ዜጎች በአገር ውስጥ ሲፈናቀሉ፣ ሌሎች ግማሽ ሚሊዮን ያህል ዜጎች ደግሞ ወደ ጎረቤት አገራት ቻድ፣ ካሜሩንና ኮንጎ መሰደዳቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 ኮሙኒስቱ አብዮተኛ ፊደል ካስትሮ ኩባን ለአምስት አሰርት ዓመታት የገዙ አምባገነን  መሪ ሲሆኑ ከታላቋ ብሪቴይን ንግስት ኤልዛቤትና ከታይላንዱ ንጉስ ቀጥሎ ለረዥም ጊዜ በስልጣን ላይ የቆዩ የዓለማችን ሦስተኛው መሪ ነበሩ፡፡ በከፍተኛ ህመም አስገዳጅነት የዛሬ 10 ዓመት ሥልጣናቸውን ለወንድማቸው ያስረከቡት ካስትሮ፤ ባለፈው አርብ በ90 ዓመታቸው ማለፋቸው ይታወቃል፡፡  
ከ40 ዓመት በላይ የግድያ ሙከራዎች፣ ወረራና የኢኮኖሚ ማዕቀብ የተደረገባቸው ፊደል ካስትሮ፤ ከስልጣን መንበራቸው ንቅንቅ ሳይሉ ዘጠኝ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ተፈራርቀዋል - ከአይዘንአወር እስከ ክሊንተን፡፡
ፊደል ካስትሮ በዓለም ረዥሙን ንግግር በማድረግ ክብረወሰን ይዘዋል፡፡ እ.ኤ.አ ሴፕተምበር 26 ቀን 1960 በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ለ4 ሰዓት ከ29 ደቂቃ ንግግር አደርገዋል። በዚህም ረዥም ንግግራቸው የዓለም ድንቃ ድንቅ ክስተቶችን  በሚመዘግበው “ጊነስ ቡክ ኦፍ ሪከርድስ” ስማቸው ሰፍሯል፡፡ በእርግጥ ካስትሮ በአገራቸው ኩባ ከዚህም የላቀ ክብረወሰን አላቸው፡፡ በ1986 ዓ.ም በሃቫና ሦስተኛው የኮሙኒስት ፓርቲ ኮንግረስ ሲካሄድ ለ7 ሰዓታት ከ10 ደቂቃዎች ያህል ንግግር አድርገዋል፡፡  
ፊደል ካስትሮ ከአሜሪካ ጋር ግንኙነት የጀመሩት ገና በለጋ ዕድሜያቸው ነበር ማለት ይቻላል። የ12 ዓመቱ ታዳጊ ካስትሮ በወቅቱ ለሁለተኛ ጊዜ ለተመረጡት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት በፃፈው ደብዳቤ፤በድጋሚ በመመረጣቸው ደስታውን ገልጾ፣የ10 ዶላር ኖት እንዲልኩለት ጠይቆ ነበር - ‹‹የ10 ዶላር ኖት ከዚህ ቀደም አይቼ አላውቅም›› በማለት፡፡
ደቡብ አፍሪካ ከዘረኛው የአፓርታይድ አገዛዝ ለመላቀቅ ያደረገችውን የነፃነት ትግል በአጋርነት የደገፉት ፊደል ካስትሮ፣ከኔልሰን ማንዴላ ጋር አንድ መፅሃፍ በትብብር ጽፈዋል፡፡  ርዕሱም፡- ‹‹HOW FAR WE SLAVES HAVE COME!›› ይሰኛል፡፡
ካስትሮ ከብዙዎቹ አምባገነን መንግስታት በተለየ በኩባ በስማቸው የተሰየሙ መንገዶች፣ ህንፃዎች ወይም ሰፈሮች የሉም፡፡ ይሄን ያደረጉትም አምልኮተ-ሰብዕ ለመፍጠር ባለመፈለጋቸው ነው ይባላል። ህልፈታቸውን ተከትሎ በኩባ ለ9 ቀናት ብሄራዊ ሀዘን የታወጀላቸው ካስትሮ፤ አሁን ከሞታቸው በኋላ መንገድ ወይም አደባባይ በስማቸው ሊሰየምላቸው እንደሚችል ተነግሯል።  
ከሀብታም ቤተሰብ እንደተወለዱ የሚነገርላቸው ካስትሮ፤ በስልጣን ላይ ሳሉ እዚህ ግባ በማይባል ዝቅተኛ ደሞዝ እንደሚተዳደሩ በመግለጽ በድህነት የሚማቅቅ ህዝባቸውን ሲያሞኙ ኖረዋል፡፡ እውነታው ግን ከድህነት ጋር የማይተዋወቁ፣ የቅንጦት ህይወት ያጣጣሙ ሚሊየነር መሆናቸው ነው፡፡ ሁነኛ የመረጃ ምንጮች እንደሚጠቁሙት፤ ጠቅላላ የሃብታቸው መጠን 900 ሚ.ዶላር ነው፡፡ በዚህም ሃብታቸው የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶችን እነ ቢል ክሊንተን፣ ባራክ ኦባማና ጆርጅ ቡሽን ይበልጣሉ፡፡
የኩባ የስለላና ደህንነት ቢሮ እንደሚለው፤ ፊደል ካስትሮ በስልጣን ዘመናቸው ከ600 በላይ የግድያ ሙከራ በአሜሪካው የስለላ ድርጅት ሲአይኤ ቢደረግባቸውም ከሞት  ተርፈው ለግማሽ ክ/ዘመን ገደማ ኮሙኒስት አገራቸውን ገዝተዋል። ካስትሮ ከሞት ጋር ድብብቆሽ መጫወት የጀመሩት ገና በወጣትነት የአብዮተኝነት ዘመናቸው ሲሆን በወቅቱ ሁለት ጊዜ ሞተዋል ተብሎ በኩባ ፕሬሶች ተዘግቦ ነበር። “ከግድያ ሙከራ መትረፍ የኦሎምፒክ ውድድር ቢሆን ኖሮ የወርቅ ሜዳልያ አሸናፊ እሆን ነበር” በሚለው ዝነኛ ንግግራቸው የሚታወቁት ካስትሮ፤የማታ ማታ በሰው እጅ ሳይሆን በተፈጥሮ እርጅና ህይወታቸው አልፏል። ሲአይኤ የኩባን ፕሬዚዳንት ለመግደል ያልፈነቀለው ድንጋይ የለም ይላሉ - መረጃዎች፡፡ እንደ ነፍሳቸው የሚወዱትን ሲጋር ከመመረዝ እስከ በአልሞ ተኳሽ ማስገደል እንዲሁም በሚወዱት የቸኮሌት ሚልክሼክ ውስጥ የተመረዘ ክኒን ከመጨመር እስከ ጫማቸውን በመርዘኛ ኬሚካል መበከል ድረስ... እና ሌሎችም የግድያ ሙከራዎች ቢደረግባቸውም አንዱም ለውጤት አልበቃም፡፡ 

  የሶማሌ ክልል ጉዞ - ከ ጉምራ ዙምራ
     (ክፍል- 2)
“አንድ ቀን  ስራ በዛብኝና ጫት ሳልቅም ውዬ ገብቼ ተኛሁ፡፡ እንደፈራሁት ሌሊት ዱካኮች መጥተው ሲጫወቱብኝ አደሩ”
“ምን አደረጉህ?”
“ሦስት ሆነው መጡና ልብስህን አውልቅ አሉኝ”
“እሺ ከዚያስ!”
“ሁለቱ እግሬን ወደ ላይ ይዘው ጭንቅላቴን ወደ መሬት ዘቀዘቁትና---የሶማሌ ጊርጊራ ታውቃለህ?”
“አዎ አውቃለሁ”
“ጊርጊራ ሙሉ ፍም ሆኖ፣ ትርክክ ብሎ የበሰለ የሺሻ እሳት ይዘው መጡና፣ በመቆንጠጫ እያነሱ በቂጤ ይከቱብኝ ጀመረ፤ ኡኡኡ እያልኩ ብጮህ ሊለቁኝ ነው፤ሲያሰቃዩኝ አደሩ.....” (ሳቅ)
***
በክፍል አንዱ የጉዞ ማስታወሻ፣ በወዳጃችን አብዱልአዚዝ ቤት እየተጫወትን እያለ ነበር ያቆምነው፡፡ እንቀጥል፡፡ አብዱል አዚዝ ምስራቅ ሓረርጌ በምትገኘው በጉርሱም ከተማ ከስራ ባልደረባዬ ቤተሰቦች ጋር በጉርብትና ያደገ ልጅ ነው፡፡ ጉርሱም ከጅግጅጋ ከተማ ጋር የምትዋሰነው የምስራቅ ሐረርጌ ዞን የመጨረሻዋ ከተማ ናት። ስለ ጉርሱም ከተማ የስራ ባልደረቦቼ ከነገሩኝ ውጭ አፈንዲ ሙተቂ የተባለው ጸሃፊ፤ “ኡመተ ፈናን ኡመተ ቀሽቲ ዲሬ ዳዋ” በሚለው መፅሃፉ ላይ እንዲህ እያለ ያነሳሳታል፡-
“ከሐረርጌ ከተሞች መካከል በጣም የሚበዙት ከመቶ ዓመት  የበለጠ እድሜ የላቸውም፡፡ ከጥንት ዘመናት ጀምሮ ለክፍለ ሃገሩ ህዝብ የንግድ፣ የትምህርትና የባህል ማእከል ሆና ስታገለግል የቆየችው ሐረር ናት፡፡ ከሐረር በመለጠቅ እድሜ ጠገብ ከተማ መሆኗ የሚነገርላት ደግሞ ጉርሱም ናት፤ “ፉኛን ቢራ”  ትባላለች በኦሮምኛ፡፡ “ከአፍንጫው አጠገብ” እንደ ማለት ነው፡፡ ከተማዋ ስያሜውን ያገኘችው ከታዋቂው “የቁንድዶ ተራራ” ጥግ የምትገኝ በመሆኗ ነው፡፡ ይህን ተራራ ከተማዋ ካለችበት ተኹኖ ሲታይ የሰው አፍንጫ የመሰለ ቅርጽ አለው፡፡ ለዚህም ነው ከግርጌው ያለችው ከተማ “ፉኛን ቢራ” (ከአፍንጫው አጠገብ ያለችው ከተማ) ተብላ የተጠራችው፡፡”
ጉርሱም የአውራጃ ከተማ በነበረች ጊዜ በወቅቱ የጃንሆይ ተወካይ አስተዳዳሪ የነበሩት መኳንንት፤ “ይህ ከተማ ሴቱም፣ ጥብሱም፣ ጉርሱም (ጉርሻው) ጣፋጭ ነው” አሉ ይባላል፡፡ ጉርሱም ቃሉ “ከጉርሻ” ተገኘ እንደ ማለት ነው፡፡ ይሔኛው እንግዲህ ባልደረቦቼ ስለ ከተማዋ ስያሜ ያሉት ነው፡፡
ታዲያ እነ አብዱልአዚዝ አብረው ሲያድጉ ወላጆቻቸው በቤቶቹ መሃከል ያለው አጥር እንዲፈርስ አድርገው፤ የአንዱ ቤት ልጅ ወደዚያኛው ቤት እየገባ የሚበላበት፣ የሚጫወትበት፤ የአንደኛው ቤት ወላጅ የዚያኛውን ቤት ልጅ ልክ እንደ ልጁ የሚመክርበት የሚቆጣጠርበት ዘመን ነበር ይላሉ- ሁለቱም ስለ ልጅነት ጊዜ ትዝታዎቻቸው መለስ ብለው ሲያወሩ፡፡
“የእነ አብዱልአዚዝ እናት ከሞተች በኋላ የእኔ እናት ነበረች እኛ የምንበላውን ለእነሱም እያበላች ያሳደገችን” አለኝ ባልደረባዬ፡፡ እውነትም የሚያስቀና የልጅነት ታሪክ ነው ያላቸው፡፡
አብዱል አዚዝ ጨዋታውን ቀጠለ፡፡ አንዱ ሱማሌ ጫት አቆማለሁ ብሎ የደረሰበትን የዱካክ ናዳ ሲናገር፡-
“አንድ ቀን  ስራ በዝቶብኝ ጫት ሳልቅም ዋልኩና ገብቼ ተኛሁ፤ ሌሊት ዱካኮች መጥተው ሲጫወቱብኝ አደሩ”
“ምን አደረጉህ?”
“ሦስት ሆነው መጡና ልብስህን አውልቅ አሉኝ”
“እሺ ከዚያስ!”
“ሁለቱ እግሬን ወደ ላይ ይዘው፣ ጭንቅላቴን ወደ መሬት ዘቀዘቁትና -- የሶማሌ ጊርጊራ ታውቃለህ?”
“አዎ አውቃለሁ”
“በጊርጊራ ሙሉ ፍም ሆኖ ትርክክ ብሎ የበሰለ የሺሻ እሳት ይዘው መጡና እሳቱን በመቆንጠጫ እያነሱ በቂጤ ይከቱብኝ ጀመረ፡፡ ኡኡኡ እያልኩ ብጮህ ሊለቁኝ ነው፡፡ ሲያሰቃዩኝ አደሩ.....” (ሳቅ)
“ሌላ ጊዜ ደግሞ እንዲህ ሆንኩላችሁ”
“ምን ገጠመህ?”
“እንዲሁ ስባዝን ዋልኩና ጫት ሳልቅም ቀኑ መሸ። ዱካክ እንደማያስተኛኝ እያወቅሁ በፍርሃት ገብቼ ተኛሁ”
“እና ዱካኮቹ መጡ?”
“መጡ?! መጡ ብቻ ሊያውም የተሳለ መጥረብያ ይዘው ነው እንጂ”
“እና ምን አደረጉህ?”
“አንዱ መጣና በዛ መጥረቢያ ጭንቅላቴን ቷ! አድርጎ ከፈተውና አንድ ፈረሱላ ሙሉ በርበሬ በአናቴ ጨመረና ሁለቱን ጆሮዎቼን ሲጠመዝዛቸው እንደ ወፍጮ ታታታታ እያለ ሞተሩ ተነሳ”
“ከዛስ? በናትህ የሚያዝናና ገጠመኝ ነው”
“ከዛማ በአፍና በአፍንጫዬ የተፈጨ የበርበሬ ዱቄት ይንቦለቦል ጀመረ፡፡ ኡኡኡ... ብዬ ብጮህ ማን ሊሰማኝ፡፡ እንደምንም ተፈጭቶ አለቀና እፎይ ተገላገልኩ ብዬ ስል--”ገና ነው ቁጭ በል!!”  አለኝ የዱካኮች አለቃ ጦሩን ይዞ --”
“ምን ቀረ ደግሞ?”  
“ሽርክት ነው እና አንድ ዙር መፈጨት አለበት” ብሎ ድጋሚ ሽርክቱን በርበሬ በአናቴ ጨመረብኝ። ወንድሜ ይሄ ሁሉ መዘዝ ከሚመመጣብኝ እንደምንም ቀዳዳ እየፈለኩ ብቅም ይሻለኛል” ብሎ እንደ አጫወተው ነገረን።
የአብዱልአዚዝ ጨዋታው አያልቅም፡፡ ነገር ግን ምሽቱ እየተጋመሰ መጣና መተኛት ግድ ሆነብን። ስለ ነገ ስራችን መቃናት ጸሎት ቢጤ አድርሼ ተኛሁ። በማግስቱ በጥዋት ገስግሰን ቢሮ ስንደርስ አንድም ሰራተኛ የለም፡፡
“ስራ የለም እንዴ?” ዘበኛውን ጠየቅን፡፡
“ሁሉም ሰራተኛ ፕሬዝዳንቱ ጽ/ቤት በአስቸኳይ እንዲገኙ ትላንት በሜሴጅ ስለተነገረ ሁሉም ወደዚያው ሄደዋል” መለሰ ጥበቃው፡፡
“እና ስንት ሰዓት ይገባሉ?”
“ዛሬ አርብም ስለሆነ ከሰዓት በኋላ ብትሞክር ይሻላል”
በዚህ መሃል ትላንት አግኝተነው የነበረ ኤክስፐርት ሲበር መጣና፤ “ቢሮ ኃላፊዋን ማግኘት ከፈለጋችሁ የፕሬዝደንቱ ስብሰባ 4፡00 ሰዓት ስለሚጀምር አብረን እንሂድና እኔ ላገናኛችሁ” አለን።
“ጥሩ ግባና እንሂድ”
“ስንት ወረዳ ላይ ነው የምትሄዱት?” በጉዞ ላይ ጠየቀን፡፡
“18 ወረዳዎች ላይ እንደርሳለን”
“ምን ያህል ቀን ትቆያላችሁ?”
“ቢያንስ አንድ ወር አካባቢ እንቆያለን”
“ታዲያ እኔ አብሬአችሁ እንድሄድ ለአለቃዬ ንገረውና እኔ የሁለት ወር አበል አሰርቼ አብሬ እሄዳለሁ”
እንደ መደንገጥም እንደ መገረምም እያሰኘኝ፤ “እኛ እንኳን በጀት የለንም፡፡ የምችል አይመስለኝም” አልኩ የአበሉ ክፍያ ጉዳይ ወደ እኛ እንዳይመጣ በመስጋት፡፡
“ስለ በጀት አትጨነቅ፤ የእኛ ቢሮ አለው፤ አንተ ብቻ ለአለቃዬ ንገረው”
እምቢ ብለው ስራዬን ያደናቅፍብኛል ብዬ ሰጋሁና “እሞክራለሁ” አልኩት “አሁን ግን ኃላፊዋን ታገናኘኘለህ አይደል?” ጥያቄ አቀረብኩለት፡፡
“ምንም ሽግር የለም፡፡ ኢናንተ አቲገቡም ውጭ ቲጠብቃላችሁ ኢኔ ኢጠራታለው”
ይህን እያወራን ከከተማው ወጣ ብሎ ከተገነባው የፕሬዝዳንቱ ቤተመንግስትና ጽ/ቤት ደረስንና ወደ በሩ አቅጣጫ ስንመለከት መለዮ ከለበሱ ጥበቃዎች ውጭ በር ላይ ማንም የለም፡፡
“አንተ ገቡ እንዴ? ስንት ሰዓት ነው?” ጠየቀ፡፡
“3፡30 ሆኗል”
“ኡ... ምን ዋጋ አለው ገቡ ማለት ነው” አለ፡፡
“እና ምን ይሻላል?”
“ቆይ እስቲ እዚ ጋር አቁም አለ!!”
“መሃል መንገድ ላይ?” ጠየቅሁ፡፡
ሹፌሩ ዳር ለመያዝ የመኪናውን ፍጥነት ቀዝቀዝ ሲያደርግ በሩን በአየር ላይ ከፍቶ ወርዶ መንገዱን አቋርጦ ወደ በሩ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ እኔም ሹፌሩም በመገረም በክላክስ ብንጠራውም “ሂዱ በቃ!!” ብሎን ነጎደ፡፡ ለካስ ተታለናል፡፡ አጅሬ ታክሲ አድርጎን ኖሯል። እየሳቅንም እየተናደድንም ከሰዓት በኋላ ከመመለስ ውጭ ሌላ አማራጭ ባለመኖሩ ወደ ማረፊያችን ተመለስን፡፡ ጭንቅ ሆነ።
የቢሮአችን የጥናቱ አስተባባሪ “ደብዳቤ አጽፎ ለመውጣት  ከሁለት ቀን በላይ መቆየት የለባችሁም!!” በማለት አጣብቂኝ ውስጥ ከቶናል። ቦታው ላይ በተጨባጭ ያለው ችግር ደግሞ በእኛ ችሎታ ብቻ የሚፈታ አይደለም፡፡ ነገና ከነገ ወዲያ ደግሞ ቅዳሜና እሁድ በመሆኑ ስራ የለም፡፡ ያለችን ብቸኛ ጊዜ አርብ ከሰዓት በኋላ ነች፡፡ ብቸኛ ዋስትናችን፡፡
“ዱአ ያስፈልጋል አሉ የቡድን አጋሮቼ!!” እውነት ሳይሆን አይቀርም አልኩ በልቤ፡፡ ለምሳ እረፍት ወደ አብዱልአዚዝ ቤት ጎራ አልንና 8፡00 ሲሆን ተመልሰን ወደ ቢሮ ሄድን፡፡
“አሁንስ ሀላፊዋ አልገቡም?” ጠየኩ፡፡
“እረ እንደውም”
“ምን ይሻለኛል ወይ ስልካቸውን ስጪኝና ልሞክር?”
“ትችላለህ” ብላ ሞባይል ቁጥሯን ሰጠችኝ። ቁጥሩን መትቼ ብደውል ስልኩ አይመልስም፡፡ ቢቸግረኝ የጽሁፍ መልእክት ላኩላት፡፡
ፈጣሪ ታረቀኝ መሰለኝ ለጸሃፊዋ ደውላ ከሌላ ባለሙያ ጋር እንድገናኝ አድርጋ ደብዳቤውን አስጨርሼ ወጣሁ፡፡ እፎይይይ.... አልኩ።
(ይቀጥላል)

Monday, 05 December 2016 08:58

የፀሐፍት ጥግ

   (ስለ ንባብ)
ጥቂት ገንዘብ ሳገኝ መፃህፍት እገዛለሁ፡፡ ከተረፈኝ ምግብና ልብሶች እገዛለሁ፡፡
ኢራስመስ  
መፅሃፍ በእጃችሁ የያዛችሁት ህልም ነው፡፡
ኔይል ጌይማን  
ከፀሃፊው ጋር ለግማሽ ሰዓት የማውራት ዕድል ባገኝ፣ መፅሃፉን ጨርሶ አላነብም ነበር።
ውድሮው ዊልሰን  
ህይወትን እንደ ጥሩ መፅሃፍ ነው የማስበው። የበለጠ ዘልቃችሁ በገባችሁ ቁጥር የበለጠ ትርጉም መስጠት ይጀምራል፡፡
ሃሮልድ ኩሽነር
ሁሉም ሰው የሚያነበውን መፃህፍት ብቻ የምታነቡ ከሆነ፣ ሁሉም ሰው የሚያስበውን ብቻ ነው የምታስቡት፡፡
ሃሩኪ ሙራካሚ
ጥሩ ልብወለድ ስለጀግና ገፀ ባህሪው እውነታው ይነግረናል፤ መጥፎ ልብወለድ ግን ስለደራሲው እውነታውን ይነግረናል፡፡
ጊልበርት ኬ.ቼስተርን
መፅሃፍ ማንበብ ለራስህ ደግመህ እንደመፃፍ ነው።
አንጌላ ካርተር
አንባቢዎችን በሁለት መደቦች እከፍላቸዋለሁ፡- ለማስታወስ የሚያነቡና ለመርሳት የሚያነቡ፡፡
ዊሊያም ሊዮን ፌልኝስ
የማታውቀው ነገር ታላቅ መፅሃፍ ይወጣዋል።
ሲድኒ ስሚዝ
መፃህፍትን ከማቃጠል የከፉ ወንጀሎች አሉ። ከእነሱም አንዱ አለማንበብ ነው፡፡
ጆሴፍ ብሮድስኪ
ዙሪያዬን በመፃህፍት ካልተከበብኩ በቀር እንቅልፍ አልተኛም፡፡
ጆርጅ ሉዊስ ቦርጌስ
መፅሃፍ ምናብን የማቀጣጠያ መሳሪያ ነው፡፡
አላን ቤኔት
ጥሩ መፅሃፍ መጨረሻ የለውም፡፡
አር.ዲ.ኩሚንግ

 · “በመናገር ነፃነት ላይ የተወሰደ እርምጃ ነው” አምነስቲ
        · “የታሰሩት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በመጣሳቸው ነው” መንግስት
               
     የአንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር መረራ ጉዲና መታሰር የዓለም አቀፍ ሚዲያዎችንና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን ትኩረት የሳበ ሲሆን አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የታዋቂው ፖለቲከኛ እስር  በእጅጉ ያሳስበኛል ብሏል፡፡ ዶ/ር መረራ አመራር አባል የሆኑበት መድረክ በበኩሉ፤ ጠንካራ መሪውን በእስር ማጣቱ የአመራር ክፍተት እንደሚፈጥርበት ጠቁሟል። ከ20 ዓመታት በላይ በተቃዋሚ ፓርቲ አመራርነት የዘለቁት የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሩ ዶ/ር መረራ፤ የታሰሩት “ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት መፍጠር ክልክል ነው” የሚለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አንቀፅ በመተላለፋቸው ነው ብሏል - መንግስት፡፡ የመድረክ ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በሰጡት አስተያየት፤ ዶ/ር መረራ በመድረክ ውስጥ የድርጅት ጉዳይን በኃላፊነት ይከታተሉ እንደነበር ጠቅሰው፤ መታሰራቸው በድርጅቱ ስራ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖና የአመራር ክፍተት እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡
“ዶ/ር መረራ በሌለበት የተሟላ ድርጅታዊ ስራ ልንሰራ አንችልም” ያሉት ፕ/ር በየነ መድረክ በጉዳዩ ላይ ውይይት አድርጎ በቅርቡ የአቋም መግለጫ እንደሚያወጣ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹እስካሁን ድረስ ወጥ አቋም ያለው ፖለቲከኛ አልገጠመኝም፤ ብዙዎቹ ተለዋዋጭ አቋም ነው ያላቸው›› ያሉት ፕ/ር፤ “መረራ ግን ወጥ አቋም በመያዝ ጠንካራ የፖለቲካ ፅናት ያለው መሪ ነው” ሲሉ አድናቆታቸውን ገልፀዋል፡፡
የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኤፌኮ) ሊቀመንበር፤ እንዲሁም የመድረክ ምክትል ሊቀመንበርና የድርጅት ጉዳይ ኃላፊው ዶ/ር መረራ፤ መታሰራቸው በእጅጉ ያሳስበኛል ያለው አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ ‹‹እስሩ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅና የመናገር መብት ላይ የተቃጣ እርምጃ ነው” ሲል ኮንኗል፡፡
በኢትዮጵያ ይፈፀማል ስለሚባለው የሰብአዊ መብት በቤልጂየም ብራሰልስ ተገኝተው ለአውሮፓ ህብረት ፓርላማ እማኝነታቸውን እንዲሰጡ የፓርላማው አባል በሆኑት እና ጎሜዝ እንደተጋበዙ የተነገረላቸው ዶ/ር መረራ፤ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ወደ አውሮፓ አምርተው በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ የፖለቲካ ቀውስ ማብራሪያ መስጠታቸው ተዘግቧል፡፡
ባለፈው ረቡዕ ከብራሰልስ ወደ አገራቸው የተመለሱ መረራ፤ የዚያኑ ዕለት ምሽት 2 ሰዓት ገደማ አሸዋ ሜዳ በሚባለው አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው እንዳሉ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የኦፌኮ አመራሮች ተናግረዋል፡፡ ከእሳቸው ጋር ይኖሩ የነበሩ ሁለት ወጣቶችም መታሰራቸውን ለማወቅ ተችሏል።
ዶ/ር መረራ በተጋበዙበት በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ  በ“አሸባሪነት” የተፈረጀው የ“ግንቦት 7” መሪ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና  በየሪዮ ኦሎምፒክ የማራቶን ውድድር አትሌት ፈይሳ ሌሊሳም ተጋብዘው ነበር ተብሏል፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አንቀፅ 1 ቁጥር 2 ስር የተመለከተውን ክልከላ ጥሰው ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት በማድረጋቸው መሆኑን የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬተሪያትን ጠቅሶ ኢቢሲ ከትላንት በስቲያ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ዶ/ር መረራ፤ በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ስለኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ምስክርነታቸው እንደሰጡ ጋብዘዋቸዋል የተባሉት አና ጎሜዝ በበኩላቸው፤ የፖለቲከኛው መታሰር ቢያስደነግጠኝም አላስገረመኝም ብለዋል፡፡ መረራ መታሰራቸው ተገቢ አለመሆኑን ከትላንት በስቲያ ለቪኦኤ የተናገሩት ጎሜዝ፤ እስካሁን ህብረቱ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የመለሳለስ አካሄድ ሲከተል መቆየቱን ጠቅሰው ጠንካራ እርምጃ እንዲወስድ የሚያሳስብ ደብዳቤ ለህብረቱ ኮሚሽን መፃፋቸውን አስታውቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ የህብረቱና የኢትዮጵያ ግንኙነት ጠንካራ መሰረት ያለው መሆኑን ገልፆ ግንኙነቱ ይሻክራል የሚል ስጋት እንደሌለው ጠቁሟል፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ ትላንት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤
‹‹ዶ/ር መረራ ጉዲና ለእስር የተዳረጉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ጥሰው በመገኘታቸው ህግ ለማስከበር ሲባል ነው›› ብለዋል፡፡
በደርግ አገዛዝ ሥርዓቱን በመቃወማቸው መንግስት 8 ዓመታት ያሰራቸው ዶ/ር መረራ፤ በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን ሲታሰሩ የአሁኑ የመጀመሪያቸው ነው ተብሏል፡፡  

የሶማሌ ክልል ጉዞ - ከጉማራ ዙምራ

   ”እንዴት ነው ሶማሌ ክልል? አሁን ሰላም ነው አይደል?” ሁሌም ስጋት የማይለየው ሾፌር ጠየቀ፡፡
”አሁንማ ምን አለ? አገር ተረጋግቷል፡፡ ከአምስት ዓመት በፊት ምእራብ ጎዴ ስሰራ፣ በቀኝ በኩል ወታደር፣ በግራ በኩል ሽፍታ እያጀበኝ ነበር የሰራሁት፡፡”
“አሁንም ሽፍታ አለ እንዴ?”
”የለም አቦ፡፡ አቲፍራ፡፡ ወንድ ልጅ አይፈራም!!”
“እንደው ቤተሰብ ያለው ሰው ይጨነቃል ብዬ ነው” ሹፌሩ መለሰ፡፡
”ቆይ አንተ ስንት ልጆች አሉህ?”
“አንድ ልጅ ነው ያለኝ፡፡”
”ሀይ!! አንድ ልጅ ወልደህ ነው፣ ሃረካት የምታበዛው፡፡ አንድ ልጅ ብቻ ምን ያደርጋል! ጨምረህ ውለድ፡፡ ሚስትህን ውለጂ በላት፡፡ እምቢ ካለች ሌላ ሚስት አግባና ውለድ፡፡ ልጅ ኽይር ነው።”
ከአስራ ሁለቱ ወራት፣ እንደ መስከረም የሚሆንልኝ ተናፋቂ ወር የለም፡፡ ምን ያደርጋል? የዘንድሮውን የመስከረም ፀጋ፣ በቅጡ ሳላጣጥመው ነው፣ ወደ ሶማሌ ክልል ለመሄድ እንድዘጋጅ፣ ከመስሪያ ቤት ማሳሰቢያ የደረሰኝ፡፡ መስከረም 10 ቀን 2009 ዓ.ም፣ ጓዜን ሸክፌ ጉዞ ጀመርኩ፡፡ ምስጋና ለፈጣኑ የክፍያ መንገድ ይሁንና፣ አዳማ ላይ ቁርስ አድርሰን፣ ቡናም ጠጥተን፣ የማይቀሬውን ረጅሙን ጉዞ ተያያዝነው፡፡ እኔም መቋጫ የሌለው የጭንቀት ድር ውስጥ መብሰልሰል ተያያዝኩት፡፡
የሶማሌ ክልል ለረጅም ጊዜ ሰላም ርቆት የቆየ መሆኑ ብቻ አይደለም ያስጨነቀኝ፡፡ ጊዜው ጥሩ አልነበረም፡፡ አገሬው ሁሉ በግጭትና በረብሻ ወሬ ውጥረት ውስጥ የገባበት ጊዜ ነው፡፡ ሁከት እና ብጥብጥን እያሰላሰሉ መጓዝ አስቸጋሪ ነው፡፡
‹‹አሁን በዚህ ሰዓት፣ ሰው ቤቱ አርፎ ቁጭ ይላል እንጂ መንገድ ይወጣል? ‹ይሄኛው መንገድ ተዘጋ፤ እዚህ ከተማ መኪና ተቃጠለ› እየተባለ፣ ሰው ገንዘብ አገኛለሁ ብሎ ከከተማ ሊወጣ ይገባል? ኧረዲያ! ክልፍልፍ ሁኜ ነው እንጂ! … ለዚያውም የቤተሰብ ሃላፊ! …›› በጭንቀት መብሰልሰል፣ ጠብ የሚል ጥቅም እንደሌለው አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ጭንቀትን አውልቆ መጣል አይቻልም፡፡ ለካ በክፉ ቀን ውስጥ ያላለፈ ሰው፣ ድንገት አስቸጋሪ ጊዜ በመጣ ወቅት፣ የሚይዘው የሚጨብጠውን አያውቅም፡፡ እኔም የክፉ ቀን ልምድ የለኝም፡፡ በዚህ የሀሳብ ወንዝ መቀጠል አልችልም፡፡ ልምድ ለማግኘት፣ “ ምነው ክፉ ቀን በሰጠኝ” ብዬ እንደመሳለቅ ይሆንባችኋል፡፡
የሶማሌ ክልል ደግሞ ጭንቀትን የሚያረጋጋ አልሆነልኝም፡፡ ለሩብ ምዕተ ዓመት መንግስት አልባ ሆና ከምትተራመሰው አገር ከሶማሊያ ጋር የተጎራበተ ክልል ነው፡፡ ከድንበር ባሻገር፣ በሞቃዲሾ፣ በባይዶዋና በመሳሰሉ የሶማሊያ ከተሞች፣ በአሸባሪዎች ጥቃት  ሰላማዊ ሰዎችና ወታደሮች መገደላቸው፣ … እንደ ዜና አይቆጠርም። የዘወትር ወሬ ነው፡፡ ግን ወሬው ብቻ አይደለም ድንበር ተሻግሮ ወደ ሶማሌ ክልል የሚዘልቀው፡፡ የሽብር ጥቃትና ግድያም፣ አልፎ አልፎ ወደ ሶማሌ ክልል ይሻገራል፡፡ እና አንዳንዶቹ ወረዳዎች ደግሞ የባሰባቸው ናቸው፡፡ “ክልሉ ውስጥ በሚገኙ አንዳንድ ወረዳዎች ውስጥ በእጀባ ልትገቡ ትችላላችሁ፡፡ እጀባ የማታገኙ ከሆነ ግን፣ አሳውቁንና እንዲቀየርላችሁ ይደረጋል” ተብሎ ተነግሮናል፡፡ … እጀባ፣ ወታደር፣ ክላሽ ፣ አስቸጋሪ አቧራማ ጉዞ … እንዲህ የሚረብሹ ሃሳቦች እየተመላለሱብኝ በጭንቀት መናወዜ አልቀረም፡፡ አጥፍቶ ጠፊ በቀበረው ፈንጂ መኪናችን ወደ ሰማይ ተተኩሳ ስትቃጠል .... ወይም አንዱ ሽፍታ በሞርታር ከርቀት ሲያጋየን …  በእዝነ ህሊና ማሰብ ይሰቀጥጣል፡፡  
ታዲያ ስሜቴ አንዱን ሀሳብ ሳይቋጭ፣ ወደ ሌላው ፈተና እየከተተኝ እንደ ፔንዱለም በሃሳብ ስወዛወዝ፣ “አለቃ ምነው ትካዜ አበዛህ”? የሚል ድምፅ አባነነኝ፡፡ አንዱ ባልደረባችን ነው፡፡ “አይ … መቼም የሚታሰብ አይጠፋ” ብዬ መለስኩ፡፡ ረጅም መንገድ፣ ያለጨዋታ አይገፋምና፣ አንዴ ሞቅ አንዴ ቀዝቀዝ እያልን ወደጨዋታ መግባታችን አልቀረም። ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ፣ ስፖርት፣ ፊልም፣ የቲቪ ወይም የሬድዮ ቻናል እያነሳን እናወራለን። ጭውውታችን ታዲያ፣ ስለእያንዳንዳችን ተፈጥሮአዊ ዝንባሌ፣ ፍላጎት፣ የፖለቲካ አቋም አንዳንዴም የእውቀት መጠን ለማወቅ የሚያስችል ሁናቴ መፈጠር ጀምሯል፡፡
የስምጥ ሸለቆ ሙቀት እና ወበቁ እየበረታ ሲመጣ፣ ሸሚዝ መክፈት፣ ቀበቶ መፍታት መቁነጥነጥ አብዝተናል፡፡ መተሃራ ከተማ ላይ፣ ቡና ጠጣንና አንዳንዶቹም በርጫቸውን ይዘው፣ በዱአ እና በዝየራ ጉዞአችንን ገፋነው፡፡ ወለንጪቲ፣ አዋሽ 7፣ ሜኤሶ፣ እና ሌሎች  ሞቅ ደብዘዝ የሚሉ ከተሞችን ተሻግረን፣ ጭሮ (በጥንት መጠሪያዋ አሰበ ተፈሪ) ደረስን፡፡ የምሳ እረፍት አድርገን እንደገና “በጠመዝማዛው …  ሽቅብ ቁልቁለት”... በምእራብ ሃረርጌ ዘወርዋራ መንገድ መጋለብ ጀመርን - ትናንሽ የሃረርጌ ከተሞችን እየገመስን፡፡
ከዚያ ሁሉ የተራራ ሰንሰለት በኋላ፣ ሜዳማ የሶማሌ በረሃዎች ይከሰታሉ ብሎ ማሰብ መቼም አስቸጋሪ ነው፡፡ አየሩና ምድሩ፣ ከቅዝቃዜ ወደ ግለት፣ ከአረንጓዴ ወደ አፈርማ ይቀየራል፡፡
ጅግጅጋ ከተማ የደረስነው በማግስቱ ረፋድ ላይ ነው፡፡ ከሶስት ዓመት በፊት የማውቃት ጅግጅጋ፣ እጅጉን ተቀይራለች፡፡ የከተማዋ እድገት ተፋጥኗል። መንገዶች እየተስፋፉ፣ ህንጻዎች እየተገነቡ ነው፡፡ የንግድ እንቅስቃሴው አጃኢብ ያስብላል፡፡ ስራችንን ለመጀመር ወደ ዞን እና ወረዳዎች ከመግባታችን በፊት ታዲያ፣ ከክልሉ መንግስት የትብብር ደብዳቤ መውሰድ ግዴታችን ስለሆነ ወደ ክልሉ ቢሮ ጎራ አልን፡፡ እንደተመኘነው አልቀናንም፡፡
“የቢሮ ሃላፊዋ አስቸኳይ ስብሰባ ላይ ናት” አለችን ጸሃፊዋ፡፡
“ምክትሏስ?” ብለን ስንጠይቅ
“እሱማ፣ አባቱ ሞተው ሃዘን ላይ ነው” ተባልን፡፡
ፍርሃትም ተስፋም ሰንቀን አዳራችንን፣ ወደ አንዱ ባልደረባችን ወዳጅ ደውለን፣ ወደ ቤት ጎራ ብንልስ ብለን ጠየቅነው፡፡ አብዱልአዚዝ ይባላል፡፡ ፈታ የማለት ባህሪ ይታይበታል፡፡
ያለንበት ድረስ መጣ፡፡ “እንዴት ናችሁ አቦ? አማን ናችሁ? … ያ የተኮራረፈ የሚመስለው የአዲስ አበባ ሰው እንዴት ነው አቦ? … ሰው በታክሲ እየሄደ አያወራ፣ አይናገር፣ የሆነ ዝጋታም እኮ ነው። እኔ ይጨንቀኛል፡፡ ሰው ሰው ሆኖ ተፍጥሮ እንዴት አያወራም? ከብት እንኳን በሽታ ሰላም ይባባላል እኮ።”
“እኔ የምልህ አብዱልአዚዝ ሚስት አገባህ አይደል?” ጠየቀ አብሮ አደጉ፡፡
“አዎ! አይሻ ነው ስሟ፡፡ ስታትስቲክስ ነው የጨረሰችው፡፡ ማስተርሷን ደግሞ በዴቨሎፕመንት ኢኮኖሚክስ ከጅግጅጋ ዩንቨርሲቲ አግኝታለች፡፡”
”አሃ ያቺ ባለፈው ስመጣ አብራህ የነበረችው ነች እንዴ?”
”አዎ...አዎ የዛን ቀን እኮ ነው ፍቅር የጀመርነው። ለካ ነበርክ? ወላሂ ጥሩ ሚስት አገኘሁ፡፡ አንተም ገደኛ ነህ አቦ!”
”ስንት ልጆች ወለድክ?”
”ሶስት ወልጃለሁ፡፡ ኢንሻላህ! አሁን ሶስተኛውን ልጃችንን በኦብራሲዮን ወልዳ ቆይ ላገግም አለቺኝ፡፡ ልጅ ኸይር ነው፡፡”(ሶማልኛ ቋንቋ ውስጥ “ፐ” ፊደል ያለ አይመስለኝም)
መኖሪያ ቤቱ፤ ጭናቅሰን መውጫ የሚባል አዲስ ሰፈር ላይ ነው፡፡ መኪና ውስጥ ገባንና ጉዞ ወደ ቤቱ ጀመርን፡፡ አልፎ አልፎ ሰፋፊ ቪላዎች ይታያሉ፡፡
”አየኸው ያን ነጭ ቪላ? የክልሉ ጸጥታ ሃላፊ የነበረ ያሰራው ቤት ነው፡፡”
”እውነትክን ነው?”
”አዎ!! ሞኝ ነው እንጂ፣ ሰው ከመንግስት ብር ሰርቆ፣ ጅግጅጋ ከተማ ላይ ቪላ ይሰራል? ወላሂ ይሄ ሰው አይደለም፡፡”
”ምን ሆነ አሁን?”
”አሁንማ አወረዱት እና አሰሩታ፡፡ ሱማሌ ሲፎግር ቤቱን “የህዝብ ክሊኒክ” ብሎታል፡፡ አታየውም? ክሊኒክ እኮ ነው የሚመስለው ”...ሳቅ
መኖሪያ ቤት ገባን፡፡ ቤት ውስጥ … ሶፋ፣ የሳሎን እቃ ጅኒ ቁልቋል ይኖራል ብላችሁ ካሰባችሁ ተሳስታችኋል፡፡ ዙሪያውን አረቢያን መጅሊስ የተነጠፈበት ሰፊ ሳሎን እና ፓወር ፖይንት ግድግዳው ላይ ተደግኗል፡፡ ከጎኑ ቴሌቪዥን ብቻ አለው፡፡ ፓወር ፖይንቱን ስመለከት፣ ዎርክ ሾፕ ወይም ስልጠና የሚሰጥበት አዳራሽ ነገር መሰለኝ፡፡
“ፓወር ፖይንቱን ምን ታደርግበታለህ?”
“እኔ ቴሌቪዥን የማየው በዚህ ነው፡፡”
ሳቅ...
“ምነው ትስቃለህ? እዛ ግብርና ቢሮ ስሰራ፣ የተሰጠኝ ነው፡፡ ወደ ሌላ ቢሮ ሲቀይሩኝ ለቤት ይሆናል ብዬ ይዤው መጣሁ፡፡ እኔ በዚህ  ማየት ለምጄ ቲሌቪዥን ይደብረኛል አቦ!! በተለይ እግር ኳስ ካለ  ይሄን ግድግዳው ላይ ቲለቃለህ፡፡ በቃ ስክሪን ነው፡፡” ... ሳቅ
”ትራስ አምጪ!” አዘዛት ትልቋን ልጁን፡፡
”አረፍ በሉ፡፡ ውሃ አምጡላቸው፡፡ ምሳ እንብላ?”
”እረ እኛ በልተን ነው የመጣነው፡፡”
”ወላሂ በሉ እስኪ?”
”ወላሂ፡፡”
”በቃ ቃሙ እናንተ እኔ ትንሽ ልብላ፡፡”
”ሃዬ!”
”እንዴት ነው ሶማሌ ክልል አሁን ሰላም ነው አይደል?” ሁሌም ስጋት የማይለየው ሾፌር ጠየቀ፡፡
”አሁንማ ምን አለ፡፡ አገር ተረጋግቷል፡፡ እኔ ከአምስት ዓመት በፊት፣ ምእራብ ጎዴ ስሰራ በቀኝ በኩል ወታደር፣ በግራ በኩል ሽፍታ እያጀበኝ ነበር የሰራሁት፡፡”
”እረ ባክህ፡፡ አሁንም ሽፍታ አለ?”
”የለም አቦ አቲፍራ፡፡ ወንድ ልጅ አይፈራም!!”
“እንደው ቤተሰብ ያለው ሰው ይጨነቃል ብዬ ነው፡፡” ሹፌሩ መለሰ፡፡
”ቆይ አንተ ስንት ልጆች አሉህ?”
አንድ ልጅ ነው ያለኝ፡፡”
”ሀይ!! አንድ ልጅ ወልደህ ነው ሃረካት የምታበዛው፡፡ አንድ ልጅ ብቻ ምን ያደርጋል፡፡ ጨምረህ ውለድ፡፡ ሚስትህን ውለጂ በላት፡፡ እምቢ ካለች ሌላ ሚስት አግባና ውለድ፡፡ ልጅ ኽይር ነው።” ሳቅ
(ይቀጥላል)




• አክሱም ቤቲንግ በአዲስ አበባ 7 ቅርንጫፎች ከፍቶ፤ በ60 ዓይነት ውርርዶች ከ100 በላይ ስፖርቶች እያጫወተ ነው፡፡
• በ20 ብር ትኬት ከ1 እስከ 20 ጨዋታዎችን በአክሱም ቤቲንግ መወራረድ ይቻላል ፤ ከፍተኛው ሽልማት እስከ 250ሺ ብር ነው፡፡
• በዓለም ዙርያ እስከ 3 ትሪሊዮን ዶላር የሚንቀሳቀስበት ኢንዱስትሪ ሆኗል፡፡
• በአፍሪካ በ27 አገራት የስፖርት ውርርድ እየተካሄደ ሲሆን የውርርድ ተቋማት ብዛታቸው 2ሺ ይደርሳል፡፡ በደቡብ አፍሪካ፤ ናይጄርያና ኬንያ ተስፋፍቷል፡፡

የስፖርት ውርርድ ሁሉንም ማህበረሰብ ሊያሳትፍ የሚችል በስፖርት ውጤቶች ላይ በመንተራስ የሚካሄድ አዝናኝና ገቢ የሚያስገኝ ጨዋታ ነው፡፡ የውርርድ ተጨዋቾች እና ተሳታፊዎች የስፖርት ውድድሮችን በመመልከት ከሚኖራቸው መዝናናት ባሻገር፤ በተለያዩ የመወራረጃ መስፈርቶች በሚሰጧቸው ግምቶች የገንዘብ ተሸላሚ የሚሆኑበትን እድል ይፈጥርላቸዋል። አወራራጅ ተቋም በተለያዩ የስፖርት ውድድሮች የውርርድ ዝርዝሮችን በመግለፅ እና የሚሸልመውን ገንዘብ በማሳወቅ የሚሰራ ሲሆን አጠቃላይ አካሄዱም በህግና ስርዓት የተመራ ነው፡፡ በስፖርት የተለያዩ ሁኔታዎች በመወራረድ በህጋዊ መንገድ እየተዝናኑ መጫወት፡፡ ለሀገር የገቢ ምንጭ ከመሆኑም በላይ  የስራ እድሎችን የሚፈጥር መስክ ነው፡፡ የስፖርት ውርርዱን በህጋዊ መንገድ መካሄዱ በህብረተሰቡ ዘንድ ህገወጥ በሆነ መንገድ በመወራረድ የሚፈጠሩ አላስፈላጊ ችግሮች ለመከላከልም የሚያግዝ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በህጋዊ መንገድ  የሚካሄዱ የስፖርት ውርርዶች በሌሎች የአፍሪካ  አገራት ባሉበት ደረጃ ላይ አይገኝም። ከ4 ዓመታት በፊት ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ በተባለ ተቋም በፈርቀዳጅነት ቢጀመርም፤ ብዙ የዘለቀ አልነበረም።  ባለፉት 8 ወራት  ግን ህጋዊ ፈቃድ አግኝቶ መስራት በጀመረው አክሱም ቤቲንግ የተባለ የስፖርት ውርርድ ተቋም መስኩ መነቃቃት ጀምሯል፡፡የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር  የስፖርት ውርርድን ለማካሄድ የሚያስችል መመርያ በኢትዮጵያ መንግስት ያፀደቀው ከ5 ዓመታት በፊት ነበር፡፡  ፍቃድ የሚያገኙ ድርጅቶች በህግ ማዕቀፍ ሆነው ውርርዱን እንዲያጫውቱ የሚያደርገው የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር አፈፃፀሙን በመከታታል በመቆጣጠር አብሮ ይሰራል፡፡ የትኛውም ድርጅት፤ ተቋም ወይም ግለሰብ ለስፖርት ውርርድ ህጋዊ ፈቃድን ማግኘት እንደሚችል  የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደሩ ያስታወቀ ሲሆን የሚሰጠው ፍቃድ በየዓመቱ የሚታደስ ነው፡፡
አክሱም ቤቲንግ እና እንቅስቃሴዎቹ
አክሱም ቤቲንግ በ300ሺ ዶላር ካፒታል  የተቋቋመ የስፖርት ውርርድ ተቋም ሲሆን 18 ሰራተኞችን በሂሳብ ሰራተኝነት፤ በሱቆች ማናጀርነት እና በሹፌርነት በመቅጠር የሚያስተዳድር ነው፡፡   በኢትዮጵያ በስፖርት ውርርድ መስክ ከፍተኛ አቅም መኖሩን የተገነዘበው ይህ ተቋም በመስኩ ዘላቂ እቅዶችን በመንደፍ እየሰራ መሆኑን ምክትል ሥ/አስኪያጁ ለስፖርት አድማስ ተናግሯል፡፡ የአክሱም ቤቲንግ ምክትል ሥ/አስኪያጅ፤ የዴቨሎፕመንት እና ሪሰርች ሃላፊ አብርሃም ተክለማርያም ይባላል፡፡ የስፖርት ጋዜጠኛ፤ የእግር ኳስ አሰልጣኝ፤ ቀድሞ በደቡብ አፍሪካ ሱፐርቤቲንግ ከተባለ የስፖርት ውርርድ ተቋም ጋር በመስራት ልምድ ያካበተ ነው፡፡ ለስፖርት ውርርድ ኢትዮጵያ አመቺ መሆኗንም በተለያዩ ማስረጃዎች ማመልከት ይቻላል፡፡ ከ90 ሚሊየን በላይ የህዝብ ብዛት ያለባት ሀገር መሆኗ አንዱ ትልቅ አቅም ነው፡፡ አዲስ አበባ ደግሞ ከተለያዩ የአፍሪካና የዓለም ሀገራት የተውጣጡ ዜጎች መናሀሪያ መሆኗም መስኩን ለማንቀሳቀስ ማመቸቱም ይጠቀሳል፡፡ በአዲስ አበባም ሆነ በሌሎች የክልል ከተሞች የስፖርት ውርርዶች የመዝናኛ አማራጮች መሆን እንዳለባቸው ለስፖርት አድማስ አስተያየት የሰጠው አብርሃም ተክለማርያም፤ የምስራቅ አፍሪካ፤ የአፍሪካን ገበያ ከዚያም አልፎ እስከ ኤስያ አህጉር በመሻገር በስፖርት ውርርድ መስክ ኢትዮጵያ ገበያውን ለመቆጣጠር እንደምትችል በማመን በአክሱም ቤቲንግ እየሰራን ነው ሲል ይናገራል። በአሁኑ ወቅት ከኢትዮጵያ ባሻገር በበርካታ ሀገራት የስፖርት ውርርዶችን እየሰራ የሚገኘው አክሱም ቤቲንግ  በቤለሩስ፣ በሰሜን ኢራቅ፣ በሞልዶቫ፣ በቆጵሮስ፣ በኬንያ፣ በዩጋንዳና በጋና የሚንቀሳቀስ ሲሆን በቀጣይ ወር ደግሞ በታንዛኒያም ቢሮውን የሚከፍት ይሆናል፡፡
ባለፉት 8 ወራት አክሱም ቤቲንግ በኢትዮጵያ የስፖርት ውርርድ ለማስፋፋት ቴክኒካዊ ስራዎችን መሰረት በማስያዝና በማስተዋወቅ ላይ አተኩሮ እየተንቀሳቀሰ ቆይቷል፡፡   ድረ ገፁን በዘመናዊ በዘመናዊ ዲዛይን በተጠቃሚዎቹ በሚመች መልኩ አደራጅቷል። የስፖርት ውርርዶችን ማካሄጃና ውድድሮችን መመልከቻ ስፍራ በዋና መስርያ ቤቱ  22 ከአውራሪስ ሆቴል ፊት ለፊት መክፈቱን ጨምሮ በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች ሰባት ቅርንጫፎች አሉት፡፡ እነዚህ ቅርንጫፎቹ ሳሪስ አዲስ ሰፈር እናት ባንክ ፊትለፊት፤ በጎተራ ኮንደሚኒዬም በሚገኘው ግቢ ላውንጅ እና ስፖርት ባር፤ ወሎ ሰፈር አካባቢ ሚና ህንፃ ላይ በሚገኘው ፍሬንድስ ኤንድ ባር ሬስቶራንት፤ ቦሌ ማተሚያቤት ጀርባ በሚገኘው ፊደል ባርና ሬስቶራንት፤ መስቀል ፍላወር አካባቢ በዋን ሞር ናይት ላውንጅ እንዲሁም አዲስ አበባ ስታድዬም ዙርያ በዛብሎን ትርጉም ቤት ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡ የአክሱም ቤቲንግ  ምክትል ሥ/አስኪያጅ አብርሃም ተክለማርያም ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው፤ በወቅቱ የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ችግር ሳቢያ የነበረ እቅዳቸው ቢስተጓጎልም ከአዲስ አበባም ውጪ በባህርዳር፤ በጎንደር፤ በመቀሌ፤ በአዳማ  እና ሀዋሳ ከተሞች ቅርንጫፎቻቸውን ለመክፈት ፍላጎት አላቸው፡፡
ሰሞኑን 22 አካባቢ ከአውራሪስ ሆቴል ፊት ለፊት ያለውን የአክሱም ቤቲንግ የስፖርት ውርርድ ቤት ጎብኝተን ነበር፡፡ ባለ 45 ኢንች የሆኑ 18 ፍላት ስክሪን ቴሌቪዥኖች አሉ፡፡ የሂሳብ ሰራተኞች በኮምፒዩተሮቻቸው ፈጣን አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ ምቹ የማረፊያ ስፍራዎች ሻይና ቡና በነፃ ነው፡፡ የስፖርት ውድድሮችን በመመልከት ጎን ለጎን ውርርድ የሚካሄድበት ይህ ቤት፤ በእረፍት ቀናቶች በሩ ለሁሉም ክፍት ነው፡፡ የስፖርት ውርርድ ተሳታፊዎች ከጓደኞቻቸው ጋር ገብተው ውድድሮችን በነፃ እየተመለከቱ የስፖርት ውርርዳቸውን እየተጫወቱ ሊስተናገዱበት ይችላሉ፡፡ የአክሱም ቤቲንግ የስፖርት ውርርዶች www.axumbet.com በሚለው ድረገፅ የሚካሄዱ ናቸው፡፡  ከ100 በላይ የስፖርት ውርርዶችን እያጫወቱ ሲሆን እግር ኳስ፣ ቅርጫት ኳስ፣ መረብ ኳስ፣ ቴኒስ፣ ራግቢና ኪርኬት … የሚጠቀሱ ናቸው፡፡  
በኢትዮጵያ ስለ ስፖርት ውርርድ በቂ እውቀትና ግንዛቤ ተፈጥሯል ለማለት አይቻልም፡፡ በርካታ እንቅስቃሴዎች ገና ያስፈልጋሉ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ህብረተሰቡ በስፖርት ውርርድ  ላይ እምነት ማሳደር አለበት፡፡ ከዚያም በኋላ ገንዘቡን አውጥቶ በነፃነት ሊጫወት ይችላል፡፡ ምክትል ሥ/አስኪያጅ አብርሃም ስለ አክሱም ቤቲንግ የግብር አከፋፈል ለስፖርት አድማስ ባደረገው ገለፃ ተቋማቸው ከጠቅላላ ገቢው 15 በመቶ ለብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር፤ 10 በመቶ ለገቢዎች እና ጉምሩክ እንዲሁም 15 በመቶ የአሸናፊነት ክፍያ በመቅረጥ ገቢ ያደርጋል፡፡   ትልቁን ተፅዕኖ እየፈጠረ ያለው የግብር አከፋፈሉ የንግድ መስኩን ለማፋፋት የሚያበረታታ አለመሆኑ ነው፡፡  
የስፖርት ውርርድ የሚያካሂድ ተቋም  ፍላጎት የሚሆነው ከተጣራ ትርፍ 15 በመቶ ለመክፈል ነው፡፡ አሁን ባለው አሰራር ከሚያስገባው ያልተጣራ ትርፍ እስከ 15% ግብር ይከፍልበታል፡፡ ይኸው የግብር አከፋፈል የስራ መስኩን ለማስፋፋት የሚደረገውን ጥረት እንደሚያጓትት ነው የአክሱም ቤቲንግ ሃላፊዎች የሚያስረዱት፡፡ የንግድ መስኩ በበቂ ሁኔታ ከተስፋፋ በኋላ አገሪቱን በከፍተኛ ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚችል የሚጠቅሱት የአክሱም ቤቲንግ ሃላፊዎች ከብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር ጋር ግልፅ መግባባት ፈጥረን ለመስራት ጥረት ማድረጋችን ይቀጥላል ይላሉ፡፡ የስፖርት ውርርድ ላይ  ወዲያውኑ የሚከፈል ነገር የለም፡፡ ተሳታፊዎች ምን ያህል እንደሚያስይዙ፤ በምን ያህል ውርርዶች ላይ እንደሚሳተፉ ወዲያውኑ ማወቅ አይቻልም፡፡ ይህም ገቢዎችን ሰብስቦ ግብር ለመክፈል በሚኖረው ሂደት ላይ ትዕግስት እንደሚያስፈልገው ያመለክታል። ህጋዊ ፈቃድ አውጥተን መስራታችን በሀገሪቱ ህግ መሰረት መንቀሳቀሳችን የስፖርት ውርርድን በኢትዮጵያ ለማስፋፋት በምናደርገው ጥረት የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር  ድጋፍ ወሳኝ ነው በማለት የአክሱም ቤቲንግ ሃላፊዎች ለስፖርት አድማስ ተናግረዋል። በቀጣይ አክሱም ቤቲንግ ከስፖርት ሚዲያዎች ጋር የመስራት እቅዶችንም ይዟል፡፡ ከሁለት የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ጋር እየተነጋገረ ሲሆን በሌሎች የኤፍኤም ራዲዮ ጣቢያዎችም ከስፖርት ውርርድ ጋር የተያያዙ ፕሮግራሞችን ለመስራት ድርድር እያደረጉ ናቸው፡፡  
በዓለም ዙርያ የሚደረጉ የስፖርት ውርርዶችን ለመወራረድ ወይንም ለመጫወት በአክሱም ቤት ዋና መስርያ ቤት ወይም በቅርንጫፎቹ በመገኘት የጨዋታውን ዝርዝር ወስደው በመመልከት ለመጫወት የፈለጉትን ቡድንና የጨዋታ አይነት ይመርጣሉ፡፡ በሌላ በኩል በድረገፅም በቀጥታ መጫወት ይችላሉ። ድረገፆቸውን ከፍቶ የምዝገባ ቅፅ መሙላት ከዚያም ስልክ ቁጥር ማስገባት፤ የምስጥር ጥያቄ መመለስ፤ ለመወራራጃ የሚያፈልገውን ገንዘብ ገቢ ማድረግ ከዚያም ውርርዱን መጀመር ነው፡፡ በአክሱም ቤቲንግ ማንኛውም ሰው በ20 ብር አንድ ቲኬት በመግዛት ከ1-20 ጨዋታዎችን መወራረድ ይችላል፡፡ በአጠቃላይ የስፖርት ውርርድ ተቋሙ ከ60 በላይ የውርርድ ጨዋታዎችን ለደንበኞቹ የሚያቀርብ ሲሆን ከፍተኛው ሽልማት እስከ 250ሺ ብር ነው፡፡ ውርርዱ የሚካሄድባቸው መንገዶች - አሸናፊውን ቡድን በመገመት መወራረድ - ትክክለኛ ውጤት በመገመት መወራረድ - የጨዋታውን የመጀመሪያ አጋማሸ ውጤት በመገመት መወራረድ - ቀድሞ ጐል የሚያስቆጥረውን ክለብ በመገመት መወራረድ - በመጀመርያው ግማሽ፤ በሁለተኛው ግማሽ እና በሙሉው የመደበኛ ጨዋታ ክፍለ ጊዜ የሚገቡ ጎሎች ብዛት በመገመት መወራረድ - እንዲሁም ሌሎች። በአክሱም ቤቲንግ የውርርድ መመርያ መሰረት በ90 ደቂቃ የእግር ኳስ ጨዋታ ውድድር ውጤት መወራረድ የሚቻል ሲሆን፤ ነገር ግን ውርርዱ የተጨማሪ ሰዓት (30 ደቂቃ) እና የመለያያ ምትን አያጠቃልልም፡፡ ሁሉም ውርርድ የሚካሄደው ጨዋታው ከመጀመሩ በፊት ይሆናል፡፡
ለስፖርት ውርርድ አፍሪካ ምቹ እየሆነች መጥታለች
የስፖርት ውርርድ በዓለም ዙርያ በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፋ የመጣ ሲሆን ትርፋማ ኢንዱስትሪ ሆኗል፡፡  በመላው ዓለም የሚንቀሳቀሱ  የስፖርት አወራራጅ እና አቋማሪ ኩባንያዎችን  በየዓመቱ ከ55ሺ በላይ የስፖርት ውድድሮችን ተንተርሰው በመንቀሳቀስ ላይ ናቸው።  በተለያዩ ጥናታዊ ዘገባዎች እንደሚጠቀሰው በዓለም ዙርያ የስፖርት ውርርድ  በየዓመቱ እስከ  3 ትሪሊዮን ዶላር በሚንቀሳቀስበት ገበያ እየተጧጣፈ ነው፡፡ በህጋዊ እና ህገወጥ የስፖርት ውርርዶችን የሚያካሂዱ አወራራጅ ተቋማት በዓለም ዙርያ ገቢያቸው ከ 700 ቢሊዮን እስከ 1 ትሪሊዮን ዶላር ይገመታል፡፡ በመላው ዓለም የስፖርት ውርርድ 65 በመቶ የገበያውን ድርሻ የተቆጣጠረው የእግር ኳስ ስፖርት ነው፡፡ እያንዳንዳቸው 12 በመቶ የገበያ ድርሻ በመያዝ የሚከተሉት የቴኒስ እና የክሪኬት ስፖርቶች ናቸው፡፡
የስፖርት ውርርድ በአሜሪካ አህጉር ተጀምሮ፤ በአውሮፓ እና በኤስያ አህጉራት በከፍተኛ ደረጃ ከተስፋፋ በኋላ ነው ወደ አፍሪካ አህጉር የመጣው፡፡ ዓለም አቀፍ የስፖርት ውርርድ ተቋማት በአፍሪካ  አህጉር ላይ ባለፉት 5 ዓመታት በትኩረት መስራት ጀምረዋል፡፡  ለዚህም የተለያዩ ምክንያቶች ይጠቀሳሉ፡፡ የመጀመርያው ምክንያት ከአፍሪካ አህጉር አጠቃላይ የህዝብ ብዛት እድሜያቸው ከ15 እስከ 27  እድሜያቸው የሆኑ ከ200 ሚሊዮን በላይ መሆናቸው ነው፡፡ በሌላ በኩል በአህጉሪቱ የየሞባይል አገልግሎት እየተስፋፋ መምጣቱ፤ የአውሮፓ እግር ኳስ ሊጎች በከፍተኛ ደረጃ ተወዳጅነት ማግኘታቸው፤ በየአገራቱ በስፖርት ውርርድ ተቋማት ገቢ ላይ ከአሜሪካ እና ከአውሮፓ አህጉራት ያነሰ የግብር ክፍያ መኖሩም ሊጠቀስ ይችላል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአፍሪካ አህጉር በ27 አገራት የስፖርት ውርርድ እየተካሄደ ሲሆን በህጋዊ እና ህገወጥ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ተቋማት ብዛት ከሁለት ሺ በላይ መሆናቸውን  መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
በአፍሪካ የስፖርት ውርርድ ገዝፎ የሚታይባቸው እና የተስፋፋባቸው  3 አገራት ደቡብ አፍሪካ፤ ናጄርያ እና ኬንያ ናቸው፡፡ የኬንያው ስፖርትፔሳ፤ የደቡብአፍሪካ ሱፓቤትስ እና የናይጄርያው ቤት9ጄኤ በአህጉሪቱ ከሚገኙ ግዙፉቹ የስፖርት ውርርድ ተቋማት ግንባር ቀደም ተጠቃሾቹ ናቸው፡፡  ፕራይስዎተርስኩፐርስ የተባለ ዓለም አቀፍ ተቋም ከዓመት በፊት ይፋ ባደረገው ጥናት በ3ቱ አገራት የስፖርት ውርርድ ኢንዱስትሪ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መሆኑ ተጠቅሶ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት የኢንዱስትሪው ገቢ በዓመት እስከ 50 ሚሊዮን ዶላር ሊደርስ እንደሚችል ተመልክቷል። በአፍሪካ እየተንቀሳቀሱ ያሉት የስፖርት ውርርድ ተቋማት አንድ ተሳታፊ ለሚያስይዘው 1 ዶላር በአማካይ እስከ 500 ዶላር በሚሸልሙበት ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
በአፍሪካ ደረጃ የስፖርት ውርርድ በከፍተኛ ደረጃ የሚካሄድባት አገር ደቡብ አፍሪካ ስትሆን በየዓመቱ 21 በመቶ እድገት እያሳየ የሚገኝ ኢንዱስትሪዋ ነው፡፡ ከፍተኛ ደረጃ ካላቸው የደቡብ አፍሪካ የስፖርት ውርርድ ተቋማት መካከል ሱፓቤትስ፤ ስፖርትቤት፤ላድብሮክስ የተባሉት ይጠቀሳሉ፡፡ በደቡብ አፍሪካ የስፖርት ውርርዶች በእግር ኳስ፤ በራግቢ፤ በክሪኬት፤ በአትሌቲክስ ስፖርቶች በስፋት የሚካሄዱ ሲሆኑ የኢንዱስትሪው ዓመታዊ ገቢ 25 ሚሊዮን ዶላር መድረሱንም መረጃዎች ያመልክታሉ። ይህም ከአገሪቱ የስፖርት መስክ ገቢ 14 በመቶ  ድርሻ ይኖረዋል፡፡ በሌላ በኩል የስፖርት ውርርድ በምእራብ አፍሪካ በከፍተኛ ደረጃ የተስፋፋ ሲሆን በተለይ በናይጄርያ እና ጋና እየገዘፈ መጥቷል፡፡ ናይጄርያ ውስጥ በተለይ በስፖርት ውርርድ እድሜያቸው ከ18 እስከ 40 የሚሆኑ ከ60 ሚሊዮን በላይ የውርርድ ደንበኞች እስከ  9 ሚሊዮን ዶላር በድምሩ በነፍስ ወከፍ በየቀኑ  15 ዶላር በማያዝ ተሳትፎ ማድረጋቸው ይጠቀሳል፡፡
የኬንያ የስፖርት ውርርድ ተቋማት
ከምስራቅ አፍሪካ አገራት የስፖርት ውርርድ በከፍተኛ ደረጃ የተስፋፋባት አገር ጎረቤታችን ኬንያ ናት፡፡ በርግጥ አንዳንድ መረጃዎች በአፍሪካ አህጉር በስፖርት ውርርድ ፈርቀዳጅ መሆኗንና በ1950ዎቹ በዓለም አቀፍ የጎልፍ፤ የቴኒስ፤ የእግር ኳስ እና ሌሎች የስፖርት ውድድሮች መጀመሯን ይጠቅሳሉ፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በኬንያ በከፍተኛ ደረጃ የተስፋፋው የስፖርት ውርርድ ላይ ስኬታማ በመሆንና በየጊዜው እድገት በማሳየት በተለይ 4 የውርርድ ተቋማት ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ በዓመት እስከ 20 ሚሊዮን ዶላር ገቢ የሚያንቀሳቅሱ ናቸው፡፡
በመጀመርያ ደረጃ የሚጠቀሰው የውርርድ ተቋም በምስራቅ አፍሪካ ብቻ ሳሆን በመላ አህጉሪቱ ከሚንቀሳቀሱት መሰል ተቋማት ግንባ ቀደም ተጠቃሽ የሆነው ስፖርትፔሳ የተባለው የውርርድ ተቋም ነው። ስፖርትፔሳ በ2013 እኤአ ላይ ፔሳን ኢስት አፍሪካ ሊሚትድ በተባለ ኩባንያ የተጀመረ ሲሆን በድረገፁ          አንድ ሚሊዮን በክፍያ የተመዘገቡ ደንበኞች በማፍራት እስከ 40 ሚሊዮን ዶላር በዘርፉ እያንቀሳቀሰ የሚገኝ ነው።  የውርርድ ተቋሙ ድረገፅ በኬንያ ብዙ ጎብኝ ካላቸው 10 ድረገፆች አንዱ ሆኖም ይጠቀሳል።
ስፖርትፔሳ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፤ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ ዩሮፓ ሊግ ውድድሮችን በመደበኛነት የሚያወራርድ ሲሆን ሌሎች የአውሮፓ ሊጎችን ጨምሮ፤ በቅርጫት ኳስ፤ በቴኒስ እና በራግቢ የሊግ እና የዓለም አቀፍ ውድድሮችም ይሰራል፡፡ ስፖርትፔሳ በስፖርት ውርርዱ ባለፉት አመታት ባገኘው ስኬት ተምሳሌት ሆኖ ሊጠቀስ የሚበቃ ሲሆን በስኬታማነቱ በአንድ ወቅት የኬንያ የሊግ ውድድር ስፖንሰር ለማድረግ የቻለ፤ ከሞባይል አገልግሎት ተቋማ ጋር ተቀናጅቶ የሚሰራ እንዲሁም የኢንቨስትመንት መስኩን ትልልቅ ፌስቲቫሎችን በማካሄድ የሚያስተዋውቅ ነው፡፡ በኬንያ ከስፖርትፔሳ ባሻገር ሌሎች የስፖርት ውርርድ ተቋማትንም መጥቀስ ይቻላል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ የሚጠቀሰው በጃምቦ ቤቲንግ ሊሚትድ ከ4 ዓመታ በፊት ተመስርቶ መንቀሳቀስ የጀመረው ቤትዌይኬንያ ነው፡፡ ይህ ተቋም በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ እውቅና ያለውና፤ በማልቲስ እና ግራኒሴይ ተቀማጭነቱን ባደረገው እንዲሁም የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ክለብ የሆነውን ዌስትሃም ስፖንሰር የሆነው ቤትዌይ ቅርንጫፍ ሲሆን ዓለም አቀፍ ደረጃ የሚንቀሰቃቀሰው ቤትዌይ ሊሚትድ በተባለ ኩባንያ ነው፡፡ በሶስተኛ ደረጃ የሚጠቀሰው ደግሞ ቤቲንኬንያ የተባለው የውርርድ ተቋም ሲሆን፤ በአፍሪካ እና በአውሮፓ ትልቁ የስፖርት ውርርድ ተቋም ጎልድቤት ስር የታቀፈ እና በኬንያ ጋምኮድ በተባለ ኩባንያ የሚሰራ ነው፡፡ ቤት የቱ፤ ሚቼዛ፤ ኤሊት ቤት ዌይ፤ ጀስትቤት፤ ላኪ2ዩ እና ኬንያ ስፖርት ቤት ሌሎቹ በኬንያ የሚነቀሳቀሱ ህጋዊ የስፖርት ውርርድ ተቋማት ናቸው፡፡