Administrator

Administrator

     የሆላንድ ካር ኩባንያ ግማሽ ባለሀብት የሆኑት ኢ/ር ታደሰ ተሰማ፤ በኩባንያቸው ላይ እየተደረገ ያለውን ምርመራ በተመለከተ ለጠ/ሚኒስትሩና ለፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቤቱታ አቀረቡ፡፡
ባለሀብቱ ህዳር 27 ቀን 2009 ዓ.ም ለዋና ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባዬና ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በፅሁፍ ባቀረቡት አቤቱታ፤ “በፍ/ቤት የኪሳራ ውሳኔ የተላለፈበትን ሆላንድ ካር ኩባንያ በተመለከተ የኪሳራውን ሂደት እንዲያከናውኑ በተሾሙት መርማሪ ዳኛ ላይ እምነት አጥቻለሁ›› ብለዋል፡፡
ባለሀብቱ እየተፈፀመ ነው ያሉት በስልጣን አለአግባብ መጠቀምና ሙስና እንዲጣራላቸው ጠይቀዋል - በአቤቱታቸው፡፡
በዘጠኝ ነጥቦች ዘርዝረው እየተፈፀሙ ናቸው ያሏቸውን ስህተቶች ያቀረቡት ባለሀብቱ፤ ኪሳራ አጋጥሞታል የተባለው ኩባንያቸው በአንድ ወቅት በሀገሪቱ ካሉ ኩባንያዎች ከፍተኛ ግብር ከፋይ የነበረና ታማኝ የኢኮኖሚ አንቀሳቃሽ ተብሎ የተሰየመ ድርጅት እንደነበር አስታውሰዋል፡፡  ሆላንድ ካር፤ ዶክ፣ አባይ፣ አዋሽ፣ ተከዜና ናኦሚ የተሰኙ አውቶሞቢሎችን በአገር ውስጥ በመገጣጠም ይታወቅ እንደነበር ይታወሳል፡፡

  አቢሲኒያ ባንክ በቅርቡ ባደረገው የባለአክሲዮኖች 20ኛ መደበኛና 11ኛ ድንገተኛ ጠቅላላ ጉባኤዎች ላይ ለግብረሰናይ ድርጅቶች እንዲለገስ የተወሰነውን የግማሽ ሚሊዮን ብር ድጋፍ ለተመረጡ 7 ግብረሰናይ ድርጅቶች ሰጠ፡፡
ባንኩ ባለፈው ሳምንት በቅርቡ ለተቀዳሚ ደንበኞች ማስተናገጃ በከፈተው ልዩ ሐበሻ ቅርንጫፍ በተደረገው የርክክብ ሥነ ስርዓት ላይ የባንኩ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሙሉጌታ አስማረ ባደረጉት ንግግር፣ ባንካችን ከምስረታው ጀምሮ ላለፉት 20 ዓመታት ከበርካታ የግብረሰናይ ድርጅቶች ጋር አብሮ በመስራት ማኅበራዊ ግዴታውን ሲወጣ ቆይቷል ብለዋል፡፡
በዕለቱ ድጋፍ የተደረገላቸው 7 ግብረሰናይ ድርጅቶች፡- የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር የ200 ሺህ ብር፣ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል የ100 ሺህ ብር፣ ለዓለም የሕፃናት ዕርዳታ ድርጅት 60 ሺህ ብር፣ ርዕይ ለትውልድ የ50 ሺህ ብር፣ ነህምያ ኦቲዝም ማዕከል የ40 ሺህ ብር፣ የጎንደር መልሶ ማቋቋምና ልማት ማኅበር የ25 ሺህ ብር፣ ፍሬገነት ኪዳን ለህፃናት የ25ሺ ብር ቼክ ከባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር ከአቶ መሰረት ታዬ እጅ ተቀብለዋል፡፡
“ከተመሰረትን አጭር ጊዜ ቢሆንም ይዘን የተነሳነው ራዕይ ትልቅ ነው፡፡ በ2020 ዓ.ም (ከ11 ዓመት በኋላ ማለት ነው) 10 ሺህ ህፃናት ራዕይ ኖሯቸው አገር የሚቀይሩ ትልቅ ቦታ የሚደርሱ ዜጎችን መፍጠር ነው” ያሉት የርዕይ ለትውልድ ፕሬዚዳንት፤ የድርጅቱ ዓላማ፣ ከተለያዩ ድርጅቶች ድጋፍ በመጠየቅ የድሃ ቤተሰብ ልጆች ምግብ እንዲበሉ ማድረግ፣ የትምህርት መርጃ መሳሪያዎችና ዩኒፎርምም ማቅረብ ነው ብለዋል፡፡

Monday, 05 December 2016 10:02

የፍቅር ጥግ

 · አንድ ላይ መሆን የቱንም ያህል አስቸጋሪ ቢሆን ግዴለኝም፤ ለብቻ ከመሆን በላይ የከፋ ነገር የለም፡፡
    ጆሴፊኔ አንጄሊኒ
· የትም ብሄድ ልዩነት የለውም፤ ሁልጊዜ ወዳንተ መመለሺያ መንገዱን አውቀዋለሁ፡፡ አንተ አቅጣጫ ማመላከቺያ ኮከቤ ነህ፡፡
   ዲያና ፒተርፍሬዩንድ
· “እወድሻለሁ” - የሁሉም ነገር መጀመሪያና መጨረሻ ይኸው ነው፡፡
   ኤፍ. ስኮት ፊትዝጌራልድ
· ሁለመናዬ ሁሉመናሽን ይወደዋል፡፡
   ጆን ሌጀንድ
· ፍቅር፤ ለሰው ልጅ ብዙዎቹ ህመሞች ድዌዎች ፈውስ ነው፡፡
   ዊሊያም ሜኒንገር
· እውነተኛ የፍቅር ታሪኮች መጨረሻ የላቸውም፡፡
   ሪቻርድ ባች
· ፍቅር እሳት ነው፡፡ ነገር ግን ልብህን ያሙቀው አሊያም ቤትህን ያቃጥለው መገመት አትችልም፡፡
   ጆአን ክራውፎርድ
· በዓይኖችህ ሳይሆን በልብህ አፍቅር፡፡
   ድሬክ
· በፍቅር ስሜት ብቻ ነው የማምነው፡፡
   ካርሴና ካፑር ክሃን
· መፈቀር ብ ቻ አ ይደለም የ ምሻው፤ መ ፈቀሬም እንዲነገረኝ ጭምር እንጂ፡፡
   ጆርጅ ኢሊዮት
· በህይወት ውስጥ አንድ ደስታ ብቻ ነው ያለው- ማፍቀርና መፈቀር፡፡
   ጆርጅ ሳንድ

Monday, 05 December 2016 09:59

ስናውቃቸው የሚገርሙን!!

 · አንድ ፓውንድ (453.6ግራም) ማር ለማምረት፣ አንድ ንብ 2 ሚሊዮን አበቦችን መቅሰም ይኖርበታል፡፡
· የዓለም የህዝብ ቁጥር እ.ኤ.አ በ2080 ወደ 10.8 ቢሊንዮ ያድጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
· በህይወት ዘመናችን ሁለት የዋና ገንዳዎች የሚሞላ ምራቅ እናመርታለን፡፡
· መዝለል የማይችል ብቸኛው አጥቢ እንስሳ ዝሆን ነው፡፡
· እንደ ጣት አሻራ ሁሉ እያንዳንዱ ሰው የተለያዩ የምላስ አሻራዎች አሉት፡፡
· የሲጋራ መለኮሽያ ላይተር የተፈለሰፈው ከክብሪት በፊት ነው፡፡
· የተራራ አንበሶች ማፏጨት ይችላሉ፡፡
· ቢራቢሮዎች ምግባቸውን የሚቀምሱት በእግሮቻቸው ነው፡፡
· ዶልፊኖች የሚተኙት አንድ ዓይናቸውን ገልጠው ነው፡፡
· የጥርስ መቦረሽያ ‹‹ኮልጌት›› በስፓኒሽ ቋንቋ ‹‹ሂድና ራስህን ስቀል›› ማለት ነው፡፡
· አንድ አማካይ ሰው በህይወት ዘመኑ 6 ወራትን ቀይ የትራፊክ መብራት ወደ አረንጓዴ እስኪለወጥ ይጠብቃል፡፡
· የሰው ልጅ ተኝቶ ሳለ፤ በአማካይ 70 የተለያዩ ነፍሳትንና
10 ሸረሪቶችን ይበላል ወይም ወደ ሆዱ ያስገባል፡፡
· ሰው እስትንፋሱን በመግታት ነፍሱን ማጥፋት
አይችልም፡፡

Monday, 05 December 2016 09:57

የማሰላሰያ ጥግ

 ለመጨረሻ ጊዜ አዲስ ነገር የሞከራችሁት መቼ ነው?
መኖር የምትችሉት ለ1 ዓመት ብቻ ቢሆን፣ ምን ለማሳካት ትፈልጋላችሁ?
ዓይናችሁን ስትጨፍኑ ምን ታልማላችሁ?
ስለራሳችሁ እጅግ አድርጋችሁ የምትወዱት ምንድን ነው?
ህይወታችሁን እንደ ፊልም ብትቆጥሩት፣ ርዕሱን ምን ትሉታላችሁ?
ራሳችሁን በ5 ቃላት እንዴት ትገልጹታላችሁ?
በጣም የምትኮሩበት ነገር ምንድ ነው?
ህይወት ትላንት ምን አስተማረቻችሁ?
ምን መጥፎ ልማዶችን ማቆም ትፈልጋላችሁ?
እናንተን ልዩ የሚያደርጋችሁ ምንድ ነው?
በጣም የምትፈልጉት ነገር ምንድን ነው?

ባለፈው 1 ዓመት የታተሙ መፃህፍት ይወዳደራሉ
     በረዥም ልቦለድ፣ በግጥምና በልጆች መፃህፍት ዘርፍ የሥነ ፅሁፍ ሥራዎች ተወዳድረው ሊሸለሙ ነው።
ኖርዝ ኢስት ኤቨንትስ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ከብሄራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መፃህፍት ኤጀንሲ ጋር በትብብር ያዘጋጁት ሆሄ የሥነፅሁፍ ሽልማት ፕሮግራም፤ አሸናፊ ደራስያንን ከመሸለም ባሻገር የንባብ ባህል እንዲስፋፋ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ላበረከቱ ክበባትንና ቤተ መፃህፍትም የሚመሰገኑበትና ዕውቅና የሚያገኙበት ይሆናል ተብሏል፡፡
የሽልማት ፕሮግራሙ አዘጋጆች ከትናንት በስቲያ በጎተ ኢንስቲትዩት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ ለውድድር የሚቀርቡት መፃህፍት ከመስከረም 1 ቀን 2008 እስከ ጳጉሜ 5 ቀን 2008 ዓ.ም ድረስ የታተሙ መሆን አለባቸው፡፡ ተወዳዳሪ መፃህፍቱ በዳኞች ኮሚቴ በተዘጋጀላቸው መስፈርቶች መሰረት የሚመዘኑ ሲሆን በዳኞች ኮሚቴ ከሚሰጠው ውጤት በተጨማሪ አንባቢያን በነፃ የስልክ መልዕክትና በድረ ገፅ የሚሰጡት ድምፅም የተወሰነ ነጥብ ይኖረዋል ተብሏል። አጠቃላይ ውጤቱ የሚታወቅ ይሆናል፡፡
በውድድሩ መሳተፍ የሚፈልጉ ደራሲያን ከታህሳስ 4-19 2009 ዓ.ም ሞርኒንግ ስታር ሞል ላይ በሚገኘው የድርጅቱ ቢሮ፣ በጎታ ኢንስቲቲዩትና በቡክላይት መፅሀፍ መደብር መመዝገብ እንዳለባቸው የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ የሽልማት ስነ ስርዓቱ በሚያዚያ ወር አጋማሽ ላይ እንደሚካሄድ ተናግረዋል፡፡


      እናት የማስታወቂያ ስራዎች ድርጅት ከጀርመን የባህል ማዕከልና ከወመዘክር ጋር በመተባበር “አማካሪው አልፍሬድ ኤልግ በምኒልክ ቤተ-መንግስት” በሚል ርዕስ በዮናስ ታረቀኝ ወደ አማርኛ በተተረጎመው ታሪካዊ መፅሀፍ ላይ በነገው ዕለት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በወመዘክር አዳራሽ ውይይት ይካሄዳል፡፡
ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ መምህር የሆኑት አቶ ብርሀኑ ደቦጭ ሲሆኑ በውይይቱ የመሳተፍ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲገኝ ተጋብዟል፡፡

የኖቤል ተሸላሚዎችን አነጋግረዋል
     የአመቱ የኖቤል የስነጽሁፍ ተሸላሚ በመሆን የተመረጠውና “ስራ ስለሚበዛብኝ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ አልገኝም” በማለቱ የዓለማችን መገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ሆኖ የሰነበተው አሜሪካዊው ድምጻዊና የሙዚቃ ግጥም ደራሲ ቦብ ዳይላን፣ ባለፈው ረቡዕ ከፕሬዚዳንት ኦባማ ጋር በዋይት ሃውስ እንዲገናኝ የቀረበለትን ግብዣ ባለመቀበል በስነስርዓቱ ላይ ሳይገኝ መቅረቱ ተዘግቧል፡፡
ኦባማ የዘንድሮ የኖቤል ተሸላሚ አሜሪካውያንን ከሽልማት ስነስርዓቱ በፊት በዋይት ሃውስ ለማግኘት ባለፈው ረቡዕ በያዙት ቀጠሮ፣ ሌሎች ተሸላሚዎች በስፍራው ቢገኙም ልማደኛው ዳይላን ግን ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ የውሃ ሽታ ሆኖ በመቅረት ዳግም የመገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ሊሆን እንደበቃ የአሶሼትድ ፕሬስ ዘገባ ይጠቁማል፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ ዳይላን ተሸላሚ መሆኑ ይፋ የተደረገ ሰሞን፣ “ከምወዳቸው ገጣሚያን አንዱ የሆነው ዳይላን ሽልማቱ ይገባዋል” በማለት የእንኳን ደስ አለህ መልዕክት ያስተላለፉለት ሲሆን  እ.ኤ.አ በ2012 ታላቁን የአገሪቱ የነጻነት ሜዳይ ሽልማት አበርክተውለት እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ምንም እንኳን ዳይላን ባይገኝም፣ ኦባማ በዕለቱ የፊዚክስ ኖቤል ተሸላሚዎቹን ዳንካን ሃልዳኔን  ማይክል ኮስተርሊዝን፣ የኢኮኖሚክስ ተሸላሚውን ኦሊቨር ሃርትን እንዲሁም የኬሚስትሪ ተሸላሚውን ሰር ጄ ፍሬዘር ስቶዳርትን  በዋይት ሃውስ በክብር ተቀብለው የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈውላቸዋል፤ ለስራቸውም እውቅና ሰጥተዋቸዋል፡፡

የሚከተለው ተረት በአበሻም አለ፡፡ የህንዱ ግን ትንሽ ለየት ይላል፡፡ እነሆ፡-
ከዕለታት አንድ ቀን አይጦች ከባድ ሰብሰባ አደረጉ፡፡ የስብሰባው ዓላማ በየጊዜው በድመት የሚደርስብንን ጥቃት እንዴት እንከላከል? የሚል ነው፡፡
ሀሳብ ብዙ ከተብላላ በኋላ እንድ ዘዴ ለመዘየድ ተወሰነ፡፡ ይኸውም፤ ‹‹ድመት ሁልጊዜ ባልታሰበ ሰዓት እየመጣ አይጦችን የማጥቃት ስልት ስላለው፤ ይኼ እንዲሰናከል ማድረግ የሚቻለው፤ ድመት አንገት ላይ ቃጭል በማሰር ነው፡፡ ይህም የሚጠቅመው ድመት አድፍጦ ሲመጣ ቃጭሉ እየጮኸ እንዲያጋልጠው ነው! ተባለ፡፡ ያኔ እኛም በየጎሬያችን ጥልቅ እንላለን፡፡››
 ሁሉም አጨበጨቡ፡፡
‹‹ለዘመናት ስንታመስ የነበረበት ሁኔታ ዛሬ መላ ተመታለት!›› በሚል ሆታውና ዕልልታው ደራ!
በመካከል ግን አንድ አስተዋይ አይጥ አንድ መሠረታዊ ጥያቄ አነሳ፡-
‹‹ለመሆኑ በድመት አንገት ላይ ቃጭሉን የሚያስር ጀግና አይጥ የቱ ነው?
እስቲ አስተያየት እንስጥበት››
ፀጥ ፀጥ ሆነ፡፡ ‹‹ማነው ደፋር?›› አለና ቀጠለ አስተዋዩ አይጥ፡፡ ወደ አንዱ አይጥ ዞር ብሎም፤
‹‹አንተ ትሻል ይሆን? ሲል ጠየቀው፡፡ አይጡም፤
‹‹እኔ የአይጥ ቅድመ- አያቶቼ ከባድ ግዝት አለብኝ፡፡ እድመት አጠገብ ከደረስክ የተረገምክ ሆነህ ቅር ብለውኛል!›› አለ፡፡
ሁለተኛው አይጥ ተጠየቀ፡፡ እሱም፤
‹‹እኔ ወደ ድመት ከተጠጋሁ የሚጥል በሽታ አለብኝ፡፡ እዛው ክልትው ነው የሚያደርገኝ!›› አለ
‹‹አንተስ?›› ተባለ ሶስተኛው፡፡
‹‹እኔ ከዚህ ቀደም በድመት ተይዤ ድመቶች ችሎት ቀርቤ፤ ሞት ተፈርዶብኝ ነበር፡፡ ዕድሜ ለእናንተና አባቴ፣ ጥበብ አስተምረውኝ ስለ ነበር አስቀድሜ የሞትኩ መስዬ ለጥ አልኩ፡፡ ልፍስፍስ ብዬ ተኛሁ፡፡ ቢያነሱኝ፣ ቢሸከሙኝ፣ ቢያገላብጡኝ ትንፍሽ ሳልል ወድቄ ቀረሁ፡፡ ሞቷል ብለው በማሰብ ቃሬዛ ሊያመጡ ሲሄዱ እኔ ፈትለክ አልኩ! ስለዚህ አሁን ድመት ሰፈር በምንም መልኩ ቢሆን ዝር ማለት የለብኝም!›› አለ፡፡
ሁሉም አይጦች በየተራ እየተነሱ ከባድ ከባድ ሰበቦችን እያቀረቡ ተቀመጡ፡፡  
አንድ አይጥ አንድ አዲስ ሀሳብ አመጣ፡-
‹‹ለምን ድመቱ ሲያንቀላፋ ሄደን ቃጭሉን አናጠልቅለትም?›› አለ፡፡
አስተዋይ አይጥ ግን ሀሳቡን ተቃወመና እንዲህ አለ፡-
‹‹የህንድ ድመት የአነር ዝርያው ይበዛል፡፡ የህንድ አነር በአፈ-ታሪክ እንደሚታወቀው፤ ሲተኛ አንድ ዓይኑን ጨፍኖ፣ አንድ ዐይኑን ገልጦ ነው፤ ይባላል፡፡ ስለዚህ አድፍጠን ብንሄድ እንኳ በሚያየው ዐይኑ ይይዘናል›› አለ፡፡
 ‹‹ታዲያ ምን በጀን?›› አሉት ሌሎቹ፡፡
አስተዋዩ አይጥም፤
‹‹የሚሻለው አንድ የአነር ጥናት ያጠኑ የገዳም አባት አሉ፡፡ እሳቸውን እንጠይቅ›› አለ፡፡
ሁሉም ተስማሙና ወደ ጠቢቡ ሄዱ፡፡ ጠቢቡም፤
‹‹አይጦች ሆይ! የአነር-ክልስ ድመት የዋዛ እንዳይመስላችሁ፡፡ ፀባዩ ህብረ-ቀለም ነው፡፡ ዓይኑን የሚጨፍነው ወተት ከሰጣችሁትና ሲጠግብ ብቻ ነው፡፡ በዛች ደቂቃ ብቻ ነው ቃጭሉን ልታጠልቁለት የምትችሉት!›› አሉ፡፡
ጥያቄው ግን ቀጠለ፡-
‹‹ወተቱንስ እንዴት ነው የምናቀርብለት? ማንስ ነው የሚያቀርበው?››
‹‹ወተቱንማ መጀመሪያ ንፁህ ወለል ላይ አፍስሳችሁ እናንተ ትበርራላችሁ፡፡ እሱን ሲልስ ቀጣዩን ወተት በሳህን ትገፉና ትጠፋላችሁ፡፡ ወደ ዋናው የወተት መድረክ ሲገባ ትጠብቁታላችሁ፤ ሲጠግብ ዓይኑን ይጨፍናል፡፡ ያኔ ነው የቃጭሉ ማንጠልጠል ሰዓት!››
አሏቸው፡፡
እንደተባለው አደረጉ፡፡ ቀናቸው፡፡
ግን ክፋት አይቆምምና ያ ድመት ሌላ ጊዜ ጓደኛውን ይዞ መጣ፡፡ እሱ ባንድ ጉድጓድ በኩል ቃጭሉን እያንቃጨለ ይመጣል፡፡ በሌላኛው የጉድጓዱ ጫፍ ግን ቃጭል የሌለውን ድመት ይልከዋል፡፡ አገር አማን ነው ብለው በዛኛው ጉድጓድ ብቅ የሚሉት አይጦች ዋጋቸውን አገኙ!
* * *
እንግዲህ ባለ ቃጭልና ቃጭል አልባ ድመት በሀገራችን በብዛት አለ፡፡ አንድ ችግር ሲፈታ ሌላ ችግር ይፈልቃል። ጀርሙ ከሥሩ- ስላልተነቀለ ነው! የጋንግሪን ልክፍት ይመስላል፡፡ ስብሰባዎች ይካሄዳሉ፡፡ ጠማጁና ተጠማጁ ይፋጃሉ፡፡ አንዱ የልማት መላ ሲፈጥር፣ ሌላው የጥፋት መላ ያደራጃል፡፡ እስከ ሚቀጥለው ስብሰባ ይሄው እርቅ- ወ-ጠብ ሥርዓት ይሆናል፡፡ ይቀጥላል፡፡ ‹‹ማንም ከማንም አይማርም›› ይላል ሎሬት ፀጋዬ፡፡
‹‹ተምረህ ተምረህ ደንቆሮ ሆነሃል!›› ይላሉ ገጣሚና ፀሀፌ-ተውኔት መንግሥቱ ለማ! አንድን ግምገማ እንዴት ነገሬን በሆድ አምቄ ፈተናውን ልለፈው? ከሆነ ጥረታችን፤ ለውጥ ወደሚቀጥለው ዓመት ግምገማ ያልፋል እንጂ የተመኘነው የተሻለ ሥርዓት አይመጣም! መቅሰስ እንጂ እራት አይሆንልንም፡፡
ብዙ በሥልጣን የባለገ ሰው መቀነሳችን ቀናነት ካለው፤ ጎጂ አይደለም፡፡ የምንተካውንም በቅንነት ማሰብ ግን ወደድንም ጠላን ይጠበቅብናል፡፡ በዕሙናዊ ባህሉ ግምገማን የመሰለ ነገር የለም! በሒሳብ ገፅታው ግን ማናቸውንም አምባገነናዊ ጥፋት ለመፈፀም በሩ ክፍት ነውና ያሳስባል፡፡ ከትናንት በስቲያ ምን ነበርን? ትናንትስ? ዛሬስ? ብለን መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ክልሎች እርስ በርሳቸው ሲጋጩ ከርመው፣ ዛሬ ችግሩ ተፈታ ስንል የትላንቱ መሰንበቻ ግጭታቸው መረጃ ተደብቀን ነበርን? ብሎ መጠየቅ ዛሬን እንድንገመግም ያግዘናል፤ የአመራሮቻችንንም ሀቀኛ ባህሪ እንድናገናዝብ ቀኝ እጅ ይሆነናል፡፡ የአመራሮች ችግር ተፈታ ስንል የህዝቦች ምሬትና ያልተፈቱ ጥያቄዎች መፍትሔ ማግኘት ጉዳይ መላ ይኖረዋል ብለን ተስፋ እናደርጋለን! ዕውን ተስፋችን ተስፋ አለውን!?
የሀገራችን ዓለማቀፋዊ ግንኙነትንም ከክልል ልቀንና ባሻገር አይተን ዕጣ-ፈንታችን ምን ይሆን? የበለፀገችው አሜሪካ ከእኛ ከድሆቹ እኩል ‹‹ምርጫ ተጭበርብሯል›› በሚባልበት ዘመን ወዴት እየተጓዝን ነው? ብሎ መጠየቅ ክፍት አእምሮ ያላቸው አገሮች ጥያቄ ሊሆን ይገባል! ያለ ዓለማዊ ግንኙነት ብቻችንን ደሴት ሆነን አንኖርምና የዓለምን ጠረን ማሽተት፣ መልኩን ማየት፣ ጣዕሙን መቅመስ፤ አካሉን መንካት ብቻ ሳይሆን በስድስተኛ ህዋሳችንም ቢሆን (with our sixth sense too) ለማጣጣም መሞከር አለብን፡፡ በአለም ላይ በሚከሰት ሂደት ሳቢያ እያንዳንዱ ሀገር ብቻ ሳይሆን በውስጡ የሚኖር ህልው ከጉዳይ መፃፍ አለበት፡፡ የህዝብ ብዛት መጨመር ለህልውናችን ምን ያህል አስጊ ነው የምንለውን ያህል፤ የህዝብ ቁጥር መቀነስስ ታላላቅ ሀገሮችን አያሳስባቸውም ወይ? ወደብ ያላቸውና የሌላቸው አገሮችስ በውሃ ላይ ካለ ባህራዊ ኃይል ጋር ምን ያህል ህልውናቸው ስጋት ላይ ነው? ታላላቅ አገሮች የንግድ ግንኙነታቸው ሲዛባ እኛን አይመለከተንም ወይ? ሰደትን የገቢ ምንጭ ያደረጉ እንደኛ ዓይነት አገሮችስ ኢኮኖሚያቸው ምን ይውጠው ይሆን? (ለምሳሌ እንደሜክሲኮ የአንበሳውን ድርሻ ለስደት ድርጎ (Remittance) ያደረጉ አገሮች የሚሰማቸው በቀል ነው የጎረቤት አገር ፍቅር?...) የራስን ኢኮኖሚ በራስ ማስተዳደር ይቻላልን? ማስተዋል የሚያሻቸው አያሌ ሂደቶች የሥጋቶቻችን እኩያ ናቸው! ጥገኛ ኢኮኖሚ የራሱን አደጋ ማስተዋል አለበት። ከአፍንጫ ሥር የራቀ መሆን አለበት፡፡
በአሜሪካና በአውሮፓ አያሌ ዛፎች አሉ፡፡ በነዚህ ዛፎች ላይ ደግሞ አያሌ የወፍ ጎጆዎች አሉ፡፡ ከአፍሪካም፣ ከእስያም፣ ከላቲን አሜሪካም የመጡ ወፎች ያረፉባቸው ዛፎች አያሌ ናቸው፡፡ የዘር፣ የቀለም፣ የሃይማኖት፣ የአመለካከት ወዘተ ባለቤት የሆኑትን ወፎች ለመግፋት ወይም ለማባረር የዓለም ኃያላን መሪዎች ያኮበከቡ በሚመስልበት በአሁን ወቅት ዕሳቤያችን ምን መሆን አለበት? ብሎ ማሰብ ደግዬ መንገድ ነው፡፡ ቀኝና ግራ ሳይባል የአክራሪዎች መንገድ ሊከሰት የሚችልበት አሳቻ ሁኔታ ሊታይ ይችላል፡፡ ‹‹ዛፉን ሳይሆን ዛፉ ላይ ያለውን ጎጆ እይ›› የሚለው አባባል የሚያሻን እዚህ ላይ ነው፡፡ ልቡና ይሰጠን!

ከአፍሪካ አንደኛ ነው

        ኢትዮጵያዊው ያሬድ ንጉሴ ዲሳሳ በዓለም ሻምፒዮና በብራዚላዊያን ጂጁትሱ ስፖርት ለግማሽ ፍፃሜ በመድረስ በ4ኛ ደረጃ ያጠናቀቀ ሲሆን ውጤቱ ለኢትዮጵያም ለአፍሪካም በታሪክ የመጀመሪያው ነው፡፡ በ2016 የዓለም ጂጁትሱ ሻምፒዮና ያሬድ ንጉሴ በመጀመሪያው ዙር ጀርመናዊ ተጋጣሚውን በማሸነፍ ሲሆን፤ በ2ኛው ዙር ደግሞ ከሩሲያው ተጋጣሚ ጋር ተገናኝቶ በስፖርቱ አዳዲስ ህጎች ጋር በተገናኘ ያስመዘገበው ውጤት ተሰርዞበት ለግማሽ ፍፃሜ መድረስ ችሏል። በጂጁትሱ የዓለም ሻምፒዮና የያሬድ አሰልጣኝ ሆነው የተሳተፉት በዓለማቀፉ የጂጁትሱ ፌዴሬሽን የምስራቅ አፍሪካ ተወካይ የሆኑትና ስፖርቱን በኢትዮጵያ በማስተዋወቅ ፈር ቀዳጅ የሆኑት ዶ/ር ፀጋዬ ደግነህ ናቸው፡፡ ዶ/ር ፀጋዬ ከጀርመን ለስፖርት አድማስ በሰጡት አስተያየት የያሬድ ውጤት ከስምንት ዓመት በፊት በኢትዮጵያ የተዋወቀውን የጂጁትሱ ስፖርት በከፍተኛ ደረጃ የሚያነቃቃና በአፍሪካ ደረጃ ግንባር ቀደም ሆኖ ሊጠቀስ የሚችል ስኬት ነው ብለውታል፡፡
በግማሽ ፍፃሜው በ56 ኪ.ግ ኮሎምቢያዊውን ተጋጣሚ ያገኘ ሲሆን በዚሁ ፉክክር ላይ በስፖርቱ በቅርቡ በተቀየሩ አዳዲስ ህጎች ሳቢያ የነበረው ብልጫ ተወስዶበት የነሐስ ሜዳሊያው ለጥቂት አምልጦታል፡፡ ያሬድ ንጉሴ የጁቬንቱስ ክለብ ሰልጣኝ ሲሆን ከዚህ በፊት በጀርመን ዱሱልዶፍ በተካሄደ አለማቀፍ ውድድር ተሳትፎም ያውቃል። ባለፈው ሰሞን በፖላንድ በተካሄደው የዓለም የጂጁትሱ ሻምፒዮና ያሬድ ንጉሴ በ4ኛ ደረጃ ማጠናቀቁ ከፍተኛ አድናቆት ያተረፈበት ሲሆን፤ ከአፍሪካ በ1ኛ ደረጃ ከመላው ዓለም በ5ኛ ደረጃ እንዲቀመጥ አስችሎታል፡፡ በሻምፒዮናው ላይ ከነበረው ተሳትፎ በኋላ በአቡዳቢ በሚካሄድ ሴሚናር ከመጋበዙም በላይ በጂጁትሱ  ስፖርት ከፍተኛ ደረጃ ካላቸው ብራዚላዊ አሰልጣኝ ጋር የሚሰራበት ዕድል ተፈጥሮለታል፡፡ በዚሁ የዓለም ሻምፒዮና ላይ 600 የጂጁትሱ ስፖርተኞችና 200 አሰልጣኞቻቸው ተካፋይ ነበሩ፡፡ በቀጣይ በፖላንድ በሚካሄደው የ2017 ወርልድ ጌምስ አፍሪካን በመወከል የሚሳተፍ ይሆናል፡፡ ወርልድ ጌምስ፣ ካራቴ፣ ሞተር ስፖርት፣ ዳርት፣ ጂዶ፣ ጂጁትሱና ሌሎች ስፖርቶችን የሚያካትት አለማቀፍ የውድድር መድረክ ነው፡፡
ዶ/ር ፀጋዬ ደግነህ ነዋሪነታቸው በጀርመን ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የጂጁትሱ ስፖርትን በማስፋፋት ፈርቀዳጅ ሚና የተጫወቱ ናቸው። በታላቁ የጀርመን የመኪና አምራች ኩባንያ መርሴዲስ ቤንዝ በፕሮጀክት ማኔጅመንትና በዳይቨርሲቲ ማኔጅመንት ለ15 ዓመታት ያገለገሉ ሲሆን ከፕሮጀክት ማኔጅመንት ጋር በተያያዘ በርካታ መፅሀፍቶችን ያዘጋጁና በተለያዩ ጊዜያትም ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት የተለያዩ ስልጠናዎችና ወርክሾፖችን ይሰጣሉ፡፡ ዶ/ር ፀጋዬ ደግነህ በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ ጂጁትሱ ዩኒየን ምክትል ሊቀመንበር ዓለማቀፉ ጂጁትሱ ማህበር አባልና የምስራቅ አፍሪካ ዞን ተወካይ እንዲሁም በዓለማቀፉ የጂጁትሱ ፌዴሬሽን የስነ ምግባር ኮሚቴ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው በማገልገል ላይ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የጂጁትሱ ስፖርትን ለማስፋፋት ከ8 ዓመታት በፊት በፍትህ ሚኒስቴር የተቋቋመ ማህበር መኖሩን ለስፖርት አድማስ የገለፁት ዶ/ር ፀጋዬ በአዲስ አበባ፣ በድሬደዋ፣ በሐረርና በሀዋሳ የጁዶ ጂጁትሱ ማህበራት ተቋቁመው እንደሚንቀሳቀሱና በአጠቃላይ እስከ 500 የጂጁትሱ  ስፖርተኞችን በማቀፍ እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡      
የጂጁትሱ ስፖርት የማርሻል አርት አይነት ስፖርት ሲሆን የመጣል የመወርወር የመጥለፍና የተለያዩ የምት ስንዘራ ቴክኒኮችን የሚተገብር ስፖርት ነው፡፡ ይህ ስፖርት በአሁኑ ወቅት ብራዚላዊያን ጂጁትሱ በሚል መጠሪያ በዓለማቀፍ ደረጃ እየተስፋፋ ሲሆን ዓለማቀፉ የኦሎምፒክ ኮሚቴ በ2020 እ.ኤ.አ ከሚካሄደው የቶኪዮ ኦሎምፒክ በኋላ የኦሎምፒክ ስፖርት ለማድረግ ትኩረት እየሰጠው ነው፡፡