Administrator

Administrator

     ‹‹ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ማለት ሐሳብንና ገንዘብን አቀናጅቶ ሥራ መፍጠር ነው፡፡ ሰዎች እዚህ ተምረው ወጥተው እንዴት የራሳቸውን ሥራ መፍጠር እንደሚችሉ ነው የምናስተምረው፡፡ ሐሳብና ገንዘብ እንዴት እንደሚቀናጁ መንገድ እናሳያለን፡፡ ከፊዚቢሊቲ ጥናት አንስቶ ማርኬቲንግና ፋይናንሻል ስትራቴጂ እንዴት እንደሚቀረጽ እናስተምራለን፡፡ ምክንያቱም ያለ ፋይናንስ (ገንዘብ) ሐሳብ ብቻውን ውጤታማ አይሆንም፡፡ ድሮ በአገራችን ገንዘብ ያለው ሰው ነጋዴ፣ ነጋድራስ ይሆን ነበር፡፡ አሁን ግን ሁኔታዎች ተለውጠዋል፡፡ ሐሳብ ሆኗል ገንዘብ፡፡ እነ ጎግል፣ እነ ፌስቡክ የሐሳብ ውጤቶች ናቸው፡፡ ሐሳብ ነው ብር እየሆነ የመጣው፡፡ እኛ የምናስተምረው ሐሳብን ከገንዘብ ጋር አቀናጅቶ እንዴት ወደ ሥራ መተርጎም እንደሚቻል ነው፡፡‹‹በዚች አገር አንድ ሰው ሐሳብ ይዞ ሲነሳ፣ ብዙም ተቀባይነት የለውም፡፡ ባንኮች እንዴት ገንዘብ ሊያበድሩት እንደሚችሉ፣ ብር ያላቸው ሰዎች እንዴት ገንዘባቸውን ሊሰጡት እንደሚችሉ እንዲቀምር ነው የምናስተምረው፡፡ አገልግሎት ሰጪዎች ደግሞ እንዴት ሊጠቀሙ እንደሚችሉ፣ ከአራትና አምስት ዓመት ገቢያቸው ጋር እንዲያስተያዩት፤ እንዴት የበለጠ ገቢ ማግኘት እንደሚችሉ፣ ገንዘባቸውን ባንክ ከሚያስቀምጡ ኢንቨስት ቢያደርጉ የተሻለ ገቢ እንደሚያገኙ ማሳመን መቻልን ነው የምናስተምረው ‹‹ከአንድ ቢዝነስ ወጥቶ እንዴት ሌላ የተሻለ ቢዝነስ መጀመር እንዳለበትም እናስተምራለን፡፡ ቀደም ሲል አያቱ ወይም አባቱ ቤንዚን ማደያ ካላቸው ልጃቸውም ቤንዚን ማደያ ነው የሚኖረው፡፡አሁን ግን ያ አይደለም ዘመናዊ ቢዝነስ፡፡ ቢዝነሱ በፊት ከነበረበት አድጎ ነው መገኘት ያለበት፤ ወደ ፈጠራ ነው መሸጋገር ያለበት፡፡ የቢዝነስ ሞዴል አስተዳደር ትምህርት ይህ ነው›› ብለዋል የዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ፕሬዚዳንትና የኤምቢ ኤ ፕሮግራም ሥራ አስፈጻሚ ዋና ዳይሬክተር አቶ አቤቱ መላኩ፡፡ ከተመሰረተ አንድ መቶ ዓመት ሊሆነው ሁለት ዓመት ብቻ የቀረው የሊንከን ዩኒቨርሲቲ አካል የሆነው ዌስተርን ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ባለፈው ሳምንት በሁለተኛ ዲግሪ በኤምቢኤ (Masters of Business Administration) ለ6ኛ ዙር፣ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን (ቢኤ) ዲግሪ ለመጀመሪያ ጊዜ ያስተማራቸውን ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት እዚህ አዲስ አበባ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ በድምቀት አስመርቋል፡፡ ለመሆኑ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ እንዴት በአገራችን (Masters of Business Administration (ኤምቢኤ) ትምህርት መጀመር ቻለ? መቼ? መልሱን አቶ አቤቱ ይነግሩናል፡፡ ከተመሰረተ 98 ዓመታትን ያስቆጠረው፣ በአሜሪካ፣ ካሊፎርኒያ ግዛት ኦክላንድ ከተማ የሚገኘው ሊንከን ዩኒቨርሲቲ በአራት ወይም በአምስት
አገሮች በኤክስቴንሽን ያስተምራል፡፡ የአፍሪካ ተወካይ ናይጀሪያ ነበረች፡፡ ይህ ካምፓስ በፀጥታ ችግር መዘጋቱን አቶ አቤቱ በማስታወቂያ ሰሙ፡፡ እንዴት አፍሪካን የሚያህል አህጉር ያለ ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ተወካይ ይቀራል? በማለት ጠየቁ እኛ ለደህንነታችን ነው ቅድሚያ
የምንሰጠው ተባሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያ አፍሪካን እንድትወክል ተመኙና ኢትዮጵያስ? በማለት ጠየቁ በኢትዮጵያ ሰላም አለ? ኢትዮጵያ (አዲስ አበባ) የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን፣ በርካታ ዓለም አቀፍና አኅጉር አቀፍ ድርጅቶች ያሉባት፣ ፈረንጆች በእኩለ ሌሊት የሚንሸራሸሩባት ናት በማለት መለሱ፡፡ “ለምን ፕሮፖዛል ጽፈህ ለባለ አደራ ቦርድ አቅርበህ አትሞክርም?” አሏቸው፡፡ ፕሮፖዛል ፅፈው አስገቡና ሰዎችም ረድተዋቸው ተቀባየነት አገኙ፡፡ የባለ አደራ ቦርዱ ሊቀ መንበር ግን ጥርጣሬ ገባቸው፡፡ ‹‹ይህ ሰው የተማረው ስለ ቢዝነስ ነው፡፡ የአካዳሚክ እውቀት የለውም፡፡ ታዲያ እንዴት ዩኒቨርሲቲውን መምራት ይችላል?” ሲሉ ጠየቁ፡፡ ቀደም ሲል አቶ አቤቱ ብሉናይል ኢንተርፕራይዝ  ኩባንያ አቋቁመው፣ ለመጀመሪያ ጊዜ አምቦ ውሃንና በደሌ ቢራን ወደ አሜሪካ ወስደው ለ5 ዓመት የሸጡና ያስተዋወቁ ሰው
ናቸው፡፡ እዚህ አገር ቤት በተፈጠረ ችግር ተቋረጠ እንጂ አምቦ ውሃው በአሜሪካ ገበያ ጥሩ ተቀባይነት አግኝቶ ነበር፡፡  ለባለአደራ ቦርዱ ሊቀመንበር ጥያቄ፣ የሊንከን ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ሲመልሱ፣ ‹‹ከአፍሪካ (ኢትዮጵያ) ውሃ አምጥቶ በአሜሪካ ገበያ መሸጥ ከቻለ፣ ይህንን
ዩኒቨርሲቲ አገር ቤት ወስዶ እንዴት ነው መምራት የሚያቅተው?” በማለት ተሟገቱላቸው፡፡ በዚህ ዓይነት በሊንከን ዩኒቨርሲቲ ተወክለው ወደ ኢትዮጵያ ተላኩ፡፡
ሊንከን ዩኒቨርሲቲ… እዚህ (ኢትዮጵያ) ሲመጣ ድንበር ተሻጋሪ ስለሚባል ትምህርት ግልጽ መመሪያ አልነበረም፡፡ ‹‹ጥርጣሬውም ስለነበር ሊፈቅዱልኝ አልፈለጉም ነበር፡፡ ሦስት ወር ሙሉ ከወዲያ ወዲህ በመመላለስ ጫማዬን ጨርሼ ምንም ውጤት ስላላገኘሁ፣ ከፍተኛ ፍርሃትና
ስጋት ገብቶኝ ነበር›› ይላሉ አቶ አቤቱ ሊንከን ዩኒቨርሲቲን በኢትዮጵያ ለማቋቋም ገጥሟቸው የነበረውን ችግር ሲያስታውሱ፡፡ በመጨረሻም  ተስፋ ቆርጠው ወደ አሜሪካ ለመመለስ ሲነሱ፣ ቀደም ሲል ያውቋቸው የነበሩትን ወዳጃቸውን፤ ‹‹ሰላም ሁን›› ለማለት ቢሮአቸው
ደወሉላቸው፡፡ ወዳጃቸውም ‹መቼ መጣህ?›› በማለት ጠየቁ፡፡ አቶ አቤቱ ‹‹አይ፤ ሳላይህ ብሄድ ውቃቢህ ያየኛል ብዬ ነው የደወልኩት እንጂ መሄዴ ነው›› አሉ፡፡፡ ወዳጃቸውም ‹‹መቼ መጣህ›› አሉ፡፡ ‹‹ለዚህ ጉዳይ ነበር የመጣሁት፡፡ አሁን ስላልተሳካልኝ ተስፋ ቆርጨ መመለሴ ነው››
በማለት መለሱ፡፡ ‹‹ስልኩን ዝጋው፤ መጣሁ›› ብለው፤ አቶ አቤቱ ወደ ነበሩበት ሄደው በመኪና ወደ ቢሯቸው ወሰዷቸውቢሮ እንደደረሱ ለምን ወደ ኢትዮጵያ እንደመጡ፤ ያደረጉትን ጥረት፣ አልሳካ ቢላቸው ተስፋ ቆርጠው ለመመለስ እንደወሰኑ በዝርዝር
አጫወቷቸው፡፡ ወዳጃቸው በሰሙት ነገር በጣም ተገረሙ፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ የሚያውቋቸው ሰዎች ስለነበሩም እነሱን በስልክ አግኝተው ስለጉዳዩ አጫወቷቸውና፤ ‹‹እንዲህ ያለ ነገር እንዴት ይታለፋል? ያገር ጉዳይ’ኮ ነው›› በማለት ፋክስ አደረጉላቸው፡፡ ከዚያም አሪጂናል ዶክመንቶችን አገላብጠው ተመለከቱ፡፡ ‹‹ ይህን ይዘህ ማን ጋር ሞከርክ?›› በማለት ጠየቋቸውየ‹‹እገሌ የሚባል ያልሞከርኩበት ባለሥልጣን የለም፡፡ በማለት መለሱ፡፡ ‹‹ለምን አንድ ሦስት ቀን አትቆይም?›› አላቸው፡፡ አቶ አቤቱም፤ ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ጉዳይ አያልቅም፡፡ ስለዚህ ተመልሼ መስራት አለብኝ፡፡ በጊዜ አልቀልድም፣ ስለ ጊዜ አጠቃቀም ነው የተማርኩት›› አላቸው  ሰዎቹም፤ ‹‹ግድ የለም፤ ተስፋ አትቁረጥ፤ እኛም እንረዳሃለን››አሏቸው፡፡
በዚህ ዓይነት ከሚመለከታቸው ቢሮዎች ጋር ግንኙነት መፍጠር ተጀምሮ ፈቃድ ተሰጣቸው፡፡ ፈቃዱን ሲያገኙም ብቻቸውን እንዲሠሩ ሳይሆን፣ አስተማማኝነቱ ከተረጋገጠ ተቋም ጋር ተዳብለው እንዲሰሩ ከኒው ጀኔሬሽን ዩነቨርሰቲ ኮሌጅ ጋር ተዳብለው በ2010 መሥራት ጀመሩ፡፡ ለአንድ ዓመት ከሰሩ በኋላ በተለያዩ ምክንያቶች ከኮሌጁ ጋር ተዳብሎ መስራቱን አስተዳደሩም ሆነ ተማሪዎች ስላልወደዱት፣ እንደገና
አመልክተው ፈቃድ ስላገኙ ነፃ ሆነው በራሳቸው መስራት መጀመራቸውን አቶ አቤቱ አስረድተዋል፡፡
 ዩኒቨርሲቲውን ለመክፈት ግን በጣም ፈታኝ ችግሮች ገጥሟቸው እንደነበር አቶ አቤቱ ይናገራሉ፡፡ ተስፋ ቆርጠው ሊመለሱ ሲነሱ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት በነበሩ ሰዎች ድጋፍ አግኝቶ (እ.ኤ.አ)፣ በ2010 ከኒውጀኔሬሽን ዩኒቨርሲቲ ጋር ተዳብሎ እንዲሠራ ፈቃድ እንደተሰጠው ገልጸዋል፡፡ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የሚያስተምረው ስለቢዝነስ ነው፡፡ ዘመናዊ የቢዝነስ ጥበብ አስተምሮ በማስተርስ (ሁለተኛ) ዲግሪ ያስመርቃል፡፡ ዘንድሮ ግን ለማስተርስ ፕሮግራም ሥልጠና ብቁ የሆኑና ተገቢውን መመዘኛ የሚያሟሉ ተማሪዎችን ለመመልመል ያስችለው ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን አስተምሮ 18 ተማሪዎችን በመጀመሪያ ዲግሪ አስመርቋል፡፡ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁ፣ በዲያግኖስቲክ ኢ-ሜጂንግ (ስካኒንግ፣ ሲኖግራፊ፣) ስፔሻላይዝድ ያደረገ ስለሆነ በሚቀጥለው ዓመት በዚህ እውቀት
አስተምሮ በመጀመሪያ ዲግሪ ለማስመረቅ አቅዷል፡፡ ነገር ግን አንድ ችግር አለበት፡፡ ይኼውም ተማሪዎች ወጥተው ልምምድ የሚያደርጉበት ሆስፒታል ያስፈልጋል ሁለተኛ፣ ለሆስፒታሉ የሚያገለግሉ መሳሪያዎች መግባት አለባቸው፡፡ መሳሪያዎቹን ለማስገባት የጉምሩክ ፈቃድ
ይፈልጋል፡፡ ፈቃዱን ለማግኘት ደግሞ ዕቃዎች መሟላት አለባቸው የሚል ችግር ቢያጋጥማቸውም ይፈታል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡ የእኛ ዩኒቨርሲቲ ልዩ ኳሊቲው (ጥራቱ) የትምህርት አሰጣጡ ካሪኩሌም የሚቀረፀው በ1919 ዓ.ም በተመሠረተውና ዕድሜ ጠገብ በሆነው
ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ነው ያሉት አቶ አቤቱ፣ ከሚያስተምራቸው 11 ኮርሶች ስምንቱን መምህራን ከአሜሪካ ሊንከን ዩኒቨርሲቲ መጥተው እንደሚያስተምሩ፣ ሦስት ኮርሶች ብቻ እዚህ ባሉ መምህራን እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡ እኛ የምንደራደረው በጥራትና ጥራት ብቻ ነው፡፡
የምናስተምራቸውን ጥቂት ሰዎች በጥራት አውጥተን ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እናደርጋለን ዩኒቨርሲቲው በትምህርት መረጃ መጻሕፍት የተሟላ መሆኑን አቶአቤቱ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ኤሌክትሮኒክስ ቤተ መጽሐፍት የተጀመረው በእኛ ዩኒቨርሲቲን ነው፡፡ ዳታ ቤዙ አሜሪካ ሆኖ ተማሪዎች እዚህ ተቀምጠው የሊንከን ዩኒቨርሲቲ ቤተ መጻሕፍት ነው የሚጠቀሙት፡፡ መጽሔትና ጋዜጦችን  ጨምሮ የበርክሌይ ዩኒቨርሲቲ ቤተ መጻሕፍት መጠቀም ይችላሉ፡፡ ከአሜሪካ የሚመጡ መምህራን በኢንተርኔት ከራሳቸው መጻሕፍት ነው የሚያስተምሩት፡፡ የእኛ
ዩኒቨርሲቲ መምህራን ለየት ያሉ ናቸው፡፡ ትምህርታቸው እንደዚህ አገር መምህራን በንድፈ ሐሳብ (ቲዮሪ) ላይ ብቻ የተመሠረተ አይደለም፡፡ ቢዝነስ ላይ ያሉና ሕይወታቸውን እየኖሩበት ያለውን ልምድ ነው የሚያስተምሩት፡፡ ለምሳሌ በምረቃው ላይ የተገኙት የባለአደራ ቦርዱ
ሊቀመንበር የህክምና ዶክተር (አንኮሎጂ- የካንሰር ስፔሻሊስት) ናቸው። ነገር ግን እዚህ ሲመጡ የሚያስተምሩት የ200 ሆስፒታሎች ኃላፊ ስለሆኑ ሊደርሺፕና ኮሙኒኬሽን ነው››  በማለት አብራርተዋል፡፡  ለአንድ አገር እድገትና ለውጥ ትምህርት እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነገር ግን ቁጥር ሳይሆን በጥራት ሲሰጥ ነው የተፈለገው ራዕይ እውን የሚሆነው ይላሉ - አቶ አቤቱ፡፡ ‹‹ የእኛ የወደፊት ዕቅድ ከመዋዕለ ህፃናት እስከ ሁለተኛ ዲግሪና ዶክትሬት ድረስ ከስር መሰረቱ ኮትኩቶ ማውጣት ነው፡፡
የእኛ ዕቅድ እንደ ሀርቫርድና እንደ ስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን ከሥር ከመሰረቱ ኮትኩቶ ማውጣት ነው፡፡ ፐሮፖዛል አስገብተን የመሬት ጥያቄም አቅርበናል” ሲሉ ተናግረዋል፡፡በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ከአሜሪካ- ሳንፍራንስኪስኮ ከሪችሞንድ ከተማ ሳንቴ የተባለ ሬስቶራንት ባለቤት ወ/ሮ መንበረ አክሊሉ በሊንከን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ኃላፊዎች ጋባዥነት ተገኝታ፣ የስኬት ታሪኳን ለተመራቂዎች ተናግራለች፡፡ በሌላ በኩል ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ለመጀመሪያ ጊዜ በተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎች ተሰማርተው ለአገር ኢኮኖሚ ዕድገት የላቀ አስተዋጽኦ ላደረጉት ለአቶ ብዙአየሁ ታደለ፣ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሰጥቷል፡፡ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ባሳለፋቸው ስድስት ዓመታት ብዙ ችግሮችን ቢያጋጥሙትም ዋናው ችግር ቢሮ ክራሲው መሆኑን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የከፍተኛ ትምህርት ጥራትና ብቃት ኤጀንሲ የሚባለው ድርጅት ገምጋሚ ብቻ ሳይሆን ተገምጋሚም ነው ለእኔ፡፡ በድንገት መጥተው የሚጠይቁት የዛሬ 30 እና 40 ዓመት የሚሠራበትን ነገር ነው፡፡ ለምሳሌ በዋይ ፋይ ዘመን ላይ እያለን፣ የግድ ገመድ ያለው ኮምፒዩተር ማሳየት የለብንም፡፡ ኔትወርኩ የታለ? በማለት ይጠይቃሉ›› ብለዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የሚጠይቀው ክፍያ ወደድ እንደሚል አቶ አቤቱ ያምናሉ፡፡ ‹‹እኛ የምናስተምረው የርቀት (non-distance) አይደለም፡፡ በክፍል ውስጥ ከተማሪዎች ጋር ፊት ለፊት (non-Distance) ነው፡፡ ስለዚህ መምህራኑ ከአሜሪካ ሲመጡ የአውሮፕላን ይከፈላል፣ ክፍል ገብተው የሚያስተምሩበት የአበል ብቻ 1400-1500 ብር ይከፈላቸዋል፡፡ ሌላው ክፍያውን የሚያንረው የማስተማሪያ ሕንፃው ኪራይ ነው፡፡ ለሕንፃው ኪራይ የሚከፈለው 85 ሺ ብር ቢቀር፣ በእርግጠኝነት የተማሪዎች ክፍያ ይቀንሳል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአዲስ አበበ ከተማ አስተዳደሩ ይህን ችግር ተግዝቦ ሕንፃ መሥሪያ ቦታ ቢሰጠን፣ ወደፊት የተማሪዎች ቁጥር ስለሚጨምር፣ የትምህርት ክፍያውም ይቀንሳል›› በማለት አስረድተዋል፡፡

እነሆ መፅሐፍት መደብር፣ ሊትማን ቡክስ እና ክብሩ መፅሐፍት መደብር በመተባበር “መፅሐፍን እንደ መሰረታዊ ፍላጎት” በሚል መሪ ቃል፣ በየወሩ መጨረሻ በሚያካሂዱት የመፅሐፍት አውደ ርዕይና የሂስ ጉባኤ፣የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ፣ “አዙሪት” በተሰኘው የደራሲ ነገሪ ዘበርቲ ልብወለድ መፅሐፍ ላይ ሂስ ይቀርባል፡፡ ሥነ ጽሁፋዊ ሂሱንየሚያቀርበው ደራሲና የፊልም ባለሙያ ዳንኤል ወርቁ እንደሆነ የዝግጅቱ አስተባባሪ አቶ በፍቅሩ ዳኛቸው ገልፀዋል፡፡“ትራኮን የመፅሐፍት አውደ ርዕይና የሂስ ጉባኤ” በየወሩ መጨረሻ ቅዳሜና እሁድ በትራኮን ታወር የሚካሄድ ሲሆን የመፅሐፍት እቁብን ጨምሮ ከገበያ የጠፉ መፅሐፍትንና አዳዲሶችን ከ20 እስከ 50 በመቶ የዋጋ ቅናሽ ለሽያጭ ይቀርቡበታል፡፡

የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ አዲሱ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሰባት አገራት ስደተኞች ለተወሰነ ጊዜ ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ከሰሞኑ ያስተላለፉትን ውሳኔ በማውገዝ፣ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የተደረጉ ተቃውሞዎችን እንደሚደግፉ ማስታወቃቸውን ኤንቢሲ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ኦባማ በቃል አቀባያቸው በኩል ባስተላለፉት መልዕክት፣ ሃይማኖትን መሰረት ባደረገ መልኩ በህዝቦች ላይ የሚደረግን አድሎአዊ አሰራር እንደሚቃወሙ ማስታወቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ትራምፕ ያስተላለፉትን ውሳኔ በመቃወም አደባባይ የወጡ ዜጎችን ድርጊት እንደሚደግፉ መግለጻቸውንም አብራርቷል፡፡ ኦባማ መንበረ ስልጣኑን ለትራምፕ ካስረከቡ ወዲህ በአዲሱ አገዛዝ ላይ ትችታቸውን ሲሰነዝሩ ይህ የመጀመሪያው እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ የሰሞኑ የትራምፕ ውሳኔ ኦባማ ከአምስት አመታት በፊት ኢራቃውያን ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ጥለውት ከነበረው የእገዳ ውሳኔ ጋር መነጻጸር እንደሌለበት ቃል አቀባዩ ይፋ ያደረጉት መግለጫ ማስታወቁን አስረድቷል፡፡
ፎክስ ኒውስ በበኩሉ፤ በአገራቱ ላይ የተወሰደው እርምጃ በኦባማ የስልጣን ዘመን የተጀመረና ህጋዊ እውቅና የተሰጠው ጉዳይ መሆኑን በማስታወስ፣ ሰባቱ አገራት ለአሜሪካ የደህንነት ስጋት መሆናቸው ተጠቅሶ፣ የአገራቱ ዜጎች ላይ የተለየ ቁጥጥር እንዲደረግ የሚደነግጉ ህጎች በ2015 እና በ2016 መውጣታቸውን ዘግቧል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ፤ አሜሪካ የወሰደቺው እርምጃ የተመድን መሰረታዊ መርሆዎች የጣሰ መሆኑን ጠቅሰው፣ ትራምፕ በሰባቱ አገራት ስደተኞች ላይ የጣሉትን እገዳ በአፋጣኝ እንዲያነሱ ከትናንት በስቲያ ባስተላለፉት መልእክት ጠይቀዋል፡፡ ሽብርተኞች ወደ አገራት ሰርገው ገብተው አደጋ የመፍጠር ዕድላቸው አሳሳቢ ስጋት መሆኑን የጠቆሙት ጉቴሬስ፤ ይሄም ሆኖ ግን ትራምፕ የወሰዱት እርምጃ አሜሪካንም ሆነ ሌሎች አገራትን ከመሰል ስጋት ለመጠበቅ የሚያስችል ሁነኛ አማራጭ አለመሆኑን አስምረውበታል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ፣ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሰባት የአለማችን አገራት ስደተኞች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ያሳለፉት የእገዳ ውሳኔ እንዳስደሰታቸው አይሲስ እና አልቃይዳን ጨምሮ የተለያዩ ጂሃዲስት ቡድኖች ማስታወቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
“ትራምፕ በአብዛኛው ሙስሊም ህዝብ ያላቸው የኢራን፣ ኢራቅ፣ ሊቢያ፣ ሶርያ፣ ሶማሊያ፣ ሱዳንና የመን ዜጎች ወደ ግዛታቸው እንዳይገቡ ያስተላለፉት ትዕዛዝ፣ ከዚህ ቀደም እንደተናገርነው አሜሪካ ከእስልምና ጋር ጦርነት ውስጥ መግባቷን የሚያረጋግጥ ነው” ሲሉ በተለያዩ ድረገጾች በኩል ባስተላለፏቸው መልዕክቶች ማስታወቃቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ፣ የትራምፕን የስደተኞች ውሳኔ የተቃወሙ 1.7 ሚሊዮን ያህል እንግሊዛውያን፣ በእንግሊዝ ሊያደርጉት ያቀዱት ይፋዊ የስራ ጉብኝት እንዲሰረዝ የሚጠይቅ ፊርማ ያሰባሰቡ ሲሆን በተቃራኒው የትራምፕን ጉብኝት በመደገፍ፣ ፊርማቸውን ያሰባሰቡ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥርም ከ200 ሺህ በላይ መድረሱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ ይህን ተከትሎም የእንግሊዝ ፓርላማ በጉዳዩ ዙሪያ ከሁለት ሳምንታት በኋላ ለመከራከር ቀጠሮ መያዙንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

ላለፉት 33 አመታት ከአፍሪካ ህብረት አባልነቷ ተገልላ የቆየቺው ሰሜን አፍሪካዊቷ አገር ሞሮኮ ሰሞኑን በአዲስ አበባ በተካሄደው 39ኛው የህብረቱ የመሪዎች ጉባኤ ላይ በተደረሰው ውሳኔ መሰረት ወደ አባልነቷ መመለሷን ህብረቱ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የህብረቱ አባል አገራት ከምዕራባዊ ሰሃራ ጋር በተያያዘ የተነሳውን ጥያቄ በተመለከተ ባለፈው ማክሰኞ ጠንከር ያለ ክርክር ካደረጉ በኋላ በደረሱት ስምምነት ሞሮኮ 55ኛዋ የህብረቱ አባል ሆና ዳግም እንድትቀላቀል ወስነዋል፡፡
“በስተመጨረሻም ወደ ቤታችን ተመልሰናል” ብለዋል የሞሮኮው ንጉስ ሞሃመድ ስድስተኛ፣ ህብረቱ አገሪቱ ወደ አባልነቷ እንድትመለስ መወሰኑን ተከትሎ ባደረጉት ንግግር፡፡ ሞሮኮ ዳግም የህብረቱ አባል ለመሆን ባለፈው አመት ሃምሌ ወር ላይ ባቀረበቺው ጥያቄ መሰረት፣ በህብረቱ አባል አገራት በተሰጠ ድምጽ ወደ አባልነቷ መመለሷ የተነገረ ሲሆን አገሪቱ ከሶስት አስርት አመታት በኋላ ወደ ህብረቱ አባልነቷ ለመመለስ ጥያቄ ማቅረቧ በውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋ ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማድረጓን ያሳያል ተብሏል፡፡
እ.ኤ.አ በ1984  የያኔው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በሞሮኮ ስር ትተዳደር ለነበረቺው ምዕራባዊ ሰሃራ፣ ራሷን የቻለች አገር ሆና መቀጠል የምትችልበትን እውቅና መስጠቱን ተከትሎ፣ ሞሮኮ ከህብረቱ አባልነቷ መውጣቷንና ለ33 አመታት ያህል ብቸኛዋ የአፍሪካ ህብረት አባል ያልሆነች አፍሪካዊት አገር ሆና መቆየቷን ህብረቱ ባወጣው መግለጫ አስታውሷል፡፡

   የቅንጦት ኑሮ የሚገፋው ተዋናዩ፣ የወር ወጪው 2 ሚ. ዶላር ነው
     “ፓይሬትስ ኦፍ ዚ ካረቢያን” በሚለው ድንቅ ፊልም የሚታወቀው ዝነኛው የፊልም ተዋናይ ጆኒ ዲፕ፣ ለመጠጥ በወር 30 ሺህ ዶላር እንደሚያወጣና በተለያዩ የቅንጦት ነገሮች በየወሩ በድምሩ በአማካይ 2 ሚሊዮን ዶላር እንደሚረጭ የዘገበው ቢቢሲ፤ ይህ ያልተገባ አባካኝነቱ ለከፋ የገንዘብ ቀውስ እየዳረገው እንደሚገኝ መነገሩንም ገልጧል፡፡
የጆኒ ዲፕ የቢዝነስ ማናጀሮች፣ግለሰቡ እንዳሻው በሚበትነው የገንዘብ አወጣጡ ሳቢያ ለከፋ ቀውስ እየተዳረገ እንደሚገኝ ማስታወቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ 14 ያህል እጅግ ውድ የመኖሪያ ቤቶችንና 12 የውድ ንብረቶች ማከማቻ ቤቶችን ለመግዛት ብቻ ከ75 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ማድረጉን መግለጻቸውን አስረድቷል፡፡
የተዋናዩ የቢዝነስ ማኔጅመንት ቡድን አባላት ይህንን መረጃ ይፋ ያደረጉት፣ ግለሰቡ ተገቢውን ግብር በወቅቱ ባለመክፈል ለከፍተኛ የገንዘብ ቅጣት ዳርገውኛል፤ በወጉ አላስተዳደሩልኝም በሚል በአባላቱ ላይ የ25 ሚሊዮን ዶላር ክስ መመስረቱን ተከትሎ እንደሆነም ዘገባው ገልጧል፡፡  
የቡድኑ አባላት በበኩላቸው፤ የጆኒ ዲፕ ዝርክርክነትና ገንዘብ አባካኝነት ራሱን ለቀውስ እየዳረገው እንደሚገኝ በመግለጽ፣ በወር 30 ሺህ ዶላር በማውጣት ከውጭ አገራት ገዝቶ ያስገባቸውን የወይን መጠጦችና ለግል አውሮፕላኑ ያወጣውን 200 ሺህ ዶላር ጨምሮ ያለአግባብ ያወጣቸውን ወጪዎች ዘርዝረው ይፋ አድርገዋል፡፡

  ብራንድ ፋይናንስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው የ2016 እጅግ ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው የዓለማችን ታዋቂ የንግድ ምልክቶች ዝርዝር ውስጥ ጎግል በቀዳሚነት ተቀምጧል፡፡
ተቋሙ በ500 የዓለማችን ታዋቂ የንግድ ምልክቶች ዙሪያ የሰራውን ጥናት ጠቅሶ ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፣ ታዋቂው የቴክኖሎጂ ኩባንያ ጎግል ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 የገበያ ዋጋውን በ24 በመቶ በማሳደግ፣ 109.5 ቢሊዮን ዶላር በማድረስ ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡ ጎግል በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016 የአለማችን እጅግ ውድ ያለው የንግድ ምልክት ሊሆን የበቃው፣ በአመቱ ያስመዘገበው የማስታወቂያ ገቢ በማደጉ ምክንያት ነው ያለው ዘገባው፤ የኩባንያው የማስታወቂያ ገቢ በዓመቱ የ20 በመቶ እድገት ማሳየቱንም አስታውቋል፡፡
ለአምስት ተከታታይ አመታት የአለማችን ቁጥር አንድ ውድ የንግድ ምልክት ሆኖ የዘለቀው አፕል በበኩሉ፣ በ2015 የነበረው 145.9 ቢሊዮን ዶላር የገበያ ዋጋ በአመቱ የ27 በመቶ ቅናሽ አሳይቶ ወደ 107.1 ቢሊዮን ዶላር ዝቅ በማለቱ ወደ ሁለተኛ ደረጃ የወረደ ሲሆን፣ ታዋቂው አማዞን በ106.4 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃን መያዙ ተነግሯል፡፡ ኤቲ ኤንድ ቲ በ87 ሚሊዮን ዶላር አራተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ፣ ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ በ76.3 ሚሊዮን
ዶላር አምስተኛ ደረጃ መያዙን ዘገባው ገልጧል፡፡

Sunday, 05 February 2017 00:00

ማራኪ አንቀፅ

  ብሔርተኝነት፣ ፅንሰ ሐሳቡና መዘዙ

     ብሔርተኝነት ከብሔር ጋር ተጣምሮና ተያይዞ የሚፍታታ አይዲዮሎጂ፣ ስሜትና በሁለቱ ላይ ተመርኩዞ የብሔሩን ዓላማ ለማሳካት የሚደረግ እንቅስቃሴ ብቻ አይደለም፡፡ ከዚያ በላይ ደርዝና ጥልቀት ያለው ፅንሰ ሐሳብ ነው፡፡ በቅድሚያ ብሔር የተሰኘውን ግንዛቤ ፍቺና ለፈረንጂኛው አቻ ትርጉም ማግኘቱ ነው ለብዙዎቹ የሚቀለው፡፡ የኢትዮጵያ የተማሪዎች እንቅስቃሴ የጆዜፍ እስታሊንን ስመ ጥር ፍቺ ዋና ማጠንጠኛ በማድረግ የተከተለውም ይህንን አቅጣጫ ነው፡፡ እሱም ቀደም ሲል የተጠቀሰውን ብሔር ማለት በታሪክ ሂደት በጋራ ቋንቋ፣ መሬት፣ ኢኮኖሚያዊ ህይወትና በጋራ ባህል (ካልቸር) በሚገለጽ/ በሚንጸባረቅ ስነ ልቦናዊ ቅኝት (Make Up) ላይ የተመሰረተ የተረጋጋ ሕዝብ ነው የሚለው ነው፡፡ በፍቺው ውስጥ ስለተቀመጠው እያንዳንዱ ቃል ብዙ፣ ብዙ ማለት ይቻላል፣ ተብሏልም፡፡ ይህንን ትርጉም እስታሊን አቶ ባወር (1881-1938) ከተባለው የኦስትሪያ የትዮሪ አፍታችና ፖለቲከኛ የተዋሰው ነው የሚሉ አሉ፡፡ ወደ እዚያ አንገባም፡፡
ፅንሰ ሀሳቡን ከበርካታ የእይታ ማዕዘናት ሲመለከቱት፣ ልክ እንደ ማንነት አስቸጋሪ ንባብ ቃል ነው፡፡ በርካታ መጽሐፍትና ድርሳናት እንደሚያመለክቱት፤ በዚያ የታሪክ መጋጠሚያ ላይ ብሔሩ ወይም ስብስብ ማጠንጠኛ አድርጎ አፅንኦት በመስጠት የራሱን ጥቅልል መንግስት ወይም መንግስት አከል አሃድ ለመመስረት ይገባኛል ጥያቄ አስነስቶ፣ የራሴ ወገን የሚላቸውን መቀስቀስ መቻሉ ላይ ነው የቁም ነገሩ እንብርትና አንደርዳሪው ግፊት። ይህ ስሜት፣ አይዲዮሎጂና እንቅስቃሴ ነው በአንድ ላይ ብሄርተኝነት የሚሰኘው፡፡ ዓላማውን ከግቡ ለማድረስ ብሔርተኝነት ከላይ ያመለከትናቸውን የጋርነቶች ሁሉ መቀስቀሻ ሊያደርግ ይችላል፤ ተራ በተራ ወይም ሁሉንም በአንድ ላይ፡፡
ኤትኔሲቲ ማኅበራዊ አደረጃጀት ነው ከተባለ ደግሞ፣ እሱም በተራው ከብሔርተኝነት ጋር ያለውን ተዛምዶና ተያያዥነት መመልከቱ ተገቢ ይሆናል። ልክ እንደ ብሔርተኝነት ኤትኒሲቲም አንድ ዓላማ ግብ ለማስመታት እስከ ተደረጀ ድረስ በሦስቱም የጋራነቶች ቀስቃሽነት በዓላማው ላይ ያነጣጠረ አካሄድ ይከተላል፡፡ ለዓላማው ግብ መምቻ ሌሎች የጋራነቶችንና አላባዎችንም ለመጠቀም ይሞካክራል። ለቅስቀሳውና ለውዝግብ የሚቀርቡት የመፍትሔ ሀሳቦች ግን የተለያዩ መሆናቸው አይቀርም፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ የዘር ፖለቲካ የተሰኘው መስተጋብር ከአጠቃቀሙ አኳያ ሲታይ ይበልጥ ኤትኒሲቲን የሚገልጽ ይመስላል፡፡
ብሔርተኝነትን እንደማንነት ማደራጃ፤ እንደ ስሜት እንደ እንቅስቃሴና እንደ አይዲዮሎጂ ጠልቀን ለመተንተንና ለማፍታታት መሞከሩ የሚያዛልቅ አይሆንም፡፡ ስብስቦችን የሚያፋጥጣቸውና የሚያጋጥማቸው የጋራነትን መመርኮዣ አድርገው በአንድ ርእሰ ጉዳይ ላይ ሳይስማሙ ሲቀሩ (ሲወዛገቡ) ነው ብለናል፡፡ በሌላ አባባል በመሃላቸው የውዝግብ ምክንያት ሲፈጠር ነው፡፡ የውዝግቡ መነሻም በአመዛኙ ብሔርተኝነተ እራሱ ነው፡፡ እሱም በተራው ከብሔራዊ መንግሥታት ምሥረታ ወዲህ የተለያዩ ስብስቦች ተቧድነው የሚሻኮቱበት፣ በአንድ መንግሥት ሥር ተጠቃልለን በአንድነት እንኑር ወይስ እያንዳንዳችን ለየራስ መንግሥት ምሥረታ እውን መሆን በየፊናችን እንንቀሳቀስ በሚለው ርእሰ ጉዳይ ላይ መስማማት ሲያቅታቸው ነው ጠቡ የሚጫረው፣ ከታሪክ መዛግብት እንደታየው፡፡ በዘመነ መንግሥተ ብሔር ምሥረታ የአብዛኛው የውዝግቦች መነሾ ይኸው ብሔርተኝነት ነበር፡፡ ገባ ተብሎ ማፍታታት ሊያስፈልግ ነው፡፡
ብሔርተኝነት ብሔሮች (ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች) የራሳቸውን መንግሥት ለመመሥረት ማንኛውም መብቶች የሚሏቸውን ሁሉ ለማስከበር ወይም ለማስመለስ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ በሙሉ በዚህ ውስጥ መካተታቸው ሊያነጋግር ይችል ይሆናል። በዚህ መጽሐፍ ይህን የተጠቀምኩት የራስን መንግሥት ለመመሥረት ከሚደረገው ተጋድሎ ጋር በአመዛኙ የተያያዙ ስሜቶችን፣ እንቅስቃሴዎችንና አይዲዮሎጂን እንዲያመለክት ነው፡፡ ከዚህ በታች የሚገኙትን ወይም እንደ ልዕለ ብሔርተኝነት ያሉትን ስሜትም ሆነ አይዲዮሎጂ ወይም እንቅስቃሴ አልፎ አልፎ ካልሆነ በስተቀር አልተካተቱም፡፡
በኋላ ላይ እንደምንመለከተው በኦሮሞ ጥያቄ ዙሪያና ሳቢያ የተቀሰቀሰውን ስሜትና የተቀረፀውን ርዕዮተ ዓለም እንዲሁም መመለሻ ሐሳቦች ብሔርተኝነት ነው ያልኳቸው፡፡ በስልጤና በጀበርቲ የመብት ጥያቄ ሳቢያና ዙሪያ የተቀሰቀሱትን ግን እንደ ትሕተ ብሔርተኝነት ስለተመለከትናቸው ብሔርተኛ አልተባሉም፡፡ ነገር ግን ከወዲሁ ተገቢ ግንዛቤ ማግኘት ያለበት፣ ጉዳዩ መታየት የሚኖርበት ስብስቡ ካነሳው የመብት ጥያቄ አንፃር እንጂ ከእድገት ደረጃው ጋር ምንም ተዛምዶ ወይም ግንኙነት ሊኖረው እንደማይገባ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ በአገራችን የሚገኙ ሁሉም ስብስቦች የእድገት ደረጃቸው ምንም ይሁን ምን ብሔረሰብ የተሰኘው፣ በተቻለ መጠን፣ የተጋነነ ግምትና ትርጉም እንዳይሰጠው ተብሎ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ጥናት ኢንስቲትዩት አጠቃቀምን በመከተል በማንኛውም የእድገት ደረጃ ላይ ሲገኝ ማንኛውም ስብስብ፣ ብሔረሰብ በሚለው አማካይ ስያሜ እንዲታወቅ መመረጡን የቱን ያህል ችግሩን እንዳቃለለ አናውቅም፡፡
ናሽናሊዝም ወይም ብሔርተኝነት ያንድ ስብስብ አባላት ከየብሔራቸው (ኔሽን) ጋር የፈጠሩት ጠንካራ ቁርኝት ነው ሊባል ይችላል፡፡ ይህ ትስስር አይዲዮሎጂ ሆኖ ከሌሎቹ ተለይተን የራሳችን መንግሥት መመሥረት አለብን ሲሉ ነው፣ ከስሜት አልፎ ከሌሎች ስብስቦች ጋር ወደ መፋጠጥና ግብግብ ተግባራዊ እንቅስቃሴ የሚገቡት፡፡ በዚህ መነሻነት ከሌሎች ዓላማቸውን ከሚፃረሩ ወይም የሚፃረሩ ከሚመስሏቸው ጋርም ይጋጫሉ፡፡ ይህ ስሜትና አይዲዮሎጂ ከጥንቱ ከጧቱ የነበረና ወደፊትም የሚኖር ነው ባዮች አሉ፡፡ በእነሱ አመለካከት መሰረቱና መነሻው ደምና የአጥንት የዘር ትውልድ ዝምድና ነው፡፡ ይህንን አመለካከት ነው ፈረንጆቹ The primordialist perspective/ የበኩራዊነት አተያይ ብለው የሚጠሩት፡፡
ሌላው አመለካከት ፈረንጆቹ The modernist perspective/ የዘመነኝነት አተያይ የሚሉት ፍረጃ ነው፡፡ እሱም ብሔርተኝነት ከተወሰነ የማኅበረሰብ አወቃቀር ጋር ተያይዞ በቅርብ ዘመን ብቅ ያለ ክስተት እንደሆነ አድርገው የሚመለከቱበት አረዳድ ነው። ዋናው ቁም ነገር ግን ስብስቡ በአባላቱ መካከል ባለው የዘር፣ የካልቸር፣ የሃይማኖትና የሌሎች ተዛማጅ የጋራነቶች ምክንያት እያንዳንዱ ብሔረሰብ በራሱ ጠቅልል መንግሥት ሥር መጠቃለል አለበት የሚለውን መሠረተ ሀሳብ የሚያቀነቅን መሆኑ ነው፡፡ በባለብዙ ብሔር አገር ውስጥ የጋራነቶችን የማይጋሩትን ራሳቸውን በራሳቸውን የሚያስተዳድሩበት አደረጃጀት ይኑር ባዮች በዚህ ውስጥ ይካተቱ ወይስ አይካተቱ የሚለው ደግሞ ራሱን የቻለ ክርክር ነው፡፡ ለጊዜው እዚያ ውስጥ እንገባም፡፡     
ምንጭ፡- (ከደራሲ ዩሱፍ ያሲን ‹‹ኢትዮጰያዊነት፤ አሰባሰቢ ማንነት፤ በአንድ አገር ልጅነት›› የተሰኘ መፅሃፍ
የተቀነጨበ፤ ህዳር 2009)

ርዕስ - በፍቅር ስም
ደራሲ - ዓለማየሁ ገላጋይ
የሕትመት ዘመን - 2009
የገጽ ብዛት - 216
የመሸጫ ዋጋ - 71.00 ብር
ማተሚያ ድርጅት - Eሪቴጅ ኅትመትና
ንግድ ኃ/የ/የግል ማህበር
የታተመበት ቦታ - አዲስ አበባ
             (ቅኝት - መኩሪያ መካሻ)

    በፍቅር ስም የዓለማየሁ ገላጋይ የአእምሮ àማቂው ስድስተኛ ልብ - ወለድ ነው፡፡  ዘንድሮ ለጥበብ አድባር ያቀረበው ግብር መሆኑ ነው፡፡  ጥበብ ምሷን አገኘች፡፡ ስራዎቹ የአዳዲሶቹ ደራሲዎቻችን አዲስ ማዕበላዊ (new  wave) አጻጻፍ አካል ነው፡፡ እኛም አዲስ የአጻጻፍ ስልት ወደ ያዘው በፍቅር ስም ድርሰት ስናመራ ፍጹም ወደ አልተጠበቀ የከተማ ዳርቻ እንደርሳለን፡፡  በመጀመሪያ ከድህነት ወለል በታች የሚኖሩ የቤተሰብ አባላትን እናገኛለን፡፡  ፍጹማዊው ድህነት ቀይዶ ይደቃቸዋል፡፡  መቸቱ ግልጽ ነው - የምናውቀው የጉለሌው የሩፋኤል ሠፈር ስለሆነ።  ጊዜው ከደርግ ዘመን ጀምሮ እስከ መጀመሪያው የኢህአዴግ ድል ማድረጊያ ወቅት የትረካ መስመሩን ይዞ ይጓዛል፡፡  ማህበራዊ አካባቢው በጊዜው በነበረ አንባገነናዊ ሥርዓት ውስጥ ይካሄዳል፡፡  በመሠረቱ የሩፋኤል ሠፈር ለኢትዮጵያ የሥነ -ጽሁፍ ታሪክ አዲስ አይደለም፡፡ በሀዲስ ዓለማየሁ፤ በብርሃኑ ድንና በሌሎችም ሥራዎች የትወና መድረክ ነበር።  በአሁኑ ጊዜ ደግሞ የከተማችን ኋላ ቀር አካባቢ ሳይሆን አይቀርም፡፡  የተረሱ፤ የተገፉ - የተገፊዎች ሠፈር መሆኑን እንገነዘባለን፡፡
የዓለማየሁ ድርሰቶች በደምሳሳው ሲታዩ የደስተዮቭስኪ፤ የቼሆቭና የላቲን አሜሪካው ገብርኤል ጋርሻ ማሪኩዝ ተጽዕኖ ይታይባቸዋል፡፡  ዓለማየሁ ልክ እንደ ማርኩዝ ሁሉ “የራሱን ዓለም“ ፈጥሯል፡፡  ይህ የራስ ዓለም ከገጽ ወደ ገጽ በተለያየ መንገድ የሚገለጽና አንባቢን ባልተለመደ ጉራንጉር ይዞ የሚነጉድ መገነጢሳዊ ልጓም አለው፡፡ የአእምሮ ምግብነቱም (መገብተ-አእምሮነቱ) እንደተጠበቀ ሁኖ፡፡
ገጾቹን በገለበጥን ቁጥር የዚች ምስኪኖች ሠፈር ሰዎች ማን እንደሆኑ? ለምን እንደሚኖሩ፤ እንዴት እንደሚኖሩ? እንመለከታለን፡፡  በዚያ ፉርጎ ቤት ውስጥ የሚኖሩት አባላት ዥንጉርጉር ናቸው፡፡  ኢትዮጵያዊ ዥንጉርጉርነት፡፡  በመካከላቸው ግጭት አለ፡፡  ድርሰቱን ያቆመውም ይኸው ነው፡፡  የሥነ - ልቡናና የዕምነት አለመጣጣም ይስተዋላል፡፡  ልክ ቼሆቭ ሲጠቀምበት እንደነበረው ሁሉ ዓለማየሁም አንባቢው በግሉ እንዲያስብ ያደርጋል፡፡  በድርሰቱ እሱ ያላሟላውን አንባቢው እንዲያሟላ ዕድል ይሰጠዋል፡፡ ለዚህ ነው በአንዳንድ የድርሰቱ ክፍሎች የተንጠለጠሉ የሚመስሉንን ጉዳዮች ራሳችን በዕዝነ-ልቡናችን እንድናጠናቅቃቸው የምንገደደው፡፡
በድርሰቱ ውስጥ የሚታዩት “ትንንሽ ሰዎች“ በውስጣዊ ማንነታቸው “ትልቅነታቸው“ ይወጣል።  ትንንሽ እንዲሆኑ ኮድኩዶ የያዛቸውን ሰንካላ ጉዳይ ዓለማየሁ አንጥሮ ያሳያል፡፡  በቀድሞ የማንነት ኩራት ውስጥ ወደፊት የተስፋ ህይወት ይታሰባል። ግን ደግሞ ህይወታቸው ከእጅ አይሻል ዶማ ነው፤ ተለውጦ አናይም፡፡  በወንፊት ላይ የሚወርድ ውሃ ይመስል ምንም አይቋጥርም፡፡ ፀሐፊው በዘÈና በሚያስደምም መንገድ ለወታደራዊው ኦሊጋርኪ ያለውን ጥላቻም አስመስክሮበታል፡፡ በደሉን ያጋልጣል፡፡
ዓለማየሁ ከአሁን ቀደም ባሳተማቸው ድርሰቶቹ በኢትዮጵያዊያን አንባቢያን ዘንድ መልካም ሥፍራን አግኝቷል፡፡  የጥበብ አድባር እጣኗን አጢሳ፤ ሽቱዋን ነስንሳ ተቀብላዋለች፡፡  የአሳታሚን ክፉ ወጥመድ አልፎ ለዚህ መብቃት በራሱ መታደል ነው፡፡  ካለፉት ድርሰቶች ለእኔ በግል «አጥቢያ» እና «ቅበላ» ማርከውኛል፡፡  ጥልቀት አላቸውና፡፡
ከላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት ደራሲው የጊዜውን አምባገነንነት ለማሳየት ቀጥታ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ አይከፍትም፡፡ እንደ ልብ - ወለድ ፀሐፊነቱ ሰዋዊ ሁኔታን (Human situation) ማሳየት ግዴታው መሆኑን በውል ተገንዝቧል።  ምንም እንኳ ግላዊ የፖለቲካ አቋም ሊኖረው ቢችልም “ትክክል“፤ “ስህተት“ በሚል የፖለቲካ አቋም ይዞ አይፈርድም፡፡  “የትናንሾቹ ሰዎች“ ህይወት እንዲህ በቀላሉ እንደማይከናወን በሰራተኛ ሠፈር ወጣቶች አሳይቷል፡፡ ገላጭ ቃላቶቹ፤ ፍልስፍናዊ ማነጻጸሪያዎቹ ወደር የላቸውም፡፡ የነፍስ ሲቃቸው ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ በተለይ አንዳንድ የሚጠቀምባቸው ቃላቶቹ የቦረን ጎረምሳ የወረወረው ጦር ሆኖ ይሰማናል፡፡ አብዛኞቹ ደግሞ ሮማውያን የገነቡአቸው የዕብነበረድ ሀውልቶች ወይም እንደ ፋርስ ወላንሳ ትንቡክ ትንቡክ ስለሚሉ አይጎረብጡንም፡፡ ይዘው ያንፈላስሱናል፡፡ አቤት ምቾት - ጣ!
ዋናው ገፀ - ባህርይ ሆኖ የሚቀርበው አባቱ (ቢዘን) ህዝባዊ ብሔርተኛ ነው፡፡ “ብዜን በሰሜን ኢትዮጵያ በኩል የገንጣይና አስገንጣይ ጫና ተቋቁሞ ኤርትራን ለጓድ መንግሥቱ ያስረከበ ተራ ኢትዮጵያዊ“ ሲል ይገልፀዋል፡፡  ይህን ሰው የዚያን ዘመን ብሔራዊነት የተጎናጸፈ ነውና የጎሳ ወይም የመንደር ልጅነት አይበግረውም፡፡  የሀገር ጉዳይ ዋነኛው የህይወት እሳቤ የሆነባቸው እልፍ አእላፍ ሰዎች ተምሳሌት ነው፡፡  በተቃራኒው ሌሎች በየመሸታ ቤቱ አሸሼ ገዳሜ ሲሉና ልጆቻቸውን ሲያሳድጉ (እሱ ልጆቹን በትኖ) እንደ ቢዘን ያሉ ሰዎች ብቻ ሞተው እንዲያኖሯቸው የሚጥሩ ስግብግብ ዜጎች መኖራቸውንም እንመለከታለን፡፡ “የሞተልሽ ቀርቶ፤ የገደለሽ በላ“ ይባል የለ? ለዚህም ነው ቢዘን ለሁለተኛ ጊዜ እንዲዘምትላቸው (እንዲሞትላቸው) የሚላከው፡፡  እዚህ ላይ ነው እንግዲህ ስለ ሀገር ጉዳይ ዕዳ የመክፈል ጣጣ በእነዚህ ልዩ በሆኑ “ትናንሽ ሰዎች“ ጫንቃ ላይ የወደቀው፡፡  ዓለማየሁ በዝምታ አልተመለከታቸውም፡፡ በስስ ብዕሩና በአሽሙራዊ አፃፃፉ ወጋ፤ ወጋ ያደርጋቸዋል፡፡
የዓለማየሁ ቀልዶችና ገለፃዎች ሠርሥረው ደም ስር ውስጥ የሚቀሩ ናቸው፡፡  አልፎ አልፎ ለማዋዣነት ስለሚያገለግሉ ጣዕም ያለው ዜማ ሆነው ይሰሙናል፡፡  የታሪክ መስመሩን ተከትለን እንድንጓዝ የሚያደርጉ ፊት ለፊታችን የተወረወሩ የወርቅ ሣንቲሞች ናቸው ብንል ማጋነን አይሆንም።  ለምሣሌ ጥሩንባን እንውሰድ፤ - “የፀበኛ በሬ ቀንድ ይመስላል፡፡  ከቅርብ አይቼው አላውቅም፤ ጉርብርብ መዳብ ነው፡፡ ፈንጣጣ ውግ የመሰሉ ጉድጓዶቹ በዕድፍ ጠቁረዋል፡፡ አፉ በክርና በፕላስቲክ ተጠቅልሎ ወፍሯል …”
ባልና ሚስቱ መሓል ዕውነተኛ የትዳር መሠረት ተጥሏል፡፡  የማይሰበር ግንኙነታቸው ጥሩና መጥፎን አሳልፎ ቆይቷ    ል፡፡  ባለቤቱ የባዕድ አምልኮና የቤተክርስቲያን ሰው ናት፡፡  ሁለቱን በአንድ ላይ ታራምዳለች፤ እንደ ማንኛውም የሰፈር ባልቴት። እናት የቤተሰቡ ዋና የህይወት ድልድይ፤ ለፍቶ አዳሪና የቤቱ ዋልታ ናት! ወጥዋ ከሩቅ የሚጣራ ባለ ሙያ፡፡
የበፍቅር ስምን የአጻጻፍ ስልት ደግሞ ለማየት እንሞክር፡፡  የዓለማየሁ የአጻጻፍ ስልት እምን ላይ እንደሚወድቅ ለመለየት አስቸጋሪ ሆኗል።  በምናባዊና በዕውኑ አጻጻፍ ስልት መሃል እንጎቻ ትረካዎች እንደ ሰንሰለት ተያይዘው የሚቀርቡ ናቸው፡፡ በሀገራችን አልተለመደም፡፡ ባለፉት 300 ዓመታት የተፈጠረውን የበርሌክስን የሥነ-ጽሁፍ (Burlesque Literature) መንገድ የተከተለ ይመስለኛል፡፡ በኋላም በ1960ዎቹ የተፈጠሩ new waves::  በርሌክስን “ወዘበሬታ አጻጻፍ“ እንበለው ይሆን? (የሥነ - ጥበብ ጠበብት አስተያየት ቢሰጡበት መልካም ይመስለኛል)፡፡ የበርሌክስ  ዋናው መለያው ህይወትን በቧልታይና አቋራጭ መንገድ ማቅረብ ነው፡፡ አጻጻፉ ያልተለመደና በፈጠራውና በድርጊቱ  መካከል አለመመሳሰል ይታያል፡፡ በድርሰቱ ውስጥ የቀረቡት ገፀ-ባህሪያትም “በአጭር ቁመት፤ በጠባብ ደረት” እንዲሉ እጥር ምጥን ያሉ ናቸው።  ወለፈንዳዊነትም ይታይባቸዋል፡፡ እንደነ ቹቹ ወይም እንደነ ቻይና ሆነው ሲቀርቡ እንመለከታለን።  አይነኬ አባባሎች ወይም ልምዶች ወደ አደባባይ ይወጣሉ፡፡
“በፍቅር ስም“  የትረካ ሰንሰለቱ ክፍል ሁለት ላይ ሲደርስ ውጥረቱ ጥልቀት ያገኛል፡፡  ታለ በመጀመሪያ መደብ (እኔ) ውስጣዊ የባህሪያት ግጭት ውስጥ የወደቀ ነው፡፡ የሚወዳት ሲፈን ስለምትወልድለት ብቻ የሚጠላት ትሆናለች፡፡  
ልክ እንደ ካፍካ ሜታሞሪፎሲስ ከአንድ አካልነት ወደ ሌላ ልዩ  አካልነት የመለወጥ አባዜም ይጠናወተዋል፡፡  በአንድ ጊዜ ከአልአዛርነት (ታለ) ወደ ቹቹነት ይለወጣል፡፡ ነፀብራቅነት ይገለጣል። ያ ከጉለሌ የተነሳው ፍቅር፤ ሠራተኛ ሠፈር ድረስ ተጋግሎ ይዘልቅና መጨረሻው ግን ፍሬ አልባ ይሆናል፡፡  ፍቅር ሲደምቅ፤ እንደ አበባ ሲፈካና  ፍሬነቱ ሲጎመራ አናይም፡፡  ፍሬው በመፈጠሩ ወይም በማርገዟ ምክንያት ከጉለሌ ላትመለስ ትወጣለች፡፡  መጥፎ ቆሌ ሆና ትቀራለች፡፡
በፍቅር ስም ከአንዳንድ ህፀፆች የፀዳ አይደለም።  በተለይ አንዳንድ ቦታ ላይ የንባብ ፍሰቱን የሚያዘናጉሉ፤ ትርጉሙን የሚያደበዝዙ አሉበት (ገፅ 133)፡፡  በክፍል አንድ የተዘጋ ፋይል በክፍል ሁለት ካለ ምክንያት ሲደገም ትኩረትን ይፈታተናል።  አንዳንድ የሰደራቸው መጠይቆችና ምልልሶች  ወደ ተራ - ፈላስፋነት እንዳያወርደው መጠንቀቅ አለበት።
ክፍል ሦስት በትንቢተ ኢሳያስ ይደመደማል። ይደመደማል ከማለት ይልቅ ንግር (foreshadow)  ሆኖ ይጠናቀቃል፡፡ ምናልባትም ደራሲው ወደፊት ጀባ ሊለን የፈለገውን የፈጠራ ሥራ ጠቁሞን ይሆን? ጊዜ መልስ ይሰጠናል። Jean-Paul Sartre የተባለው ደራሲ፤ “ለምን እንጽፋለን?“  በሚለው ጽሑፍ አንድ ገጠመኙን ያጋራናል። አንድ ጀማሪ ሰዓሊ አስተማሪውን፤ “መቼ ይሆን ስዕሌ መጠናቀቁን የማውቀው?” ሲል ይጠይቀዋል።  አስተማሪውም፤ “በመደመም ስሜት ውስጥ ሆነህ ስዕልህን ስትመለከትና ለራስህ እኔ ነኝ ይህን የፈጠርኩት! ማለት ስትችል ነው” ብሎ መለሰለት ይለናል፡፡  ስለዚህ ዓለማየሁም “ፈጠርኩ እንጂ” “አላደርገውም!” እንዳይል የጥበብ አድባር ትታደገው።    

Sunday, 05 February 2017 00:00

የግጥም ጥግ

  እኛ እና እድገት
እንደ ዜናውማ ….. እንደሚናፈሰው፣
ቀድመነው ሄደናል ….. እድገትን አልፈነው፣
ግን ወሬውን ትተን ….. እውነቱን ካሰብነው፣
ለእኛ የመሰለን ….. ጥለነው የሄድነው፣
ብዙ ዙር ደርቦን ….. ከኋላ ቆሞ ነው፡፡

     የቀን ጨረቃ
ፀሐይ ከለገመች
ቀን ላይ መውጣት ትታ፣
ለጉም ለደመናው
ካሳለፈች ሰጥታ፣
ታስረክባትና
የራሷን ፈረቃ፣
ትምጣና ታድምቀው
የእኛን ቀን ጨረቃ፡፡

    እንባህን ቅመሰው
መስታወት አትሻ
ሰውም አታስመሰክር
እንባህን ቅመሰው
ለማንም ሳትነግር፡፡
ውሃ ውሃ ካለህ
የጨው ጣዕም ከሌለው
ኡኡታህን አቁም
ለቅሶህ የውሸት ነው!
        (ከገጣሚ ሳምሶን ይርሳው ጌትነት “ምልክት” የግጥም መድበል

“ምን አይነቱ ነውር የማያውቅ አሳማ ነው!...” - ሪሃና
     “ያሉት ከሚጠፋ፣ የወለዱት ይጥፋ!...”
ብለዋል - ትራምፕ፡፡
በምርጫ ቅስቀሳ ዘመቻቸው ላይ፣ “ከተመረጥኩ ስደተኞች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ እከለክላለሁ” ሲሉ የከረሙት አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ፤ በለስ ቀንቷቸው ባሸነፉና ወደ ነጩ ቤት ሰተት ብለው በገቡ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ፣ ቃላቸውን ጠብቀው ያሉትን አደረጉና ብዙዎችን አስደነገጡ፡፡
“የአገሬንና የህዝቤን ደህንነት ለመጠበቅና ሰርጎ ገብ ሽብርተኞችን ለመከላከል ስል፣ ለማንኛውም አገር ስደተኞችና ለሰባት አገራት ዜጎች በጊዜያዊነት ድንበሬን ዘግቻለሁ!...” በማለት፣ በብዙዎች ዘንድ የሚወራ እንጂ የማይተገበር ተደርጎ የተወሰደውን አስደንጋጭ ነገር ማድረጋቸውን በይፋ አወጁ፡፡
ትራምፕ ባለፈው አርብ በሰባት የተለያዩ አገራት ላይ የጣሉት የጉዞ ገደብ፣ ብዙዎችን በድንጋጤ ክው ያደረገ አነጋጋሪ፣ አስደንጋጭ፣ አከራካሪ አለማቀፍ ክስተት ሆነ፡፡ ጉዳዩ የሰባቱ አገራትና የአሜሪካ አልያም የስደተኞችና የተወላጆች ብቻ ጉዳይ አልሆነም፡፡ የአለማችንን ህዝቦችና የአለማችንን መንግስታት ያነጋገረና ድንበር ሳያግደው ርቆ በመጓዝ በየጓዳው የገባ ሰሞንኛ ጉዳይ ሆነ፡፡
የትራምፕ ውሳኔ በአለማችን ፖለቲከኞች ብቻም ሳይሆን በመዝናኛው መስክ የአለማችን ከዋክብት ዘንድም ድንጋጤንና ቁጣን ፈጥሯል። ከእውቅ የሆሊውድ ተዋንያን እስከ አለማቀፍ የሙዚቃ ከዋክብት፣ በርካታ የአለማችን ዝነኞች በትራምፕ አስደንጋጭ ውሳኔ ዙሪያ አስተያየታቸውን በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡
የአለማችን ዝነኞች ለትራምፕ ውሳኔ የሰጡትን ምላሽ በተመለከተ መገናኛ ብዙሃን ካወጧቸው ዘገባዎች በጥቂቱ እንጨልፍ!...
ከቀናት በኋላ በሎሳንጀለስ በደማቅ ሁኔታ ለሚከናወነው ታላቁ የኦስካር ሽልማት ከታጩት መካከል አንዱ ነው - ዳይሬክተሩ አስጋር ፋራዲ፡፡
“ዘ ሴልስማን” በሚለው ፊልሙ ለሽልማት የታጨውና ያቺን ልዩ ቀን በጉጉት ሲጠብቅ የሰነበተው ዳይሬክተሩ አስጋር ፋራዲ፤ ያቺ ልዩ ቀን ከመድረሷ በፊት ያልጠበቀውን መርዶ ሰማ፡፡ በዚያች ቀን በሎሳንጀለስ ተገኝቶ፣ የጓጓለትን ሽልማት መቀበል አይችልም፡፡ ምክንያቱም ኢራናዊ ነው። ኢራናዊ ደግሞ፣ በትራምፕ ትዕዛዝ ወደ አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለ የሽብር ተጠርጣሪ ነው፡፡
ዋታኒ - “ማይ ሆምላንድ” በሚለው ፊልሟ በዘንድሮው ኦስካር፣ በዘጋቢ ፊልም ዘርፍ ለሽልማት የታጨቺው ሶርያዊቷ ሃላ ካሚልም፣ ትራምፕ በክፉ አይናቸው ካዩዋት አገር የተገኘች ናትና፣ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ እንድትገኝ አይፈቀድላትም፡፡ በዚህ አስደንጋጭ ውሳኔ ክፉኛ ማዘኗን ገልጻለች- ሃላ ካሚል፡፡
የትራምፕ ውሳኔ ካስደነገጣቸውና ካሳዘናቸው የአለማችን ዝነኞች መካከል ትጠቀሳለች - ዝነኛዋ ድምጻዊት ሪሃና፡፡ ድምጻዊቷ ትራምፕ ውሳኔውን ባስተላለፉ በነጋታው፣ ጉዳዩን በተመለከተ በትዊተር ባሰራጨቺው ጽሁፍ፣ “አስቀያሚ ነገር ነው!... የሰማሁት ነገር እጅግ አስደንጋጭ ነው!... አይናችን እያየ፣ አሜሪካ እየጠፋች ነው!...” ብላለች፡፡
ሪሃና ይህን ብላ አላበቃችም...
“ምን አይነቱ ነውር የማያውቅ አሳማ ነው!...” ስትል ጋሼ ትራምፕን በገደምዳሜ ወርፋቸዋለች፡፡
ታዋቂው የሆሊውድ የፊልም ዳይሬክተር ማይክል ሙር በበኩሉ፣ “በመላው አለም የምትገኙ ሙስሊም ጎረቤቶቻችን ሆይ፡ እኔ እና በአስር ሚሊዮኖች የምንቆጠር ሌሎች አሜሪካውያን ይቅርታ እንጠይቃችኋለን፡፡ አብዛኛው የአሜሪካ ህዝብ ለዚህ ሰውዬ ድምጹን አልሰጠም!...” በማለት በትዊተር ገጹ መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡
ጆን ሌጀንድ በበኩሉ፤ “እኛ አሜሪካውያንና ፕሬዚዳንት ትራምፕ ለአሜሪካ ያለን ራዕይ ፍጹም ተቃራኒ ነው!...” ብሏል፤ ባለፈው ቅዳሜ ምሽት በተከናወነው የፕሮዲዩሰርስ ጊልድ ሽልማት ስነስርዓት ላይ ባደረገው ንግግር፡፡
በዚያው ዕለት የሙዚቃ ኮንሰርቱን ለአድናቂዎች ያቀረበው ድምጻዊው ብሩስ ስፕሪንግስተን በበኩሉ፤ “አሜሪካ የስደተኞች አገር ናት፡፡ የሰውዬው ውሳኔ ኢ-ዲሞክራሲያዊና ከአሜሪካ እሴቶች ውጭ ነው!...” በማለት በትራምፕ ውሳኔ ማዘኑን ገልጧል፡፡
“ወደ አሜሪካ የመጣሁት ከ32 አመታት በፊት ነው፡፡ በዚህች አገር ነዋሪ በመሆኔ ለመጀመሪያ ጊዜ ያፈርኩት ግን፣ ትናንት ነው!...” በሚል በትራምፕ ውሳኔ ማግስት በትዊተር ሃዘኑን የገለጸው ደግሞ፣ “ዘ ቲፒንግ ፖይንት” በሚለው መጽሃፉ የሚታወቀው ደራሲ ማልኮም ግላድዌል ነው፡፡
የተርሚኔተሩ ድንቅ ተዋናይና የቀድሞው የካሊፎርኒያ ገዢ አርኖልድ ሽዋዚንገርም በትራምፕ ውሳኔ መከፋቱን አልደበቀም፡፡ “ይህ እጅግ የለየለት እብደት ነው!... ደደቦች ተደርገን እንድንቆጠር የሚያደርግ አጉል ውሳኔ ነው!...” ብሏል ሽዋዚንገር ከ”ፒውፕል መጋዚን” ጋር ሰኞ ዕለት ባደረገው ቃለ ምልልስ፡፡
“ስደተኞች ሽብርን ሽሽት ርቀው የሚጓዙ እንጂ፣ ሽብርተኞች አይደሉም” የሚለው መረር ያለ ምላሽ ደግሞ፣  የአሜሪካዊቷ ድንቅ የፊልም ተዋናይ የኬሪ ዋሽንግተን ነው፡፡ ዝነኞች ምንም ይበሉ ምን፣ትራምፕ ግን በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት ለአሜሪካውያን ቃል የገቡትን ሁሉ ሳያጓድሉ እንደሚፈጽሙና አሜሪካንን ዳግም ታላቅ እንደሚያደርጓት በአገኟት አጋጣሚ ሁሉ ከመናገር ወደ ኋላ ብለው አያውቁም፡፡ ለመተግበርም ወደ ኋላ እንደማይሉ ሰሞኑን በግልጽና በድፍረት አሳይተዋል።