Administrator

Administrator

6 ቢሊዮን ዶላር ያህል በሪልእስቴት ዘርፍ ኢንቨስት ተደርጓል ተብሏል

  አዲስ አበባ በሪልእስቴት ዘርፍ ኢንቨስትመንት ከአፍሪካ ከተሞች በ3ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝና የከተማዋ የሪልእስቴት ልማት ዘርፍ ኢንቨስትመንት፣ 6 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ የዓለም ባንክ ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የአፍሪካ ዋና ዋና ከተሞች ወቅታዊ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት አስታውቋል፡፡
የታንዛንያዋ ዳሬ ሰላም በሪልእስቴት ልማት ዘርፍ ከአፍሪካ ከተሞች በአንደኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የከተማዋ የሪልእስቴት ኢንቨስትመንት 12 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ የገለጸ ሲሆን፣ የ9 ቢሊዮን ዶላር የሪልእስቴት ኢንቨስትመንት ባለቤት የሆነቺው የኬንያ ርዕሰ መዲና ናይሮቢ፣ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝም አስረድቷል፡፡
በአፍሪካ ከተሞች የሪልእስቴት ዘርፍ ልማት እየተስፋፋ ቢመጣም፣ የከተማ ነዋሪዎች ከነፍስ ወከፍ ገቢያቸው ጋር ሲነጻጸር የመኖሪያ ቤት ፍላጎታቸውን ለማሟላት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚያወጡም የጠቆመው ሪፖርቱ፤ በአንዳንድ የአህጉሪቱ ከተሞች የመሬት ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመሄድ በአሜሪካ በሚሸጥበት ዋጋ መሸጥ መጀመሩንም አክሎ ገልጧል፡፡
የአህጉሪቱ የከተማ ነዋሪዎች ቁጥር እስከ 2050 ድረስ በ170 ሚሊዮን እንደሚጨምር እንዲሁም አሁን ያለው የከተማ ነዋሪ ህዝብ ቁጥር በ25 አመታት ጊዜ ውስጥ በእጥፍ በማደግ 1 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ይህም በመሆኑ የአህጉሪቱ ከተሞች የመኖሪያ ቤት ግንባታን ጨምሮ ከህዝብ ቁጥር እድገቱ ጋር የሚመጣጠን ሰፊ የመሰረተ ልማት አውታሮች ግንባታ ማካሄድ እንደሚጠበቅባቸው አስረድቷል፡፡
የአፍሪካ ከተሞች እጅግ ውድ ከሆኑ የአለማችን ከተሞች ተርታ እንደሚመደቡ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ከሌሎች ተመሳሳይ ገቢ ያላቸው የአለማችን አገራት ከተሞች ጋር ሲነጻጸር በ30 በመቶ ያህል የበለጠ ውድ መሆናቸውንና ይህም ከተሞቹ አለማቀፍ ኢንቬስተሮችን እንዳይስቡ እክል እንደፈጠረባቸው ገልጧል፡፡

“ፐርሰንት ከደመወዝ ተቀንሶ አይከፈልም፤ አሠራሩም ሕጋዊ አይደለም” /ክፍለ ከተማው/
    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ “የደብረ ተኣምራት ዳግማዊት ጻድቃኔ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ሠራተኞች፤ ለተፈቀደላቸው የደመወዝ ጭማሪ ማጽደቂያ፣ ለሀገረ ስብከቱ ሓላፊዎች የተሰጠው ብር 50 ሺሕ ጉቦ እንዲመለስ ታዘዘ፤” በሚል ርእስ፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ያወጣው ዘገባ፣ “ያልተጣራና መሠረተ ቢስ ነው” ሲሉ ሀገረ ስብከቱና የደብሩ ጽ/ቤት አስተባበሉ፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ ካላት ከማንኛውም ገቢ ላይ ሃያ በመቶውን የሀገረ ስብከቱን ድርሻ እንድትከፍል በቃለ ዐዋዲው መደንገጉን በማስተባበያቸው አስታውሰው፤ በዘገባው የተጠቀሰውና ከደብሩ ጽ/ቤት ወጣ የተባለው 50ሺ ብርም፣ በወቅቱ ያልተከፈለ የደብሩ የሃያ ፐርሰንት ውዝፍ ሒሳብ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ይህም፣ ሀገረ ስብከቱን ወክሎ በሚሠራው በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ስም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተከፈተው ተንቀሳቃሽ ሒሳብ ገቢ መደረጉን በመጥቀስ ደረሰኙን በአስረጅነት አቅርቧል፡፡ “ወደ ተቋሙ ባንክ የገባውን ገንዘብ ለግለሰቦች እንደተሰጠ አስመስሎ መዘገቡ ሚዛናዊነት የጎደለው ነው፤” ሲልም ዘገባውን ተቃውሟል፡፡ የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ መጋቤ ሠናያት የቻለው ለማ በበኩላቸው፤ “የደብሩ የሃያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ መከፈል ያለበት ከደብሩ ገቢ እንጂ ከሠራተኞች ደመወዝ ተቀንሶ መሆን የለበትም፤ የሁለት ወሩ የደመወዝ ጭማሪም የተቀነሰው፣ የጽ/ቤቱ ሓላፊዎች በራሳቸው ወስነው እንጂ፣ የሚመለከተው ሰበካ ጉባኤ በተገኘበት እንዳልሆነ ጽ/ቤታቸው ባደረገው የሰነድና የገጽ ለገጽ ማጣራት ማረጋገጡን ገልጸዋል፡፡ ገቢ ተደርጓል ስለተባለው 50ሺ ብር የተጠየቁት ሥራ አስኪያጁ፣ “የክፍለ ከተማው ጥያቄ የ50ሺሕ ብር አከፋፈል ሒደት አይደለም፤ ከግለሰቦች ላይ የተቀነሰው የገንዘብ አከፋፈል ሒደትና አሠራር ትክክል አይደለም፤ ፍትሐዊ አይደለም፤ ነው፤” በማለት ከደመወዝ ጭማሪው ጋር ግንኙነት እንደሌለው አስረድተዋል፡፡


ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

“እና - እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…” (“እሳት ወይ አበባ”)

“እና - እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…”    (“እሳት ወይ አበባ”)

መግቢያ
ታኅሣሥ 29 ቀን፣ 2009 ዓ.ም. በዓለ ገና፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ዕድገትና ደረጃን በሚመለከት በጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን ትምህርት ቤት በሚያስተምር ግለሰብ ዋና የመረጃ ሰጪነት፣ ዘጋቢ ፕሮግራም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ተላልፎ ነበር፤ የፕሮግራሙ አቀራረብም፣ የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬን ማዕከል ያደረገ ነበር፡፡ እንዲኽ ዓይነት ይዘት ያለውን የዶክመንተሪ አቀራረብ፣ አሜሪካኖች* “Charm offensive” ይሉታል፡፡
ይህን ሲሉ፣ ኾን ተብሎና ታቅዶ፣ የራስን የማንነት ውበትና በጎነት አጉልቶ በማውጣት የሚቀርብ ድርጊትን መግለጻቸው ነው፡፡ ይህንኑ የራስ መልክአ ውዳሴ ወደ አማርኛ ስንተረጉመው፣ “አጀብ እዩልኝ” ተብሎ ሊገለጽ ይችላል፡፡ ዶክመንተሪው በዋናነት፣ የዩኒቨርሲቲውን ጉዳይ ያነሣ ቢመስልም፣ ዐቢይ ትኩረቱ ግን፣ ፕሬዝዳንቱን እንዲኹም የሥራ አፈጻጸማቸውን አጉልቶ ለማውጣት ያለመ ነው፡፡ ኾኖም፣ እውነታው* በመልክአ ውዳሴው ከቀረበው የዩኒቨርሲቲው ኹኔታ እንዲኹም፣ ከፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ ገጸ ሰብእና ጋር ሲነጻጸር ፈጽሞ የተራራቀ ነው፡፡    
ይህን ጽሑፍ እንዳዘጋጅ የወዲያው ሰበብ የኾነኝ፣ ይህንኑ የእውነታ መራራቅና መጣረስ ለማሳየት በማሰብ ነው፡፡ ኹለተኛውና ዋነኛው የጽሑፌ መንሥኤ ግን፤ በፕሬዝዳንት አድማሱ እና በቦርዱ ሊቀ መንበር አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን ይኹንታ ሰጪነት፣ በዩኒቨርሲቲው ቅጽር የተካሔደው የዛፍ ምንጠራ ድርጊትና የሕንፃ ግንባታ አስከትሎት ጉዳይ ነው፡፡
ይህ መጣጥፍ፣ የኹለት ክፍሎችን ቅንብር የያዘ ነው፡፡ አንደኛው* የዩኒቨርሲቲውን ዛፍ ምንጠራ እና የዕውቅ ሥነ ውበታዊ መገለጫውን መገፈፍ በየአንጻሩ ማሳየት ሲኾን፤ ኹለተኛው ደግሞ፣ ዛፍ ምንጠራው፣ የዩኒቨርሲቲውን መካነ አእምሯዊ ተልእኮ ለማሳካት ሳይኾን፣ የፕሬዝዳንቱንና ፈቃድ የሰጡትን ሹመኞች ፍላጎትና ጥቅም ታሳቢ ያደረገ ፕሮጀክት መኾኑን በጥቂቱ ማሳየት ነው፡፡
ኢንዱስትሪ እና ዩኒቨርስቲ
የማኅበራዊ ሳይንስ ተመራማሪውና በኢትዮጵያ ጉዳዮች በርካታ ጥናቶችን ያሳተሙት ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን፣ ከኅልፈታቸው ጥቂት ዓመታት ቀደም ብለው* “Powers of the Mind: The Renovation of Liberal Learning in America” በሚል ርእስ፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ፍልስፍና መጽሐፍ አሳትመው ነበር፡፡ ፕሮፌሰር ሌቪን፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ምንነት በርካታ ጥልቅ ሐሳቦችን የገለጹ ቢኾንም፤ ከዚኽ መጣጥፍ ዋና ይዘትና መንፈስ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለውን አንዱን አገላለጻቸውን ብቻ ወስደናል፡፡
ፕሮፌሰር ሌቪን፣ “ዩኒቨርሲቲ፣ በኢንዱስትሪ የውጤታማነት መለኪያ መስፈርት ሊመዘን አይገባም፤” ይላሉ፡፡ እንደ እርሳቸው አገላለጽ፣ ዩኒቨርሲቲ በኢንዱስትሪ መለኪያ የማይመዘንበት ምክንያት* በይዘት፣ በዓላማም ኾነ በውጤት ከኢንዱስትሪ የተለየ በመኾኑ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ዩኒቨርሲቲ እንደ ኢንዱስትሪ ገበያ የሚፈልገውን ብቻ ፈብርኮ የሚያቀርብ ሳይኾን፣ ተማሪዎች፣ ለጥናትና ምርምር የተኮተኮተ አእምሯዊ ማሕቀፍ እንዲኖራቸው ለማስቻል የተደበረ የዕውቀት ኀሠሣ ማዕከል በመኾኑ ነው፡፡
ይህን መሠረታዊ የዩኒቨርሲቲ እና የኢንዱስትሪ ባሕርያዊ ልዩነት በውል ባለመገንዘብ፤ የወቅቱ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፤ መድረክ ባገኙባቸው አጋጣሚዎችና ከላይ በጠቀስነው “የአጀብ እዩልኝ” ዶክመንተሪያቸው ሳይቀር፤ ስለሚመሩት ዩኒቨርሲቲ ሲገልጹ፣ ደጋግመው የሚጠቀሙባቸው ዕዝሎችና ቅጽሎች፡- ‹አደረጃጀት›፣ ‹ሽፋን›፣ ‹ቅበላ›፣ ‹ቁጥር›፣ ‹ግንባታ›፣ ‹የኃይል ትስስር›፣ ‹ፕሮጀክት›፣ ‹አንድ ለአምስት› … ወዘተ. ናቸው፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት ቅጽሎችና ሐረጎች፤ የኢንዱስትሪ የምርታማነትና የውጤት ደረጃ አመልካች መለኪያዎች፤ የአንድ ፋብሪካ የምርት ቁጥጥር ሓላፊ ወይም የሕንፃ ግንባታ ተቆጣጣሪ “ካቦ”፣ በሚያቀርበው ሪፖርት የሚጠቀማቸው ቃላት እንጂ፣ “ⷈሉ አመክሩ ወዘሠናየ አጽንዑ”(ኹሉን መርምሩ መልካሙንም አጽንታችኹ ያዙ) የሚለውን ታላቅ ኃይለ ቃል ይዞ የተነሣን፣ የማእምራን መዲና የኾነ ዩኒቨርሲቲን መንፈስ የሚወክል ወይም የሚመጥን አይደለም፡፡
“አድማሱ ዛፍ የመነጠረበት ዘመን”
የዚኽን ንኡስ ርእስ ሐሳብ የወሰድኹት፣ በጎጃም ጠቅላይ ግዛት ታዋቂ ከኾነና በስፋት ከሚነገር ታሪክ ወስዶ፣ አንድ ወዳጄ በአንድ ወቅት ያጫወተኝን ትረካ መሠረት አድርጌ ነው፡፡ ትረካው በአጭሩ ሲቀርብ እንደሚከተለው ነው፡፡
ልዑል ራስ ኃይሉ እና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ፣ በራስ ካሳ ሥር ታስረው በነበሩት በልጅ ኢያሱ ከእስር ቤት ማምለጥ፤ ራስ ኃይሉ፣ “ተሻርከው አስመልጠዋል” በሚል ምክንያት የከረረ ጠብ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ልዑል ራስ ኃይሉም ከጎጃም አገረ ገዥነት ተሽረው በእስርና በግዞት ይሰደዳሉ፡፡ በምትካቸውም፣ ከንቲባ ማተቤ ደረሶ ደብረ ማርቆስን ተሾሙ፡፡ ይህን የሥልጣን ሽግግር አገሬው ስላልወደደው፣ የራስ ኃይሉን ልጅ ፊታውራሪ አድማሱ ኃይሉን ይዞ ተቃውሞ ቀሰቀሰ። በጊዜውም በደብረ ማርቆስ ቤተ መንግሥት ግምጃ ቤት ውስጥ በግብር የተሰበሰበና የራስ ኃይሉም የግል ንብረት የነበረ ሀብት፤ “የሸዋ ሹመኞች መጥተው ሊወስዱት ነው፤” ተብሎ ስለተወራ፤ እነፊታውራሪ አድማሱ፤ “ይህ ንብረት ሸዋ ከሚሻገር ጎጃሜ ይውሰደው!” በማለት፤ ግምጃ ቤቱን ከፍተው በሕዝብ አስመዘበሩት፡፡ ይህም ድርጊት እስከ ዛሬ በጎጃም፣ “አድማሱ ያፈረሰው ጊዜ” ተብሎ ሲወሳ ይኖራል፡፡
ወደ ጥንተ ነገራችን ስንመለስ፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፣ “ለዩኒቨርሲቲው ማስፋፊያ ሕንፃ መገንባት አስፈላጊ ነው፤” በሚል መነሻ፣ የቅጽረ ግቢው ግርማ ሞገስ ኾኖ በዓለም የሚታወቀውን ዐጸድ በማስመንጠር፣ የማይበጅ አፍራሽ ተግባር ፈጽመዋል፡፡
የኹለቱም “አድማሱ”ዎች ድርጊት፣ በጥቅሉ “የአፍራሽ” ቅጽል ተሰጥቶት ቢገለጽም፤ የመጀመሪያው አድማሱ የተነሡበት መንፈስ፣ ለጎጃም ሕዝብ ወገንተኝነት የቆመ ሲኾን፤ ይህም ድርጊታቸው በጊዜው በሕግ ቢያስጠይቃቸውም፣ ከሞራል አንጻር ሲታይ ግን የሚያስኰንናቸው ጉዳይ አይደለም፡፡ የኹለተኛው አድማሱ አፍራሽነት ግን፤ በሕግም ኾነ በሞራል መስፈርት ያስጠይቃቸዋል፡፡ ይኸውም፣ ከዩኒቨርሲቲው ቅጽር ሥነ ውበት አንጻር የሚያስጠይቅ ስሕተት ተፈጽሟል፤ የሚል እምነት ስላለኝ ነው፡፡
የመጀመሪያው አድማሱ አፍራሽነት፣ ስሕተት ከተባለ መግፍኤው፣ ለሕዝብ ከመቆም ሲኾን፤ የኹለተኛው አድማሱ የአፍራሽነት ድርጊት ግላዊና መለካዊ (ሥልጣን ሰገድ) ከመኾን የመነጨ ነው፤ ማለት እንችላለን። በመኾኑም፣ የቀዳሚው አድማሱ ድርጊት፣ አንድ ማኅበረሰባዊ ተረክ ኾኖ እንደቆየን ኹሉ፣ የዩኒቨርስቲው አድማሱ የደን ምንጣሮ አፍራሽነትም ለትውልድ ሲነገር ይኖራል፡፡
የደን ምንጣሮው፡- ከሥነ ሕይወት፣ ከሥነ ውበት እና ከፎክሎር አተያዮች አንጻር፤
ሀ/ሥነ ሕይወት
የዛፍን ምንነትና ኹለንተናዊ ጥቅም አስመልክተው፣ ወ/ሮ ዕሌኒ መኩሪያ የተባሉ ዕውቅ ጋዜጠኛ፤ “ዛፎች ለሕይወት” በሚል ርእስ በ2005 ዓ.ም. መጽሐፍ አዘጋጅተው ነበር፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ስለ ዛፍ እና ሥነ ሕይወት* ማብራሪያዎች፣ ፎቶግራፎች፣ ግጥሞችና መጣጥፎች ተካተውበታል፡፡ የእኒኽ ዓይነት መጻሕፍት ዓላማ፤ ዛፍ እንዳይመነጠርና ለዛፍ ክብካቤ እንዲደረግ አበክሮ ማሳሰብ በመኾኑ፤ ስለ ሥነ ሕይወት እና ሥነ ምኅዳር ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ኾኖ አግኝቼዋለኹ። ይህን በመሰለ ጥረት፣ ለማኅበረሰቡ የዛፍን ጥቅም በወል ለማስጨበጥና ለማስተማር በሚሞከርበት ጊዜ፤ ዩኒቨርሲቲው፣ ሲኾን፣ ከነወ/ሮ ዕሌኒ መኩሪያ ጋር በአስተማሪነት ይሰለፋል ብለን ስናስብ፤ በተቃራኒው የዛፍ ጭፍጨፋ ተግባር ላይ ተሰልፎ መገኘቱ ብዙዎችን አሳዝኗል፡፡
የወቅቱ የዩኒቨርሲቲው አመራር እና አስተዳደር፣ ዩኒቨርሲቲው ለመጪው ትውልድ የሚያገለግል ዐጸድ መትከልና አኹን ያሉትንም መከባከብ ሲገባው፤ ራሱ ያልተከለውንና ከዘመናት በፊት የነበረውን ደን መመንጠሩ፣ ዩኒቨርሲቲው፣ ስለ አካባቢ ጥበቃ አስፈላጊነት ለማኅበረሰቡ ለማስተማር የነበረውን የዕውቀትና የሞራል ልዕልና እንዲያጣ ምክንያት ኾኗል፡፡
እንዲኽ ያለው ብዝኃ ሕይወትን የመጠበቅና የመከባከብ ሓላፊነት፤ እንደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያለው ተቋም ይቅርና በዜግነት ደረጃ እንኳን ግለሰብ ሊፈጽመው እንደሚገባ፤ በአንድ ወቅት ደጃዝማች ዘውዴ ገብረ ሥላሴ፣ የደን ምንጠራን በመቃወም ካሳዩት አርኣያነት የምንረዳው ነው፡፡
ከጥቂት ዐሥርት ዓመታት በፊት፣ በፈረንሳይ ለጋሲዮንና በቤላ መካከል በሚገኝ በአንድ በደን በተሸፈነ ይዞታ ላይ ምንጣሮ ሊካሔድ አስተዳደራዊ ውሳኔ ተላልፎ ነበር፡፡ በተጠቀሰው አካባቢ ያለው ደን፣ ከአዲስ አበባ ምሥረታ ኹለትና ሦስት ምእተ ዓመታት ቀድሞ የነበረና ሀገር በቀል ዕፀዋትን የያዘ ነው፡፡ ደጃዝማች ዘውዴ፣ በእነዚኽ ዕፀዋት ላይ የተላለፈው የምንጣሮ ውሳኔ እጅግ የተሳሳተ መኾኑን ለመግለጽ፣ የአካባቢውን ማኅበረሰብ አስተባብረው ተቃውሟቸውን በማቅረብ  ምንጣሮውን ማስቀረት መቻላቸው ይነገርላቸዋል፡፡    
ከደጃዝማቹ አርኣያነት ያለው ዜግነታዊ ተግባርና እነወ/ሮ ዕሌኒ ካሳተሙት የደን ኹኔታን ከሚያሳይ መጽሐፍ መንፈስ፣ በብዙ መልኩ፣ ለተፈጥሮ በተለይም ለደን ክብካቤ መቆም እንደሚገባን እንረዳለን፡፡ በአንጻሩ፣ የዩኒቨርሲቲው ድርጊት አሳዛኝ ከመኾን አልፎ መንግሥታዊ ይኹንታ ላለማግኘቱ ማረጋገጫ የለንም። በመኾኑም፣ ስሕተቱ፣ የዩኒቨርሲቲው አመራር ብቻ ሳይኾን፣ መንግሥትን ወክሎ የተቀመጠው የቦርዱም ሓላፊነት ያለበት ጭምር እንደኾነ ልብ ይሏል፡፡
ለ/ሥነ ውበት  
አንድ ሰው* ስለ ጥበብ፣ ስለ ተፈጥሮ፣ ስለ ውበት… ወዘተ. መረዳት የሚችለው፣ ለተፈጥሮ የሚማልል ንቁና ሥሡ ስሜት ሲኖረው ነው፡፡ ይህ ስሜት ደግሞ፣ በተፈጥሮ የሚገኝ ብቻ ሳይኾን፣ ከትምህርት እና ከአድናቆት ጋር በተያያዘ ስሜታችን ሲኮተኮትና ሲሠለጥን የሚገኝ ነው፡፡ ግለሰቡ ውስጣዊ ጉጉት ካለው በእነዚኽ ጉዳዮች ይደነቃል፤ ይደመማል፤ ይማረካል፤ ይማራል፤ ይቆረቆራል፡፡ ነገር ግን፣ ግለሰቡ፣ የሥነ ውበት መማረክ ከሌለው፣ ውስጡ በሥነ ውበት ስእነት(ኢከሃሊነት) የተሞላ ሕጹጽ ነው፤ ማለት ነው፡፡
ይህን ለመግለጽ፣ አንዳንድ ሠዓሊዎች ግድግዳ ላይ የተሰቀለን ሥነ ጥበባዊ ሥራ አይተው፣ “ከፊል ቦታ ላይ ‘dead spot’ ስላለው መስተካከል አለበት” የሚል ሞያዊ አገላለጽ ይጠቀማሉ፤ ቀለም አንሶታል፤ ሕይወት አልባ ነው፤ ለዛ የለውም፤ ደብዝዟል፤… ወዘተ. ማለታቸው ነው፡፡ ይህን ብሂል ወደ ሰው ስናመጣው፣ ግለሰቡ ወይም ግለሰቧ፣ ሥነ ውበትን ለማድነቅ የሚያስችላቸው የስሜት ሕዋሳቸው በድኗል ወይም አልተኮተኮተም ማለት ነው፡፡ በመኾኑም፣ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንትና ይኹንታ የሰጡት የቦርድ ሹመኞች፤ ከሥነ ውበት ክሂል አንጻር ርምጃቸውን ስናየው፣ የሥነ ውበት አድናቆት ስእነት(ኢከሃሊነት) ሰለባ መኾናቸውን በግልጽ እንረዳለን።
ታላቁ ባለቅኔና ጸሐፌ ተውኔት ጸጋዬ ገብረ መድኅን፣ በ“እሳት ወይ አበባ” ግጥሙ ላይ፣ ስለ ክሂለ ቢስነት (dead spot) ከተቀኘው ጥቂት ስንኞችን እንጥቀስ፤
“እና - እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…”
በመኾኑም፣ በዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ የነበረው ተፈጥሮ የለገሰን ውበት በሚገፈፍ ጊዜ፣ ምን ዓይነት ኹኔታ ይፈጠራል? ብሎ መጠየቁ ተገቢ ነው፡፡ ይህን የሥነ ውበት ረድኤት በተመለከተ፣ ኹለት ፈላስፎች ተጠቃሽ አስተምህሯቸውን በሚከተለው መልኩ አስቀምጠውልን አልፈዋል፡፡
የመጀመሪያው፣ የ18ኛው መ/ክ/ዘ ፈላስፋ ኢማኑኤል ካንት፣ በወሳኝ የሥነ ውበት ድርሳኑ (Critique of Judgment)፣ ሥነ ውበትን በመሠረቱ ሲተረጉመው* “Purposiveness without a purpose” ይለዋል፡፡ ይህም ማለት፣ “ይህ ነው” ተብሎ በግኡዛዊ መስፈርት የማይለካ ኾኖ ግብ ያለው እንደ ማለት ነው፡፡ በእርሱ አገላለጽ፡- ተዝናኖት፣ አማሕልሎት እና ሥነ ውበት ያለው ተፈጥሮም ኾነ ጥበብ፣ ከውስጡ ቀጥተኛ የኾነ የተሰፈረ ዓላማ፣ አመክንዮ ወይም ጥቅም የተቀመጠለት አይደለም። ይልቁንም፤ ውብ የኾነ ነገር ማለት፤ ከውስጡ ምንም ቀጥተኛ ጥቅም ሳናገኘበት፣ በውበቱ ብቻ የምንወደው ወይም የምናደንቀው፤ የረቂቁ ሰብአዊ ተፈጥሯችን የሥነ ውበት አድናቆት ስሕበትና “ረኃብ” በሚፈጥርብን ልዩ ፍላጎት ብቻ የምንወደው ማለት ነው፡፡
ይህን ካንታዊ የሥነ ውበት ገለጻ፤ በሀገራችን ነባር አስተምህሮ ለማንጸር ብንሞክር፣ በቤተ ክህነት የሥነ ፍጥረት ትምህርት ያለውን አጠይቆ እንደ አብነት መጥቀስ እንችላለን፡፡ እንደ አስተምህሮው፣ አዝማደ ፍጥረታት በየወገናቸው ስለ ሦስት ምክንያት (ረብሕ) ተፈጥረዋል፡፡ እኒኽም፣ አንደኛው* ለአንክሮ (ለመደመም)፣ ኹለተኛው* ለተዘክሮ (ለተምህሮ)፤ ሦስተኛው* ለምግበ ሥጋ ወነፍስ ናቸው፡፡
ኢማኑኤል ካንት፣ “ቀጥተኛ የተሰፈረ ጥቅም የሌለው ግን ረብ ያለው፤” የሚለውን አገላለጹን፤ ጥንታዊው የቤተ ክህነት አስተምህሮ፣ “ምክንያተ አንክሮ” ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር ዓለምን የፈጠረው፣ ጥቂቱን ለጥቅመ ሥጋ ወነፍስ ሲኾን፤ ብዙውን ግን ለአድናቆት፣ ለመደመም፣ “ወይ የአምላክ ሥራ!” ብለን በአንክሮ የመለኮትን ምስጢር እንድናስተውል፣ የመንፈስ ተመስጦና የልቡና ሐሤት እንድናገኝበት ነው፡፡ ይህን ተሰጥሞ ልቡና እና መንፈሰ ሐሤት የቤተ ክህነቱ አስተምህሮ፥ “አንክሮ” ይለዋል፡፡
ይህን የኢትዮጵያ ጥንታዊ አስተምህሮ እና የኢማኑኤል ካንት “የአንክሮ እና የተደሞ” መሠረተ ሐሳብ፤ ከዛሬው የአዲስ አበባው ዩኒቨርሲቲ የአድማሱ ጸጋዬ አስተዳደር መጠበቅ የዋህነት መኾኑን፣ በዛፍ ምንጠራ - ተማስሎ - ድርጊት ፍንትው ብሎ ታይቷል፤ አስተዳደራዊ አስተሳሰቡ፣ ሥነ ፍጥረት፣ ከጥቅመ ሥጋ ያለፈ ረብሕ እንደሌለው በማያሻማ ኹኔታ አሳይቷልና፡፡         
ፍሬድሪክ ሺለር የተባለው የ19ኛው መ/ክ/ዘመን የሥነ ጥበብ ሰው፣ “Letters on the Aesthetic Education of Man” በሚል ርእስ በጻፈው ጦማር፣ ስለ ሥነ ውበት ምንነት በእጅጉ አስደማሚ የኾነ አጭር ጽሑፍ አቅርቧል፡፡ ጽሑፉ፣ በርከት ያሉ ርእሰ ጉዳዮችን ቢያነሣም፣ ከፍጥረት የሚገኝ ውበት ሰውን ሊያጎናጽፍ ስለሚችለው ሐሤት እንደሚከተለው አትቷል፤
ሺለር እንደሚለው፣ የግለሰቡም ኾነ የማኅበረቡ ልዩነት፣ ሥነ ውበት ፊት ሲቀርብ፣ ልዩነቱ ኹሉ ይቀርና በመስሕቡ ተማርኮ ኹሉም፣ እያንዳንዱም ያለ ልዩነት እኩል ለሥነ ውበት ይማልላል፡፡
ይህን የሺለር ሐሳብ ይዘን፣ ዩኒቨርሲቲውን በምናይበት ጊዜ፣ ትላንት ዛፉ ሳይቆረጥ፣ ማንኛችንንም ሊያግባቡን ያልቻሉ* የብሔር፣ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት፣ የጾታ፣ የመደብ… ወዘተ. አመለካከቶች ሳያግዱን፤ በግቢው ውስጥ የነበረውን መስሕብ ያለው ዐጸድ ያለ ልዩነት በአንድነት እናደንቅ ነበር፡፡ በአኹኑ ወቅት ግን፣ ይህ ዐጸድ ተጨፍጭፎ በፎቆች ሲተካ፣ ሺለር እንዳለው፣ ከተፈጥሮ ውበት ይገኝ የነበረው ንጽረታዊ አንድነት ተጓድሎ፣ ኹላችንም የጋራ አጽድቆት በማንሰጠው ፎቅ ተተክቷል፡፡
እዚኽ ላይ፣ አስተውሎት እንዲኖረን ይገባል ብዬ የማስበው፣ አገዛዙ፣ የጋራ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ዕሴቶችን የመናድ ባሕርያዊ መገለጫው፤ በቅጽሩም ላይ፣ እንደተለመደው፣ ዜጎች ወደ ግቢው ሲዘልቁ የሚያገኙትን ተፈጥሯዊ የጋራ ደስታ በማውደም እንድንለያይ የማድረግ ተግባሩን እንደተያያዘው እንገነዘባለን፡፡
ሐ/ ፎክሎር
የሰው እና የሥነ ሕይወት መስተጋብር፣ በቅርቡ ከምዕራቡ ዓለም የተዋስነው ወይም በሰበካ የተቀበልነው ጉዳይ ሳይኾን፣ ከጥንት ጀምሮ በተለያዩ የአገራችን ማኅበረሰብ ባህል ውስጥ የነበረ አስተሳሰብና ልማድ ነው፡፡ በአገራችን ማኅበረሰቦች ነባር ባህል ውስጥ፣ ስለ ዛፍ ያለው እሳቤ የተለያየ ቢኾንም፣ በአብዛኛው ዛፍ በሰው ልጅ ሕይወት ያለው አገልግሎት ሥሉጥ እንደኾነ እንረዳለን፡፡
ከአገልግሎቱም መካከል፣ ዛፍ፡- መሰብሰቢያ፣ እርስ በርስ መመካከርያ፣ መጠለያ፣ ዕርቅና አፈርሳታ ማካሔጃ ከመኾኑም በላይ፣ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ በመኾን ያገለግላል፡፡ ዛፍ፣ በአንዳንድ ማኅበረሰብ ባህል ውስጥ የማንነት ትእምርት ሲኾን፣ ዛፍን ከሕይወት መሠረት ጋራ በማያያዝ፣ የራሳቸውን ጥንተ አመጣጥ በሐተታ - ተፈጥሯዊ - ሚት መልክ የሚያቀርቡ ማኅበረሰቦች በአገራችን እንዳሉ፤ ሰሎሞን ተሾመ፣  “ፎክሎር፤ ምንነቱ እና የጥናቱ የትኩረት አቅጣጫ” በሚለው መጽሐፉ ገልጿል፡፡  
በተጨማሪም፣ “ዛፍ የሌለው ደብር* ጽሕም የሌለው መምህር” እንዲሉ፣ አብያተ ክርስቲያናትን በርቀት እይታ የምንለያቸው፣ በዙሪያቸውና በግቢያቸው በከበቧቸው ታላላቅ ዐጸዶች ትእምርታዊነት ነው፡፡ ገዳም ማለትም፣ በአንድ ገጹ* ዱር፣ ጫካ፣ የአራዊት መናኸርያ እንደማለት ነው፡፡(ኪዳነ ወልደ ክፍሌ፣ 302)
ማጠቃለያ
ሰው ምሉእነትን የሚጎናጸፈው፣ ለቁመተ ሥጋው የሚያስፈልገውን ምግብ ስላገኘ ብቻ አይደለም፡፡ ታላቁ መጽሐፍ እንደሚለውም፣ “የሰው ልጅ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡፡” ይልቁንም፣ ከፍጥረታት ኹሉ የሚለየው የአእምሮ እና የመንፈስ ምግብ ጥያቄው ትልቅ ቦታ ይይዛል፡፡ የአንድ ዩኒቨርሲቲ ተቀዳሚ ሚና፣ ይህንኑ፣ የሰው ልጅ በተፈጥሮ ለማወቅ በብርቱ የሚሻውን አእምሯዊና መንፈሳዊ “መፍቅድ” ለማሟላት መጣር ነው፡፡
ከላይ የጠቀስናቸው ፕ/ር ዶናልድ ሌቪን፣ “በአንዳንድ ዩኒቨርስቲዎች ውስጥ በኅብረ ሠናይ (Common Good) እና በጥቅም - ተኮር - ሠናይ (Utilitarian Good) መካከል ውጥረት ይኖራል፤” ይላሉ፡፡ በእነኚኽ ተፃራሪም ተደጋጋፊም ውጥረቶች መካከል፣ አንድ ዩኒቨርሲቲ በጎ መልክ ይዞ ሊወጣ የሚችለው፣ የጋራ ሠናይ ፍላጎትን፣ ከጥቅም ተኮር ፖሊሲ በላይ በማስቀደም ሲጓዝ ነው። ይህ ሲኾን ግን፣ ጥቅም ተኮር ሠናይነትን አምዘግዝጎ ይጥለዋል ማለት ሳይኾን፤ ይኸው ጥቅም ተኮርነት በጋራው ሠናይ ፍላጎት ውስጥ ተካብቶ የሚቀመጥ በመኾኑ ነው። በአንጻሩ፣ ጥቅም ተኮር ሠናይ፣ የጋራ ሠናይ ፍላጎትን በምልአት ይዞ አይገኝም፡፡
ፕሬዝዳንት አድማሱ፣ የዩኒቨርሲቲውን ልዕልና እና አካዳሚያዊ ንጽሕ (Chastiti) በማስደፈር፣ መንግሥት* “ዕድገት እና ልማት” የሚለውን ፖሊሲ ለማንሰራፋት በሙሉ ልብ ስለ ተሰማሩ፣ በቅጽሩ ውስጥ ያሉት ዐጸዶች ተቆርጠው፣ “ልማት” ለሚባለው ጣዖት ሰለባ እንዲኾኑ አድርገዋል፡፡ ከአእምሯዊ ይልቅ አካላዊ መስፋፋትን አብልጦ አትኩሮት መስጠት፣ የትምህርት ፈላስፎች እንደሚሉት፣ በ“ዳይናሶራዊ ሲንድረም” መለከፍ ነው፡፡
ይኸውም፣ ዳይናሶር፣ ስዒረ ፍጥረት የደረሰበት አካላዊ ግዘፉ እየፋፋ፣ አእምሯዊ ኃይሉ እያጸጸ ቆይቶ፣ ራሱን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ወደማይችልበት ክስመት ደርሶ ህልውናው በመጥፋቱ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም፣ ከምሥረታው አንስቶ የካበተ ምሁራዊ ጥሪትና የታላላቅ ልሂቃን እርሾ ባይኖረው ኖሮ፣ እንደ ፕሬዝዳንት አድማሱ ተግባር፣ የዳይናሶር ሲንድረም ሰለባ ይኾን ነበር፡፡
በተጨማሪም፣ ዩኒቨርሲቲው የተፈደቀለትን በጀት ሙሉ በሙሉ ባለመጠቀም፣ በየዓመቱ በርካታ ሚሊዮን ብሮችን ተመላሽ እንደሚያደርግ የታወቀ ነው፡፡ ይህም ኾኖ እያለ፣ ለዩኒቨርሲቲው ተጨማሪ ገቢ እየተባለ በፕሬዝዳንቱ ቢሮ ፕሮጀክት ተቀርጾ* ከበሬ ማድለብ እስከ ዕንቁላል መሸጥ፤ አልፎም የሱፐር ማርኬት የንግድ ሱቆች የማቋቋሙን ተግባር ተያይዞታል፡፡ እዚኽ ላይ ልብ ልንለው የሚገባን፣ የገንዘብ እጥረት በሌለበት ኹኔታና የተፈደቀለትንም በጀት በአግባቡ ሳይጠቀም፣ ተጨማሪ ገንዘብ ያስፈልገኛል በሚል ሰበብ፣ ከዕውቀት ጋር ባልተያያዙ ንግዶች ላይ መሰማራቱ በብዙ መልኩ ስሕተት ነው፡፡
ዩኒቨርሲቲው ኹሌም ሊተጋበት የሚገባው፣ ነገር ግን፣ ኹሌም በምልአት የማያሳካው ዋናው የአእምሮ ጥሪትንና ጠፍታን ማካበትና ማረጋገጥ ኾኖ ሳለ፣ ባላገደደው ንግዳዊ ተልእኮ ውስጥ መሰማራቱ አስገራሚ ነው፡፡ ምናልባት፣ የመጀመሪያ ተልእኮውን (የአእምሮ ሥልጥንና) ካሟላ በኋላ ወደ ንግድ ቢገባ፣ ችግር አይኖረውም ይኾናል፡፡   
በርግጥ ዩኒቨርሲቲው፣ ከሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች ጋራ እንደ ዩኒቨርሲቲ ሲለካ፣ ደረጃው እያሽቆለቆለ መምጣቱ ከማንም ያልተደበቀ እውነታ ቢኾንም፤ የግቢው “ግርማ ሞገሳዊ” የውጭ ገጽታ ግን፣ ኹሌም የሚደነቅና በተለያዩ ሀገራት ጎብኚዎች ጭምር የተመሰከረለት ነበር፡፡ ይህን ግርማ ሞገሱን፣ ዛሬ በፕሬዝዳንት አድማሱ ተነጥቆ ዕርቃኑን ቆሟል፡፡
የዛፉ ምንጣሮ፣ ለዩኒቨርስቲው አካላዊ መስፋፋት አማራጭ የሌለው አመክንዮ ተደርጎ በእነ ፕሬዝዳንት አድማሱ ጥቅም ተኮር አስተሳሰብ ይገለጽ ይኾናል፡፡ ከኹሉ በፊት፣ “አማራጭ የለሽ” ይሉት ይኸው ህወሓታዊ ሜታፊዝክስ(የእኛ ሐሳብ* ትክክለኛው እና ብቸኛው ነው፤ የሚል የሐሳብ ሞኖፖሊ)፣ በተለያዩ አጀንዳዎች እንዳየነው፣ አስቀድሞ የተቆረጠንና የተፈጠመን ነገር፣ ያለተገዳዳሪ ሐሳብ ለማስፈጸም የሚጠቀሙት ዘይቤ ነው፤ ፕሬዝዳንቱም፣ የዚኹ፣ “አማራጭ የለም፤” ባይ የሥርዓቱ ፍልስፍና ሰባኪና አስፈጻሚ ኾነው እናገኛቸዋለን፡፡ በአንጻሩ፣ ዩኒቨርሲቲው፣ እንደ መካነ አእምሮ፣ የአማራጭ የለሽ ፍልስፍናን ሽሮ፣ ለተለያዩ ፕሮብሌሞች ኊልቊ መሳፍርት የሌላቸው አማራጮችን የማቅረብ ሓላፊነት አለበት፡፡ ዩኒቨርሲቲው ለሚፈልገው የማስፋፊያ ሥራ ሌሎች የቦታ አማራጮችን መጠየቅ ሲችል፤ ሥነ ውበትን ገርስሶ፣ የኮንስትራክሽን ጣቢያና የፎቆች ጫካ የመሰለ ትዕይንት መፍጠር ተገቢ አይደለም፡፡
የደን ምንጣሮውንና የሕንፃ ማስፋፊያውን፣ ከፕሬዝዳንቱና ከበላይ ሹሞቻቸው ሕጸጽ አኳያ በየአንጻሩ ለማሳየት ሞክረናል፡፡ በዚኽ ጉዳይ ላይ፣ የዩኒቨርሲቲው ግድፈት የሚያሳየው፣ የ“ኤፒስቲሚክ” እና የ“ኤስቴቲክ” ችግርን ብቻ ሳይኾን፤ የአንድ ቢሊዮን ብር ፕሮጀክትን በ‘ካፒቴንነት’ ለማስተዳደር ከመሻት የመነጨ እንደኾነ መገመት አያስቸግርም፡፡ መቼም፣ ዜጎች ብቻ ሳይኾኑ፣ “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል” እንዲሉ፣ የአማሳኞቹ ቡድን በስም ዝርዝር ባይነገረንም፣ ስለ ሙስናው መንሰራፋት አንዳንድ የሥርዐቱ ሹመኞችም ቢኾኑ በይፋ ያመኑበት ጉዳይ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሙስና ዕንብርት ተብለው የተለዩና ብዙዎችን ካስማሙት ቀዳሚዎቹ፡- የመሬት አስተዳደር፣ የመንገድና የሕንፃ ግንባታ፣ የገቢዎች እና ጉምሩክ አሠራር ላይ የሚታየው ምዝበራ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም፣ የአንድ ቢሊዮን ብር በጀት በተያዘለት የግንባታ ፕሮጀክት ውስጥ ሲገባ፤ በተለይ ኦዲት ተደርጎ የማያውቅ ተቋም ከመኾኑ የተነሳ፣ ምንም ዓይነት የሙስና እንቅስቃሴ በፕሮጀክቱ ላይ አይካሔድም ብሎ ማመን ተላላነት ነው፡፡
ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት አጠያያቂ በኾነበት በአኹኑ ጊዜ፤ በየትኛውም ተቋም ስላለው ሙስና ሐቁን መናገር በጣም ያስቸግራል፤ ለዚኽም ነው፣ ልዑል ራስ ካሳ ኃይሉ፣ “ፍኖተ አእምሮ” በተሰኘው መጽሐፋቸው፡- “ነጻነትን ተከባከቧት፤ እውነት ራሷን ትጠብቃለች” ያሉት፡፡ ነጻነት በሀገራችን ገና የተደላደለ ቦታ ስላላገኘች፣ ለጊዜው እውነት ሸሸግ ብላ ለመቀመጥ ስለምትገደድ፣ እኛም፣ ስለ ሙስና ከዚኽ በላይ ለማተት ኹኔታው እንደማይፈቅድልን በመረዳት፣ የያዝነውን በልባችን እንደያዝን ሐሳባችንን በዚኹ እናሳርፋለን፡፡

Saturday, 11 February 2017 12:54

የዘላለም ጥግ

(ታላላቅ ሰዎች
በመሞቻቸው ሰዓት)
- “ማምለጫ ሰበብ እየፈለግሁ ነው”
ደብሊው ሲ. ፊልድስ
(አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይና ኮሜዲያን)
- “በእግዚአብሔር እ መኑ እ ናም ም ንም
የሚያስፈራችሁ ነገር አይኖርም”
ጆናታን ኤድዋርድስ
(የክርስቲያን ሰባኪና የስነ-መለኮት ልሂቅ)
- “ምድር ወደ ኋላ ስትሸሽ፣ መንግስተ ሰማያት
ሲከፈት ይታየኛል፡፡ እግዚአብሔር እየጠራኝ
ነው”
ዲ.ኤል.ሙዲ
(አሜሪካዊ ወንጌላዊና ደራሲ)
- “ሞት፤ የዘላለማዊነትን ቤተ መንግስት
የሚከፍት ታላቅ ቁልፍ ነው”
ጆን ሚልተን
(የብሪቲሽ ገጣሚ)
- “በአስር ደቂቃ ዘግይቻለሁ፡፡ እኔ ማርፈድ
አልወድም፡፡ ፀሎቱ ጋ ልክ በ11 ሰዓት መገኘት
እፈልጋለሁ፡፡”
ማሃትማ ጋንዲ
(የህንድ የነፃነት ንቅናቄ መሪ)
- “ዛሬ በጣም ሞቃት ነው”
ጄሲ ጄምስ
(አሜሪካዊ የባቡር ላይ ዘራፊ)
- “ሁልጊዜም ጋደም ስል የተሻለ እናገራለሁ”
ጄምስ ማዲሰን
(የአሜሪካ 4ኛ ፕሬዚዳንት)
- “በቃ ተይኝ!”
(ነርሷ የእግር እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ስትጠይቀው)
ጎሬ ቪዳል
(አሜሪካዊ ደራሲ)
- “እስቲ ወደ አባታችን ቤት ልሂድ”
ጆን ፖል (ዳግማዊ)
(የሮማን ካቶሊክ ቤ/ክርስቲያን ጳጳስ)
- “ለብቻዬ ተይኝ፤ ደህና ነኝ”
(ለነርሱ የተናገረው)
ባሪ ዋይት
(አሜሪካዊ ሙዚቀኛ)
- “እና ሞት ይሄ ነው - ይሁና”
ቶማስ ካርሊሌ
(የስኮትላንድ ፈላስፋና የታሪክ ምሁር)
- “የሰሙኝ እንኳን አይመስለኝም”
(ራሱን ከማጥፋቱ በፊት የተናገረው)
ዩክዮ ሚሺማ
(ጃፓናዊ ደራሲ)

Sunday, 12 February 2017 00:00

ገራገሩን -ስለ አገረ ሩሲያ!

- አሜሪካ እ.ኤ.አ በ1867 የአላስካ ግዛትን ከሩሲያ ላይ የገዛችው በ7.2 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ነበር፡፡
- በሩሲያ በታላቁ ፒተር የአገዛዝ ዘመን፣ጺም ያላቸው ወንዶች በሙሉ ለመንግስት ግብር እንዲከፍሉ ይደረግ ነበር - “የፂም ግብር”በሚል፡፡
- እ.ኤ.አ እስከ 2013 ዓ.ም ድረስ በሩሲያ ቢራ እንደ አልኮል መጠጥ አይቆጠርም ነበር፡፡
- ሩሲያ በኒውክሌር የጦር መሳሪያዎች ብዛት በዓለም ላይ ቀዳሚ ናት፡፡ ከ8400 በላይ የኒውክሌር የጦር መሳሪያዎች አሏት፡፡
- እ.ኤ.አ ከ1959 አንስቶ የሩሲያ ሳይንቲስቶች፣ቀበሮዎችን ልክ እንደ ውሻ ለማዳ አድርገዋቸዋል - የቤት እንስሳት፡፡
- የሩሲያ 20 ባለፀጎች አጠቃላይ ድምር ሀብት ከ227 ቢ. ዶላር በላይ ሲሆን ይሄም ከፓኪስታን ጠቅላላ አመታዊ ምርት ይበልጣል፡፡
- እያንዳንዱ ሩሲያዊ በዓመት 18 ሊትር አልኮል ይጠጣል፡፡
- በሩሲያ አማካይ በህይወት የመቆየት ጣሪያ ለወንዶች 59 ዓመት ሲሆን ለሴቶች 73 ዓመት ነው፡፡
- ስታሊን ስደተኛ ነበር፤8 ዓመት እስኪሞላው ድረስ የሩሲያ ቋንቋ መማር አልጀመረም፡፡ አፉን የፈታው በጆርጂያን ቋንቋ ነው፡፡
- ሩሲያ ቢያንስ 15 ምስጢራዊ ከተሞች እንዳሏት ይታመናል፡፡ የእነዚህ ከተሞች ስምም ሆነ ስፍራ የማይታወቅ ሲሆን የውጭ ዜጎች ወደነዚህ

ሥፍራዎች እንዲጠጉ አይፈቀድላቸውም፡፡
- ሞስኮ በዓለም ላይ ትልቁ የማክዶናልድ ሬስቶራንት አላት፡፡

   የዚያድ ባሬን ከስልጣን መውረድ ተከትሎ እንደ አገር መቆም ተስኗት አሳር መከራዋን ስትቆጥር የዘለቀቺው፣ የእርስ በእርስ ጦርነት፣ የጽንፈኛ ቡድኖች ጥቃት፣ ድርቅና ርሃብ እየተፈራረቁ ያደቀቋት ሶማሊያ፤ ከ25 አመታት በኋላ ሰሞኑን ታሪካዊ የተባለውን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ አከናውናለች፡፡በሙስና የታማው፣ በሽብር ስጋት የታጀበው፣ ተስፋ የተጣለበትና ለወራት የዘለቀው የሶማሊያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሂደት፣ ባለፈው ረቡዕ በተሳካ ሁኔታ ተጠናቀቀ፡፡የተረጋጋች አገር፣ የተሻለ ኑሮ፣ ዘላቂነት ያለው ሰላም፣ ብልህና አዋቂ መንግስት፣ ከትናንት የተሻለ ነገ የናፈቀው የሶማሊያ ህዝብ፣ ነገውን የሚወስንለትን ወሳኝ ሰው፣ ቀጣዩን የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ለማወቅ ጓጓ፡፡“ማን ይሆን ተረኛው?...” ሲል ጠየቀ፡፡
“ፎርማጆ ነው!...” አለ የምርጫ ውጤቱ፡፡
የሶማሊያ ዘጠነኛው ፕሬዚዳንት በመሆን መንበረ ስልጣኑን ለመረከብ የተመረጠው ወሳኙ ሰው፣ ፎርማጆ ነው፡፡
“ሶማ-አሜሪካዊ”ው ፎርማጆየምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ በርካታ የአለማችን መገናኛ ብዙሃን፣ ምርጫውን በተመለከተ ያወጧቸው ዘገባዎች ርዕሶች ተመሳሳይና ስላቅ ቢጤ ያዘሉ ነበሩ፡፡ ብዙዎቹ ዘገባዎች ከአዲሱ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ስም ጋር፣ የጥምር ዜግነት ባለቤትነታቸውንም ጭምር በማጉላት የተቀናበሩ ናቸው፡፡እርግጥ ነው...
ቀጣዩ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት አሜሪካዊ ዜግነት ያላቸው መሆናቸው ያልተለመደ ቢሆንም፣ የአገሪቱ ህግ ግን የሌላ አገር ዜግነት ያለው ሶማሊያዊ በፕሬዚዳንትነት እንዳይወዳደር የማያግድ ነውና፣ ጉዳዩ ከጊዜያዊ ግርምት አልፎ ፖለቲካዊ ጥያቄ አላስከተለም፡፡ በምርጫው ያሸነፉት የሶማሊያና የአሜሪካ ዜግነት ያላቸው የ55 አመቱ ሞሃመድ አብዱላሂ ሞሃመድ ፎርማጆ ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ ከ2010 እስከ 2011 በነበሩት ስምንት ወራት አገሪቱን በጠቅላይ ሚኒስትርነት የመሩት ፎርማጆ፣ በ1993 በታሪክ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ሲያገኙ፣ በ2009 ደግሞ ከስቴት ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኒውዮርክ፣ በፖለቲካል ሳይንስ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ተቀብለዋል፡፡በዋሽንግተን የሶማሊያ አምባሳደር በመሆን ያገለገሉትና የአራት ልጆች አባት የሆኑት ፎርማጆ፤ እ.ኤ.አ ከ1985 አንስቶ ነዋሪነታቸው በአሜሪካ
ነው፡፡ ቤተሰቦቻቸውም አሁንም ድረስ በአሜሪካ ነው የሚገኙት፡፡
“አዲሲቷን ሶማሊያ እፈጥራለሁ፣ በጽንፈኛው ቡድን አልሻባብ ላይ እዘምታለሁ፣ ከአለም አንደኛ አድርጎ ስማችንን በአጉል የሚያስጠራውን ሙስናን በቁርጠኝነት እዋጋለሁ!...” ሲሉ ቃል ገብተዋል፤ ፎርማጆ ድላቸውን ተከትሎ ባደረጉት ንግግር፡፡ድምጽ 100 ሺህ ዶላር ይሸጣል!...
የሶማሊያ ምርጫ ስርዓት በአንዳንድ አገራት ቢሰራበትም፣ ከተለመዱት የምርጫ ስርዓቶች ወጣ ያለ ነው፡፡
በመጀመሪያ የአገሪቱ የጎሳ መሪዎችና የአገር ሽማግሌዎች፤ የፓርላማ አባላትንና ሴናተሮችን ይመርጣሉ፡፡ እነዚሁ ተመራጮች በተራቸው፣ ለፕሬዚዳንትነት ለመወዳደር በዕጩነት ለቀረቡ ተወዳዳሪዎች ድምጻቸውን ይሰጣሉ፡፡ በሶስት ዙር በሚሰጥ ድምጽ በሚደረግ ማጣሪያም
አሸናፊው ፕሬዚዳንት ይለያል፡፡በዚህ መልኩ በተከናወነው የዘንድሮው ምርጫም 14 ሺህ ያህል የጎሳ መሪዎችና የአገር ሽማግሌዎች የመረጧቸው 329 የፓርላማ አባላትና ሴናተሮች፣ በተወዳዳሪነት ለቀረቡት 21 ዕጩዎች ድምጻቸውን ሰጥተዋል፡፡በስተመጨረሻም...
በስልጣን ላይ የቆዩትና ለሁለተኛ የስልጣን ዘመን ይቀጥላሉ የሚል ከፍተኛ ግምት ተሰጥቷቸው የነበሩት ሃሰን ሼክ ሙሃሙድ 97 ድምጽ በማግኘት ሽንፈትን ሲያስተናግዱ፣ ሞሃመድ አብዱላሂ ሞሃመድ ፎርማጆ ፎርማጆ 184 ድምጽ በማግኘት አሸንፈዋል፡፡ይህም ሆኖ ግን...
ታሪካዊ የተባለው ምርጫ በሙስና መታማቱ አልቀረም፡፡ተቀማጭነቱ በሞቃዲሾ የሆነው ማርካቲ የተባለ የጸረ ሙስና ተቋም በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ባወጣው ሪፖርት፤ በምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ፣ መራጮች በገንዘብ ተደልለው ድምጻቸውን እንዲሰጡ እየተደረገ ነው ብሏል፡፡በዚህ መልኩ በሙስና ድምጻቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ ያልሆኑ የህዝብ ተወካዮች፣ የመራጭነት መብታቸውን ከመገፈፍ አንስቶ እስከ ግድያ የሚደርስ ጥቃት እንደሚፈጸምባቸው እንደተዛተባቸውም ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡አንዳንድ የህዝብ ተወካዮች ለአንድ የፓርላማ አባል ድምጻቸውን ለመስጠት፣ እስከ 30 ሺህ ዶላር የሚደርስ ገንዘብ በሙስና መልክ እንደተሰጣቸውና፣ በፕሬዚደንትነት ለመወዳደር የቀረቡ አንዳንድ ዕጩዎች በበኩላቸው፤ የፓርላማ አባላቱ እንዲመርጧቸው  እስከ 100 ሺህ ዶላር የሚደርስ ገንዘብ መደለያ (ጉቦ) እንደሰጡም ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡ አውሮፕላን ጣቢያ - ምርጫ ጣቢያበአለማችን የምርጫ ታሪክ በአውሮፕላን ጣቢያ ውስጥ የተከናወነ የመጀመሪያው ምርጫ ሳይሆን አይቀርም ተብሏል - የሰሞኑ የሶማሊያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፡፡የአገሪቱን አንድ ሶስተኛ ግዛት ያህል ተቆጣጥሮ የሚገኘው ጽንፈኛው ቡድን አልሻባብ፣ የሽብር ጥቃት በመፈጸም ምርጫውን ሊያስተጓጉል ይችላል ተብሎ በመሰጋቱ ሳቢያ፣ የምርጫ ስነስርዓቱ በሞቃዲሾ በሚገኝ የፖሊስ አካዳሚ ቅጽር ግቢ ውስጥ እንዲደረግ ነበር የታሰበው፡፡ በኋላ ላይ ግን፣ የተሻለ የጸጥታ ሁኔታና የተጠናከረ ጥበቃ ያለበት ስፍራ መፈለግ እንዳለበት ተወሰነ፡፡ በዚህም መሰረት ምርጫው በአገሪቱ እጅግ የተጠናከረ ጥበቃ ያለበት ስፍራ እንደሆነ በተነገረለት የሞቃዲሾ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ እንዲከናወን ተደርጓል፡፡አልሻባብ የምርጫ ሂደቱን ለማወክ መሞከሩ አይቀርም የሚለው ስጋት እንቅልፍ የነሳው የአገሪቱ መንግስት፣ በሞቃዲሾ የትራፊክ እንቅስቃሴ ለ8 ሰዓት ሙሉ ለሙሉ እንዲዘጋ ከማድረግ ባለፈ፣ የሞቃዲሾ አውሮፕላን ጣቢያም መጪም ሆነ ሂያጅ አውሮፕላንን ላያስተናግድ ተዘግቶ ነው የዋለው፡፡ህዝቡ ፈንድቋል...
የምርጫው ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሶማሊያውያን በመዲናዋ ሞቃዲሾ ጎዳናዎች ላይ በመውጣት በደስታ ሲፈነጥዙ ታይተዋል፡፡ በፎርማጆ ማሸነፍ የፈነደቁ ወታደሮችም በደስታ ተኩስ፣ ሞቃዲሾን ሲያደምቋት አምሽተዋል ተብሏል፡፡ሰውዬው ምንም እንኳን የዳሮድ ጎሳ አባል ቢሆኑም፣ የተሻለች አገርን ተስፋ ያደረጉ ሶማሊያውያን ግን፣ ጎሳ ሳይለዩ አደባባይ በመውጣት ለፕሬዚዳንቱ ያላቸውን ድጋፍ ገልጸዋል፡፡ በኬንያ ዳባብ የስደተኞች ካምፕ የሚገኙ በርካታ ሶማሊያውያንም ደስታቸውን እንደገለጹ ተዘግቧል፡፡



አንዳንድ ተረት ተደጋግሞ ይነገራል፡፡ ነገር ግን ወይ ስለማይገባ፣ አሊያም ቸል ስለሚባል እንደገና መደገሙ ግዴታ ይሆናል፡፡ የዛሬውም
ከዓመታት በፊት ያልነው ነው፡፡ (አንድ የፈረንጅ ጸሐፊ “As no one listens we should say it again…” ይላል፡፡ የሚሰማ ስለሌለ እንደገና
መናገር አለብን፤ ማለቱ ነው።)
እኛም እንድገመው፤ አሻሽለን፡-
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ገበሬ የእርሻ ስራውን አጠናቆ ወደ ቤቱ እየመጣ ነበር፡፡
ጦጢት ደግሞ እንደ ልማዷ ዛፉ ላይ ሆና ገበሬው ሲመጣ ታየዋለች፡፡ ገበሬው ከዘር ዝሪ እንደሚመጣ ታውቋታል፡፡ ወቅቱ የዘር መዝሪያ ጊዜ
መሆኑን ተገንዝባለች፡፡ ስለሆነም የዘራው ዘር እሷ የምትበላው ዓይነት ከሆነ፣ ሄዳ እየፈለፈለች እያወጣች ልትበላ ነውና መረጃ ፈልጋለች፡፡
ስለዚህ ገበሬውን ለማወጣጣት በትህትና ትጠይቀዋለች፡፡
“ገበሬ ሆይ! እርሻ ምን መሳይ ነው?”
ገበሬ፤
“ሁሉ አማን፣ ሁሉ ሰላም ነው!”
ጦጢት፤
“ዛሬ የዘር ጊዜ ነው አይደል?”
ገበሬ፤
“አዎ የዘር ጊዜ ነው፡፡ በየዓይነቱ ዘር ይዘራል”
ጦጢት፤
“ዘንድሮ ምን ተዘራ?”
ገበሬ፤
“ምን ያልተዘራ አለ፡፡ በቆሎ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣ ስንዴ፣ ሽምብራ፣ ባቄላ፣ ቦሎቄ፣ … ምኑ ቅጡ? ሁሉም የየአቅሙን ይዘራል፡፡ መሬቱ፤ መሬት ነውና

ሁሉንም ይቀበላል”
ጦጢት፤
“እንደው ደፈርሺኝ አትበለኝና አንድ ጥያቄ እንድጠይቅህ ትፈቅድልኛለህ?”
ገበሬ፤
“እስካሁን የፈለግሺውን እንድትናገሪ ፈቅጄልሽ የለ?”
ጦጢት፤
“አይ ይሄኛው ወሳኝ ነው ብዬ ስለማምን ነው፡፡ ልጠይቅህ?”
ገበሬ፤
“ኧረ ጠይቂ፤ ምንም ችግር የለም”
ጦጢት፤
“አመሰግናለሁ፡፡ እንደው ዘንድሮ አንተ ምን ዘራህ?” አለችው
ገበሬ፤ ጦጢት ሄዳ እንደምትቦጠቡጠው ያውቃልና እሷ የማትፈለፍለውን እህል አስቦ መናገር አለበት፡፡ አሰላ አሰላና፤ በትህትና፡-
“ጦጢት ሆይ፤ እኔ ዘንድሮ የዘራሁት ተልባ ነው” አላት፡፡
(ጦጣ ለመፈርፈር በጣም የሚያስቸግራት ተልባ ነው)
ጦጢት፤
“በጣም ግሩም! በቃ ወርደን እናየዋለና! ወርደን እናየዋለን!” አለችው፡፡
*         *       *
ጦጢት የእኛ አገር ነገር የገባት ነው የምትመስለው፡፡ ከላይ የተነገረውን መሬት ወርዶ ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡
ዲሞክራሲ ሰፍኗል ተብለናል፡፡ መሬት ወርደን እናረጋግጥ! ፍትህ ሰፍኗል ተብለናል፡፡ መሬት ወርደን እናረጋግጥ! (Justice delayed Justice
denied የዘገየ ፍትህ እንደሌለ ይቆራል - ዕውነት ነው?)
የሕግ የበላይነት አለ ተብለናል፡፡ “ፍትህ የተዘጋጀ ዳቦ አይደለም” የሚለው አባባል ነው ተግባራዊ? ታች ወርደን እናረጋግጥ! ማንም የበላይ
የበታቹን እንዳሻው አይበድልም? እናጣራ!
“ዳሩ ዳኛ የለም ልተወው ግዴለም” እያልን አንዘልቀውም፡፡ ወርደን እንየው!
ትምህርት፤ በወላጅ፤ በመምህርና በተማሪ ሶስት - ማዕዘን (Triangular) ግንኙነት እያማረ ነው ተብለናል፡፡ እስቲ መሬት ወርደን እንየው፡፡
ጤና፤ በየጣቢያዎቹ ለህዝቡ በሚያመች ዘዴ ተሰልቶ ዝግጁ ሆኗል ተብለናል፡፡ መዳኒት አለ? የበቃ ህክምና አለ? ጤና ኬላ በቂ ነው? እስቲ
ጦጢት እንዳለችው፤ ይዋጥልን እንደሆን ወርደን እንየው! የመንገድ ሥራ ተሳክቶ ተጠናቋል፤ ተብለናል፡፡ ዘላቂ ናቸው አይደሉም? ወርደን
እናጣራ! አገራችን ሰላም ሆናለች፤ ተብለናል፡፡ ወደ ሰሜን፣ ወደ ምሥራቅ፣ ወደ ደቡብ ምዕራብ ወርደን እንታዘብ፡፡ መሬት የያዘውን አይለቅምና
ወርደን እንየው፡፡ በሀቅ እንዘግበው!
ሀብት፤ በፍትሐዊ መልክ ይከፋፈላል ተብለናል፡፡ እኩልነት ቤት - ደጁን ሞልቶታል ተብሏል፡፡ እስቲ ወርደን ኢወገናዊ መሬት መኖሩን አይተን
እንርካ! የትራፊክ አደጋ ቀንሷል እንባላለን፡፡ መሻሻል አለመሻሻሉን፣ ትራፊክ ሜዳው ላይ ወርደን እንየው! የመልካም አስተዳደር ችግር ነበር
ተብለናል፡፡ ዛሬስ? ወርደን ማየት ነው!
አገራችን የአሸባሪዎች ኮሪደር ናት ተብለናል፡፡ ዕውነት የሽብር ድልድይ ነን? ወርደን ማየት የአባት ነው! የአገራችን ፌደራሊዝም እና ክልላዊ
መስተዳድሮች አካሄድ የተቀናጀና የሰመረ ግንኙነት ያለው ነው ተብለናል፡፡ ወርደን እንየው! ባቄላ፣ በቆሎ ወይስ ተልባ? እናጣራ፡፡ እንናበባለን?
በፓርቲ አባላት መካከል ልባዊ መግባባት፣ ወቅታዊ መናበብ አለ? ተቃዋሚዎች ከአሉታዊ ፅንፍ ወጥተዋል ወይ? ወርደን እንየው!
መንግሥት በግል ሚዲያዎች ላይ ያለው ዕምነት ምን ይመስላል? ዛሬም “በሬ ወለደ ይላሉ” ነው? ዛሬም “የሌሎች አፍ ናቸው” ነው? ዛሬም
“ፀረ-መንግሥት” ናቸው ነው? ዛሬም መታሰራቸው ልክ ነው? ዛሬም የሚታኑና የማይታመኑ ሚዲያዎች አሉ? ወርደን እንያቸው!
በአገራችን ሙስና ጉዳይ የማንስማማበት ምክንያት ያለ አይመስልም፡፡ ይሰረቃል፡፡ ይዘረፋል፡፡ ችግሩ ግን የማይደፈሩ ሰራቂዎችና ዘራፊዎች አሉ
የሉም? ነው፡፡ ጥያቄው ግልፅ ነው!፡፡ ስለዚህ ወርደን እንየው!
ከሁሉም በላይ ደግሞ ከውጪ ያለውን አጋር ወይም ሐሳዊ ወዳጅ መንግስት የምናምነው ምን ያህል ነው? ሴትዮዋ ጓሮ ለሚጠብቃትና
እያስነጠሰ ምልክት ለሚሰጣት ውሽማዋ፣ የባሏን ቤት ውስጥ መኖር ለመንገር፣
“አንት የጓሮ ድመት፣ ምንም ብታነጥስ ዛሬ በዓል (ባል) ነውና፣ ቅጠልም አልበጥስ” እንዳለችው ያንን እየደጋገምን የምንጓዝበት ዲፕሎማሲ
ያስኬደናል ወይ?
ከገዛ ህዝባችን መግባባትና መስማማት እንጂ ከሌሎች በምናገኘው ገቢ (fund) ወይም ድጎማ መተማመን ብዙ አያራምደንም፡፡ የሚያዛልቀን
የህዝብ ሀብት ነው! መቼም ቢሆን ነባርም መፃኢም ህልውናችን የሚወሰነው በህዝባችን ፍቅር ነው!
“አገባሽ ያለ ላያገባሽ
ከባልሽ፣ ሆድ አትባባሽ”
የሚለውን ተረት ሳንታክት ማሰብ ለሀገር ልማትና ዕድገት መሰረት ይሆነናል! አንርሳው!

    በአፍሪካ በየዓመቱ ከአንድ ቢሊዮን በላይ ህፃናት የተለያዩ ጥቃቶች እንደሚደርሱባቸው የጠቆመው “ወርልድ ቪዥን” የተሰኘው አለማቀፉ ግብረ ሰናይ ድርጅት፤ የአህጉሪቱ መሪዎች ህፃናትን ከጥቃት እንዲታደጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡ ወርልድ ቪዥን በህፃናት ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለማስቆም
አገራት የበኩላቸውን እንዲወጡ ለመጠቆምና ለመቀስቀስ ሰሞኑን በአዲስ አበባ ሂልተን ሆቴል ባዘጋጀው የውይይት ፕሮግራም ላይ በአህጉሪቱ የሚገኙ ህፃናት ከፍተኛ በደል እንደሚፈፀምባቸው በዝርዝር ተገልጿል፡፡ የጉልበት ብዝበዛ፣ ያለ እድሜ ጋብቻ፣ የሴት ልጅ ግርዛት እንዲሁም ህፃናትን ያለ እድሜያቸው ለጦርነት የማዋልና በቀጥታ የግጭት ሰለባ የመሆን አደጋዎች እንደተበራከቱ ተመልክቷል፡፡ ከ200 በላይ የሚሆኑ
ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ አመራሮች በሂልተኑ ውይይት ላይ ተገኝተው የአህጉሪቱ ህፃናት ፍዳ በሚያበቃበት ሁኔታ ላይ የመከሩ ሲሆን “የሴት ልጅ ግርዛትን በተመለከተ፣ ከዚህ በኋላ ለድርጊቱ ምንም ትዕግስት የለንም” በሚል መርህ ሁሉም ወገን ድርጊቱን እንዲቃወምና የአህጉሪቱ ሴት ህፃናት ከግርዛት እንዲድኑ ጥሪ ተላልፏል፡፡ ከኢትዮጵያ፣ ከኡጋንዳና ከደቡብ ሱዳን የተውጣጡ የህፃናት ተወካዮችም
በአቻዎቻቸው ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች እንዲቆሙ ጥሪ አቅርበዋል።

Sunday, 12 February 2017 00:00

“ጉዛራ ዛሬ” ይመረቃል

     በኢትዮጵያዊ ፕሮፌሽናል የአደን ባለሙያ የተሰራውና ከ17 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበታል የተባለው “ጉዛራ ሆቴል” ዛሬ ይመረቃል፡፡በአደን ሙያ ከዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ሙሉ ፈቃድ ተሰጥቶአቸው ለረዥም አመታት በሙያው ሲሰሩየቆዩት አቶ ተሾመ አደም፤ በቱሪዝም ዘርፉ ለዓመታት ያዳበሩትን ዕውቀትና ልምድ ተጠቅመው፣ የቱሪስቱን ፍላጎት ለማሟላት በሚያስችል መልኩ ሆቴሉን መስራታቸውን ተናግረዋል፡፡ሲኤምሲ ስዓሊተ ምህረት አካባቢ የተሰራውና ከ20 ለሚበልጡ ኢትዮጵያውያን የሥራ ዕድል ፈጥሯል የተባለውይኸው ሆቴል፤ ዛሬ ታላላቅ የመንግስት ባለስልጣናት በሚገኙበት እንደሚመረቅ ተገልጿል፡፡

     ‹‹ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ማለት ሐሳብንና ገንዘብን አቀናጅቶ ሥራ መፍጠር ነው፡፡ ሰዎች እዚህ ተምረው ወጥተው እንዴት የራሳቸውን ሥራ መፍጠር እንደሚችሉ ነው የምናስተምረው፡፡ ሐሳብና ገንዘብ እንዴት እንደሚቀናጁ መንገድ እናሳያለን፡፡ ከፊዚቢሊቲ ጥናት አንስቶ ማርኬቲንግና ፋይናንሻል ስትራቴጂ እንዴት እንደሚቀረጽ እናስተምራለን፡፡ ምክንያቱም ያለ ፋይናንስ (ገንዘብ) ሐሳብ ብቻውን ውጤታማ አይሆንም፡፡ ድሮ በአገራችን ገንዘብ ያለው ሰው ነጋዴ፣ ነጋድራስ ይሆን ነበር፡፡ አሁን ግን ሁኔታዎች ተለውጠዋል፡፡ ሐሳብ ሆኗል ገንዘብ፡፡ እነ ጎግል፣ እነ ፌስቡክ የሐሳብ ውጤቶች ናቸው፡፡ ሐሳብ ነው ብር እየሆነ የመጣው፡፡ እኛ የምናስተምረው ሐሳብን ከገንዘብ ጋር አቀናጅቶ እንዴት ወደ ሥራ መተርጎም እንደሚቻል ነው፡፡‹‹በዚች አገር አንድ ሰው ሐሳብ ይዞ ሲነሳ፣ ብዙም ተቀባይነት የለውም፡፡ ባንኮች እንዴት ገንዘብ ሊያበድሩት እንደሚችሉ፣ ብር ያላቸው ሰዎች እንዴት ገንዘባቸውን ሊሰጡት እንደሚችሉ እንዲቀምር ነው የምናስተምረው፡፡ አገልግሎት ሰጪዎች ደግሞ እንዴት ሊጠቀሙ እንደሚችሉ፣ ከአራትና አምስት ዓመት ገቢያቸው ጋር እንዲያስተያዩት፤ እንዴት የበለጠ ገቢ ማግኘት እንደሚችሉ፣ ገንዘባቸውን ባንክ ከሚያስቀምጡ ኢንቨስት ቢያደርጉ የተሻለ ገቢ እንደሚያገኙ ማሳመን መቻልን ነው የምናስተምረው ‹‹ከአንድ ቢዝነስ ወጥቶ እንዴት ሌላ የተሻለ ቢዝነስ መጀመር እንዳለበትም እናስተምራለን፡፡ ቀደም ሲል አያቱ ወይም አባቱ ቤንዚን ማደያ ካላቸው ልጃቸውም ቤንዚን ማደያ ነው የሚኖረው፡፡አሁን ግን ያ አይደለም ዘመናዊ ቢዝነስ፡፡ ቢዝነሱ በፊት ከነበረበት አድጎ ነው መገኘት ያለበት፤ ወደ ፈጠራ ነው መሸጋገር ያለበት፡፡ የቢዝነስ ሞዴል አስተዳደር ትምህርት ይህ ነው›› ብለዋል የዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ፕሬዚዳንትና የኤምቢ ኤ ፕሮግራም ሥራ አስፈጻሚ ዋና ዳይሬክተር አቶ አቤቱ መላኩ፡፡ ከተመሰረተ አንድ መቶ ዓመት ሊሆነው ሁለት ዓመት ብቻ የቀረው የሊንከን ዩኒቨርሲቲ አካል የሆነው ዌስተርን ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ባለፈው ሳምንት በሁለተኛ ዲግሪ በኤምቢኤ (Masters of Business Administration) ለ6ኛ ዙር፣ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን (ቢኤ) ዲግሪ ለመጀመሪያ ጊዜ ያስተማራቸውን ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት እዚህ አዲስ አበባ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ በድምቀት አስመርቋል፡፡ ለመሆኑ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ እንዴት በአገራችን (Masters of Business Administration (ኤምቢኤ) ትምህርት መጀመር ቻለ? መቼ? መልሱን አቶ አቤቱ ይነግሩናል፡፡ ከተመሰረተ 98 ዓመታትን ያስቆጠረው፣ በአሜሪካ፣ ካሊፎርኒያ ግዛት ኦክላንድ ከተማ የሚገኘው ሊንከን ዩኒቨርሲቲ በአራት ወይም በአምስት
አገሮች በኤክስቴንሽን ያስተምራል፡፡ የአፍሪካ ተወካይ ናይጀሪያ ነበረች፡፡ ይህ ካምፓስ በፀጥታ ችግር መዘጋቱን አቶ አቤቱ በማስታወቂያ ሰሙ፡፡ እንዴት አፍሪካን የሚያህል አህጉር ያለ ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ተወካይ ይቀራል? በማለት ጠየቁ እኛ ለደህንነታችን ነው ቅድሚያ
የምንሰጠው ተባሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያ አፍሪካን እንድትወክል ተመኙና ኢትዮጵያስ? በማለት ጠየቁ በኢትዮጵያ ሰላም አለ? ኢትዮጵያ (አዲስ አበባ) የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን፣ በርካታ ዓለም አቀፍና አኅጉር አቀፍ ድርጅቶች ያሉባት፣ ፈረንጆች በእኩለ ሌሊት የሚንሸራሸሩባት ናት በማለት መለሱ፡፡ “ለምን ፕሮፖዛል ጽፈህ ለባለ አደራ ቦርድ አቅርበህ አትሞክርም?” አሏቸው፡፡ ፕሮፖዛል ፅፈው አስገቡና ሰዎችም ረድተዋቸው ተቀባየነት አገኙ፡፡ የባለ አደራ ቦርዱ ሊቀ መንበር ግን ጥርጣሬ ገባቸው፡፡ ‹‹ይህ ሰው የተማረው ስለ ቢዝነስ ነው፡፡ የአካዳሚክ እውቀት የለውም፡፡ ታዲያ እንዴት ዩኒቨርሲቲውን መምራት ይችላል?” ሲሉ ጠየቁ፡፡ ቀደም ሲል አቶ አቤቱ ብሉናይል ኢንተርፕራይዝ  ኩባንያ አቋቁመው፣ ለመጀመሪያ ጊዜ አምቦ ውሃንና በደሌ ቢራን ወደ አሜሪካ ወስደው ለ5 ዓመት የሸጡና ያስተዋወቁ ሰው
ናቸው፡፡ እዚህ አገር ቤት በተፈጠረ ችግር ተቋረጠ እንጂ አምቦ ውሃው በአሜሪካ ገበያ ጥሩ ተቀባይነት አግኝቶ ነበር፡፡  ለባለአደራ ቦርዱ ሊቀመንበር ጥያቄ፣ የሊንከን ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ሲመልሱ፣ ‹‹ከአፍሪካ (ኢትዮጵያ) ውሃ አምጥቶ በአሜሪካ ገበያ መሸጥ ከቻለ፣ ይህንን
ዩኒቨርሲቲ አገር ቤት ወስዶ እንዴት ነው መምራት የሚያቅተው?” በማለት ተሟገቱላቸው፡፡ በዚህ ዓይነት በሊንከን ዩኒቨርሲቲ ተወክለው ወደ ኢትዮጵያ ተላኩ፡፡
ሊንከን ዩኒቨርሲቲ… እዚህ (ኢትዮጵያ) ሲመጣ ድንበር ተሻጋሪ ስለሚባል ትምህርት ግልጽ መመሪያ አልነበረም፡፡ ‹‹ጥርጣሬውም ስለነበር ሊፈቅዱልኝ አልፈለጉም ነበር፡፡ ሦስት ወር ሙሉ ከወዲያ ወዲህ በመመላለስ ጫማዬን ጨርሼ ምንም ውጤት ስላላገኘሁ፣ ከፍተኛ ፍርሃትና
ስጋት ገብቶኝ ነበር›› ይላሉ አቶ አቤቱ ሊንከን ዩኒቨርሲቲን በኢትዮጵያ ለማቋቋም ገጥሟቸው የነበረውን ችግር ሲያስታውሱ፡፡ በመጨረሻም  ተስፋ ቆርጠው ወደ አሜሪካ ለመመለስ ሲነሱ፣ ቀደም ሲል ያውቋቸው የነበሩትን ወዳጃቸውን፤ ‹‹ሰላም ሁን›› ለማለት ቢሮአቸው
ደወሉላቸው፡፡ ወዳጃቸውም ‹መቼ መጣህ?›› በማለት ጠየቁ፡፡ አቶ አቤቱ ‹‹አይ፤ ሳላይህ ብሄድ ውቃቢህ ያየኛል ብዬ ነው የደወልኩት እንጂ መሄዴ ነው›› አሉ፡፡፡ ወዳጃቸውም ‹‹መቼ መጣህ›› አሉ፡፡ ‹‹ለዚህ ጉዳይ ነበር የመጣሁት፡፡ አሁን ስላልተሳካልኝ ተስፋ ቆርጨ መመለሴ ነው››
በማለት መለሱ፡፡ ‹‹ስልኩን ዝጋው፤ መጣሁ›› ብለው፤ አቶ አቤቱ ወደ ነበሩበት ሄደው በመኪና ወደ ቢሯቸው ወሰዷቸውቢሮ እንደደረሱ ለምን ወደ ኢትዮጵያ እንደመጡ፤ ያደረጉትን ጥረት፣ አልሳካ ቢላቸው ተስፋ ቆርጠው ለመመለስ እንደወሰኑ በዝርዝር
አጫወቷቸው፡፡ ወዳጃቸው በሰሙት ነገር በጣም ተገረሙ፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ የሚያውቋቸው ሰዎች ስለነበሩም እነሱን በስልክ አግኝተው ስለጉዳዩ አጫወቷቸውና፤ ‹‹እንዲህ ያለ ነገር እንዴት ይታለፋል? ያገር ጉዳይ’ኮ ነው›› በማለት ፋክስ አደረጉላቸው፡፡ ከዚያም አሪጂናል ዶክመንቶችን አገላብጠው ተመለከቱ፡፡ ‹‹ ይህን ይዘህ ማን ጋር ሞከርክ?›› በማለት ጠየቋቸውየ‹‹እገሌ የሚባል ያልሞከርኩበት ባለሥልጣን የለም፡፡ በማለት መለሱ፡፡ ‹‹ለምን አንድ ሦስት ቀን አትቆይም?›› አላቸው፡፡ አቶ አቤቱም፤ ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ጉዳይ አያልቅም፡፡ ስለዚህ ተመልሼ መስራት አለብኝ፡፡ በጊዜ አልቀልድም፣ ስለ ጊዜ አጠቃቀም ነው የተማርኩት›› አላቸው  ሰዎቹም፤ ‹‹ግድ የለም፤ ተስፋ አትቁረጥ፤ እኛም እንረዳሃለን››አሏቸው፡፡
በዚህ ዓይነት ከሚመለከታቸው ቢሮዎች ጋር ግንኙነት መፍጠር ተጀምሮ ፈቃድ ተሰጣቸው፡፡ ፈቃዱን ሲያገኙም ብቻቸውን እንዲሠሩ ሳይሆን፣ አስተማማኝነቱ ከተረጋገጠ ተቋም ጋር ተዳብለው እንዲሰሩ ከኒው ጀኔሬሽን ዩነቨርሰቲ ኮሌጅ ጋር ተዳብለው በ2010 መሥራት ጀመሩ፡፡ ለአንድ ዓመት ከሰሩ በኋላ በተለያዩ ምክንያቶች ከኮሌጁ ጋር ተዳብሎ መስራቱን አስተዳደሩም ሆነ ተማሪዎች ስላልወደዱት፣ እንደገና
አመልክተው ፈቃድ ስላገኙ ነፃ ሆነው በራሳቸው መስራት መጀመራቸውን አቶ አቤቱ አስረድተዋል፡፡
 ዩኒቨርሲቲውን ለመክፈት ግን በጣም ፈታኝ ችግሮች ገጥሟቸው እንደነበር አቶ አቤቱ ይናገራሉ፡፡ ተስፋ ቆርጠው ሊመለሱ ሲነሱ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት በነበሩ ሰዎች ድጋፍ አግኝቶ (እ.ኤ.አ)፣ በ2010 ከኒውጀኔሬሽን ዩኒቨርሲቲ ጋር ተዳብሎ እንዲሠራ ፈቃድ እንደተሰጠው ገልጸዋል፡፡ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የሚያስተምረው ስለቢዝነስ ነው፡፡ ዘመናዊ የቢዝነስ ጥበብ አስተምሮ በማስተርስ (ሁለተኛ) ዲግሪ ያስመርቃል፡፡ ዘንድሮ ግን ለማስተርስ ፕሮግራም ሥልጠና ብቁ የሆኑና ተገቢውን መመዘኛ የሚያሟሉ ተማሪዎችን ለመመልመል ያስችለው ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን አስተምሮ 18 ተማሪዎችን በመጀመሪያ ዲግሪ አስመርቋል፡፡ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁ፣ በዲያግኖስቲክ ኢ-ሜጂንግ (ስካኒንግ፣ ሲኖግራፊ፣) ስፔሻላይዝድ ያደረገ ስለሆነ በሚቀጥለው ዓመት በዚህ እውቀት
አስተምሮ በመጀመሪያ ዲግሪ ለማስመረቅ አቅዷል፡፡ ነገር ግን አንድ ችግር አለበት፡፡ ይኼውም ተማሪዎች ወጥተው ልምምድ የሚያደርጉበት ሆስፒታል ያስፈልጋል ሁለተኛ፣ ለሆስፒታሉ የሚያገለግሉ መሳሪያዎች መግባት አለባቸው፡፡ መሳሪያዎቹን ለማስገባት የጉምሩክ ፈቃድ
ይፈልጋል፡፡ ፈቃዱን ለማግኘት ደግሞ ዕቃዎች መሟላት አለባቸው የሚል ችግር ቢያጋጥማቸውም ይፈታል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡ የእኛ ዩኒቨርሲቲ ልዩ ኳሊቲው (ጥራቱ) የትምህርት አሰጣጡ ካሪኩሌም የሚቀረፀው በ1919 ዓ.ም በተመሠረተውና ዕድሜ ጠገብ በሆነው
ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ነው ያሉት አቶ አቤቱ፣ ከሚያስተምራቸው 11 ኮርሶች ስምንቱን መምህራን ከአሜሪካ ሊንከን ዩኒቨርሲቲ መጥተው እንደሚያስተምሩ፣ ሦስት ኮርሶች ብቻ እዚህ ባሉ መምህራን እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡ እኛ የምንደራደረው በጥራትና ጥራት ብቻ ነው፡፡
የምናስተምራቸውን ጥቂት ሰዎች በጥራት አውጥተን ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እናደርጋለን ዩኒቨርሲቲው በትምህርት መረጃ መጻሕፍት የተሟላ መሆኑን አቶአቤቱ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ኤሌክትሮኒክስ ቤተ መጽሐፍት የተጀመረው በእኛ ዩኒቨርሲቲን ነው፡፡ ዳታ ቤዙ አሜሪካ ሆኖ ተማሪዎች እዚህ ተቀምጠው የሊንከን ዩኒቨርሲቲ ቤተ መጻሕፍት ነው የሚጠቀሙት፡፡ መጽሔትና ጋዜጦችን  ጨምሮ የበርክሌይ ዩኒቨርሲቲ ቤተ መጻሕፍት መጠቀም ይችላሉ፡፡ ከአሜሪካ የሚመጡ መምህራን በኢንተርኔት ከራሳቸው መጻሕፍት ነው የሚያስተምሩት፡፡ የእኛ
ዩኒቨርሲቲ መምህራን ለየት ያሉ ናቸው፡፡ ትምህርታቸው እንደዚህ አገር መምህራን በንድፈ ሐሳብ (ቲዮሪ) ላይ ብቻ የተመሠረተ አይደለም፡፡ ቢዝነስ ላይ ያሉና ሕይወታቸውን እየኖሩበት ያለውን ልምድ ነው የሚያስተምሩት፡፡ ለምሳሌ በምረቃው ላይ የተገኙት የባለአደራ ቦርዱ
ሊቀመንበር የህክምና ዶክተር (አንኮሎጂ- የካንሰር ስፔሻሊስት) ናቸው። ነገር ግን እዚህ ሲመጡ የሚያስተምሩት የ200 ሆስፒታሎች ኃላፊ ስለሆኑ ሊደርሺፕና ኮሙኒኬሽን ነው››  በማለት አብራርተዋል፡፡  ለአንድ አገር እድገትና ለውጥ ትምህርት እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነገር ግን ቁጥር ሳይሆን በጥራት ሲሰጥ ነው የተፈለገው ራዕይ እውን የሚሆነው ይላሉ - አቶ አቤቱ፡፡ ‹‹ የእኛ የወደፊት ዕቅድ ከመዋዕለ ህፃናት እስከ ሁለተኛ ዲግሪና ዶክትሬት ድረስ ከስር መሰረቱ ኮትኩቶ ማውጣት ነው፡፡
የእኛ ዕቅድ እንደ ሀርቫርድና እንደ ስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን ከሥር ከመሰረቱ ኮትኩቶ ማውጣት ነው፡፡ ፐሮፖዛል አስገብተን የመሬት ጥያቄም አቅርበናል” ሲሉ ተናግረዋል፡፡በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ከአሜሪካ- ሳንፍራንስኪስኮ ከሪችሞንድ ከተማ ሳንቴ የተባለ ሬስቶራንት ባለቤት ወ/ሮ መንበረ አክሊሉ በሊንከን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ኃላፊዎች ጋባዥነት ተገኝታ፣ የስኬት ታሪኳን ለተመራቂዎች ተናግራለች፡፡ በሌላ በኩል ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ለመጀመሪያ ጊዜ በተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎች ተሰማርተው ለአገር ኢኮኖሚ ዕድገት የላቀ አስተዋጽኦ ላደረጉት ለአቶ ብዙአየሁ ታደለ፣ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሰጥቷል፡፡ሊንከን ዩኒቨርሲቲ ባሳለፋቸው ስድስት ዓመታት ብዙ ችግሮችን ቢያጋጥሙትም ዋናው ችግር ቢሮ ክራሲው መሆኑን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የከፍተኛ ትምህርት ጥራትና ብቃት ኤጀንሲ የሚባለው ድርጅት ገምጋሚ ብቻ ሳይሆን ተገምጋሚም ነው ለእኔ፡፡ በድንገት መጥተው የሚጠይቁት የዛሬ 30 እና 40 ዓመት የሚሠራበትን ነገር ነው፡፡ ለምሳሌ በዋይ ፋይ ዘመን ላይ እያለን፣ የግድ ገመድ ያለው ኮምፒዩተር ማሳየት የለብንም፡፡ ኔትወርኩ የታለ? በማለት ይጠይቃሉ›› ብለዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የሚጠይቀው ክፍያ ወደድ እንደሚል አቶ አቤቱ ያምናሉ፡፡ ‹‹እኛ የምናስተምረው የርቀት (non-distance) አይደለም፡፡ በክፍል ውስጥ ከተማሪዎች ጋር ፊት ለፊት (non-Distance) ነው፡፡ ስለዚህ መምህራኑ ከአሜሪካ ሲመጡ የአውሮፕላን ይከፈላል፣ ክፍል ገብተው የሚያስተምሩበት የአበል ብቻ 1400-1500 ብር ይከፈላቸዋል፡፡ ሌላው ክፍያውን የሚያንረው የማስተማሪያ ሕንፃው ኪራይ ነው፡፡ ለሕንፃው ኪራይ የሚከፈለው 85 ሺ ብር ቢቀር፣ በእርግጠኝነት የተማሪዎች ክፍያ ይቀንሳል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአዲስ አበበ ከተማ አስተዳደሩ ይህን ችግር ተግዝቦ ሕንፃ መሥሪያ ቦታ ቢሰጠን፣ ወደፊት የተማሪዎች ቁጥር ስለሚጨምር፣ የትምህርት ክፍያውም ይቀንሳል›› በማለት አስረድተዋል፡፡