Administrator

Administrator

አብርሃም ግዛው ኢንተርቴይመንትና ስራዎች ድርጅት ከካሌብ ሆቴል ጋር በመተባበር ‹‹ድሮና ዘንድሮ›› የተሰኘ ዓለም አቀፍ የፍቅረኞች ቀንን ታሳቢ ያደረገ የመዝናኛ ፕሮግራም ማክሰኞ ይካሄዳል፡፡
    በፕሮግራሙ ላይ ታዋቂ ሰዎች፣ ረጅም ጊዜ በትዳር ያሳለፉ ጥንዶች የፍቅር ህይወታቸውን የሚያወጉበትና ልምድ የሚያካፍሉበት መድረክ መዘጋጀቱ የተገለፀ ሲሆን “የፍቅረኞች ቀን” በአገራችን መከበሩ ጥሩና መጥፎ ጎኑ ተነስቶ ውይይት ይደረጋል ተብሏል፡፡ በተጨማሪ አዝናኝ ገጠመኞች፣ ሙዚቃ፣ ትዊስትና ሳልሳ ዳንስ፣ ስታንዳፕ ኮሜዲና ሌሎችም የመዝናኛ ፕሮግራሞች ለታዳሚው እንደሚቀርቡ ለማወቅ ተችሏል።

ከአሜሪካ ታላላቅ ኩባንያዎች ግማሽ ያህሉ በስደተኞች የተቋቋሙ ናቸው

     ጎግል፣ አፕል እና ማይክሮሶፍትን ጨምሮ 127 የአሜሪካ ታላላቅ ኩባንያዎች፣ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ ያወጡት የስደተኞች የጉዞ ገደብ የስደተኞችን ህጎችና ህገ-መንግስቱን የሚጥስ ነው በሚል የተቃወሙት ሲሆን በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ በጋራ ክስ መመስረታቸው ተዘግቧል፡፡
በአብዛኛው በቴክኖሎጂ መስክ ላይ የተሰማሩት እነዚህ ኩባንያዎች፣ በጋራ በመሰረቱት ክስ፤ ስደተኞች በአሜሪካ ኢኮኖሚ ላይ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱ በመጠቆም፣ ትራምፕ ስደተኞች ለተወሰነ ጊዜ ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ መከልከላቸው በአገሪቱ ኩባንያዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ በመሆኑ ሊነሳ ይገባል በሚል በክሳቸው ማመልከታቸውን ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡ ስደተኞች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ መከልከላቸው የአገሪቱ ኩባንያዎች የውጭ አገራት ምርጥ ባለሙያዎችን እንዳይቀጥሩና እንዳያሰሩ እክል ይፈጥራል ያሉት ኩባንያዎቹ፤ ተመልሰው የመግባታቸው ጉዳይ አስተማማኝ ካለመሆኑ ጋር በተያያዘ ሰራተኞቻቸውን ወደ ሌሎች አገራት ለስብሰባና ለልምድ ልውውጥ ለመላክ እንደሚያስቸግራቸውም ገልጸዋል፡፡
ከአሜሪካ 500 ታላላቅ ኩባንያዎች መካከል 200 ያህሉ በሌሎች አገራት ስደተኞችና ከስደተኞች በተወለዱ ልጆች የተቋቋሙ መሆናቸውን ታዋቂው ፎርቹን መጽሄት በቅርቡ ይፋ ባደረገው መረጃ ማስታወቁን ያስታወሱት ኩባንያዎቹ፤” ይህም በንግድና ቢዝነሱ መስክ የጎላ ሚና የሚጫወቱትን ስደተኞች ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ መከልከል ኢኮኖሚውን ማዳከምና አዳዲስ ኩባንያዎች እንዳይፈጠሩ እንቅፋት መፍጠር እንደሆነ ያመለክታል” ማለታቸውንም ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡

በፕሬዚዳንትነት ደመወዝ ካገኙት በደራሲነት ያገኙት በ5 እጥፍ ይበልጣል
     የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ከሴኔት አባልነት እስከ ፕሬዚዳንትነት በፖለቲካው አለም በነበራቸው የ12 አመታት ቆይታ፣ የሚስታቸውን ገቢና ከመጽሃፍት ሽያጭ ያገኙትን ገንዘብ ጨምሮ በድምሩ 20.5 ሚ. ዶላር ማግኘታቸውን ፎርብስ መጽሄት በሳምንቱ መጀመሪያ ባወጣው ዘገባ ገልጧል፡፡
ኦባማ እና ባለቤታቸው ሚሼል እ.ኤ.አ ከ2005 እስከ 2016 ባሉት አመታት፣ ከኩባንያ ቦርድ አባልነት 130 ሺህ ዶላር፣ ከፕሬዚዳንትነት ደመወዝ 3.1 ሚሊዮን ዶላር፣ ከሴኔት አባልነት ደመወዝ 610 ሺህ ዶላር፣ ከሚስታቸው የቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ደመወዝ 760 ሺህ ዶላር፣ ከመጽሃፍት ሽያጭ 15.6 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ከተለያዩ ገቢዎች 250 ሺህ ዶላር - በድምሩ 20.5 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝተዋል ተብሏል፡፡
ኦባማ በ12 አመታት ካፈሩት አጠቃላይ ገንዘብ ከሰባ በመቶ በላይ የሚሆነውን ያገኙት ለንባብ ካበቋቸው መጽሃፍት ሽያጭ ሲሆን፣ ኦዳሲቲ ኦፍ ሆፕ እና ኦፍ ዚ አይ ሲንግ - ኤ ሌተር ቱ ማይ ዶውተርስ ከተሰኙት ሁለት መጽሃፍት ብቻ 8.8 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸው ተነግሯል፡፡
ኦባማ በፕሬዚዳንተነት ስልጣን ላይ በቆዩባቸው ስምንት አመታት ብቻ 10.8 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘታቸውን የጠቆመው ፎርብስ፤ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ 3.1 ሚሊዮን ዶላር ያህሉ ከመንግስት በደመወዝ መልክ የተከፈላቸው፣ 120 ሺህ ዶላር የሚሆነው ደግሞ ከኢንቨስትመንቶች በትርፍ መልክ ያገኙት እንደሆነ ገልጧል፡፡
በ2009 አመት 5.6 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኙት ኦባማ፣ በፕሬዚዳንትነት በቆዩባቸው አመታት ገቢያቸው ከአመት አመት እየቀነሰ በመምጣት በ2015 ላይ 450 ሺህ ዶላር መድረሱን ያስታወሰው ፎርብስ፤ ይህም የሆነው የመጽሃፍት ሽያጭ ገቢያቸው እያሽቆለቆለ በመምጣቱ ሰበብ ነው ብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ኦባማና ባለቤታቸው ሚሽል ኦባማ እ.ኤ.አ ከ2005 እስከ 2015 ድረስ ባሉት አስር አመታት ካገኙት አጠቃላይ ገቢ 8 በመቶ ያህሉን ወይም 1.6 ሚሊዮን የሚሆነውን ለበጎ ምግባር ስራ በስጦታ መልክ ማበርከታቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

ተመድ የአገሪቱን ባለስልጣናት በጦር ወንጀል እንዲከስ ተጠይቋል
     የሶርያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት በአራት አመታት ጊዜ ውስጥ ከ13 ሺህ በላይ ሰዎችን በጅምላ በስቅላት ማስገደላቸውን አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ባወጣው ሪፖርት እንዳለው፣ እ.ኤ.አ ከ2011 እስከ 2015 በነበሩት አመታት፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ባሻር አላሳድ ምክትሎችን ጨምሮ ከፍተኛ ባለስልጣናት ባስተላለፏቸው የግድያ ትዕዛዞች፣ ከአገሪቱ መዲና ደማስቆ በስተሰሜን በሚገኘው ሳይድኒያ የተባለ እስር ቤት ውስጥ ከ13 ሺህ በላይ ዜጎች በአሰቃቂ ሁኔታ በስቅላት ተገድለዋል፡፡
በእስር ቤቱ እጅግ ዘግናኝ የግርፋትና የማሰቃየት ተግባራት ይፈጸሙ እንደነበር ያወሳው ተቋሙ፤ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በእስር ቤቱ በየሳምንቱ በአማካይ እስከ 50 የሚደርሱ ሰዎች በስቅላት ይገደሉ እንደነበር በመጥቀስ፣ ከ2015 በኋላ ባለው ጊዜ ውስጥም በሺህዎች የሚቆጠሩ ሌሎች ሰዎች በተመሳሳይ ሁኔታ ተገድለዋል ብሎ እንደሚያምን አስታውቋል፡፡
በእስር ቤቱ ታስረው የነበሩ 31 እስረኞችን፣ ከ50 በላይ ባለስልጣናትንና ባለሙያዎችን በማነጋገር ያገኘውን መረጃ መሰረት አድርጎ ሪፖርቱን ማጠናቀሩን የጠቆመው ተቋሙ፤ አብዛኛዎቹ ግድያዎች የተፈጸሙት ከ2 ደቂቃ በላይ በማይዘልቁ የይስሙላ የፍርድ ቤት ክርክሮች በተላለፉ ውሳኔዎች ይሁን እንጂ፣ የግድያዎቹ ትክክለኛ መነሻ በከፍተኛ ባለስልጣናቱ የተላለፉ ፖለቲካዊ ውሳኔዎች ናቸው ብሏል፡፡
የሶርያ መንግስት ባለስልጣናት በእስር ቤቱ የፈጸሙት የስቅላት ግድያ ድርጊት በጦር ወንጀለኝነት ያስከስሳቸዋል ያለው ተቋሙ፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በጉዳዩ ዙሪያ ተጨማሪ ምርመራ እንዲያደርግና ባለስልጣናቱን ለህግ እንዲያቀርብ ጠይቋል፡፡

 የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ የአገሪቱ ጦር ወረራ ቢፈጸምበት በአስተማማኝ ሁኔታ መመከት የሚችልበት ወቅታዊ ዝግጁነት እንዳለው የሚያረጋግጥ፣ አፋጣኝ ፍተሻ እንዲደረግና አየር ሃይሉ ለጦርነት ብቁ በሆነ መልኩ እንዲዘጋጅ ድንገተኛ ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
የአገሪቱን የመከላከያ ሚኒስትር ሰርጌ ሾይጉን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ፕሬዚዳንት ፑቲን የአገሪቱ የመከላከያ ተቋማትና ወታደሮች ለጦርነት ዝግጁ መሆናቸውን ለመገምገም የሚያስችል ምርመራ እንዲደረግ ባለፈው ማክሰኞ ያዘዙ ሲሆን፣ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናትም ጦሩን ዝግጁ የማድረግ ስራ መጀመሩን አረጋግጠዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህንን ትዕዛዝ ያስተላለፉት ሩስያ ከአንዳንድ የኔቶ አባል አገራትና ከሌሎች የአለማችን ሃያላን አገራት ጋር ያላት ግንኙነት ውጥረቱ እየጨመረ ባለበት ወቅት ነው ያለው ዘገባው፤ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕም በቅርቡ የሩስያን ወታደራዊ ዘመቻዎች መኮነናቸውን አስታውሷል፡፡
ሩስያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወታደራዊ እንቅስቃሴዋንና ዝግጁነቷን እያስፋፋች መምጣቷንና በአዲሱ የፈረንጆች አመት 2017፣ የጦር ታንኮችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግን ጨምሮ ወታደራዊ አቅሟን ይበልጥ ለማጠናከርና ለማስፋፋት አቅዳ እየሰራች እንደምትገኝም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

ወደዚህ ዓለም የመጣችው በኃይል ጥቃት ነው። እናቷን አንድ ሻምበል አስገድዶ ይደፍራታል። በዚያው ጥቃት ተፀነሰች፡፡ እንደማንኛውም ህፃን ከ9 ወር በኋላ በደብረማርቆስ ከተማ ተወለደች። እንደ ወጉ ቢሆን ህፃን ልጅን እናትና አባት ነበሩ የሚያሳድጉት፡፡ እሷ ግን ለዚህ ፀጋ አልታደለችም። አባቷን ስለማታውቅ እናቷ ብቻዋን አሳደገቻት - መንበረ አክሊሉን፡፡
አሜሪካ ሳንፍራንሲስኮ ነዋሪ የሆነችውን ወ/ሮ መንበረን አግኝቼ ይህንን ቃለ ምልልስ ያደረግነው፣ ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ የሊንከን ኮሌጅ ለ6ኛ ዙር ኤምቢኤ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ያስተማራቸውን 45 ተማሪዎች በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ ባስመረቀበት ወቅት የቢዝነስ ተሞክሮዋን፣ ያሳለፈችውን መጥፎ ህይወትና አሁን የደረሰችበትን ስኬት ለተማሪዎቹ እንድትናገር ዩኒቨርሲቲው ጋብዟት መጥታ ነው፡፡
እናቷ ብቸኛ በመሆንዋ የራሷንና የልጇን ህይወት ለመለወጥ ትፍጨረጨር ነበር፡፡ ኑሮዋን ለማሸነፍ ጠጅ ንግድ ጀመረች፡፡ የጠጅ ንግዱ ደራላት፡፡ “የማገኘው ገንዘብ ለልጄና ለራሴ ኑሮ ይበቃናል፡፡ ተመስገን! ይህንኑ ይባርክልኝ” ብላ አልተቀመጠችም፡፡ እንዲያውም ኮማሪትነትን አጧጧፈችው፡፡
ጥረቷ ሰመረላትና ጠጅ ቤቱን ወደ ሆቴልነት ለወጠችው፡፡ ሆቴሉን ከፍታ ያለ ዕረፍት ስትሰራ ገበያው ደራላት፡፡ ደንበኞቿን ለማስደሰት ሌት ተቀን ስትጥር አንድ ቀን ያልታሰበ ነገር ተፈጠረ፡፡ በመጠጥ ቤቱ ሲጠጣ የቆየ አንድ ሻምበል ሰክሮ፤ “ሂሳብ አልከፍልም” በማለት አምባጓሮ ፈጠረ። በዚህ ጊዜ “የተጠቀምከውን ሂሳብማ ልትከፍለኝ ይገባል” በማለት ፖሊስ ስትጠራ፣ የታጠቀውን ሽጉጥ አውጥቶ ተኩሶ ገደላት፡፡
መንበረ በዚያን ወቅት የ10 ዓመት ልጅ ስትሆን፤ በንጉሥ ተክለሃይማኖት ት/ቤት የ6ኛ ክፍል ተማሪ ነበረች፡፡ እናቷ ስትገደል አይታለች፡፡ አሁን ወላጅ አልባ ሆነች፡፡ በዚህ ጊዜ አዲስ አበባ የነበሩት ታላቅ ወንድሟና ታላቅ እህቷ እናሳድጋታለን ብለው አመጧት፡፡ ዳግማዊ ምኒልክ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ገብታ ትምህርቷን እስከ 12ኛ ክፍል ተማረች፡፡
ታላቅ ወንድሟ “ዩኒቨርሲቲ ገብተሽ ትምህርትሽን ቀጥይ” ብሏት ነበር፡፡ እሷ ግን “ተዋናይ መሆን ነው የምፈልገው” ብላ አሻፈረኝ አለች፡፡ እንደፈለገችው የትወና ትምህርቱን ተከታትላ ተዋናይ ሆነችና ብሔራዊ ቴአትርና ራስ ቴአትር ተቀጥራ ሰራች፡፡
በዚህ ወቅት አለቃዋና የልጇ አባት ከሆነው ሰው ጋር ተዋውቃና ተግባብተው ፍቅር ጀመሩ፡፡ ፍቅረኛዋ ስኮላርሺፕ አግኝቶ ጣሊያን ከሄደ በኋላ፣ “ታዋቂ ተዋናይ መሆን ትችያለሽና እዚህ ነይ” ብሎ የግብዣ ወረቀት ላከላት፡፡ እሺ! ብላው ጣሊያን ሄደች፡፡ ቤተሰቦቿ (እህትና ወንድሟ) ወደ ጣሊያ መሄዷን አልወደዱም ነበር፡፡ ምክንያቱም እዚህም እያሉ ፍቅረኛዋ ጥሩ ሰው እንዳልሆነ ያውቃሉ፡፡ ይጎዳትና ይደበድባት ነበር፡፡ እንዲያውም አንድ ጊዜ አፍንጫዋን ሰብሯት ሆስፒታል ሁሉ ገብታ ነበር። በዚህ የተነሳ ተከትላው እንድትሄድ ስላልፈለጉ “ይቅርብሽ” ብለዋት ነበር፡፡
መንበረ ግን የወንድምና የእህቷን ምክር አልተቀበለችም፡፡ ወጣትነት፣ ፍቅርና ከሀገር የመውጣት ፍላጎቱ ተደማምረው ተከትላው ኢጣሊያ ሄደች፡፡ ሮም ከተማ አብረው መኖር ጀመሩ፡፡ የፍቅረኛዋ ባህርይ ግን አልተለወጠም፤ እንዲያውም ባሰበት፡፡ ሮም በደረሰች ሦስተኛ ወሯ ፀነሰች፡፡ ፍቅረኛዋ ይደበድባትና ይጎዳት ነበር፡፡ መጨረሻ ላይ ፊቷንና ክንዷን በሲጋራ አቃጠላት፡፡ ዘጠኝ ወር ሲሞላትም ጉዳትና ድብደባው አልቀረላትም፡፡ እንዲያውም ሊገድላት ይፈልግ ጀመር፡፡ በዚህ ጊዜ ግፉ ስለበዛባት ከቤት ወጥታ ጠፋች፡፡
ለመውለድ 6 ቀን ነበር የቀራት፡፡ ገንዘብ የላት፣ ቋንቋ አታውቅ፣ የምትጠጋው ዘመድ የላት፤ … ወጥታ ቤተ ክርስቲያን በረንዳ ላይ ተቀመጠች። ቀኑ እየመሸ ሲሄድ መጠጊያ ስለሌላት እዚያው በረንዳ ላይ ለማደር ወሰነች፡፡ በዚህ ጊዜ አማርኛ የሚናገሩ አንድ ኢጣሊያዊ ቄስ፤ አይተዋት ጠጋ ብለው ምን እንደሆነች ጠየቋት፡፡ እሷም ታሪኳን ዘርዝራ አጫወተቻቸው፡፡ ቄሱም፤ “ልትወልጂ ድርስ ስለሆንሽ መንገድ ላይ ማደር የለብሽም፤ እኔ ቦታ አገኝልሻለሁ” ብለው ወደ ማዘር ቴሬሳ የሴቶች መጠለያ ወሰዷት፡፡
መጠለያው ውስጥ በአልኮል፤ በአደንዛዥ ዕፅ፣ በሴተኛ አዳሪነት፣ … ወንጀል የተከሰሱ ሴቶች ነበሩ፡፡ ራሷን ከእነሱ ጋር አመሳስላ ቆየች፡፡ እዚያ በገባች በ6ኛ ቀኗ ልጇን ወለደች፡፡ ከ3 ወር በኋላ የቤት ውስጥ ሰራተኛነት ስራ አግኝታ ወጣች፡፡ ሳህን እያጠበች፣ ቤት እያፀዳች፣ ምግብ እየሰራች፣ ልብስ አጥባ እየተኮሰች፣ … አጠቃላይ የቤት ውስጥ ስራ እየሰራች ልጇን አሳደገች፡፡ ስራውን ወድዳና አክብራ፣ ልጇ 11 ዓመት እስኪሞላው ድረስ እዚያው ቤት ሰራች፡፡ በዚህ ጊዜ አንድ መጥፎ አጋጣሚ ተፈጠረ - አሰሪዋ ሞቱ፡፡
እሷም “እስከ መቼ ድረስ ነው በቤት ሰራተኝነት የምቀጥለው? ይኼ ስራማ የህይወቴ መጨረሻ መሆን የለበትም፤ ልጄ ነፍስ ካወቀልኝ ህይወቴን የመለወጥ ትልቅ ህልም አለኝ፡፡” በማለት አሰበች። ምን እንደምትሆን፣ ምን እንደሚያጋጥማት አታውቅም፡፡ ሆኖም “በምንም ዓይነት መንገድ እንደዚህ ሆኜ መቅረት የለብኝም፡፡ ጠንክሬ በሥነ - ሥርዓት ከሰራሁ፤ እለወጣለሁ” የሚል እምነትና ጥንካሬ በውስጧ ስለነበር፣ ሁለተኛ የስደት ህይወት ለመጀመር ልጇን ይዛ አሜሪካ ገባች፡፡
አሜሪካ ሳንፍራንሲስኮ ካሊፎርኒያ ውስጥ ሪችሞንድ በተባለች ከተማ አረፈች፡፡ እዚያም ሳሉቴ ኢቪታ (በጣሊያኒኛ ጤና ማለት ነው) በተባለ ሬስቶራንት ውስጥ በሰዓት ሰባት ዶላር እየተከፈላት፣ እንግዳ ሲመጣ ተቀብሎ ማስቀመጥ ሥራ አገኘች። በዚያን ጊዜ ለእሷ 7 ዶላር ትልቅ ገንዘብ ነበር። ሥራዋ፤ በፈገግታ እንግዶችን ተቀብሎ ወንበር ሰጥቶ ማስቀመጥ ቢሆንም፣ ስራው እንዳያመልጣት በማለት የማትሰራው ነገር አልነበረም፡፡ ግድግዳ ታጥባለች፣ መስኮት ትወለውላለች፣ ወለል ታፀዳለች። የሥራ ባልደረቦቿ “ይኼ ያንቺ ስራ አይደለም፡፡ ያንቺ ስራ ጥሩ ለብሶ፣ በር ላይ ቆሞ በፈገግታ ሰዎችን መቀበልና ማስቀመጥ ብቻ ነው” በማለት ይመክሯት ነበር፡፡ እሷ ግን ምክራቸውን አልተቀበለችውም፡፡ ኢጣሊያ እያለች ከንጋቱ 11 ሰዓት እስከ እኩለ ሌሊት ያለ ዕረፍት ትሰራ ስለነበር፣ አልከበዳትም፤ እንዲያውም አጠነከራት እንጂ፡፡ ደሞዟም 8፣ 9፣ 10፣ … ዶላር እያለ አድጎ የማታ ማታ የሬስቶራንቱ ሥራ አስኪያጅ ሆነች፡፡
በዚህ ዓይነት ለ6 ዓመት እንደሰራች ባለቤቱ ሳሉቴን መሸጥ ፈለገና ለሰራተኞቹ ማስጠንቀቂያ ሰጠ፡፡ በውሃ ላይ የተሰራ፣ ሳንፍራንሲስኮን ዙሪያዋን ማሳየት የሚችል በከተማዋ (ሪች ሞንድ) ትልቅ ሬስቶራንት ነበር ሳሉቴ፡፡ በሬስቶራንቱ ውስጥ መንበረ ተወዳጅ፡፡ ተወዳጅነትን ያገኘችው የኢጣሊያ ቋንቋ አቀላጥፋ ስለምትናገር፣ ጠንካራ ሰራተኛ ስለሆነች፣ የተዋናይነት ስሜትና ተግባቢነት በውስጧ ስላለ ነው፡፡ የእሷን ጥንካሬና ቅልጥፍና ለማየት የሚመጡ ደንበኞች “መንቢን ልናጣ ነው፣ ምን ይሻላል?” ይሉ እንደነበር ተናግራለች፡፡
ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ፣ ያላሰበችውና ያልጠበቀችው ነገር ተፈጠረ፡፡ “ስራ ፈልጉ” የሚል ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው፣ አንድ በስራዋና በቅልጥፍናዋ እንዲሁም በቋንቋዋ ይማረክ የነበረ ኢጣሊያናዊ ደንበኛቸው፣ “መንቢ፣ ምንድነው እቅድሽ?” ሲል ጠየቃት፡፡ እሷም፤ “ምንም! እቅድ የለኝም፡፡ ስራ እፈልጋለሁ፣ ወይም ሬስቶራንቱን የሚዙ ሰዎች ከቀጠሩኝ እዚሁ እሰራለሁ” አለች። ያ ኢጣሊያናዊ በማግሥቱ ከልጁና ከሚስቱ ጋር መጥቶ፣ “መንቢ፣ እኔም እንዳንቺ ከጣሊያ አገር በ13 ዓመቴ ወጥቼ ነው እዚህ ሀብታም የሆንኩት። ዓለም ለእኔ ጥሩ ስለሆነች ያገኘሁትን ሁሉ መልሼ ለሌሎች ሰዎች መስጠት አለብኝ” አላት፡፡ “እናስ?” በማለት ጠየቀችው፡፡ “እናማ፤ የትም አትሄጂም። ገንዘብ አበድርሻለሁ፡፡ ይህንን ሬስቶራንት ትገዣለሽ” አላት። መንበረም፣ “እኔ አልችልም። በምን እውቀቴ ነው የማስተዳድረው?” አለች፡፡ “ምንም እውቀት አያስፈልግሽም፡፡ ጠንካራ ሰራተኛ ነሽ፡፡ ለሬስቶራንቱ 24 ሰዓት ትሰሪ ነበር። ወደፊትም 24 ሰዓት መሥራት ነው፤ ለውጥ የለውም” በማለት ብትከስርም ምንም እንደማያገኝ እያወቀ     “በአምስት ዓመት ትከፍይኛለሽ፤ ካልቻልሽም ሌላ እጨምርልሻለሁ” በማለት አስፈርሞ ግማሽ ሚሊዮን ዶላር አበደራት።
መንበረ፣ ከልጅነቷ ጀምሮ ጠንካራ ሰራተኛ ስለሆነች፣ ብዙ ችግር ያሳለፈች፣ መኖሪያ አጥታ መጠለያ ውስጥ የኖረች ስለነበር … እኒህ ሁሉ መከራዎች ድፍረትና ጥንካሬ ሰጧት፡፡ ሌት ተቀን ጠንክራ በመስራት የአምስት ዓመቱን ብድር በአንድ ዓመት ከፍላ ጨረሰች፡፡ ይህን ዕዳ ለመክፈል ያየችው ፍዳ አይጣል ነው፡፡ ሌሊት መነሳት፣ ከወዲያ ወዲህ ሲወዛወዙ መዋል እጅግ ከባድ ነበር፡፡ ከመድከሟና ከመዛሏ የተነሳ መኪና መንዳት አቅቷት፣ ሦስትና አራት ቀን ሬስቶራንቱ ውስጥ ለማደር እንደተገደደች ትገልጻለች፡፡ “ዛሬ እኔም ሬስቶራንቱም ታዋቂ ሆነናል” ትላለች፤ መንበረ። በሳሉንቴ ሬስቶራንት 6 ዓመት በአስተናጋጅነት፣ 16 ዓመት በባለቤትነት በአጠቃላይ ለ22 ዓመታት መስራቷን፣ ሬስቶራንቱ 18 ሰራተኞች እንዳሉት ተናግራለች፡፡ መንበረ “እግዚአብሔር ለእኔ እንዲህ ደግ ከሆነ፣ እኔስ ምንድነው ማድረግ ያለብኝ” በማለት አሰበች፡፡ እዳዋን ከፍላ ከጨረሰች ከአንድ ዓመት በኋላ፤ “እኔም ከእነሱ አንዷ ነበርኩ” በማለት ጎዳና ተዳዳሪዎችን አሰበች፡፡ በዓመት አንድ ቀን “የድሆች ቀን” በማለት፣ 1,500 ለሚሆኑ የጎዳና ተዳዳሪዎች እራት ታበላለች፡፡ በሥነ ስርዓት ተቀብለው፣ ሁለትና ሶስት ሹካ አስቀምጠው፣ ክሪስታል ብርጭቆ አኑረው፣ እንደማንኛውም 100ና 200 ዶላር እንደሚከፍል እንግዳ ተስተናግደው ይሄዳሉ፡፡ ሐኪሞችን በማስተባበር ኢንፍሉዌንዛ እንዳይዛቸው ክትባት እንዲያገኙ፤ የደም ግፊት ካለባቸው እንዲለኩና ምክር እንዲሰጣቸው ይደረጋል፡፡ በራባቸው ጊዜ ደግሞ ወደ ሬስቶራንቱ መጥተው ምግብ እንዲወስዱ ነግረው ያሰናብቷቸዋል፡፡
ይህ በየዓመቱ የሚደረግ ግብዣ መንበረን በአሜሪካ እንድትታወቅ አደረጋትና “ሆሊ ኔምስ” የተባለ ዩኒቨርሲቲ፣ “ስደተኛ ሆና ይህን የመሰለ የተቀደሰ ተግባር በመፈጸሟ ልትሸለም ይገባል” በማለት የክብር ዶክትሬት ዲግሪ እንደሰጣት ገልጻለች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እሷን እያዩ ፈረንጆችም መተባበር ስለጀመሩ፣ በከተማዋ አስተዳደር የሚመራ ፋውንዴሽን ከፍታለች፡፡ ይህ ደግሞ ለሌላ ተግባር አነሳሳት፡፡
አሜሪካ ውስጥ “ማዘርስ ዴይ” ይከበራል። በዚህ ዕለት ባል ያላቸው ዕድለኛ እናቶች የሽቶ፣ የአበባ … ስጦታ ይበረከትላቸዋል፡፡ ጥሩ እራትም ይጋበዛሉ። መንበረ፤ በእናቶች ዕለት “በመጠለያ ውስጥ የሚኖሩ ድሃ እናቶችን እናስብ” በማለት በመጠለያ ውስጥ የሚኖሩትን እናቶች በሙሉ አሰባስባ እራት ታበላለች። ድሃ እናቶች ወደ ግብዣው ስፍራ ከመምጣታቸው በፊት ልጆቻቸውን የሚጠብቅላቸው ሰው ይመደብላቸዋል፣ ፀጉራቸውን እንዲሰሩ ይደረጋል፡፡ የአዕምሮ ሐኪሞችን አስተባብራ እንዲመረምሯቸው፣ እንዲመክሯቸውና እንዲያበረታቷቸው ታደርጋለች፡፡
የልጃገረዶች ፕሮጀክትም አላት፡፡ ጥሩ ውጤት ኖሯቸው ትምህርት ቤት መሄድ ለማይችሉ 8 ልጃገረዶች በየወሩ እየከፈለች በግል ት/ቤት እያስተማረች ነው፡፡ ይህ የልጃገረዶች ፕሮጀክት ወደ ኢትዮጵያም ዘልቋል፡፡ በደብረ ማርቆስ ከተማ ውስጥ የእናቷ ቤት በነበረበት ቦታ፣ ባለ 3 ፎቅ ህንፃ በ300 ሺህ ዶላር አሠርታ፣ 80 ልጃገረዶችን ለማስተማር ዝግጅት መጀመሯን ገልጻለች፤ ወ/ሮ መንበረ አክሊሉ፡፡
ያ በኢጣሊያ ማዘር ቴሬሳ መጠለያ ውስጥ የተወለደው የመንበረ ልጅ፤ በሚቀጥለው ዓመት ከኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ በዶክትሬት ዲግሪ ይመረቃል።     
ወ/ሮ መንበረ በዳንግላ ከተማ ጋሹና ሆቴል ውስጥ ሼፍ ሆና ስትሰራ፣ የቀድሞ ፍቅረኛዋ ፊቷ ላይ አሲድ ደፍቶባት ጉዳት ለደረሰባት መሰረት ንጉሤ 5 ሺህ ዶላር መላኳን፣ ሐኪሞች፣ የመሠረትን ጉዳት አይተው መታከምና መዳን እንደምትችል ስለገለጹላት አሜሪካ ወስዳ ለማሳከም ዝግጅት እያደረገች መሆኑን ተናግራለች፡፡   

6 ቢሊዮን ዶላር ያህል በሪልእስቴት ዘርፍ ኢንቨስት ተደርጓል ተብሏል

  አዲስ አበባ በሪልእስቴት ዘርፍ ኢንቨስትመንት ከአፍሪካ ከተሞች በ3ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝና የከተማዋ የሪልእስቴት ልማት ዘርፍ ኢንቨስትመንት፣ 6 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ የዓለም ባንክ ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የአፍሪካ ዋና ዋና ከተሞች ወቅታዊ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት አስታውቋል፡፡
የታንዛንያዋ ዳሬ ሰላም በሪልእስቴት ልማት ዘርፍ ከአፍሪካ ከተሞች በአንደኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የከተማዋ የሪልእስቴት ኢንቨስትመንት 12 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ የገለጸ ሲሆን፣ የ9 ቢሊዮን ዶላር የሪልእስቴት ኢንቨስትመንት ባለቤት የሆነቺው የኬንያ ርዕሰ መዲና ናይሮቢ፣ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝም አስረድቷል፡፡
በአፍሪካ ከተሞች የሪልእስቴት ዘርፍ ልማት እየተስፋፋ ቢመጣም፣ የከተማ ነዋሪዎች ከነፍስ ወከፍ ገቢያቸው ጋር ሲነጻጸር የመኖሪያ ቤት ፍላጎታቸውን ለማሟላት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚያወጡም የጠቆመው ሪፖርቱ፤ በአንዳንድ የአህጉሪቱ ከተሞች የመሬት ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመሄድ በአሜሪካ በሚሸጥበት ዋጋ መሸጥ መጀመሩንም አክሎ ገልጧል፡፡
የአህጉሪቱ የከተማ ነዋሪዎች ቁጥር እስከ 2050 ድረስ በ170 ሚሊዮን እንደሚጨምር እንዲሁም አሁን ያለው የከተማ ነዋሪ ህዝብ ቁጥር በ25 አመታት ጊዜ ውስጥ በእጥፍ በማደግ 1 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ይህም በመሆኑ የአህጉሪቱ ከተሞች የመኖሪያ ቤት ግንባታን ጨምሮ ከህዝብ ቁጥር እድገቱ ጋር የሚመጣጠን ሰፊ የመሰረተ ልማት አውታሮች ግንባታ ማካሄድ እንደሚጠበቅባቸው አስረድቷል፡፡
የአፍሪካ ከተሞች እጅግ ውድ ከሆኑ የአለማችን ከተሞች ተርታ እንደሚመደቡ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ከሌሎች ተመሳሳይ ገቢ ያላቸው የአለማችን አገራት ከተሞች ጋር ሲነጻጸር በ30 በመቶ ያህል የበለጠ ውድ መሆናቸውንና ይህም ከተሞቹ አለማቀፍ ኢንቬስተሮችን እንዳይስቡ እክል እንደፈጠረባቸው ገልጧል፡፡

“ፐርሰንት ከደመወዝ ተቀንሶ አይከፈልም፤ አሠራሩም ሕጋዊ አይደለም” /ክፍለ ከተማው/
    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ “የደብረ ተኣምራት ዳግማዊት ጻድቃኔ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ሠራተኞች፤ ለተፈቀደላቸው የደመወዝ ጭማሪ ማጽደቂያ፣ ለሀገረ ስብከቱ ሓላፊዎች የተሰጠው ብር 50 ሺሕ ጉቦ እንዲመለስ ታዘዘ፤” በሚል ርእስ፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ያወጣው ዘገባ፣ “ያልተጣራና መሠረተ ቢስ ነው” ሲሉ ሀገረ ስብከቱና የደብሩ ጽ/ቤት አስተባበሉ፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ ካላት ከማንኛውም ገቢ ላይ ሃያ በመቶውን የሀገረ ስብከቱን ድርሻ እንድትከፍል በቃለ ዐዋዲው መደንገጉን በማስተባበያቸው አስታውሰው፤ በዘገባው የተጠቀሰውና ከደብሩ ጽ/ቤት ወጣ የተባለው 50ሺ ብርም፣ በወቅቱ ያልተከፈለ የደብሩ የሃያ ፐርሰንት ውዝፍ ሒሳብ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ይህም፣ ሀገረ ስብከቱን ወክሎ በሚሠራው በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ስም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተከፈተው ተንቀሳቃሽ ሒሳብ ገቢ መደረጉን በመጥቀስ ደረሰኙን በአስረጅነት አቅርቧል፡፡ “ወደ ተቋሙ ባንክ የገባውን ገንዘብ ለግለሰቦች እንደተሰጠ አስመስሎ መዘገቡ ሚዛናዊነት የጎደለው ነው፤” ሲልም ዘገባውን ተቃውሟል፡፡ የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ መጋቤ ሠናያት የቻለው ለማ በበኩላቸው፤ “የደብሩ የሃያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ መከፈል ያለበት ከደብሩ ገቢ እንጂ ከሠራተኞች ደመወዝ ተቀንሶ መሆን የለበትም፤ የሁለት ወሩ የደመወዝ ጭማሪም የተቀነሰው፣ የጽ/ቤቱ ሓላፊዎች በራሳቸው ወስነው እንጂ፣ የሚመለከተው ሰበካ ጉባኤ በተገኘበት እንዳልሆነ ጽ/ቤታቸው ባደረገው የሰነድና የገጽ ለገጽ ማጣራት ማረጋገጡን ገልጸዋል፡፡ ገቢ ተደርጓል ስለተባለው 50ሺ ብር የተጠየቁት ሥራ አስኪያጁ፣ “የክፍለ ከተማው ጥያቄ የ50ሺሕ ብር አከፋፈል ሒደት አይደለም፤ ከግለሰቦች ላይ የተቀነሰው የገንዘብ አከፋፈል ሒደትና አሠራር ትክክል አይደለም፤ ፍትሐዊ አይደለም፤ ነው፤” በማለት ከደመወዝ ጭማሪው ጋር ግንኙነት እንደሌለው አስረድተዋል፡፡


ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

“እና - እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…” (“እሳት ወይ አበባ”)

“እና - እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…”    (“እሳት ወይ አበባ”)

መግቢያ
ታኅሣሥ 29 ቀን፣ 2009 ዓ.ም. በዓለ ገና፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ዕድገትና ደረጃን በሚመለከት በጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን ትምህርት ቤት በሚያስተምር ግለሰብ ዋና የመረጃ ሰጪነት፣ ዘጋቢ ፕሮግራም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ተላልፎ ነበር፤ የፕሮግራሙ አቀራረብም፣ የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬን ማዕከል ያደረገ ነበር፡፡ እንዲኽ ዓይነት ይዘት ያለውን የዶክመንተሪ አቀራረብ፣ አሜሪካኖች* “Charm offensive” ይሉታል፡፡
ይህን ሲሉ፣ ኾን ተብሎና ታቅዶ፣ የራስን የማንነት ውበትና በጎነት አጉልቶ በማውጣት የሚቀርብ ድርጊትን መግለጻቸው ነው፡፡ ይህንኑ የራስ መልክአ ውዳሴ ወደ አማርኛ ስንተረጉመው፣ “አጀብ እዩልኝ” ተብሎ ሊገለጽ ይችላል፡፡ ዶክመንተሪው በዋናነት፣ የዩኒቨርሲቲውን ጉዳይ ያነሣ ቢመስልም፣ ዐቢይ ትኩረቱ ግን፣ ፕሬዝዳንቱን እንዲኹም የሥራ አፈጻጸማቸውን አጉልቶ ለማውጣት ያለመ ነው፡፡ ኾኖም፣ እውነታው* በመልክአ ውዳሴው ከቀረበው የዩኒቨርሲቲው ኹኔታ እንዲኹም፣ ከፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ ገጸ ሰብእና ጋር ሲነጻጸር ፈጽሞ የተራራቀ ነው፡፡    
ይህን ጽሑፍ እንዳዘጋጅ የወዲያው ሰበብ የኾነኝ፣ ይህንኑ የእውነታ መራራቅና መጣረስ ለማሳየት በማሰብ ነው፡፡ ኹለተኛውና ዋነኛው የጽሑፌ መንሥኤ ግን፤ በፕሬዝዳንት አድማሱ እና በቦርዱ ሊቀ መንበር አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን ይኹንታ ሰጪነት፣ በዩኒቨርሲቲው ቅጽር የተካሔደው የዛፍ ምንጠራ ድርጊትና የሕንፃ ግንባታ አስከትሎት ጉዳይ ነው፡፡
ይህ መጣጥፍ፣ የኹለት ክፍሎችን ቅንብር የያዘ ነው፡፡ አንደኛው* የዩኒቨርሲቲውን ዛፍ ምንጠራ እና የዕውቅ ሥነ ውበታዊ መገለጫውን መገፈፍ በየአንጻሩ ማሳየት ሲኾን፤ ኹለተኛው ደግሞ፣ ዛፍ ምንጠራው፣ የዩኒቨርሲቲውን መካነ አእምሯዊ ተልእኮ ለማሳካት ሳይኾን፣ የፕሬዝዳንቱንና ፈቃድ የሰጡትን ሹመኞች ፍላጎትና ጥቅም ታሳቢ ያደረገ ፕሮጀክት መኾኑን በጥቂቱ ማሳየት ነው፡፡
ኢንዱስትሪ እና ዩኒቨርስቲ
የማኅበራዊ ሳይንስ ተመራማሪውና በኢትዮጵያ ጉዳዮች በርካታ ጥናቶችን ያሳተሙት ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን፣ ከኅልፈታቸው ጥቂት ዓመታት ቀደም ብለው* “Powers of the Mind: The Renovation of Liberal Learning in America” በሚል ርእስ፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ፍልስፍና መጽሐፍ አሳትመው ነበር፡፡ ፕሮፌሰር ሌቪን፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ምንነት በርካታ ጥልቅ ሐሳቦችን የገለጹ ቢኾንም፤ ከዚኽ መጣጥፍ ዋና ይዘትና መንፈስ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለውን አንዱን አገላለጻቸውን ብቻ ወስደናል፡፡
ፕሮፌሰር ሌቪን፣ “ዩኒቨርሲቲ፣ በኢንዱስትሪ የውጤታማነት መለኪያ መስፈርት ሊመዘን አይገባም፤” ይላሉ፡፡ እንደ እርሳቸው አገላለጽ፣ ዩኒቨርሲቲ በኢንዱስትሪ መለኪያ የማይመዘንበት ምክንያት* በይዘት፣ በዓላማም ኾነ በውጤት ከኢንዱስትሪ የተለየ በመኾኑ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ዩኒቨርሲቲ እንደ ኢንዱስትሪ ገበያ የሚፈልገውን ብቻ ፈብርኮ የሚያቀርብ ሳይኾን፣ ተማሪዎች፣ ለጥናትና ምርምር የተኮተኮተ አእምሯዊ ማሕቀፍ እንዲኖራቸው ለማስቻል የተደበረ የዕውቀት ኀሠሣ ማዕከል በመኾኑ ነው፡፡
ይህን መሠረታዊ የዩኒቨርሲቲ እና የኢንዱስትሪ ባሕርያዊ ልዩነት በውል ባለመገንዘብ፤ የወቅቱ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፤ መድረክ ባገኙባቸው አጋጣሚዎችና ከላይ በጠቀስነው “የአጀብ እዩልኝ” ዶክመንተሪያቸው ሳይቀር፤ ስለሚመሩት ዩኒቨርሲቲ ሲገልጹ፣ ደጋግመው የሚጠቀሙባቸው ዕዝሎችና ቅጽሎች፡- ‹አደረጃጀት›፣ ‹ሽፋን›፣ ‹ቅበላ›፣ ‹ቁጥር›፣ ‹ግንባታ›፣ ‹የኃይል ትስስር›፣ ‹ፕሮጀክት›፣ ‹አንድ ለአምስት› … ወዘተ. ናቸው፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት ቅጽሎችና ሐረጎች፤ የኢንዱስትሪ የምርታማነትና የውጤት ደረጃ አመልካች መለኪያዎች፤ የአንድ ፋብሪካ የምርት ቁጥጥር ሓላፊ ወይም የሕንፃ ግንባታ ተቆጣጣሪ “ካቦ”፣ በሚያቀርበው ሪፖርት የሚጠቀማቸው ቃላት እንጂ፣ “ⷈሉ አመክሩ ወዘሠናየ አጽንዑ”(ኹሉን መርምሩ መልካሙንም አጽንታችኹ ያዙ) የሚለውን ታላቅ ኃይለ ቃል ይዞ የተነሣን፣ የማእምራን መዲና የኾነ ዩኒቨርሲቲን መንፈስ የሚወክል ወይም የሚመጥን አይደለም፡፡
“አድማሱ ዛፍ የመነጠረበት ዘመን”
የዚኽን ንኡስ ርእስ ሐሳብ የወሰድኹት፣ በጎጃም ጠቅላይ ግዛት ታዋቂ ከኾነና በስፋት ከሚነገር ታሪክ ወስዶ፣ አንድ ወዳጄ በአንድ ወቅት ያጫወተኝን ትረካ መሠረት አድርጌ ነው፡፡ ትረካው በአጭሩ ሲቀርብ እንደሚከተለው ነው፡፡
ልዑል ራስ ኃይሉ እና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ፣ በራስ ካሳ ሥር ታስረው በነበሩት በልጅ ኢያሱ ከእስር ቤት ማምለጥ፤ ራስ ኃይሉ፣ “ተሻርከው አስመልጠዋል” በሚል ምክንያት የከረረ ጠብ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ልዑል ራስ ኃይሉም ከጎጃም አገረ ገዥነት ተሽረው በእስርና በግዞት ይሰደዳሉ፡፡ በምትካቸውም፣ ከንቲባ ማተቤ ደረሶ ደብረ ማርቆስን ተሾሙ፡፡ ይህን የሥልጣን ሽግግር አገሬው ስላልወደደው፣ የራስ ኃይሉን ልጅ ፊታውራሪ አድማሱ ኃይሉን ይዞ ተቃውሞ ቀሰቀሰ። በጊዜውም በደብረ ማርቆስ ቤተ መንግሥት ግምጃ ቤት ውስጥ በግብር የተሰበሰበና የራስ ኃይሉም የግል ንብረት የነበረ ሀብት፤ “የሸዋ ሹመኞች መጥተው ሊወስዱት ነው፤” ተብሎ ስለተወራ፤ እነፊታውራሪ አድማሱ፤ “ይህ ንብረት ሸዋ ከሚሻገር ጎጃሜ ይውሰደው!” በማለት፤ ግምጃ ቤቱን ከፍተው በሕዝብ አስመዘበሩት፡፡ ይህም ድርጊት እስከ ዛሬ በጎጃም፣ “አድማሱ ያፈረሰው ጊዜ” ተብሎ ሲወሳ ይኖራል፡፡
ወደ ጥንተ ነገራችን ስንመለስ፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፣ “ለዩኒቨርሲቲው ማስፋፊያ ሕንፃ መገንባት አስፈላጊ ነው፤” በሚል መነሻ፣ የቅጽረ ግቢው ግርማ ሞገስ ኾኖ በዓለም የሚታወቀውን ዐጸድ በማስመንጠር፣ የማይበጅ አፍራሽ ተግባር ፈጽመዋል፡፡
የኹለቱም “አድማሱ”ዎች ድርጊት፣ በጥቅሉ “የአፍራሽ” ቅጽል ተሰጥቶት ቢገለጽም፤ የመጀመሪያው አድማሱ የተነሡበት መንፈስ፣ ለጎጃም ሕዝብ ወገንተኝነት የቆመ ሲኾን፤ ይህም ድርጊታቸው በጊዜው በሕግ ቢያስጠይቃቸውም፣ ከሞራል አንጻር ሲታይ ግን የሚያስኰንናቸው ጉዳይ አይደለም፡፡ የኹለተኛው አድማሱ አፍራሽነት ግን፤ በሕግም ኾነ በሞራል መስፈርት ያስጠይቃቸዋል፡፡ ይኸውም፣ ከዩኒቨርሲቲው ቅጽር ሥነ ውበት አንጻር የሚያስጠይቅ ስሕተት ተፈጽሟል፤ የሚል እምነት ስላለኝ ነው፡፡
የመጀመሪያው አድማሱ አፍራሽነት፣ ስሕተት ከተባለ መግፍኤው፣ ለሕዝብ ከመቆም ሲኾን፤ የኹለተኛው አድማሱ የአፍራሽነት ድርጊት ግላዊና መለካዊ (ሥልጣን ሰገድ) ከመኾን የመነጨ ነው፤ ማለት እንችላለን። በመኾኑም፣ የቀዳሚው አድማሱ ድርጊት፣ አንድ ማኅበረሰባዊ ተረክ ኾኖ እንደቆየን ኹሉ፣ የዩኒቨርስቲው አድማሱ የደን ምንጣሮ አፍራሽነትም ለትውልድ ሲነገር ይኖራል፡፡
የደን ምንጣሮው፡- ከሥነ ሕይወት፣ ከሥነ ውበት እና ከፎክሎር አተያዮች አንጻር፤
ሀ/ሥነ ሕይወት
የዛፍን ምንነትና ኹለንተናዊ ጥቅም አስመልክተው፣ ወ/ሮ ዕሌኒ መኩሪያ የተባሉ ዕውቅ ጋዜጠኛ፤ “ዛፎች ለሕይወት” በሚል ርእስ በ2005 ዓ.ም. መጽሐፍ አዘጋጅተው ነበር፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ስለ ዛፍ እና ሥነ ሕይወት* ማብራሪያዎች፣ ፎቶግራፎች፣ ግጥሞችና መጣጥፎች ተካተውበታል፡፡ የእኒኽ ዓይነት መጻሕፍት ዓላማ፤ ዛፍ እንዳይመነጠርና ለዛፍ ክብካቤ እንዲደረግ አበክሮ ማሳሰብ በመኾኑ፤ ስለ ሥነ ሕይወት እና ሥነ ምኅዳር ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ኾኖ አግኝቼዋለኹ። ይህን በመሰለ ጥረት፣ ለማኅበረሰቡ የዛፍን ጥቅም በወል ለማስጨበጥና ለማስተማር በሚሞከርበት ጊዜ፤ ዩኒቨርሲቲው፣ ሲኾን፣ ከነወ/ሮ ዕሌኒ መኩሪያ ጋር በአስተማሪነት ይሰለፋል ብለን ስናስብ፤ በተቃራኒው የዛፍ ጭፍጨፋ ተግባር ላይ ተሰልፎ መገኘቱ ብዙዎችን አሳዝኗል፡፡
የወቅቱ የዩኒቨርሲቲው አመራር እና አስተዳደር፣ ዩኒቨርሲቲው ለመጪው ትውልድ የሚያገለግል ዐጸድ መትከልና አኹን ያሉትንም መከባከብ ሲገባው፤ ራሱ ያልተከለውንና ከዘመናት በፊት የነበረውን ደን መመንጠሩ፣ ዩኒቨርሲቲው፣ ስለ አካባቢ ጥበቃ አስፈላጊነት ለማኅበረሰቡ ለማስተማር የነበረውን የዕውቀትና የሞራል ልዕልና እንዲያጣ ምክንያት ኾኗል፡፡
እንዲኽ ያለው ብዝኃ ሕይወትን የመጠበቅና የመከባከብ ሓላፊነት፤ እንደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያለው ተቋም ይቅርና በዜግነት ደረጃ እንኳን ግለሰብ ሊፈጽመው እንደሚገባ፤ በአንድ ወቅት ደጃዝማች ዘውዴ ገብረ ሥላሴ፣ የደን ምንጠራን በመቃወም ካሳዩት አርኣያነት የምንረዳው ነው፡፡
ከጥቂት ዐሥርት ዓመታት በፊት፣ በፈረንሳይ ለጋሲዮንና በቤላ መካከል በሚገኝ በአንድ በደን በተሸፈነ ይዞታ ላይ ምንጣሮ ሊካሔድ አስተዳደራዊ ውሳኔ ተላልፎ ነበር፡፡ በተጠቀሰው አካባቢ ያለው ደን፣ ከአዲስ አበባ ምሥረታ ኹለትና ሦስት ምእተ ዓመታት ቀድሞ የነበረና ሀገር በቀል ዕፀዋትን የያዘ ነው፡፡ ደጃዝማች ዘውዴ፣ በእነዚኽ ዕፀዋት ላይ የተላለፈው የምንጣሮ ውሳኔ እጅግ የተሳሳተ መኾኑን ለመግለጽ፣ የአካባቢውን ማኅበረሰብ አስተባብረው ተቃውሟቸውን በማቅረብ  ምንጣሮውን ማስቀረት መቻላቸው ይነገርላቸዋል፡፡    
ከደጃዝማቹ አርኣያነት ያለው ዜግነታዊ ተግባርና እነወ/ሮ ዕሌኒ ካሳተሙት የደን ኹኔታን ከሚያሳይ መጽሐፍ መንፈስ፣ በብዙ መልኩ፣ ለተፈጥሮ በተለይም ለደን ክብካቤ መቆም እንደሚገባን እንረዳለን፡፡ በአንጻሩ፣ የዩኒቨርሲቲው ድርጊት አሳዛኝ ከመኾን አልፎ መንግሥታዊ ይኹንታ ላለማግኘቱ ማረጋገጫ የለንም። በመኾኑም፣ ስሕተቱ፣ የዩኒቨርሲቲው አመራር ብቻ ሳይኾን፣ መንግሥትን ወክሎ የተቀመጠው የቦርዱም ሓላፊነት ያለበት ጭምር እንደኾነ ልብ ይሏል፡፡
ለ/ሥነ ውበት  
አንድ ሰው* ስለ ጥበብ፣ ስለ ተፈጥሮ፣ ስለ ውበት… ወዘተ. መረዳት የሚችለው፣ ለተፈጥሮ የሚማልል ንቁና ሥሡ ስሜት ሲኖረው ነው፡፡ ይህ ስሜት ደግሞ፣ በተፈጥሮ የሚገኝ ብቻ ሳይኾን፣ ከትምህርት እና ከአድናቆት ጋር በተያያዘ ስሜታችን ሲኮተኮትና ሲሠለጥን የሚገኝ ነው፡፡ ግለሰቡ ውስጣዊ ጉጉት ካለው በእነዚኽ ጉዳዮች ይደነቃል፤ ይደመማል፤ ይማረካል፤ ይማራል፤ ይቆረቆራል፡፡ ነገር ግን፣ ግለሰቡ፣ የሥነ ውበት መማረክ ከሌለው፣ ውስጡ በሥነ ውበት ስእነት(ኢከሃሊነት) የተሞላ ሕጹጽ ነው፤ ማለት ነው፡፡
ይህን ለመግለጽ፣ አንዳንድ ሠዓሊዎች ግድግዳ ላይ የተሰቀለን ሥነ ጥበባዊ ሥራ አይተው፣ “ከፊል ቦታ ላይ ‘dead spot’ ስላለው መስተካከል አለበት” የሚል ሞያዊ አገላለጽ ይጠቀማሉ፤ ቀለም አንሶታል፤ ሕይወት አልባ ነው፤ ለዛ የለውም፤ ደብዝዟል፤… ወዘተ. ማለታቸው ነው፡፡ ይህን ብሂል ወደ ሰው ስናመጣው፣ ግለሰቡ ወይም ግለሰቧ፣ ሥነ ውበትን ለማድነቅ የሚያስችላቸው የስሜት ሕዋሳቸው በድኗል ወይም አልተኮተኮተም ማለት ነው፡፡ በመኾኑም፣ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንትና ይኹንታ የሰጡት የቦርድ ሹመኞች፤ ከሥነ ውበት ክሂል አንጻር ርምጃቸውን ስናየው፣ የሥነ ውበት አድናቆት ስእነት(ኢከሃሊነት) ሰለባ መኾናቸውን በግልጽ እንረዳለን።
ታላቁ ባለቅኔና ጸሐፌ ተውኔት ጸጋዬ ገብረ መድኅን፣ በ“እሳት ወይ አበባ” ግጥሙ ላይ፣ ስለ ክሂለ ቢስነት (dead spot) ከተቀኘው ጥቂት ስንኞችን እንጥቀስ፤
“እና - እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…”
በመኾኑም፣ በዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ የነበረው ተፈጥሮ የለገሰን ውበት በሚገፈፍ ጊዜ፣ ምን ዓይነት ኹኔታ ይፈጠራል? ብሎ መጠየቁ ተገቢ ነው፡፡ ይህን የሥነ ውበት ረድኤት በተመለከተ፣ ኹለት ፈላስፎች ተጠቃሽ አስተምህሯቸውን በሚከተለው መልኩ አስቀምጠውልን አልፈዋል፡፡
የመጀመሪያው፣ የ18ኛው መ/ክ/ዘ ፈላስፋ ኢማኑኤል ካንት፣ በወሳኝ የሥነ ውበት ድርሳኑ (Critique of Judgment)፣ ሥነ ውበትን በመሠረቱ ሲተረጉመው* “Purposiveness without a purpose” ይለዋል፡፡ ይህም ማለት፣ “ይህ ነው” ተብሎ በግኡዛዊ መስፈርት የማይለካ ኾኖ ግብ ያለው እንደ ማለት ነው፡፡ በእርሱ አገላለጽ፡- ተዝናኖት፣ አማሕልሎት እና ሥነ ውበት ያለው ተፈጥሮም ኾነ ጥበብ፣ ከውስጡ ቀጥተኛ የኾነ የተሰፈረ ዓላማ፣ አመክንዮ ወይም ጥቅም የተቀመጠለት አይደለም። ይልቁንም፤ ውብ የኾነ ነገር ማለት፤ ከውስጡ ምንም ቀጥተኛ ጥቅም ሳናገኘበት፣ በውበቱ ብቻ የምንወደው ወይም የምናደንቀው፤ የረቂቁ ሰብአዊ ተፈጥሯችን የሥነ ውበት አድናቆት ስሕበትና “ረኃብ” በሚፈጥርብን ልዩ ፍላጎት ብቻ የምንወደው ማለት ነው፡፡
ይህን ካንታዊ የሥነ ውበት ገለጻ፤ በሀገራችን ነባር አስተምህሮ ለማንጸር ብንሞክር፣ በቤተ ክህነት የሥነ ፍጥረት ትምህርት ያለውን አጠይቆ እንደ አብነት መጥቀስ እንችላለን፡፡ እንደ አስተምህሮው፣ አዝማደ ፍጥረታት በየወገናቸው ስለ ሦስት ምክንያት (ረብሕ) ተፈጥረዋል፡፡ እኒኽም፣ አንደኛው* ለአንክሮ (ለመደመም)፣ ኹለተኛው* ለተዘክሮ (ለተምህሮ)፤ ሦስተኛው* ለምግበ ሥጋ ወነፍስ ናቸው፡፡
ኢማኑኤል ካንት፣ “ቀጥተኛ የተሰፈረ ጥቅም የሌለው ግን ረብ ያለው፤” የሚለውን አገላለጹን፤ ጥንታዊው የቤተ ክህነት አስተምህሮ፣ “ምክንያተ አንክሮ” ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር ዓለምን የፈጠረው፣ ጥቂቱን ለጥቅመ ሥጋ ወነፍስ ሲኾን፤ ብዙውን ግን ለአድናቆት፣ ለመደመም፣ “ወይ የአምላክ ሥራ!” ብለን በአንክሮ የመለኮትን ምስጢር እንድናስተውል፣ የመንፈስ ተመስጦና የልቡና ሐሤት እንድናገኝበት ነው፡፡ ይህን ተሰጥሞ ልቡና እና መንፈሰ ሐሤት የቤተ ክህነቱ አስተምህሮ፥ “አንክሮ” ይለዋል፡፡
ይህን የኢትዮጵያ ጥንታዊ አስተምህሮ እና የኢማኑኤል ካንት “የአንክሮ እና የተደሞ” መሠረተ ሐሳብ፤ ከዛሬው የአዲስ አበባው ዩኒቨርሲቲ የአድማሱ ጸጋዬ አስተዳደር መጠበቅ የዋህነት መኾኑን፣ በዛፍ ምንጠራ - ተማስሎ - ድርጊት ፍንትው ብሎ ታይቷል፤ አስተዳደራዊ አስተሳሰቡ፣ ሥነ ፍጥረት፣ ከጥቅመ ሥጋ ያለፈ ረብሕ እንደሌለው በማያሻማ ኹኔታ አሳይቷልና፡፡         
ፍሬድሪክ ሺለር የተባለው የ19ኛው መ/ክ/ዘመን የሥነ ጥበብ ሰው፣ “Letters on the Aesthetic Education of Man” በሚል ርእስ በጻፈው ጦማር፣ ስለ ሥነ ውበት ምንነት በእጅጉ አስደማሚ የኾነ አጭር ጽሑፍ አቅርቧል፡፡ ጽሑፉ፣ በርከት ያሉ ርእሰ ጉዳዮችን ቢያነሣም፣ ከፍጥረት የሚገኝ ውበት ሰውን ሊያጎናጽፍ ስለሚችለው ሐሤት እንደሚከተለው አትቷል፤
ሺለር እንደሚለው፣ የግለሰቡም ኾነ የማኅበረቡ ልዩነት፣ ሥነ ውበት ፊት ሲቀርብ፣ ልዩነቱ ኹሉ ይቀርና በመስሕቡ ተማርኮ ኹሉም፣ እያንዳንዱም ያለ ልዩነት እኩል ለሥነ ውበት ይማልላል፡፡
ይህን የሺለር ሐሳብ ይዘን፣ ዩኒቨርሲቲውን በምናይበት ጊዜ፣ ትላንት ዛፉ ሳይቆረጥ፣ ማንኛችንንም ሊያግባቡን ያልቻሉ* የብሔር፣ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት፣ የጾታ፣ የመደብ… ወዘተ. አመለካከቶች ሳያግዱን፤ በግቢው ውስጥ የነበረውን መስሕብ ያለው ዐጸድ ያለ ልዩነት በአንድነት እናደንቅ ነበር፡፡ በአኹኑ ወቅት ግን፣ ይህ ዐጸድ ተጨፍጭፎ በፎቆች ሲተካ፣ ሺለር እንዳለው፣ ከተፈጥሮ ውበት ይገኝ የነበረው ንጽረታዊ አንድነት ተጓድሎ፣ ኹላችንም የጋራ አጽድቆት በማንሰጠው ፎቅ ተተክቷል፡፡
እዚኽ ላይ፣ አስተውሎት እንዲኖረን ይገባል ብዬ የማስበው፣ አገዛዙ፣ የጋራ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ዕሴቶችን የመናድ ባሕርያዊ መገለጫው፤ በቅጽሩም ላይ፣ እንደተለመደው፣ ዜጎች ወደ ግቢው ሲዘልቁ የሚያገኙትን ተፈጥሯዊ የጋራ ደስታ በማውደም እንድንለያይ የማድረግ ተግባሩን እንደተያያዘው እንገነዘባለን፡፡
ሐ/ ፎክሎር
የሰው እና የሥነ ሕይወት መስተጋብር፣ በቅርቡ ከምዕራቡ ዓለም የተዋስነው ወይም በሰበካ የተቀበልነው ጉዳይ ሳይኾን፣ ከጥንት ጀምሮ በተለያዩ የአገራችን ማኅበረሰብ ባህል ውስጥ የነበረ አስተሳሰብና ልማድ ነው፡፡ በአገራችን ማኅበረሰቦች ነባር ባህል ውስጥ፣ ስለ ዛፍ ያለው እሳቤ የተለያየ ቢኾንም፣ በአብዛኛው ዛፍ በሰው ልጅ ሕይወት ያለው አገልግሎት ሥሉጥ እንደኾነ እንረዳለን፡፡
ከአገልግሎቱም መካከል፣ ዛፍ፡- መሰብሰቢያ፣ እርስ በርስ መመካከርያ፣ መጠለያ፣ ዕርቅና አፈርሳታ ማካሔጃ ከመኾኑም በላይ፣ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ በመኾን ያገለግላል፡፡ ዛፍ፣ በአንዳንድ ማኅበረሰብ ባህል ውስጥ የማንነት ትእምርት ሲኾን፣ ዛፍን ከሕይወት መሠረት ጋራ በማያያዝ፣ የራሳቸውን ጥንተ አመጣጥ በሐተታ - ተፈጥሯዊ - ሚት መልክ የሚያቀርቡ ማኅበረሰቦች በአገራችን እንዳሉ፤ ሰሎሞን ተሾመ፣  “ፎክሎር፤ ምንነቱ እና የጥናቱ የትኩረት አቅጣጫ” በሚለው መጽሐፉ ገልጿል፡፡  
በተጨማሪም፣ “ዛፍ የሌለው ደብር* ጽሕም የሌለው መምህር” እንዲሉ፣ አብያተ ክርስቲያናትን በርቀት እይታ የምንለያቸው፣ በዙሪያቸውና በግቢያቸው በከበቧቸው ታላላቅ ዐጸዶች ትእምርታዊነት ነው፡፡ ገዳም ማለትም፣ በአንድ ገጹ* ዱር፣ ጫካ፣ የአራዊት መናኸርያ እንደማለት ነው፡፡(ኪዳነ ወልደ ክፍሌ፣ 302)
ማጠቃለያ
ሰው ምሉእነትን የሚጎናጸፈው፣ ለቁመተ ሥጋው የሚያስፈልገውን ምግብ ስላገኘ ብቻ አይደለም፡፡ ታላቁ መጽሐፍ እንደሚለውም፣ “የሰው ልጅ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡፡” ይልቁንም፣ ከፍጥረታት ኹሉ የሚለየው የአእምሮ እና የመንፈስ ምግብ ጥያቄው ትልቅ ቦታ ይይዛል፡፡ የአንድ ዩኒቨርሲቲ ተቀዳሚ ሚና፣ ይህንኑ፣ የሰው ልጅ በተፈጥሮ ለማወቅ በብርቱ የሚሻውን አእምሯዊና መንፈሳዊ “መፍቅድ” ለማሟላት መጣር ነው፡፡
ከላይ የጠቀስናቸው ፕ/ር ዶናልድ ሌቪን፣ “በአንዳንድ ዩኒቨርስቲዎች ውስጥ በኅብረ ሠናይ (Common Good) እና በጥቅም - ተኮር - ሠናይ (Utilitarian Good) መካከል ውጥረት ይኖራል፤” ይላሉ፡፡ በእነኚኽ ተፃራሪም ተደጋጋፊም ውጥረቶች መካከል፣ አንድ ዩኒቨርሲቲ በጎ መልክ ይዞ ሊወጣ የሚችለው፣ የጋራ ሠናይ ፍላጎትን፣ ከጥቅም ተኮር ፖሊሲ በላይ በማስቀደም ሲጓዝ ነው። ይህ ሲኾን ግን፣ ጥቅም ተኮር ሠናይነትን አምዘግዝጎ ይጥለዋል ማለት ሳይኾን፤ ይኸው ጥቅም ተኮርነት በጋራው ሠናይ ፍላጎት ውስጥ ተካብቶ የሚቀመጥ በመኾኑ ነው። በአንጻሩ፣ ጥቅም ተኮር ሠናይ፣ የጋራ ሠናይ ፍላጎትን በምልአት ይዞ አይገኝም፡፡
ፕሬዝዳንት አድማሱ፣ የዩኒቨርሲቲውን ልዕልና እና አካዳሚያዊ ንጽሕ (Chastiti) በማስደፈር፣ መንግሥት* “ዕድገት እና ልማት” የሚለውን ፖሊሲ ለማንሰራፋት በሙሉ ልብ ስለ ተሰማሩ፣ በቅጽሩ ውስጥ ያሉት ዐጸዶች ተቆርጠው፣ “ልማት” ለሚባለው ጣዖት ሰለባ እንዲኾኑ አድርገዋል፡፡ ከአእምሯዊ ይልቅ አካላዊ መስፋፋትን አብልጦ አትኩሮት መስጠት፣ የትምህርት ፈላስፎች እንደሚሉት፣ በ“ዳይናሶራዊ ሲንድረም” መለከፍ ነው፡፡
ይኸውም፣ ዳይናሶር፣ ስዒረ ፍጥረት የደረሰበት አካላዊ ግዘፉ እየፋፋ፣ አእምሯዊ ኃይሉ እያጸጸ ቆይቶ፣ ራሱን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ወደማይችልበት ክስመት ደርሶ ህልውናው በመጥፋቱ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም፣ ከምሥረታው አንስቶ የካበተ ምሁራዊ ጥሪትና የታላላቅ ልሂቃን እርሾ ባይኖረው ኖሮ፣ እንደ ፕሬዝዳንት አድማሱ ተግባር፣ የዳይናሶር ሲንድረም ሰለባ ይኾን ነበር፡፡
በተጨማሪም፣ ዩኒቨርሲቲው የተፈደቀለትን በጀት ሙሉ በሙሉ ባለመጠቀም፣ በየዓመቱ በርካታ ሚሊዮን ብሮችን ተመላሽ እንደሚያደርግ የታወቀ ነው፡፡ ይህም ኾኖ እያለ፣ ለዩኒቨርሲቲው ተጨማሪ ገቢ እየተባለ በፕሬዝዳንቱ ቢሮ ፕሮጀክት ተቀርጾ* ከበሬ ማድለብ እስከ ዕንቁላል መሸጥ፤ አልፎም የሱፐር ማርኬት የንግድ ሱቆች የማቋቋሙን ተግባር ተያይዞታል፡፡ እዚኽ ላይ ልብ ልንለው የሚገባን፣ የገንዘብ እጥረት በሌለበት ኹኔታና የተፈደቀለትንም በጀት በአግባቡ ሳይጠቀም፣ ተጨማሪ ገንዘብ ያስፈልገኛል በሚል ሰበብ፣ ከዕውቀት ጋር ባልተያያዙ ንግዶች ላይ መሰማራቱ በብዙ መልኩ ስሕተት ነው፡፡
ዩኒቨርሲቲው ኹሌም ሊተጋበት የሚገባው፣ ነገር ግን፣ ኹሌም በምልአት የማያሳካው ዋናው የአእምሮ ጥሪትንና ጠፍታን ማካበትና ማረጋገጥ ኾኖ ሳለ፣ ባላገደደው ንግዳዊ ተልእኮ ውስጥ መሰማራቱ አስገራሚ ነው፡፡ ምናልባት፣ የመጀመሪያ ተልእኮውን (የአእምሮ ሥልጥንና) ካሟላ በኋላ ወደ ንግድ ቢገባ፣ ችግር አይኖረውም ይኾናል፡፡   
በርግጥ ዩኒቨርሲቲው፣ ከሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች ጋራ እንደ ዩኒቨርሲቲ ሲለካ፣ ደረጃው እያሽቆለቆለ መምጣቱ ከማንም ያልተደበቀ እውነታ ቢኾንም፤ የግቢው “ግርማ ሞገሳዊ” የውጭ ገጽታ ግን፣ ኹሌም የሚደነቅና በተለያዩ ሀገራት ጎብኚዎች ጭምር የተመሰከረለት ነበር፡፡ ይህን ግርማ ሞገሱን፣ ዛሬ በፕሬዝዳንት አድማሱ ተነጥቆ ዕርቃኑን ቆሟል፡፡
የዛፉ ምንጣሮ፣ ለዩኒቨርስቲው አካላዊ መስፋፋት አማራጭ የሌለው አመክንዮ ተደርጎ በእነ ፕሬዝዳንት አድማሱ ጥቅም ተኮር አስተሳሰብ ይገለጽ ይኾናል፡፡ ከኹሉ በፊት፣ “አማራጭ የለሽ” ይሉት ይኸው ህወሓታዊ ሜታፊዝክስ(የእኛ ሐሳብ* ትክክለኛው እና ብቸኛው ነው፤ የሚል የሐሳብ ሞኖፖሊ)፣ በተለያዩ አጀንዳዎች እንዳየነው፣ አስቀድሞ የተቆረጠንና የተፈጠመን ነገር፣ ያለተገዳዳሪ ሐሳብ ለማስፈጸም የሚጠቀሙት ዘይቤ ነው፤ ፕሬዝዳንቱም፣ የዚኹ፣ “አማራጭ የለም፤” ባይ የሥርዓቱ ፍልስፍና ሰባኪና አስፈጻሚ ኾነው እናገኛቸዋለን፡፡ በአንጻሩ፣ ዩኒቨርሲቲው፣ እንደ መካነ አእምሮ፣ የአማራጭ የለሽ ፍልስፍናን ሽሮ፣ ለተለያዩ ፕሮብሌሞች ኊልቊ መሳፍርት የሌላቸው አማራጮችን የማቅረብ ሓላፊነት አለበት፡፡ ዩኒቨርሲቲው ለሚፈልገው የማስፋፊያ ሥራ ሌሎች የቦታ አማራጮችን መጠየቅ ሲችል፤ ሥነ ውበትን ገርስሶ፣ የኮንስትራክሽን ጣቢያና የፎቆች ጫካ የመሰለ ትዕይንት መፍጠር ተገቢ አይደለም፡፡
የደን ምንጣሮውንና የሕንፃ ማስፋፊያውን፣ ከፕሬዝዳንቱና ከበላይ ሹሞቻቸው ሕጸጽ አኳያ በየአንጻሩ ለማሳየት ሞክረናል፡፡ በዚኽ ጉዳይ ላይ፣ የዩኒቨርሲቲው ግድፈት የሚያሳየው፣ የ“ኤፒስቲሚክ” እና የ“ኤስቴቲክ” ችግርን ብቻ ሳይኾን፤ የአንድ ቢሊዮን ብር ፕሮጀክትን በ‘ካፒቴንነት’ ለማስተዳደር ከመሻት የመነጨ እንደኾነ መገመት አያስቸግርም፡፡ መቼም፣ ዜጎች ብቻ ሳይኾኑ፣ “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል” እንዲሉ፣ የአማሳኞቹ ቡድን በስም ዝርዝር ባይነገረንም፣ ስለ ሙስናው መንሰራፋት አንዳንድ የሥርዐቱ ሹመኞችም ቢኾኑ በይፋ ያመኑበት ጉዳይ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሙስና ዕንብርት ተብለው የተለዩና ብዙዎችን ካስማሙት ቀዳሚዎቹ፡- የመሬት አስተዳደር፣ የመንገድና የሕንፃ ግንባታ፣ የገቢዎች እና ጉምሩክ አሠራር ላይ የሚታየው ምዝበራ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም፣ የአንድ ቢሊዮን ብር በጀት በተያዘለት የግንባታ ፕሮጀክት ውስጥ ሲገባ፤ በተለይ ኦዲት ተደርጎ የማያውቅ ተቋም ከመኾኑ የተነሳ፣ ምንም ዓይነት የሙስና እንቅስቃሴ በፕሮጀክቱ ላይ አይካሔድም ብሎ ማመን ተላላነት ነው፡፡
ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት አጠያያቂ በኾነበት በአኹኑ ጊዜ፤ በየትኛውም ተቋም ስላለው ሙስና ሐቁን መናገር በጣም ያስቸግራል፤ ለዚኽም ነው፣ ልዑል ራስ ካሳ ኃይሉ፣ “ፍኖተ አእምሮ” በተሰኘው መጽሐፋቸው፡- “ነጻነትን ተከባከቧት፤ እውነት ራሷን ትጠብቃለች” ያሉት፡፡ ነጻነት በሀገራችን ገና የተደላደለ ቦታ ስላላገኘች፣ ለጊዜው እውነት ሸሸግ ብላ ለመቀመጥ ስለምትገደድ፣ እኛም፣ ስለ ሙስና ከዚኽ በላይ ለማተት ኹኔታው እንደማይፈቅድልን በመረዳት፣ የያዝነውን በልባችን እንደያዝን ሐሳባችንን በዚኹ እናሳርፋለን፡፡

Saturday, 11 February 2017 12:54

የዘላለም ጥግ

(ታላላቅ ሰዎች
በመሞቻቸው ሰዓት)
- “ማምለጫ ሰበብ እየፈለግሁ ነው”
ደብሊው ሲ. ፊልድስ
(አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይና ኮሜዲያን)
- “በእግዚአብሔር እ መኑ እ ናም ም ንም
የሚያስፈራችሁ ነገር አይኖርም”
ጆናታን ኤድዋርድስ
(የክርስቲያን ሰባኪና የስነ-መለኮት ልሂቅ)
- “ምድር ወደ ኋላ ስትሸሽ፣ መንግስተ ሰማያት
ሲከፈት ይታየኛል፡፡ እግዚአብሔር እየጠራኝ
ነው”
ዲ.ኤል.ሙዲ
(አሜሪካዊ ወንጌላዊና ደራሲ)
- “ሞት፤ የዘላለማዊነትን ቤተ መንግስት
የሚከፍት ታላቅ ቁልፍ ነው”
ጆን ሚልተን
(የብሪቲሽ ገጣሚ)
- “በአስር ደቂቃ ዘግይቻለሁ፡፡ እኔ ማርፈድ
አልወድም፡፡ ፀሎቱ ጋ ልክ በ11 ሰዓት መገኘት
እፈልጋለሁ፡፡”
ማሃትማ ጋንዲ
(የህንድ የነፃነት ንቅናቄ መሪ)
- “ዛሬ በጣም ሞቃት ነው”
ጄሲ ጄምስ
(አሜሪካዊ የባቡር ላይ ዘራፊ)
- “ሁልጊዜም ጋደም ስል የተሻለ እናገራለሁ”
ጄምስ ማዲሰን
(የአሜሪካ 4ኛ ፕሬዚዳንት)
- “በቃ ተይኝ!”
(ነርሷ የእግር እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ስትጠይቀው)
ጎሬ ቪዳል
(አሜሪካዊ ደራሲ)
- “እስቲ ወደ አባታችን ቤት ልሂድ”
ጆን ፖል (ዳግማዊ)
(የሮማን ካቶሊክ ቤ/ክርስቲያን ጳጳስ)
- “ለብቻዬ ተይኝ፤ ደህና ነኝ”
(ለነርሱ የተናገረው)
ባሪ ዋይት
(አሜሪካዊ ሙዚቀኛ)
- “እና ሞት ይሄ ነው - ይሁና”
ቶማስ ካርሊሌ
(የስኮትላንድ ፈላስፋና የታሪክ ምሁር)
- “የሰሙኝ እንኳን አይመስለኝም”
(ራሱን ከማጥፋቱ በፊት የተናገረው)
ዩክዮ ሚሺማ
(ጃፓናዊ ደራሲ)