Administrator

Administrator

በየቀኑ ዩቲዩብ ላይ የሚጫኑ ቪዲዮዎች ርዝማኔ 65 አመታት ያህል ነው
    በታዋቂው ድረገጽ ዩቲዩብ አማካይነት ለእይታ የቀረቡ የተለያየ አይነት ይዘት ያላቸው ቪዲዮዎች በአንድ ቀን ውስጥ ብቻ ከ 1 ቢሊዮን ሰዓታት በላይ በአለም ዙሪያ በሚገኙ የድረገጹ ተጠቃሚዎች እንደሚታዩ ተዘገበ፡፡
   በዩቲዩብ የሚታዩ ቪዲዮዎች ብዛት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ እንደሚገኝ የዘገበው ዎልስትሪት ጆርናል፤ የድረገጹ ቪዲዮዎች በአንድ ቀን ውስጥ የሚታዩበት ሰዓት ባለፉት አምስት አመታት በአስር እጥፍ ያህል ማደጉን ጠቁሟል፡፡  ወደ ዩቲዩብ ድረገጽ የሚጫኑ ቪዲዮዎች ቁጥርም እጅግ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ሲሆን በየቀኑ በድረገጹ ላይ የሚጫኑ ቪዲዮዎች አጠቃላይ የሚፈጁት ጊዜ እርዝማኔ 65 አመታት ያህል እንደሚደርስም ኩባንያው አስታውቋል፡፡   እ.ኤ.አ በ2005 ስራ የጀመረው ዩቲዩብ፣ በመላው አለም በሚገኙ የቪዲዮ ተመልካቾች ተቀዳሚ ምርጫ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ ድረገጹ ገቢም በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን አክሎ ገልጧል፡፡

 ኦባማ እና ሚሼል አዳዲስ መጽሃፍትን ለማሳተም ከ65 ሚ. ዶላር በላይ ይከፈላቸዋል
    የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦማባ በዘንድሮው የፈረንሳይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንዲወዳደሩ የሚጠይቅ የድጋፍ ፊርማ የማሰባሰብ ዘመቻ በድረገጽ አማካይነት መጀመሩንና እስካሁን ድረስም ከ42 ሺህ በላይ ሰዎች ሃሳቡን በመደገፍ ፊርማቸውን ማስፈራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የዘመቻው አስተባባሪዎች ኦባማ በመጪው ግንቦት ወር  በሚካሄደው የፈረንሳይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንዲወዳደሩ የድጋፍ ፊርማ ማሰባሰብ የጀመሩት፣ ሃሳባቸው ህጋዊ ተቀባይነት እንደማያገኝ ቢያውቁም፣ ለምርጫው በዕጩነት የቀረቡት የአገሪቱ ዜጎች ይህ ነው የሚባል ብቃት የሌላቸው መሆናቸውን ለማስመስከር በማሰብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በሳምንቱ መግቢያ  ላይ በተጀመረውና ለቀናት በዘለቀው የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ፣ ከ42 ሺህ በላይ ሰዎች ድጋፋቸውን መግለጻቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አስተባባሪዎቹ 1 ሚሊዮን ያህል ለማድረስ አቅደው በስፋት እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙና በፓሪስ ጎዳናዎች ላይ ኦባማ 2017 የሚል መፈክር የተጻፈባቸው ፖስተሮች በስፋት መሰራጨታቸውን አመልክቷል፡፡
ኦባማ ለፈረንሳይ ፕሬዚዳንትነት እንዲወዳደሩ የሚጠይቀው የድጋፍ ድምጽ ከሚሊዮን አልፎ ቢሊዮንና ትሪሊዮን ፊርማዎችን ቢያሰባስብም፣ የአገሪቱ ህግ የውጭ ዜግነት ያለው ሰው ለፕሬዚዳንትነት መወዳደር እንደማይችል የሚደነግግ በመሆኑ ከንቱ ድካም ሆኖ እንደሚቀር ዘገባው አስረድቷል፡፡
በሌላ በኩል፣ ባራክ ኦባማ እና ባለቤታቸው ሚሼል ኦባማ፤ ሁለት አዳዲስ መጽሃፍቶቻቸውን ለንባብ የሚያበቁበትንና ከ65 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ እንደሚያገኙበት የተነገረለትን የህትመት ስምምነት ውል መፈጸማቸው ባለፈው ማክሰኞ ተዘግቧል፡፡
ኦባማ በዋይት ሃውስ የነበራቸውን የስምንት አመታት ቆይታ የሚዳስሱበትን፣ ሚሼል ደግሞ አነቃቂ ይዘት ያለው ነው የተባለውን መጽሃፍት ለንባብ ለማብቃት ከታዋቂው አሳታሚ ኩባንያ ፔንጉዊን ራንደም ሃውስ ጋር በድምሩ ከ65 ሚሊዮን ዶላር በላይ ስምምነት መፈጸማቸውን የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፤ የመጽሃፍቱ ርዕሶችም ሆነ ለገበያ የሚበቁበት ጊዜ ይፋ አለመደረጉን ጠቁሟል።
ኦባማ እና ሚሼል ከአሳታሚው ኩባንያ ከሚከፈላቸው ገንዘብ ዳጎስ ያለውን ለበጎ አድራጎት ስራ ለማዋል ማቀዳቸውን ያስታወቀው ዘገባው፤ መጽሃፍቶቹን ለማሳተም በርካታ አሳታሚ ኩባንያዎች መወዳደራቸውንና  ፔንጉዊን ራንደም ሃውስ የተጠቀሰውን ገንዘብ በማቅረብ ውድድሩን ማሸነፉንና ይህ ዋጋ በአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች የማስታወሻ መጽሃፍ ክፍያ ታሪክ ከፍተኛው መሆኑን አመልክቷል፡፡
የስልጣን ዘመናቸው ማብቃቱን ተከትሎ ለንባብ ባበቋቸው መጽሃፍት ከፍተኛውን ክፍያ በማግኘት ቀዳሚነቱን ይዘው የቆዩት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን መሆናቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ክሊንተን በ2004 ለንባብ ላበቁት ማይ ላይፍ የተሰኘ መጽሃፍ ከአሳታሚያቸው የተከፈላቸው ገንዘብ 15 ሚሊዮን ዶላር እንደነበርም  ጠቅሷል፡፡
ኦባማ ከዚህ ቀደም ለንባብ ያበቋቸው ድሪምስ ፍሮም ማይ ፋዘር እና ዘ ኦዳሲቲ ኦፍ ሆፕ የተሰኙ ሁለት መጽሃፍት በሚሊዮኖች ቅጂ መቸብቸባቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ የሚሼል ኦባማ ብቸኛ መጽሃፍ ደግሞ በ2012 ያሳተሙት አሜሪካን ግሮውን የተባለ በምግብ ዝግጅትና በተክሎች እንክብካቤ ዙሪያ የሚያጠነጥን መጽሃፍ መሆኑን አስረድቷል፡፡

      የፓኪስታን አለማቀፍ አየር መንገድ ባለፈው ጥር ወር ላይ ከካራቺ ወደ ሳኡዲ አረቢያዋ ከተማ መዲና ባደረገው በረራ፣ መጫን ከሚገባው የመንገደኛ ቁጥር በላይ 7 ትርፍ መንገደኛ መጫኑን እንዳመነ ኒውስ 18 ድረ-ገጽ ዘግቧል፡፡  የአየር መንገዱ ሰራተኞች ጥር 20 ቀን በረራውን ባደረገውና 409 ሰዎችን የማሳፈር አቅም ባለው ቦይንግ 777 አውሮፕላን ውስጥ ተጨማሪ 7 መንገደኞችን በማሳፈር፣ ለአደጋ የሚያጋልጥ ጉዞ እንዲደረግ በመፍቀዳቸው በህግ እንደሚጠየቁና አየር መንገዱ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝም ዘገባው ገልጧል፡፡
  በትርፍ የተጫኑት መንገደኞች ረጅም ሰዓታት የሚፈጀውን ጉዞ ያለምንም መቀመጫ፣ ቆመው እንደጨረሱት የአገሪቱ ጋዜጦች ቢዘግቡም፣ አየር መንገዱ ግን ይህን ማስተባበሉንና በረራው ያለምንም ችግር እንደተጠናቀቀ ማስታወቁን ድረ ገጹ ጠቁሟል።  አውሮፕላኖች መጫን ከሚገባቸው የመንገደኛ ቁጥር በላይ እንዲጭኑ መፍቀድ፣ የኦክስጂን አቅርቦት ካለመኖር፣ ከመተፋፈግና ከተያያዥ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ አውሮፕላኑንና ተሳፋሪዎቹን ለከፋ አደጋ እንደሚያጋልጥና በአቪየሽን ህግ መሰረት ከፍተኛ ቅጣት እንደሚያስጥልም ዘገባው አስታውቋል፡፡

   የቀጣይ 6 አመታት የፕሮግራም ስትራቴጂውን ይፋ አድርጓል
     በኢትዮጵያ በውሃ፣ የአካባቢ ንጽህና እና የስነ ጤና አጠባበቅ ላይ ትኩረት አድርጎ በመስራት ብቸኛው መንግስታዊ ያልሆነ አለማቀፍ ድርጅት የሆነው ዎተርኤይድ ኢትዮጵያ፤ ባለፉት ስድስት አመታት በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ባከናወናቸው ተግባራት 1.3 ሚሊዮን ያህል ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረጉን ያስታወቀ ሲሆን ከ2016 እስከ 2021 ባሉት ቀጣይ አመታት የተጠናከረ ስራ ለማከናወን የሚያስችለውን አዲስ የፕሮግራም ስትራቴጂ ባለፈው ማክሰኞ ይፋ አድርጓል፡፡
ለስድስት አመታት በዘለቀውና ዘንድሮ በተጠናቀቀው የፕሮግራም ስትራቴጂ ዘመን ከአጋር አገር በቀል ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት በአገሪቱ አምስት ክልሎች የሚገኙ ከ1.3 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን የውሃ፣ የአካባቢ ንጽህናና የስነ ጤና አጠባበቅ አገልግሎቶች ተጠቃሚ ማድረጉን የገለጸው ዎተርኤይድ ኢትዮጵያ፤ በቀጣይም አገልግሎቶቹን በስፋት ለማዳረስ የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን ለማከናወን ማቀዱን አስታውቋል፡፡
የውሃ፣ የመስኖና የኤሌክትሪክ ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ፍሬነሽ መኩሪያ በካፒታል ሆቴል በተከናወነው የድርጅቱ የፕሮግራም ስትራቴጂ ማስተዋወቂያ ስነስርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የውሃ፣ የአካባቢ ንጽህናና የስነ ጤና አጠባበቅ አገልግሎቶችን እ.ኤ.አ እስከ 2030 በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ለሁሉም ዜጎች በተሟላ መልኩ ለማዳረስ የተያዘውን አገራዊ እቅድ በማሳካት ረገድ ዎተርኤይድ ኢትዮጵያ የራሱን ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ በሚሊኒየሙ የልማት ግቦች ውስጥ የተካተተውን የውሃ አቅርቦት ግብ ማሳካት ችላለች ያሉት ወ/ሮ ፍሬነሽ፤ የአካባቢ ንጽህና ግብን ለማሳካት በተደረገው ጥረት መልካም ውጤት ቢመዘገብም፣ ግቡን ለማሳካት ተጨማሪ ርብርብ ማድረግ እንደሚገባ በመጥቀስ፣ ለዚህ ደግሞ ዎተር ኤይድን ጨምሮ በመስኩ የሚሰሩ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት የሚያደርጉት የተቀናጀ ርብርብ ወሳኝ መሆኑን አስምረውበታል፡፡
በሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የውሃ፣ የአካባቢ ንጽህናና የስነ ጤና አጠባበቅ አገልግሎቶችን አጠቃላይ አቅርቦት ፍትሃዊና ዘላቂ በሆነ መልኩ ለማሟላት ግብ ተቀምጦ እየተሰራ እንደሚገኝ የጠቆሙት ወ/ሮ ፍሬነሽ፤ ለዕቅዱ መሳካት ባለድርሻ አካላት ከመንግስት ጎን እንዲቆሙ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የዎተርኤይድ ኢትዮጵያ ካንትሪ ዳይሬክተር ቤተልሄም መንግስቱ በበኩላቸው፤ ባለፉት 20 አመታት በአገሪቱ የውሃ፣ የአካባቢ ንጽህናና የስነ ጤና አጠባበቅ አገልግሎቶችን አጠቃላይ አቅርቦት ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ጉልህ ውጤቶች መመዝገባቸውን አስታውሰው፣ ዎተርኤይድ ኢትዮጵያም በመስኩ የተመዘገቡ ውጤቶችን በተቀናጀ አሰራር የበለጠ በማሳደግና የተቀመጡ ግቦችን በማሳካት ረገድ የራሱን አስተዋጽኦ ለማበርከት የሚያስችለውን የቀጣይ አመታት የፕሮግራም ስትራቴጂ መቅረጹን ገልጸዋል፡፡
ድርጅቱ በቀጣይም በመስኩ የሚታዩ አንዳንድ ችግሮችን በመቅረፍ፣የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ፣ የዘላቂ ልማት ግቦችንና በሴክተሩ የተቀመጠውን የ”ዋን ዋሽ” ብሄራዊ ፕሮግራም ግቦችን ለማሳካት በመንግስት እየተደረገ ያለውን ጥረት እንደሚያግዝም አስረድተዋል፡፡
የዎተርኤይድ ኢትዮጵያ አገልግሎቶችን በፍትሃዊና በዘላቂነት ለማዳረስ የሚያስችሉ የስርዓት ቀረጻ ስራዎችን እንዲሁም በብሄራዊ፣ በክልላዊና በወረዳ ደረጃ በመስኩ ለተሰማሩ ባለድርሻ አካላት የአቅም ግንባታ ድጋፎችን ማድረግ ከጀመረ 30 አመታትን ያህል ያስቆጠረ ሲሆን አለማቀፉ ዎተርኤይድም በ37 የተለያዩ የአለማችን አገራት ሰፋፊ ስራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል፡፡

Tuesday, 07 March 2017 00:00

የፀሐፍት ጥግ

· ዘፈን ያው ዘፈን ነው፡፡ ግን አንዳንድ ዘፈኖች አሉ … አንዳንድ ዘፈኖች በጣም ግሩምናቸው፡፡ የቢትልስ “yesterday” የሚለው ዘፈን ዓይነት፡፡ እስቲ ግጥሙን አዳምጡት፡፡
   ቹክ ቤሪ
· የድሮ የዘፈን ግጥሞቼን ብመለከታቸው በቁጣ የተሞሉ ነው የሚመስሉት፤ ግን ባዶ ናቸው፡፡ በህይወቴ ውስጥ ባዶነት ነበረ፡፡
   ቢሊ ጆ አርምስትሮንግ
· በሙዚቃዬና በዘፈን ግጥሞቼ፣ የሰዎችን ህይወት ለመንካት እፈልጋለሁ፡፡
   ሮሚዮ ሳንቶስ
· ብዙ ልዋሽ እችላለሁ፤ በዘፈን ግጥሞቼ ውስጥ ግን ፈፅሞ ውሸት የለም፡፡
   ኮርትኔይ ላቭ
· ብዙ ጊዜ የዘፈን ግጥሞች ሀዘንና ትካዜ ይበዛቸዋል፡፡
   ዊል ቻምፒዮን
· የዘፈን ግጥሞችን እንዳብራራ ልትጠይቁኝ አትችሉም፤ ምክንያቱም አላደርገውም፡፡
   ሎዩ ሪድ
· የዘፈን ግጥሞችን የምንሰራው በከፍተኛ ጥንቃቄ ነ ው፤ ማ ንንም ማ ስቀየም አንፈልግም፡፡
   ቢል ሃሌይ
· የማስታወሻ ደብተር ይዤ የዘፈን ግጥሞች ለመፃፍ የምቀመጥ ዓይነት ሰው አይደለሁም፡፡
   ጄምስ ቪንሴንት ማክሞሮው
· ከ11 እስከ 15 ዓመት ባለው ዕድሜዬ ያደመጥኳቸውን ዘፈኖች ግጥም ብቻ ነው የማውቀው፡፡
   ኤልዛቤት ባንክስ
· ሁልጊዜ እንደፃፍኩ ነው፤ ተንቀሳቃሽ ስልኬ በሃሳቦች ጢም ብሎ የተሞላ ነው - በዜማዎች፣ በግጥሞችና የመሳሰሉት፡፡
   ኤሊዛ ዱሊትል
· ለእኔ ሙዚቃ መስራት ከቀላል ዜማ ይጀምራል፤ ከዚያ በኋላ ግጥም ይከተላል፡፡
   ሊዮን ብሪጅስ
· የራፕ ሙዚቃ ድንቅ ነው፤ ውብ፡፡ ችግሩ ያለው ከግጥሞቹ ነው፡፡ ግጥሞቹን ከሚፅፋቸው ሰው - ያ ነው ችግሩ፡፡
   ኢማኑኤል ጃል
· እንደሚመስለኝ አንድ ዘፈን ውብ ግጥሞች እስካሉት ድረስ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡
   ጁሊ አንድሪውስ
· የዘፈን ግጥሞቼ የራሴ ወይም የጓደኞቼ የህይወት ተሞክሮ ትናንሽ ታሪኮች ናቸው፡፡
   ሳዴ አዱ
· በዙሪያዬ ጊታር መኖር አለበት፡፡ ሻወር ውስጥ ሆኜ እዘፍናለሁ፡፡ በመኖሪያ ቤት አካባቢ እዘፍናለሁ፡፡ ሙዚቃው በሁለተኛ ደረጃ የሚመጣ ነው፡፡ ቅድምያ የሚሰጠው ለግጥሙ ነው፡፡
   ኢሚሎዩ ሃሪስ

 አዛውንቱ ፕሬዚዳንት
ሮበርት ገብርኤል ሙጋቤ እ.ኤ.አ ፌብሯሪ 21, 1924 ዓ.ም ነው የተወለዱት - በዚምባቡዌ ደቡባዊ ርሆዴዥያ ግዛት፡፡ ሮበርት ሙጋቤ አሁን 91 ዓመታቸው ሲሆን በመላው ዓለም ከሚገኙ መሪዎች ሁሉ በዕድሜ አዛውንቱ ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡
በእናት ያደጉት ሙጋቤ
ሰዎች አምባገነን ተፈጥሮአቸውን በመመልከት ብቻ ሙጋቤ በፈላጭ ቆራጭ አባት ነው ያደጉት ብለው ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ እውነቱ ግን ሌላ ነው። የሙጋቤ አባት አናጢ ነበሩ፡፡ ትንሹ ሙጋቤ ባልተለመደ መልኩ ሥርዓት ያለውና ጥብቅ ታዳጊ ነበር፡፡ በርግጥ አስቸጋሪ የልጅነት ጊዜ ነው ያሳለፈው፡፡ ሁለቱንም ታላላቅ ወንድሞቹን በሞት ያጣው ገና በህጻንነቱ ነበር፡፡ አባቱ በደቡብ አፍሪካ የጄሱይት ሚሽን ዘንድ ለመስራት ከቤተሰቡ ከተለዩ በኋላ ወደ ቤት አልተመለሱም፡፡ በዚህም የተነሳ መምህር የነበሩት እናቱ፣ሙጋቤንና ሦስት ወንድሞቹን ለብቻቸው ማሳደግ ነበረባቸው። ሙጋቤ ከብት በመጠበቅና ገንዘብ በሚያስገኝ የጉልበት ሥራ በመሰማራት፣ እናቱንና ቤተሰቡን እየደገፈ ነው ያደገው፡፡  
ብቸኛው የነፃነት ማግስት መሪ
ሙጋቤ እ.ኤ.አ በ1963 የብሪቲሽን ቅኝ አገዛዝ የሚታገለውን ZANU የተሰኘ የተቃውሞ ንቅናቄ መሰረቱ፡፡ በ1980 የብሪቲሽ አገዛዝ ሲያከትም የአዲሲቷ የዚምባቡዌ ሪፐብሊክ ጠ/ሚኒስትር ሆኑ። በ1987 የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በመሆን ተመረጡ። ሙጋቤ አገሪቱ ከቅኝ አገዛዝ ነጻ ከወጣችበት ጊዜ አንስቶ ብቸኛው የዚምባቡዌ መሪ ናቸው፡፡  
ለረዥም ዓመት በወህኒ ቤት
ሙጋቤ የወግ አጥባቂውን አናሳ - ነጭ የርሆዴዥያ መንግስት የሚቃወም ንቅናቄ መሪ ነበሩ፡፡  ይሄን ተከትሎም ወህኒ ቤት ተወርውረዋል። ከ1964-1974 ለአስር ዓመት ያህልም ታስረው ነበር፡፡ በወህኒ ቤት ሳሉ ታዲያ ሥራ አልፈቱም። ሌሎች እስረኞችን የእንግሊዝኛ ቋንቋ ያስተምሩ የነበረ ከመሆኑም በላይ ከለንደን ዩኒቨርስቲ በርቀት ትምህርት ሁለት የህግ ድግሪዎችን አግኝተዋል፡፡
ከፖለቲካ በፊት መምህር
ምንም እንኳ በደቡባዊ ርሆዴዥያ ብዙ ሰዎች ከሰዋስዎ ትምህርት ባያልፉም ሙጋቤ ግን ደህና ትምህርት ለማግኘት ዕድል ቀንቷቸዋል፡፡ እስከ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ድረስ በሚሲዮናውያን የተማሩት ሙጋቤ፤በ1945 ዓ.ም ከካቱማ ቅዱስ ፍራንሲስ ዛቪዬር ኮሌጅ ተመርቀዋል፡፡ ለቀጣዮቹ 15 ዓመታትም በርሆዴዥያና በጋና ያስተማሩ ሲሆን ተጨማሪ ትምህርታቸውንም በደቡብ አፍሪካው ፎርት ሃሬ ዩኒቨርሲቲ ተከታትለዋል፡፡
ህዝባቸውን አስተምረዋል
በአምባገነኑ ሙጋቤ ላይ በርካታ ትችቶች ቢሰነዘሩም የፕሬዚዳንትነት ሥልጣን ከያዙበት ጊዜ አንስቶ የአገራቸውን የትምህርት ሥርዓት በከፍተኛ ደረጃ መቀየራቸው ግን ማንም የሚመሰክረው ሃቅ ነው፡፡ በሳቸው የአገዛዝ ዘመን ማንበብና መጻፍ የሚችለው የዚምባቡዌ ህዝብ ወደ 90 በመቶ ገደማ ደርሷል፡፡ ለዚህ ስኬት ደግሞ ትምህርት ወዳድነታቸው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱ ይነገራል፡፡ ሙጋቤ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች 7 ድግሪዎችን የተቀበሉ ሲሆን ኢኮኖሚክስ፣ ትምህርት፣ አስተዳደር፣ህግና የመሳሰሉትን ያካልላል፡፡
የማንቀላፋት ልማድ ተጠናውቷቸዋል
ለበርካታ ዓመታት ዚምባቡዌን በመምራት የሚታወቁት ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤በተለያዩ ስብሰባዎችና ኮንፍረንሶች ላይ ሲያንቀላፉ በተደጋጋሚ በካሜራ ተይዘዋል፡፡ አንዳንዶች ይሄን የማንቀላፋት ሱሳቸውን ከዕድሜ ጋር ሲያገናኙት፣”ብዙ ስለሚያስቡ ነው” ብለው ምክንያት የሚሰጡም አሉ፡፡ ምክንያቱ ምንም ይሁን ምንም ግን እሳቸው በተለያዩ አቀማመጦች እንቅልፋቸውን መለጠጥ ይችሉበታል፡፡ አገራዊ ጉባኤ ይሁን ዓለም አቀፍ ለሳቸው ለውጥ የለውም፤ ጉባኤው እስኪጠናቀቅ ድረስ የእንቅልፍ ሱሳቸውን በቅጡ ይወጡታል፡፡
በቅርቡ የተያዙት የናይጄሪያ አዲሱ ፕሬዚዳንት ጀነራል ሙሃማዱ ቡሃሪ ሲመተ - በዓል ላይ ነበር። እንደተለመደው እንቅልፋቸውን ሲለጥጡ በሰሃራ ሪፖርተሮች የካሜራ ዓይን ውስጥ ወድቀዋል - ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፡፡
የክብር ድግሪዎችን ተነጥቀዋል
ሙጋቤ በተለይ በ1980ዎቹ ዓመታት ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ዩኒቨርሲቲዎች በርካታ የክብር ድግሪዎችንና ማዕረጎችን ተቀብለው ነበር፡፡ ግን ምን ያደርጋል----በአገራቸው ከነበረው የሰብአዊ መብት ጥሰቶችና የዲሞክራሲያዊ ሂደት መጨናገፍ ጋር በተያያዘ ቢያንስ ሦስቱን ተነጥቀዋል፡፡
በጁን 2007 ዓ.ም የእንግሊዙ ኢድንበርግ ዩኒቨርሲቲ በ1984 ዓ.ም የሰጣቸውን የክብር ድግሪ ሰርዞባቸዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ከዓለም አቀፍ ታዋቂ ሰው ላይ የሰጠውን የክብር ድግሪ ሲነጥቅ ሙጋቤ የመጀመሪያው ነበሩ ተብሏል፡፡ በጁን 2008 ዓ.ም የማሳቹሴት ዩኒቨርሲቲ እንዲሁ በ1986 ዓ.ም የሰጣቸውን የህግ የክብር ድግሪ ነጥቋቸዋል፡፡ በሴፕቴምበር 2008 ደግሞ የሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ በ1990 ዓ.ም የሰጣቸውን የህግ የክብር ድግሪ መልሶ ወስዶባቸዋል፡፡ ምን ይሄ ብቻ ---- በ1994 ዓ.ም ከእንግሊዟ ዳግማዊት ኤልዛቤት የተሰጣቸውን የክብር ማዕረግም በጁን 2008 ዓ.ም ተነጥቀዋል፡፡
ከሥልጣን የመውረድ ሃሳብ የላቸውም
ሮበርት ሙጋቤ ለ7 ጊዜ ያህል በምርጫ ያሸነፉ ቢሆንም ምርጫዎቹ ግን በማጭበርበርና መራጮችን በማስፈራራት የተካሄዱ እንደነበር ይነገራል፡፡ ብዙዎች “ሙጋቤ እንዴት ሥልጣን አይሰለቻቸውም?” ብለው ይጠይቁ ይሆናል፡፡ የሚገርመው ግን እሳቸው ከሥልጣን የመውረድ ሃሳቡ እንኳን የሌላቸው መሆኑ ነው፡፡ በመጪው የ2018 ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የመወዳደር ዕቅድ እንዳላቸውም በቅርቡ አረጋግጠዋል፡፡ የዕድሜዬ መግፋት ጥንካሬዬን አልቀነሰውም ብለዋል - የ91 ዓመቱ አዛውንት ሮበርት ሙጋቤ፡፡
 መጻህፍት አሳትመዋል  
ሙጋቤ በርካታ መጻህፍትን ለንባብ ያበቁ ሲሆን ከእነሱም መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡-
The Third Chimurenga: Inside the Third Chimurenga (2001)
War,Peace and Development in Contemporary Africa (1987)
The Role of the University in the process of Social Transformation (1983)
Our War of Liberation (1983)

 አንዳንድ ተረት ሲደገም የበለጠ ይገባል፡፡ ምናልባት ልቡናችን ሁሌም እኩል ክፍት ስለማይሆን ሊሆን ይችላል፡፡ አንድም የበለጠ ወቅታዊ ሁኔታ አግኝቶ ሊሆን ይችላል፡፡ በሌላ አጣዳፊ ጉዳይ አዕምሮአችን ሲወጠር ጠንከርና በሰል ያለውን ጉዳይ ምን ተደጋግሞ ቢነገረን የማንሰማበት ጊዜ አለ፡፡ ውሎ አድሮ ሁኔታው ሲሻሻል ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ ከአስራ አንድ ዓመት በፊት የተረትነውን ዛሬ የምንደግመው ለዚህ ነው፡፡
አንድ የሩቅ ምስራቅ ፌዘኛና ብልህ አዛውንት ነበሩ አሉ፡፡ በጣም ከሚታወቁበት ነገር አንዱ ግማሽ ህይወታቸውን ከሀገራቸው ውጪ ሲሰደዱና በምህረት ሲመለሱ የኖሩ መሆናቸው ነው፡፡
ታዲያ አንደኛው አገር አለቃ ገብረ ሀና ብዙ የሚነገሩላቸው ወጎች አሉ፡፡
አንድ ጊዜ የአገሩ ንጉሥ እኒህን አዛውንት አግንተዋቸው ሁለቱ እንደሚከተለው ያወጋሉ፡፡
ንጉሥ - እንደምን ሰነበቱ አባቴ?
አዛውንቱ - እንደ አገሬው
ንጉሥ - ከየት ነው የሚመጡት?
አዛውንት - ከፀሐይ መውጫ
ንጉሥ - ወደየት ይሄዳሉ?
አዛውንት - ወደ ፀሐይ መውጫ
ንጉሥ - እንዴት? ከፀሐይ መውጫ እየመጡ፣ ወደ ፀሐይ መውጫ ሊሄዱ ይችላሉ? ብለው በመገረም ይጠይቃሉ፡፡
አዛውንቱም - እሱ በሦስት መንገድ ይወሰናል
ንጉሥ - በምን በምን?
አዛውንት - አንደኛ በማንነትዎ ነው፡፡ ማለትም ፀሐይ ልትጠልቅብኝ ነው ብለው የሚያስቡ ከሆነ ወደ ፀሐይ መውጫ እንደሚሄዱ ያምናሉ፡፡ ሁለተኛ/በአነሳስዎ ማለትም መንገድ የጀመሩት በጨለማ ከሆነ መድረሻዎ ሲነጋጋ ስለሚሆን ወደ ፀሐይ መውጫ ሄዱ ማለት ነው፡፡ መንጋቱ አይቀርምና፡፡ ሦስተኛው/ወሳኝ ነገር የአቅጣጫና የእንቅስቃሴ ግንዛቤዎ ነው፡፡ እንዴት ቢባል ዘወር ብለው ፀሐይን ቢመለከቷት እየተከተለችኝ ነው? እያሳደደችኝ ነው? ብለው መጠየቅዎ አይቀርም፡፡” አሉና አስረዷቸው፡፡
በሌላ ጊዜ ደግሞ እንደዚሁ እኒያ አዛውንት ንጉሡ ፊት ይቀርባሉ፡፡
ንጉሡ፡- ምነው ጢምዎ እንደዚህ ረዘመ - ሲሉ ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱም - የአገር ነገር ከብዶት - ሲሉ ይመልሳሉ፡፡
ቀጥሎም ንጉሡ፡- እስከ ዛሬ ካጋጠሙዎት መሪዎች የትኛውን ያደንቃሉ?- ብለው ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱም - ዐይኔን ሳልታወር በፊት ሊመራኝ የቻለውን ነው - ብለው ይመልሳሉ፡፡
ቆይተው ከስደት ሲመለሱ ንጉሡ ያስጠሯቸውና፤
የውጪ አገር ኑሮዎንና የ፣.አገር ውስጥ ኑሮዎትን ሲያወዳድሩት የቱን ወደዱት - ሲሉ ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱ - እሱማ እንደቆምኩበት ቦታ ይለያያል፡፡ እዚህ ስሆን ያንን እወደዋለሁ፡፡ እዚያ ስቆም ደግሞ ይሄንን እወድደዋለሁ፡፡
ከርመው ከርመው፣ ደግሞ ከስደት ሲመለሱ፤
ንጉሡ፡- ከስደት ምን ይዘህ ወደ አገርህ ተመለስህ? - ሲሉ ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱም - ንጉሥ ሆይ፤ ዱሮ ይዤ የወጣሁትን ችግር ይዤ ነው የተመለስኩት፡፡ ማንም የነካብኝ የለም፡፡ …አሉ ይባላል፡፡
*          *        *
  የስደት ቦቃ የለውም፡፡ በኢኮኖሚም ይሁን በፖለቲካ፣ ወይም በማናቸውም ማህበራዊ ችግር፤ ምንም ዓይነት ስም ብንሰጠው፣ አንዴ ከሀገር ከወጣን ስደተኞች ነን፡፡ ስለዚህም የስደትን ገፈት መቅመሳችን አይቀሬ ነው፡፡
“ከአገሩ የወጣ አገሩ እስኪመለስ
ቢጭኑት አህያ ቢለጉሙት ፈረስ”
       *    *     *
“ወይ አዲስ አበባ ወይ አራዳ ሆይ
አገርም እንደሰው ይናፍቃል ወይ”
        *   *  *  
“እረ ሰው እረ ሰው
ዐይኔን ሰው ራበው”
እኒህንና ሌሎችም በቅኔ ባኮ ውስጥ ያሉ ግጥሞች፣ የዚያው የስደት አባዜ አስረጆች ናቸው፡፡ ሁሉም ውስጣቸው የስደት ምሬት ቃና አላቸው፡፡ እነዚህ ላይ ዶናልድ ትራምፕ ሲጨመርባቸው፤ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ይሆናል፡፡ ከላይ በተረቱ ውስጥ እንዳየነው፤ “ዱሮ ይዤ የወጣሁትን ችግር ይዤ ነው የተመለስኩት” እንደተባለው ነው፡፡ ስደት የማንነት ጠላት ነው፡፡ ብዙ ነገሮችን ያስረሳል፡፡ የራሱ አጉይ - መነፅር አለውና አመለካከትን ያንጋድዳል፡፡ ጥንቃቄ ካልተደረገበት፣ ጠባይንም ያስለውጣል፡፡ “ዞሮ ዞሮ ከቤት፣ ኖሮ ኖሮ ከመሬት” መግባት አሌ አይሉት ሀቅ ነውና፣ ለዘመድ አዝማድ፣ ለወዳጅና ለሀገር ቁም ነገር ልሥራ ማለት ብልህነት ነው፡፡ ከራስ አልፎ ለወገን ማሰብ፣ ለወገን መትረፍ፣ ልብና ልቦና ላለው ሁሉ ታላቅ ተግባር ነው፡፡ በጎ አድራጎትን ማሰብ አያሌ ህፃናትን ለመታደግ በር ከፋች ነው፡፡ ለአያሌ እናቶች መድህን ነው፡፡ የርሀብን ስፋት፣ የድርቅን ብዛት ነግ - ሠርክ ብናወራው ሰቆቃው ውስጥ ላለው ህዝብ ዳቦ አይሆነውም፡፡ ድህነት ሲያወሩት ቢውሉ፣ ያው ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ እንደ ዋና ገብተው ካላዩት አይማሩትም፡፡ ውስጡ ሙስና እያለ፣ ውስጡ ፀረ-ዲሞክራሲነት እያለ፣ ውስጡ ኢ-ፍትሀዊነት እያጠጠ፣ ድህነትን ተረት እናደርጋለን ማለት የአፍ ወግ ብቻ ይሆናል፡፡ ፀሐፌ - ተውኔቱ፤ ድህነት በአፍ አይገባም ያለውን አለመዘንጋት ነው፡፡
ሀገራችን የጀግኖች ሀገር ለመሆኗ ዛሬ ብዙ ምስክር መቁጠር አያሻም፡፡ አድዋ ማግስት ላይ ቆሞ ይህን መጠየቅ የዋህነት ነው፡፡ ይልቁንም የትናንቱን ጀግንነት ለአሁኑ ትውልድ እንዴት እናስጨብጠው ነው ጥያቄው፡፡ ከዘመናዊነት ጋር የትናንቱን ጀግንነት እንዴት እናዋህደው ነው ጉዳዩ፡፡ ባህሉን ያልረሳና ከዓለም ጋርም እኩል የሚራመድ ጀግና ትውልድ እንዴት እንፍጠር ማለት ግዴታችን ነው፡፡ አጓጉል ትውልድ የአባቱን መቃብር ይንድ” እንዳይሆን ምን ዘዴ እንዘይድ እንበል፡፡ ከአንገት በላይ ሳይሆን ከአንጀቱ የሀገርን ጉዳይ የሚያይ ትውልድ እንዴት እናፍራ? ባህሉንና ግብረ ገብነቱን፣ ትምህርቱን አጥብቆና ጠንቅቆ፤ አውቆ እንዲጓዝ ምን ይደረግ? ካልኩ ካለፈው ራስ - ወዳድነት እንዴት እናላቀው? ያለፈ ታሪኩ ባለታላቅ ዝና፣ ነገው ግን ኦና (with glorious past but no future እንዲሉ ፈረንጆቹ) እንዳይሆን ምን እናድርግ? ወጣት የነብር ጣት በማለት ብቻ ወኔ አይጠመቅም፡፡ መራር ሀሞት ከመሬት አይበቅልም፡፡ በተግባራዊ ግንዛቤው፣ ንቃቱ፣ ብቃቱ እና ሽንጥን ገትሮ መንቀሳቀሱ፣ መኖሩን ቀርቦ መመርመር፣ ከሌለም ቀርቦ ማስተማር ያስፈልጋል፡፡ ለሀገሩ መኖሩን ማረጋገጥ ያስፈልጋል! ስለወጣቱ እኩል እሳቤ ካልኖረንና፤ እኛ ራሳችንም የጋራ ቤት እንዳለን ሳናስተውል መቻቻል ጠፍቶብን ከተናቆርን፤ የምናወርሰውም ያንኑ በቂምና በሸር የተሞላ ሀገር ነው፡፡ ያንኑ አፈ - ቅቤ ልቤ - ጩቤ ሥርዓት ነው፡፡ አንዱ ሲያልፍለት ሌላው ለመመቅኘት እንቅልፍ የሚያጣበትን ህይወት ነው፡፡ ዕድሜ ልካችንን፤ “ደስ አይበላችሁ ባለ ምጣዶች፣ ልንጋግረው ያሰብነውን አገነፋነው” እየተባባልን አንዘልቀውም! ቆም ብለን እናስብ!

 ድርቁን ተከትሎ አስከፊ ረሀብ ሊከሰት እንደሚችል ተመድ አስጠንቅቋል
               መንግሥት የእርዳታ ጥሪ ቢያቀርብም እስካሁን ምላሽ አላገኘም
               እስከ 15 ሺህ ብር ይሸጡ የነበሩ ከብቶች፣ 500 ብር ድረስ እየተሸጡ ነው
                              
    በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል የድርቅ አደጋ በመቶ ሺዎች የሚገመቱ ሰዎችን ያፈናቀለ ሲሆን ከሩብ ሚሊዮን በላይ ህፃናት ትምህርታቸውን እንዲያቋርጡ ውጪ ማድረጉንም የተባበሩት መንግስታት የእርዳታና የሰብአዊ ድጋፍ ድርጅት (UNOCHA) ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል በድርቅ ከተጎዱ አካባቢዎች አንዱ በሆነው የኦሮሚያ ክልል፣ ቦረና ዞን ያሉ አርሶ አደሮች በህይወት የተረፉ ከብቶቻቸውን በርካሽ ዋጋ እየሸጡ መሆኑን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
ድርቅ ባጠቃቸው የቦረና አካባቢዎች በጉዳዩ ላይ ጥናት በማድረግ ላይ የሚገኙ ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ በደህናው ጊዜ እስከ 15 ሺህ ብር ይሸጡ የነበሩ በሬዎች፤ በአሁን ወቅት ከ500 እስከ 1 ሺህ ብር ድረስ እየተሸጡ ሲሆን ከ500 እስከ 1 ሺህ 500 ብር ይሸጡ የነበሩ በጎችና ፍየሎች ደግሞ በ80 እና በ90 ብር እየተሸጡ ነው ተብሏል፡፡
ከብቶቹ በአብዛኛው በአካላዊ ቁመናቸው የተጎዱ በመሆኑ፣ ፈላጊ ስለሌላቸው አርብቶ አደሮቹ በርካሽ ዋጋ ለመሸጥ መገደዳቸውን ባለሙያዎቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡፡፡
የከብቶች ሞትም እንደቀጠለ መሆኑን የጠቆሙት አጥኚዎች በተለይ የመጠጥ ውሃ ችግሩ ተባብሶ መቀጠሉን ገልፀው፤ መንግስት በቦቴ ውሃ እያቀረበ ቢሆንም በበቂ መጠን አለመሆኑን አመልክተዋል፡፡
ወቅታዊ ሪፖርቱን ሰሞኑን ይፋ ያደረገው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በበኩሉ፤ በተለይ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል የሚሊዮኖችን ህይወት አደጋ ላይ ለጣለው ድርቅ መንግስትና የእርዳታ ለጋሽ ተቋማት ውሃና ምግብ በማቅረብ እየተረባረቡ ቢሆንም ከአደጋው አስከፊነት አንፃር በቂ አይደለም ብሏል፡፡
በድርቁ ምክንያት 228 ሺህ ህፃናት ትምህርት ማቋረጣቸውን ይፋ ያደረገው ሪፖርቱ፤ ከእነዚህ ውስጥ 183 ሺህ 090 የሶማሌ ክልል ህፃናት ሲሆኑ 44 ሺህ 571 የሚሆኑት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡ በሁለቱ ክልሎች ማለትም በኦሮሚያ በድርቁ ምክንያት 141 ት/ቤቶች፣ በሶማሌ ክልል 437 ት/ቤቶች በድምሩ 578 ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውን ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
ምግብና ውሃ ፍለጋ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ አባወራዎች ከቀዬአቸው መፈናቀላቸውን የጠቆመው የተመድ የእርዳታና ሰብአዊ ድጋፍ ድርጅት ሪፖርቱ፤ ከተፈናቀሉት ውስጥ 163 ሺህ ያህሉ ለትምህርት የደረሱ ህፃናት መሆናቸውን አመልክቷል፡፡ እነዚህን ተፈናቃይ ህፃናት ለ75 ቀናት ሊመመገብ 5.9 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግም ተገልጿል፡፡
በእርዳታ አሰጣት ደንብ ለአንድ ሰው በቀን ውስጥ 5 ሊትር ውሃ መቅረብ ያለበት ቢሆንም በአሁን ወቅት ለአንድ ሰው በቀን እየቀረበ ያለው በአማካይ 2.1 ሊትር ውሃ መሆኑን የተመድ ሪፖርት ጠቁሞ፤ የውሃ ክፍፍሉም ፍትሃዊ አለመሆኑንና ከወረዳ ወረዳ እንደሚለያይ አስታውቋል፡፡
በአጠቃላይ ለ5.6 ሚሊዮን የተረጂዎች 1 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ እርዳታ እንደሚያስፈልግና ይህ እርዳታ በአፋጣኝ ካልተገኘ ሁኔታው ወደ አስከፊ ረሃብ ሊቀየር እንደሚችል አሳስቧል፡፡
ተመድ መንግስት ከለጋሽ ድርጅቶች ጋር በመሆን የእርዳታ ርብርብ እያደረጉ ነው ቢልም መንግስት በበኩሉ፤ ለድርቁ አደጋ የእርዳታ ጥሪ ቢያቀርብም እስካሁን ምላሽ አለማግኘቱን አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አፍሪካን በተመለከተ ባወጣው ሪፖርቱ፣ ኢትዮጵያን ጨምሮ በድርቅ በተጎዱ፣ ከሠሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ ሃገራት፣ በአሁኑ ወቅት ከ20 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስቸኳይ የእርዳታ ርብርብ እንደሚፈልጉ አስታውቆ፤ አለማቀፉ ማህበረሠብ እጁን እንዲዘረጋ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

 በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016 ብቻ በአዲስ አበባ ከተማ ከ30 ሚ. ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው 20 አዳዲስ እጅግ ባለጸጋ ሚሊየነሮች መፈጠራቸውን “ናይት ፍራንክ” የተባለ አለማቀፍ የሃብት ጥናትና አማካሪ ተቋም ሰሞኑን ባወጣው የ2017 አለማቀፍ የሃብት ስርጭት አመታዊ ሪፖርት አስታውቋል፡፡ ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ የሆነው ተቋሙ፤ በ89 የአለማችን አገራት ውስጥ በሚገኙ 125 ከተሞች ላይ ያደረገውን ጥናት መሰረት በማድረግ፣ ለ11ኛ ጊዜ ባወጣው ሪፖርቱ፤ በአዲስ አበባ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው አዳዲስ ሚሊየነሮች ቁጥር ከአንድ አመት በፊት ከነበረው በ10 በመቶ በማደግ፣ በ2016 አመት 20 መድረሱን የጠቆመ ሲሆን፣ ይህ ቁጥር በመጪዎቹ ዘጠኝ አመታት በእጥፍ በማደግ 40 ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት አስታውቋል፡፡  
በአዲስ አበባ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016፣ ከ1 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ሰዎች ቁጥር 800 መድረሱን የገለጸው ሪፖርቱ፣ ከ10 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ሚሊየነሮች ቁጥር ደግሞ 40 ደርሷል ብሏል፡፡
ሪፖርቱ በአፍሪካ አህጉር በመጪዎቹ ዘጠኝ አመታት ከፍተኛ የሚሊየነሮች ቁጥር እድገት ይመዘገብባቸዋል ብሎ የጠቀሳቸው አገራት፡- ኢትዮጵያ፣ ሞሪሽየስ፣ ታንዛኒያ፣ ኡጋንዳ፣ ኬንያ እና ሩዋንዳ ሲሆኑ፣ በመላው አለም ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ሰዎች ቁጥር በዘጠኝ አመታት ጊዜ ውስጥ በ43 በመቶ ያድጋል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጧል፡፡
ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በመላው አለም ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው 6 ሺህ 340 አዳዲስ ሚሊየነሮች መፈጠራቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ይህን ያህል የሃብት መጠን ያላቸው የአለማችን ሚሊየነሮች አጠቃላይ ቁጥር 193 ሺህ 490 መድረሱንም አክሎ ገልጧል፡፡
በሚሊየነሮች ቁጥር ከአለማችን አገራት ከፍተኛውን ጭማሪ ታስመዘግባለች ተብላ የምትጠበቀው ቬትናም ስትሆን፣ በአገሪቱ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ዜጎች ቁጥር በዘጠኝ አመታት ጊዜ ውስጥ በ170 በመቶ ያድጋል ተብሎ እንደሚገመትም ተነግሯል፡፡

Monday, 27 February 2017 08:14

የቢዝነስ ጥግ

- የእውነተኛ ሥራ ፈጣሪ የህይወት ዓላማ ዓለምን መለወጥ ነው፡፡
  ቢል ድራይቶን
- የንግድ ሥራ ፈጣሪ ከሆንክ፣ ከተለመደው ወጣ ብለህ ማሰብ አለብህ፡፡
  ዋይኔ ሮጀርስ
- ልጄ አሁን “ሥራ ፈጣሪ” ነው፡፡ ሥራ ከሌለህ እንደዚያ ነው የሚሉህ፡፡
  ቴድ ተርነር
- ሦስት ጊዜ የንግድ ሥራ ፈጥሬአለሁ፡፡ ሦስት ኩባንያዎችንም መስርቼአለሁ፡፡
  ማርክ አንድሬሰን
- ሁሉም ሰው ሥራ ፈጣሪ ሊሆን ይችላል፤ ሀብታም ሥራ ፈጣሪዎች የሚሆኑት ግን በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
  ሮበርት ኪዩሳኪ
- ዛሬ በንግድ ሥራ ፈጣሪነት ዘርፍ ብዙ አማራጮች አሉ፡፡
  ኢክላስ ዜንስትሮም
- ከራሴ ጋር እንዲህ ስል ተማከርኩ፡- “የንግድ ሥራ ፈጠራን እያስተማርኩ ነው፤ ስለዚህ ራሴ የንግድ ስራ ፈጣሪ መሆን አለብኝ”
  ዳን ሼችትማን
- ዶናልድ ትራምፕ የንግድ ሥራ ፈጣሪ ነው፡፡
  ስቲቭ ባኖን
- የንግድ ሥራ ፈጣሪ መሆን ከባድ ነው፡፡ በጣም በጣም ከባድ፡፡
  ዴቪድ ኤስ.ሮዝ
- የንግድ ሥራ ፈጠራ፤ በአስቸጋሪ ኢኮኖሚ ውስጥ ህይወታችንን የምንቆጣጠርበት መንገድ ነው፡፡
  ሎርል ግሬይነር
- ሥራ ፈጣሪዎች በሳምንት 40 ሰዓት መስራትን ለማስቀረት፣ በሳምንት 80 ሰዓት ለመስራት ፈቃደኞች ናቸው፡፡
  ሎሪ ግሬይነር
- የንግድ ሥራ ፈጠራ፤ ለችግሮች አትራፊ መፍትሄዎች የመፈለግ ጥበብ ነው፡፡
  ብሪያን ትሬሲ