Administrator

Administrator

 በጋዜጠኛ ደራሲና የቋንቋ መምህር ደሳለኝ ማሰሬ የተሰነደው ‹‹የፍቅር ሳቅ›› የግጥም ስብስብ መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሀፉ ወጣቱን መሰረት ባደረጉ ማህበራዊ፣ ባህላዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ከ60 በላይ ግጥሞችን ማካተቱ የመፅሀፉ አዘጋጅ ጋዜጠኛ የቋንቋ መምህርና ደራሲ ደሳለኝ ማስሬ
ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በ96 ገፅ የተቀነበው መፅኀፉ በ40 ብር ከ50 ሳንቲም እየተሸጠ ሲሆን ደራሲው በቅርቡ ለንባብ የሚያበቃው የቋንቋ መፅሀፍ በመጠናቀቅ ላይ መሆኑንም ገልጿል፡፡

 70ኛው ግጥምን በጃዝ ረቡዕ ግንቦት 2 ቀን 2009 ዓ.ም ከምሽቱ 12 ሠዓት ጀምሮ በራስ ሆቴል ይካሄዳል፡፡
በዚህ ምሽት ላይ የስነፅሁፍ ምሁሩ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ገጣሚ ተርጓሚና ጋዜጠኛ ነብይ መኮንን፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብት፣ ፍቃዱ ተ/ ማርያም፣ ይታገሡ ጌትነት እና ኤልያስ ሽታሁን ይሣተፋሉ ተብሏል፡፡ በእለቱ በሽመልስ አበራ እና እታፈራሁ መብራቱ የተዘጋጀ አጭር ተውኔት እንደሚቀርብም ተጠቁሟል፡፡

  አራቱ የ1980ዎቹ ኮከብ ድምፃውያን ከሮሃ ባንድ ጋር ዘፈኖቻቸውን ያቀርባሉ

    ግንቦት 12ቀን 2009 ዓ.ም በግዮን ሆቴል ይካሄዳል በተባለው በዚህ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ በወቅቱ ‹‹ሁሉም ቢተባበር›› በሚለው የጋራ ዜማቸው ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፉትና የ1980ዎቹ አራት ምርጥ ድምፃውያን፡- አረጋኸኝ ወራሽ፣ ፀሐዬ ዩሐንስ፣ ፀጋዬ እሸቱና ንዋይ ደበበ እንደሚሳተፉበት የኮንሰርቱ አዘጋጅ ከትናንት በስቲያ በአዚማን ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ገልፀዋል፡፡
የኮንሰርቱ አዘጋጅ ታምር ማስታወቂያ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን መለሰ እንደገለፀው፤ የሙዚቃ ኮንሰርቱ በአገራችን ዘመናዊ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ሥፍራ የነበራቸው ድምፃውያን ከሮሃ ባንድ ጋር በመሆን ያን ዘመን የሚያስታውሱ ሥራዎችን በሺዎች ለሚቆጠሩ አድናቂዎቻቸው ያቀርባሉ፡፡
የሙዚቃ ኮንሰርቱ ከተለመደው የሙዚቃ ኮንሰርት የተለየ መሆኑን የገለፀው አቶ ሰለሞን፤ ከእነዚህ ጉዳዮች መካከል በኢትዮጵያ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ‹‹ወርቃማው ዘመን›› እየተባለ በሚጠራው የ1980ዎቹ ዓመታት ያለፉ በዘመኑ ምርጥ የተባሉ የሙዚቃ ሥራዎችን ሲያጣጥሙ የነበሩ አድናቂዎች ከሚወዷቸው ድምፃውያን ጋር የሚገናኙበትን እድል የሚፈጥር መሆኑ ዋንኛው ነው ብሏል፡፡ ድምፃውያኑ ከሮሃ ባንድ ጋር በጋራ በሚያቀርቡት በዚህ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ ከ10ሺ በላይ ታዳሚዎች ይገኙበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ከኮንሰርቱ ገቢ 10 በመቶ አገር በቀል ለሆኑ የእርዳታ ድርጅቶች ለመስጠት መታሰቡንም አቶ ሰለሞን ተናግረዋል፡፡
ከኮንሰርቱ መጠናቀቅ በኋላ የኢትዮጵያን ዘመናዊ ሙዚቃ ታሪክ የሚያስታውስና በተለይም በ1970ዎቹና 80ዎቹ መጨረሻ ድረስ ባለው ጊዜ ላይ ትኩረቱን አድርጎ የሚዘጋጅ የአንድ ሰዓት ትኩል ዘጋቢ ፊልም እንደሚዘጋጅና ሲዲውም ከኮንሰርቱ መጠናቀቂያ በኋላ በሚዘጋጅ የምስጋና ፕሮግራም ላይ እንደሚመረቅ የኮንሰርቱ አዘጋጆች በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሚዘጋጀው ኮንሰርት ከተጠናቀቅ በኋላ በ3 ዋና ዋና የክልል ከተሞች ተመሳሳይ የሙዚቃ ኮንሰርት ለማዘጋጀት ዕቅድ መያዙንም አቶ ሰለሞን ተናግረዋል፡፡

   · “ይሄ ማዕከል ተሰርቶ በነጋታው በሞትኩ” (አርቲስት ፋንቱ ማንዶዬ)
                      · “በሁሉም ከተሞች የአረጋውያን ማዕከላት ይገነባሉ”

          ሜሪ ጆይ የልማት ማህበር የዛሬ 8 ዓመት የአረጋዊያን ሁለገብ አገልግሎት ማዕከል ለመገንባት በሀዋሳ ከተማ 6 ሺህ ካ.ሜ ቦታ የተረከበ ሲሆን በ2003 ዓ.ም ግንባታው ተጀምሮ ዘንድሮ ተጠናቅቋል፡፡ የምረቃ ስነ-ስርዓቱ በመጪው ግንቦት 12 ይካሄዳል ተብሏል፡፡ የዛሬ ሁለት ሳምንት ቅዳሜ ከተለያዩ ሚዲያዎች የተውጣጡ ጋዜጠኞች ማዕከሉን ከጎበኙ በኋላ የድርጅቱ መስራችና ዋና ዳይሬክተር ሲስተር ዘቢደር ዘውዴ፣ ጋዜጣዊ መግለጫም ሰጥተዋል፡፡
   በስፍራው የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ስለ ማዕከሉ ግንባታ አጠቃላይ ሂደት፣ ለአረጋውያን ስለሚሰጣቸው አገልግሎቶች፣ በድሬደዋና በአርባ ምንጭ ሊገነቡ ስለታቀዱት የአረጋዊያን ማዕከላትና ተያያዥ ጉዳዮች
አንስታ ሲስተር ዘቢደርን አነጋግራቸዋለች፡፡

    ማዕከሉን ገንብቶ ለማጠናቀቅ ምን ያህል ጊዜና ገንዘብ ወሰደ?
በጎ ፈቃደኞች በሙያቸው የለገሱትን ገንዘብ ሳይጨምር 12.5 ሚ. ብር ወስዷል፡፡ የህንፃ ዲዛይኑን አርክቴክት አሰፋ ገበየሁ በነፃ ነው የሰሩልን። በወቅቱ በነበረው ገበያ ዲዛይኑ 350 ሺህ ብር የሚያወጣ ነበር፡፡ ህንፃው ተጀምሮ እስኪያልቅ የክትትልና የማማከር ስራውን ለ6 ዓመት የሰሩልን ወጣቶች፣ MDC የተባለ የህንፃ ስራ አማካሪዎች ናቸው፡፡ ስራ አስኪያጁ ዳዊት ይባላል፡፡ እነዚህ ልጆች ከማማከር ባለፈ የግንባታ እቃ ሲያልቀብን ከራሳቸው እያቀረቡ በነፃ ሲረዱን ቆይተዋል፡፡ የእነዚህ ልጆች እገዛ በገንዘብ ሲሰላ ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ይሆናል። የሀዋሳ ከተማ የግንባታ እቃ ባለ ሱቆች፣ከሴራሚክ ጀምሮ የተለያየ ቁሳቁስ ድጋፍ አድርገውልናል፡፡ የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን፣ አርቲስቶች፣ ባለሀብቶችና ባለሙያዎች እገዛ ባይጨመርበት ኖሮ፣ አጠቃላይ ህንፃው ከ20 ሚ. ብር በላይ ይፈጅብን ነበር፡፡ ማእከሉ ከሚለይባቸው ዋናውና አንዱ በኢትዮጵያዊያን መገንባቱ ነው። በዚህ የብዙ ኢትዮጵያዊያን አሻራ ባረፈበት ህንፃ መጠናቀቅ የብዙ ሰዎች ደስታ ተገልጿል፡፡ ብዙ ተስፋ አስቆራጭ ጊዜያትን አሳልፈን ነው ያጠናቀቅነው፡፡
ማዕከሉ ለአረጋዊያን መጠነ ሰፊ አገልግሎት ይሰጣል ተብሏል፡፡ እስቲ ዋና ዋናዎቹን ይንገሩን …
ከመጀመሪያው ጀምሮ ማዕከሉን ለመገንባት ስንነሳ፣ አንድ አረጋዊ ምን ያስፈልገዋል የሚለውን አጥንተን ነው፡፡ ስለዚህ የተሟላ ክሊኒክ አለው፡፡ ምግብ ያስፈልጋቸዋል፤ ለዚህም ካፍቴሪያ አላቸው። ቤተ መፅሀፍት፣ ኮምፒዩተር ላብ፣ ዶክሜንቴሽን ማዕከል፣ ጌም ሴንተር፣ ቴሌቪዥን መመልከቻ ክፍል አለው፡፡ ሲደክማቸው የሚያርፉበት የወንድና የሴት ክፍሎችም አሉት፡፡ ብቻ አንድ አረጋዊ ያስፈልገዋል ተብሎ የሚታሰበው ነገር ሁሉ ተሟልቶለታል፡፡
የማዕከሉ ክፍሎች በተለያዩ ባለሀብት ድርጅቶች ስም የተሰየሙበት ምክንያት ምንድን ነው?
እንግዲህ “50 ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክም ነው፤ ለ50 ሰው ጌጡ ነው” ይባላል፡፡ እኛም ህንፃው ተገንብቶ ራዕያችን እንዲሳካ፣አንድ ሰው ወይም አንድ ድርጅት ገንዘብ እንዲሰጠን ከማስጨነቅ፣  የተለያዩ ባለሀብቶችና የሀዋሳ ከተማ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ስም በመሰየም ክፍሎቹን በገንዘብ እንዲደግፉ ነው ያደርገነው፡፡ ለምሳሌ ጂምናዚየሙን  - ይርጋለም ኮንስትራክሽን፣ ሻወር ቤቱን - ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኙ የማሪያም ማህበርተኞች (በአምስት ሺህ ዶላር)፣ ሴራሚኩን - የሀዋሳ ከተማ ሴራሚክ ሱቆች፣ ሰርቶ ማሳያውን አንዱን ክፍል - ንፋስ ስልክ ቀለም ፋብሪካ፣ ሌላኛውን አንበሳ ጫማ፣---- ስፖንሰር አደረጉ፡፡
በሌላ በኩል ሁለቱንም የማረፊያ ክፍሎች፣ ናርዶስ ወ/ሰንበት የተባለች ዱባይ የምትገኝ ባለሀብት፣ ሱቁን - የጂት መቻል የተባለ የሀዋሳ ነዋሪ፣ በሱቁ አንዳንድ ነገር ለሚሰሩበት ሶስት ሲንጀርና 32 ሺህ ብር - አበባ የተባለች ግለሰብ ለግሳለች፡፡
ክሊኒኩን ሃዋሳ የሚገኘው ያኔት ሆስፒታል ስፖንሰር አድርጓል፡፡ በሳምንት ሁለት ቀን በሆስፒታሉ ያሉ ስፔሻሊስቶች፤ አረጋዊያንኑን እዛው ወስደው ሊያክሙልን ቃል ገብተዋል፡፡ አለነታላንድ የተባለው የንግድ ድርጅት - መታሻ ክፍሉን፣ ጁፒተር ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ - አንዱን መታሻ ክፍል፣ ታካሚዎች ቁጭ ብለው ህክምና የሚጠብቁበትን ክፍል - ዋሪት ሙሉ ጥላ (አቶ ለገሰ ዘሪሁን) ስፖንሰር ሲያደርጉ፣ ሎቢውን በ360 ሺህ ብር ዮድ አቢሲኒያ አድርገውታል፡፡ ኢታብ ሳሙና በ260 ሺህ ብር - ካፍሬቴሪያውን ስፖንሰር አድርገዋል፤ የማናጀሩ ቢሮ፣ የፀሀፊው፣ የበጎ ፍቃደኞቹ ቢሮና ሌሎችም በስፖንሰሮች ተሰርተው በስማቸው ተሰይሟል፡፡ አጥሩን እንኳን የከተማው ከንቲባ ፅ/ቤት ነው፣በ900 ሺህ ብር ያጠረው፡፡ ግቢውን እያስዋበ ያለውም የከተማው ማዘጋጃ ቤት ነው፡፡ ጋትስ አግሮ ኢንዱስትሪ፤ቤተ መፅሀፍቱን ስፖንሰር ሲያደርጉ ሌዊ ሪዞርት በበኩሉ፤ ኮምፒዩተር ላቡንና ዶክሜንቴሽን ክፍሉን ስፖንሰር አድርጓል፡፡ ብቻ በአጠቃላይ ለዚህ ማዕከል እውን መሆን፣ ቅን ልብ ያላቸው በርካታ ግለሰቦችና ተቋማት ከፍተኛ ትግል አድርገዋል፡፡ ይሄ እንግዲህ የሚዲያውም አስተዋፅኦ ታክሎበት ነው ለዚህ የበቃው፡፡ ሁሉንም እናመሰግናለን፡፡
ማዕከሉ ስራ ሲጀምር ምን ያህል አረጋዊያንን ያስተናግዳል?
እያንዳንዱ አገልግሎት ቢያንስ መቶ ሰው ያስተናግዳል፡፡ ጠቅላላው አገልግሎቱ ተጠቃሚ ያደርጋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ቀደም ብዬ እንዳልኩት፤ ይህን ማዕከል ልዩ የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንደኛው በኢትዮጵያዊያን ብቻ መሰራቱ ሲሆን ሁለተኛው በተለያዩ ስፖንሰር አድራጊ ባለሀብቶችና ግለሰቦች እያንዳንዱ ክፍል መሰየሙ ነው፡፡ ሶስተኛው በሃዋሳ ከተማ የሚገኙ የአልጋ ቁራኛ አረጋዊያንን እያሰሰ፣ ምግብ ለሌላቸው ምግብ ያቀርባል፤ ይህን የሚሰሩ በጎ ፈቃደኞን አሰልጥነናል፡፡ በሌላ በኩል በቀደመውና በአሁኑ ትውልድ መካከል ክፍተት እንዳይኖር አረጋዊያን ለወጣቱ ልምዳቸውንና፣ እውቀታቸውን የሚያካፍሉበት አዳራሽ ከማዕሉ ጀርባ ይገነባል። በኪነ ጥበብ፣ በታሪክና መሰል ጉዳዮች ዙሪያ በመወያየት ወጣቶች አገራቸውን እንዲያውቁ ይደረጋል፡፡ ኢትዮጵያውያንን አስተባብረን  ነው አዳራሹን የምንገነባው፡፡ አዳራሹ ከ500 ሰው በላይ የሚይዝ ትልቅና ዘመናዊ ነው የሚሆነው። ለሰርግ፣ ለጉባኤና ለስብሰባዎች እየተከራየ፣ ማዕከሉን ይደግፋል የሚል እቅድ ይዘናል። ሌላው ጥናትን መሰረት ያደረገ ዘላቂ የአረጋዊያን ድጋፍ ለመስጠት፣ ‹‹ኮሚዩኒቲ ሰርቪስ›› በሚለው ዲፓርትመንታቸው በኩል ከሃዋሳ ዩኒቨርስቲ ጋር በንግግር ላይ ነን፤ ይሄም የሚሳካ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ የሙያና ቴክኒክ ትምህርት ቤቱ፤ ለ30 አረጋዊያን በነፃ ስልጠና ሰጥቶልናል፡፡ ሜሪ ጆይ፤ ቫይረሱ በደማቸው ያለባቸው አረጋዊያን ማህበርን አቋቁሟል፤ ስልጠናውም ቅድሚያ የተሰጠው ለእነሱ ነው፡፡ ከስልጠናው በኋላ ስራ እየሰሩ ራሳቸውን እንዲችሉ አድርገናቸዋል፡፡
ማዕከሉ ሥራ ሲጀምር ዓመታዊ በጀቱ ምን ያህል ይሆናል?
አመታዊ በጀቱ 1.5 ሚ ብር ነው፡፡ ይህንን ገንዘብ ከባለሀብቶች፣ ከታዋቂ አርቲስቶች፣ ከመንግስትና ከንግዱ ማህበረሰብ ነው የምናሰባስበው፡፡ አሁን ያቀድነው ለአንድ አመት የሚሆነውን በጀት ዘግተን ለመጀመር ነው፤ ማሰባሰብም ጀምረናል፡፡ ለምሳሌ ግርማዬ ፈረደ የተባሉ ባለሀብት ወይም ሲጂኤፍ ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ - 130 ሺህ ብር፣ ቢጂአይ ኢትዮጵያ - 300 ሺህ ብር ለመነሻ የሰጡን ሲሆን የደቡብ ክልል መስተዳደር 750 ሺህ ብር ሊሰጠን ቃል ገብቶልናል፡፡
ሜሪ ጆይ በአርባ ምንጭና በድሬደዋ ተመሳሳይ ማዕከላትን ለመገንባት ከዓመታት በፊት እንቅስቃሴ መጀመሩን አውቃለሁ፡፡ ከምን ደረሰ?
በሁለቱም ቦታዎች እንቅስቃሴ ጀምረናል፡፡ በአሁኑ ወቅት አርባ ምንጭ ላይ ወደ 2 ሚ. ብር አለን፡፡ ድሬደዋ እንቅስቃሴው በጣም ሄዷል፤ እንዲያውም ፀደቀ የተባለ ወጣት ባለሀብት፣ 600 ሺህ ብር አውጥቶ አጥሩን አጥሮታል፡፡ እዛ የምንሰራው ከዳዊት አረጋዊያን ማህበርና ከከተማው ፅ/ቤት ጋር ነው፡፡ በቅርቡ ግንባታ ይጀመራል፡፡ ግንባታው የሚካሄደው በ5 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ ነው፡፡ የአርባ ምንጩን ግንባታ ለመጀመር ጠረጋ ተጀምሯል፡፡ የአርባ ምንጩ በ10 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፍ ነው፡፡ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እነዚህም ማዕከላት እንደ ሀዋሳው እውን ይሆናሉ፡፡ ሶስቱ ማዕላት ስራ ላይ ሲሆኑ ለየከተማዎቹ አረጋዊያን እያንዳንዳቸው በወር ለ5 ሺህ ሰው አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ በአጠቃላይ በወር 15 ሺህ አረጋዊያን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡
ሜሪ ጆይ ዋና ፅ/ቤቱ ያለው አዲስ አበባ ነው። በሌላ በኩል ታዋቂና አንጋፋ አርቲስቶች በበጎ ፍቃደኝነት የሚደግፉት ነው፡፡ ሁላችሁም ደግሞ አረጋዊ ወደመሆኑ እየሄዳችሁ ነው፡፡ መጀመሪያ ለራሳችሁ ማረፊያ አዲስ አበባ ላይ ማዕከል ሳታቋቁሙ እንዴት ወደ ክልል ሄዳችሁ?
መጀመሪያ አዲስ አበባ ላይ ለመገንባት ነበር እኮ እንቅስቃሴ የጀመርነው፡፡ ቦታ አጥተን ነው፤ ለአዲስ አበባ የመደብነውን 2 ሚ. ብር ይዘን ሀዋሳ የሄድነው። ቦታ ጠይቀን በጣም ረጅም ጊዜ ሲፈጅብን ሀዋሳ ሄደን፣ አቶ ሽፈራው ሽጉጤን ስንጠይቅ፣ “ይሄ ተገኝቶ ነው” ብለው፣ በ10 ቀናት ውስጥ ነው ያየሽውን አይን የሆነ ቦታ የሰጡን፡፡ ቦታው በዛን ጊዜ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተከልክሎ ነበር፡፡ አቶ ሽፈራው ግን ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ተነጋግረው፣ በ10 ቀናት ውስጥ ካርታ አገኘን፤ ይሄ ሞራል ሰጠን። የአዲስ አበባን ብር ይዘን፣ እዛ ጀመርን፤ ይሄው ለመጠናቀቅ በቃ፡፡
አሁንስ የአዲስ አበባውን ማዕከል ለመገንባት የቦታው ጉዳይ ተስፋ ሰጪ ነው?
አዎ መገንባቱ አይቀርም፤ ካልሆነ ሜሪ ጆይ የራሱ ቢሮ ግቢ ውስጥም ቢሆን በጣም ዘመናዊ ማዕከል ይገነባል፡፡ እንዳልሺው ያው እኛም ወደ አረጋዊነቱ እያመራን በመሆኑ ነገ ማረፊያ ያስፈልገናል፡፡ ለአዲስ አበባ አረጋዊያንና ለራሳችን ማዕከሉን ለመገንባት፣ ከአርቲስት በጎ ፈቃደኞቻችንና አጋሮቻችን ጋር በምክክር ላይ ነን፡፡
ከብዙ ውጣ ውረድና ፈተና በኋላ ማዕከሉ ተጠናቅቆ ማየት ምን ዓይነት ስሜት ይፈጥራል?
በጣም ደስ ብሎኛል፤ ያው አንዳንዴ ደስታን በቃላት መግለፅ ያስቸግራል፤ እንደውም አርቲስት ፋንቱ ማንዶዬ ለዚህ ማዕከል ገንዘብ ለማሰባሰብ በሚደረገው እንቅስቃሴ ብዙ ፈተና ገጥሞታል። ግማሹ እያለ የለም ሲያስብለን፣ ሌላው በሩን ሲዘጋብን እሱ፣ ብዙ ችግር ከእኔ ጋር አሳልፏል። መጨረሻ ላይ የምንሰራበት ብር ሁሉ አጥተን፤ ‹‹እንደው ይሄ ማዕከል ተሰርቶ በነጋታው በሞትኩ›› ብሎ ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ትልቅ ነው። አንዳችንም በቁጥር ሳንጎድል ማዕከሉ ተጠናቀቀ። ሲጀመር የነበራችሁ ጋዜጠኞች፣ ባለፈው ቅዳሜ ቦታው ላይ ተገኝታችሁ በማዕከሉ ጋዜጣዊ መግለጫ ስሰጥ፣ከምቆጣጠረው በላይ የሆነ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ በመጨረሻ ለዚህ ህልም እውን መሆን ከፍተኛ ድርሻ ያላቸውን አርቲስቶች፤ የሀዋሳ ከተማ የመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ ነጋዴዎች፣ በአዲስ አበባና በውጭ የሚገኙ ባለሀብቶችና ግለሰቦች፣ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶችና መገናኛ ብዙሀን ትልቅ ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ አብረውን የደከሙትን ሁሉ ብድራታቸውን ፈጣሪ ይክፈላቸው እላለሁ፤ አመሰግናለሁ፡፡ “ይቻላል” የሚለውን መንፈስ አዳብረናል፤ አይደለም በሶስት ከተሞች በአገራችን በሁሉም ከተሞች የአገር ባለውለታዎች የሚዝናኑበት፣ የሚታከሙበት፣ የሚጨዋወቱበት ማዕከላት ይገነባሉ፡፡

  በጥንት ዘመን የነበረ አንድ ንጉሥ ታላላቅ፣ ጠበብት፣ መኳንንት፣ መሣፍንት እንዲሁም የጦር ኃይል አባላትን ጨምሮ ህዝቡን ሰበሰበና አገር ለማዳንና ህልውናዋ ተጠብቆ እንድትቆይ ወሳኝ እኔ ነኝ የሚል እጁን ያውጣና ምክንያቱን ያስረዳኝ አሉ፡፡
በመጀመሪያ የጦር አበጋዙ ተነስቶ፤
“አገር የማድን፣ የአገርን ህልውና የማስጠብቅ እኔ ነኝ” አለ፡፡
ሁለተኛ የተነሳው ምሁሩ ነበር፤
“ያለ እኔ ዕውቀት አገር ደህንነቷና ህልውናዋ አይጠበቅም፡፡ ምንም ነገር ስትሰሩ፣ እኔን ያማክሩ አለ፡፡ ስለ ጦር መሳሪያም ቢሆን መሰረቱ የእኔ እውቀት ነው!” አለ፡፡
ሦስተኛው ገበሬው ነው፡፡
“እኔ ካላመረትኩ ሁሉም ከንቱ ነው ንጉሥ ሆይ፡፡ ስለዚህ በልተው ካላደሩ፣ ምንም አይሰሩ!” አለ፡፡
ነጋዴው ተነሳ፡-
“የጦር መሳሪያውንም፣ የምሁራኑንም የምርምር ዕቃ፣ የገበሬውንም ምርት የሚያንቀሳቅሰው የእኔው የንግድ ሥራ ነው! በእኔ ኃይል ነው የአገርን ደህንነትና ህልውና የሚያቆዩት ንጉሥ ሆይ!” አለና ተቀመጠ፡፡
የቢሮ ኃላፊው እጁን አውጥቶ ተነሳና፤
“ንጉሥ ሆይ! የተናገሩት ሁሉ ዕውነት ነው፡፡ ነገር ግን የጽህፍት ሥራና የቢሮክራሲ ደም - ሥር ካልታከለበት ከንቱ ነው፡፡ የእኔን ቢሮክራሲ የማያከብር ዋጋ አይኖረውም!”
የጥበብ ሰው ተነስቶ - “አገርን የሚያሽር የጥበብ ሥራ ነው! ምንም ነገር ተነስቶ ጥበብ ካልተጨመረበት ዐይን አይገባም፡፡ ህይወት አይኖረውም!” አለ፡፡
የፋይናንስ አላፊው፤
“ንጉሥ ሆይ! ምንም አያሳስብም፡፡ ያለ ሂሳብ፣ ያለ ፋይናንስ ማንም የትም አይንቀሳቀስም! እኔ ሂሳብ ከተቆጣጠርኩ፤ አገር አማን ናት!” አለ፡፡
በመጨረሻ አንዲት ምስኪን ሴት ተነስታ፡- “ንጉሥ ሆይ! ምንም ተባለ ምን፣ ወሳኙ ፍቅር ነው፡፡ ፍቅር ነው ገዢው!” አለች፡፡
ንጉሡ አሰቡ አሰቡና፤ “ያለ ፍቅር ምንም ነገር ከንቱ ነው፡፡ አማካሪዬ ትሆኛለሽ” አሉና ደመደሙ፡፡
*           *        *
“እስከ ዛሬ ጥሩ ጦርነት አልነበረም፡፡ መጥፎ ሰላምም ታይቶ አያውቅም!” ይላል ፍራንክሊን፡፡ ታላቅ ጦርነት አንድ አገር ላይ ሦስት አሻራ ትቶ ያልፋል፡-
ሀ. የአካል ጉዳተኞች ሠራዊት
ለ. የሐዘንተኞች ሠራዊት
እና     ሐ. የሌቦች ሠራዊት
የጀርመናውያን ተረት
ይሄ ሁሉ የፍቅር መጎናፀፊያ በሌላት አገር የሚከሰት ነው፡፡ ከቤተሰብ እስከ ህብረተሰብና እስከ ጎረቤት አገር ፍቅር ከሌለ የሚከሰት ብዙ ጎዶሎ ሥፍራ አለ፡፡ ያንን ለመሙላት የሞቀ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡ ጦር፣ ትምህርት፣ ምርት፣ ንግድ፣ ቢሮክራሲ፣ ጥበብ፣ ፋይናንስ ወዘተ … ሁሉም የፍቅር ተገዢ መሆን አለባቸው - አለዛ ሰላም አይኖርም!
የዓለም ኢንፎርሜሽን ቀን እናከብራን፡፡
የፍትሕ ቀን እናከብራለን፡፡
የፕሬስ ቀን እናከብራለን፡፡
የአረጋውያን ቀን እናከብራለን፡፡
የወጣቶች ቀን እናከብራለን፡፡
የቫላንታይን ቀንም እናከብራን፡፡
የእጅ መታጠብ ቀንም እናከብራለን!
ምኑ ቅጡ! አያሌ የምናከብራቸው ቀናት አሉ፤ ይኖራሉም፡፡ ወደንም ይሁን ሳንወድም! የዓለምም ይሁን የአገር! ወጣም ወረደ፤ ሁሉም ፍቅር ይፈልጋሉ፡፡ ፍቅሩን በዛ አድርጎ ይስጠን!
ክፉ ክፉውን በማሰብ አገር አናድንም፡፡ መግባባት፣ መናበብ፣ መቀራረብ፣ ውዝግብን ከየሆዳችን ማውጣት፣ ለመፋቀር መዘጋጄት … የአገር ፍቅር መሰረት ነው፡፡ የጀግንነት ምልክት ፍቅርን መላበስ ነው!
ለወታደሩ ፍቀር ይስጠው፡፡ ለምሁሩ ፍቅር ይስጠው፡፡ ለሂሳብ አዋቂው ፍቅር ይስጠው፡፡ ለነጋዴው ፍቅር ይስጠው! ለጥበብ ሰው ፍቅር ይስጠው! አገር በፍቅር ትድን ዘንድ ለሁላችንም ፍቅር ይስጠን፣ ብርታት እና ፅናቱን ይስጠን!
ኮስተር ብለን ካሰብን ምርት ያለ ፍቅር አይመጣም፡፡ ዕድገት ያለፍቅር አይመጣም፡፡ የመንፈስ ተሐድሶ ፍቅርን ይሻል፡፡ ለውጥ ፍቅርን ይሻል፡፡ A change is equal to rest የሚለው የአይንስታይን አባባል መለወጥ ማረፍ ነው እንደማለት ነው፤ ትርጉሙ እያደር ሊገባን ግድ ነው፡፡ እረፍት የሰላም መደላድል ነው፡፡ ለውጡ እየገተባን፣ ለአዲሱ ሁኔታ ተገዢ መሆንን ይጠይቃል! Resist conservatism! እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ፡፡ “ወግ - አጥባቂነት ይውደም” የሚለው የዱሮ መፈክር ይበልጥ ይገልጠው ይሆናል! መንገዶች ሁሉ ወደ ለውጥ ያመሩ ዘንድ ዐይናችንን እንግለጥ!!
ለውጥ ፍቅር ይፈልጋል፡፡ ምነው ቢሉ ፍቅር ያላት አገር ሽለ-ሙቅ ናት (Fertile) ወላድ ናትና! ምርታማ ናትና! ለዚያ ያብቃን!

የድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) “ኢትዮጵያ” የተሰኘው 5ኛ ዓልበም ባለፈው ረቡዕ ከ50 ብር እስከ 100 ብር መሸጡ ታውቋል፡፡
አልበሙን በ10 ዶላር ለኢንተርኔት ሽያጭ ያቀረበው “cdbaby” የተሰኘው ድረ ገፅ በበኩሉ፤ የድምፃዊው አልበም የኢትዮጵያን የሙዚቃ አልበም በሽያጭ ክብረ ወሰን የሰበረ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በአጠቃላይ በመጀመሪያው ዙር ግማሽ ሚሊዮን የሙዚቃ አልበም ታትሞ መሰራጨቱ የተገለፀ ሲሆን አልበሙ ለሲዲ አዟሪዎች መልካም የገበያ ዕድል እንደፈጠረላቸው ታውቋል፡፡
ቦሌ ድልድይ አካባቢ ረቡዕ ጠዋት 2 ሰዓት ገደማ የድምፃዊውን አልበም ሲሸጥ አግኝተን ያነጋገርነው አዟሪ፤ ቀደም ሲል መፅሃፍ እያዞረ ይሸጥ እንደነበረ ጠቁሞ፤ መደበኛ ስራውን ለጊዜው በመተው የድምፃዊውን አልበም እየሸጠ መሆኑን ገልጿል፡፡ ከማለዳው 11 ሰዓት ጀምሮ እስከ ጠዋቱ 1 ሰዓት ድረስ ከ50 በላይ አልበሞችን እያንዳንዱን በመቶ ብር ሂሳብ መሸጡንም ጠቁሟል፡፡ የተወሰኑ አልበሞችንም በ80 እና በ70 ብር መሸጡን ተናግሯል፡፡
አልበሙን ገዝቶ በታክሲ ውስጥ እያዳመጠ ያገኘነው የታክሲ ሹፌር በበኩሉ፤ ባለፈው ረቡዕ አልበሙ ሊያልቅ ይችላል በሚል ስጋት ጠዋት 12 ሰዓት ላይ አውቶብስ ተራ አካባቢ በ100 ብር መግዛቱን ገልፆ ይህን ያደረገውም ድምፃዊውን ስለሚያደንቀውና ታሪካዊውን አልበም እንዳያጣ በመስጋት መሆኑን ተናግሯል፡፡
“እውነተኛው የኦሮሞ እና አማራ ታሪክ” በተሰኘ አነጋጋሪ መፅሃፋቸው የሚታወቁት ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ በፌስቤክ ገፃቸው ባሰፈሩት አስተያየት፤ “ቴዎድሮስ ካሣሁንንና ሙዚቃውን ለምን ህዝብ ይወዳቸዋል?” በሚል ርዕስ ባሰፈሩት ማስታወሻ፤ ሙዚቃዎቹ ባለፉት 25 ዓመታት እንደ ሰደድ እሳት የተዛመተውን ዘረኝነት የሚቃወሙና ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ በመሆናቸው ብለዋል።
በርካታ የፌስቡክ ተከታይ ያለው ዘውዳለም ታደሰ በበኩሉ፤ ድምፃዊው “አፄ ቴዎድሮስ” በሚለው ዘፈኑ፤ አፄ ቴዎድሮስን ዳግም እንዳነገሳቸው ፅፏል፡፡ በዚህ ዘፈን ኢትዮጵያዊነት ከፍ ብሎ እንደተሰበከም ገልጿል፡፡ አብዛኞቹ የአርቲስቱ አድናቂዎች ሀገራዊ ይዘት ያላቸውን ሙዚቃዎች እንደወደዷቸው በፌስቡክ ገፃቸው ላይ አስፍረዋል፡፡
ዱከም ኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ አዲስ በተቋቋመው “ቆልያ ሲዲና ዲቪዲ አምራች” ድርጅት በተመረተውና በቀላሉ ኮፒ ለማድረግ ያስቸግራል በተባለው ሲዲ የታተመው የቴዲ አፍሮ “ኢትዮጵያ” አልበም ከወጣበት ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በሲዲ ማዞር ስራ ላይ ተሰማርተው የማያውቁ ግለሰቦች ሳይቀሩ ሲዲውን በፍጥነት እየሸጡ መሆኑን በተዘዋወርንባቸው ፒያሳ፣ አራት ኪሎ፣ መርካቶ፣ መስቀል ፍላወርና ካዛንቺስ አካባቢዎች ለማረጋገጥ ችለናል፡፡ አልበሙን ለማከፋፈል ባለፈው ማክሰኞ የክልልና የአዲስ አበባ ነጋዴዎች ረጅም ወረፋ ሲጠብቁ እንደነበር የገለፁት ምንጮቻችን፤ አልበሙን ለማከፋፈል ለምዝገባ ሲመጡ የሚፈልጉትን የሲዲ መጠን ግማሽ ክፍያ በባንክ ቅድሚያ ከከፈሉ በኋላ ለመውሰድ ሲመጡ ደግሞ ሙሉ ክፍያ የከፈሉበትን የባንክ ደረሰኝ ያሳዩ እንደነበር ምንጮቻችን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
አልበሙ መውጣት ከነበረበት ሁለት ሳምንት ዘግይቶ መውጣቱ የሚታወቅ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ ሲዲው በተለመደው ከቨር ለገበያ ቢቀርብ ለአየር ብክለት ጉዳት ይጋለጣል በመባሉ አሁን ባለው የካርቶን ከቨር ለመለወጥ ሲባል ሁለት ሳምንት መዘግየቱን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ ይህንንም ስራ በፍጥነት ለመሰራት 200 ያህል ጊዜያዊ ሰራተኞች ተቀጥረው ከቨሩንና ግጥም የተፃፈበትን ቡክሌት ሲያጥፉ እንደቆዩ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ 500 ሺህ ከቨርና ቡክሌቱ እያንዳንዱ በአራት አራት ብር የተሰራ ሲሆን የተቀጠሩት ጊዜያዊ ሰራተኞች አንዷን ከቨር ለማጠፍ በ20 ሳንቲም ሂሳብ መስማማታቸውንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ለከቨሩ እና ለቡክሌቱ ስራ በጠቅላላ ወደ 5 ሚ. ብር መውጣቱም ተገልጿል፡፡

•    ከ2001 ጀምሮ 374 ቢመዘገቡም አሁን ያሉት 57 ብቻ ናቸው
* ፈቃድ ያገኙ ኤፍኤም ጣቢያዎች ችግር ገጥሞናል አሉ  
     የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን፤ባለፉት ዘጠኝ ወራት ወደ 40 የሚጠጉ አዳዲስ የግል ጋዜጦችና መፅሔቶችን መመዝገቡንና በመላው ሃገሪቱ የግል ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ቁጥር 30 መድረሱን የጠቆመ ሲሆን ፈቃድ የወሰዱ የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች በበኩላቸው፤በተለያዩ ችግሮች የተነሳ ወደ ሥራ መግባት አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡
አዳዲስ ጋዜጦችና መፅሄቶችን ለመጀመር ያሰቡ በርካታ ድርጅቶች ወደ ብሮድካስት ባለስልጣን እየቀረቡ መስፈርቱን አሟልተው ሲገኙ እውቅና እየተሰጣቸው መሆኑን የገለጹት የባለስልጣኑ ም/ዳይሬክተር አቶ ልኡል ገብሩ፤ከዚህ ቀደም እውቅና ተሰጥቷቸው ሥራ ያልጀመሩ ፕሬሶች ዋና ችግራቸው ማስታወቂያ መሆኑን እንደጠቆሟቸው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡  
ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ 374 ጋዜጦችና መፅሔቶች (118 ጋዜጦች እና 256 መፅሔቶች) ወደ ስራ ለመግባት እውቅና ጠይቀው የተሰጣቸው ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ገበያው ላይ ያሉት ነባሮቹን ጨምሮ 14 ጋዜጦች እና 43 መፅሄቶች ብቻ እንደሆኑ ተገልጿል፡፡ በብሮድካስት ሚዲያዎች በኩል 35 የግል ሬዲዮና የቴሌቪዥን ጣቢያዎች (30 ሬዲዮ፣5 ቴሌቪዥን) ወደ ገበያው መቀላቀላቸውን የጠቆሙት ምክትል ዳይሬክተሩ፤56 የሃገሪቱ ብሔረሰብ ቋንቋዎችም የብሮድካስት ቋንቋ ወደመሆን መሸጋገራቸውን አስታውቀዋል፡፡
አዳዲሶቹ የሬዲዮና ቴሌቪዥን ጣቢያዎች አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎች እንደሚገኙ የጠቆሙት አቶ ልኡል፤በአገሪቱ 97 የህዝብ /የመንግስት ሬዲዮና ቴሌቪዥን ጣቢያዎች መኖራቸውን ገልጸዋል፡፡  
በቅርቡ ፈቃድ ከተሰጣቸው 3 የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች መካከል አንዳቸውም ሥራ ያልጀመሩ ሲሆን ከእነዚህ አንዱ የሆነው የ"አሃዱ ኤፍኤም"ዳይሬክተር አቶ ጥበቡ በለጠ ፤ለጣቢያው አስፈላጊ የሆኑ የስቱዲዮና ማሰራጫ እቃዎችን በአስቸጋሪ ሁኔታ፣ ከፍተኛ ቀረጥ ከፍለው ማስገባታቸውን ጠቁመው፤ሁሉም ነገር ተጠናቆ ፉሪ ላይ ማሰራጫ ጣቢያ ከተተከለ በኋላ በመብራት እጦት እስካሁን ወደ ስራ መግባት አለመቻላቸውን ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡  
ኤፍኤም ጣቢያው ያለ ምንም ስራና ገቢ፣ለሰራተኞች ደሞዝና ለቢሮ ኪራይ ወጪ እያወጣ መሆኑን የገለጹት አቶ ጥበቡ፤የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት የመብራት ችግሩን እንዲፈቱላቸው ጠይቀዋል፡፡

የቀብር ሥነ ስርአቱ ትናንት ተፈፅሟል
የአንጋፋው የህግ ባለሙያና የፖለቲካ ሊቅ አሰፋ ጫቦ የቀብር ስነ ስርዓት በአዲስ አበባ መንበረ ፀባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን ተፈፅሟል፡፡
ላለፉት 25 ዓመታት በአሜሪካ በስደት ኑሮውን ሲመራ የቆየው አሰፋ ጫቦ፤ ድንገት ባደረበት ህመም በዚያው ሀገር በሚገኝ ሆስፒታል ሲረዳ ቆይቶ ሚያዚያ 15 ቀን 2009 ዓ.ም ህይወቱ ማለፉ የሚታወስ ሲሆን አስክሬኑም ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ከአሜሪካ ወደ አዲስ አበባ እንደመጣ  ታውቋል፡፡ አስክሬኑ ከቀኑ 9 ሰዓት አዲስ አበባ ቦሌ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የደረሰ ሲሆን ቤተሰቦቹ እና በርካታ አድናቂዎቹ እንዲሁም ወዳጆቹ አቀባበል አድርገውለታል፡፡
ለአገሩ ትልቅ ፍቅርና አክብሮት የነበረው አሰፋ፤ በህይወት ሳለ የዘወትር ምኞቱና ጉጉቱ አገሩ መግባት እንደነበር ባለፈው ሳምንት ከአዲስ አድማስ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረገችው ብቸኛ ሴት ልጁ ተናግራ ነበር፡፡
በብዙዎች ዘንድ በተባ ብዕሩ የሚታወቀው አሰፋ ጫቦ፤ አዲስ አድማስን ጨምሮ በተለያዩ ጋዜጦች ላይ በሳልና ተወዳጅ የፖለቲካ መጣጥፎችን ይፅፍ የነበረ ሲሆን በቅርቡም “የትዝታ ፈለግ” የተሰኘ መፅሐፍ ማሳተሙ ይታወሳል፡፤
አቶ አሰፋ ጫቦ የአንዲት ሴት እና የሦስት ወንዶች አባት ሲሆን በ75 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡


• የችግሮች ዋነኛ መንሥኤ፥ የሕግና የሥርዓት መጣስና ዘመኑን የዋጀ አለመሆን ነው፤ ተብሏል
• ቅዱስ ሲኖዶስ፥ ለውጡን የሚያስተባብርና የሚያስፈጽም አካል እንደሚሠይም ይጠበቃል
• ምልአተ ጉባኤው፣ በይደር በተያዘው የአዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመትም እንደሚነጋገር ተጠቁሟል
  ላለፉት ሁለት ሺሕ ዓመታት አያሌ ፈተናዎችን በመቋቋም ሐዋርያዊና ሀገራዊ ተልእኮዋን ስትወጣ የቆየችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ችግሮች ዋነኛ መንሥኤ፥ “የሕግና የሥርዓት መጣስና ዘመኑን የዋጀ አለመሆን ነው፤” ያለው አንድ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና በማስጠበቅና ቀጣይነቷን በማረጋገጥ ለትውልድ ለማሸጋገር፣ መዋቅሯን መልሶ ማደራጀት፤ ሕጎቿን፣ ደንቦቿንና መመሪያዎቿን በፍጥነት በማስተካከል የለውጥ ሥራ ማካሔድ እንደሚኖርባት አሳሰበ፡፡
ጥናቱን ያቀረበው፥ በተመረጡ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንትና ምእመናን ስብጥር የተቋቋመውና ባለፈው ዓመት ጥቅምት ላይ በቅዱስ ሲኖዶስ የተሠየመው ከፍተኛ ኮሚቴ ሲሆን፤ ችግሮችን ከሥር መሠረታቸው ለማረምና ለማስተካከል የሚያስችል አዲስ መዋቅርና አደረጃጀት እንዲሁም መሠረታዊ የሆኑ ሕጎችን፣ ደንቦችንና የአሠራር ሥርዓቶችን በመቅረጽና መልክ በማስያዝ የለውጥ ሥራውን የሚያካሒድ፣ ራሱን የቻለ የባለሞያ አካል መሠየምና በአስቸኳይ መተግበር እንደሚያስፈልግ አሳስቧል፡፡
ከላይ ወደ ታች፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ የሚደርሰውን መዋቅር፣ ተግባርና ሓላፊነት፥ ከተጠሪነት፣ የሰው ኃይል አደረጃጀትና የማስፈጸም አቅም ጋራ በማዛመድ የገመገመው ጥናቱ፥ መዋቅራዊ አደረጃጀቱ በአግባቡ አለመዘርጋቱን፤ የዕዝ ሰንሰለቱ፥ የላላ፣ የተንዛዛ፣ ለሓላፊነትና ለተጠያቂነት የማያመች መሆኑ፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ዋነኛ ችግሮች በመሠረታዊ መንሥኤነት አስቀምጧል፡፡
የቋሚ ሲኖዶሱን መዋቅርና አደረጃጀት በቀዳሚነት ያነሣው ጥናቱ፣ የቅዱስ ሲኖዶሱን የዕለት ተዕለት ሥራዎች ለማከናወን በምልአተ ጉባኤ ቢወከልም፣ አባላቱ በየሦስት ወሩ መቀያየራቸው፣ ጉዳዮችን በስፋትና በጥልቀት አጥንቶ በመወሰን በኩል የአሠራር ችግር ማስከተሉን አመልክቷል፡፡
የፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት፣ ለፓትርያርኩ የአስተዳደር አገልግሎት ድጋፍና ለጽሕፈት ነክ ሥራዎች ቢታሰብም፣ ያለአግባብ ራሱን የቻለ ከፍተኛ የመዋቅርና የሥልጣን አካል አድርጎ እንደሚሠራ ጠቅሶ፥ “ለሕግና ሥርዓት መዛባት፣ ለመልካም አስተዳደር ዕጦትና ለመሳሰሉ ችግሮች ቀዳዳ የከፈተ አሠራር ሆኖ ታይቷል፤” ብሏል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የቤተ ክርስያኒቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አካልና የሥራ መሪ ኾነው ሳለ፣ የቋሚ ሲኖዶሱ አባል ሆነው መሥራታቸውም ለቁጥጥር እንደማያመችና ፍትሕ ሊያዛባ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡
የቁጥጥርና ምርምራ አገልግሎት፣ የሥርዓትና ሥነ ምግባር ኮሚሽን፣ የመንፈሳዊ ፍርድ ቤት፣ የሊቃውንት ጉባኤና የውጭ ጉዳይ መምሪያዎች፣ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን፣ የመንፈሳውያን ኮሌጆች፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና መመሪያዎች፣ የአህጉረ ስብከት ጽ/ቤቶችና የሥራ ዘርፎች እንዲሁም የአጥቢያ ሰበካ ጉባኤ መዋቅራዊ አደረጃጀት፣ ሓላፊነትና ተጠሪነት፥ ከውጤታማ የአሠራር ሥርዓት፣ ከመፈጸም ብቃት፣ ከሥራ ቅልጥፍናና የውሳኔ አሰጣጥ አኳያ ያሉባቸው ችግሮች በጥናቱ ከተዳሰሱት መካከል ይገኙበታል፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አወቃቀር፣ እንደሌሎች አህጉረ ተመሳሳይ ሆኖ አለመደራጀቱንና “የቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት ነው” የሚለው ድንጋጌም ግልጽ ባለመሆኑ ለበርካታ ውዝግቦች መነሻ መሆኑን ጥናቱ አስረድቷል፡፡ ይህን በመጠቀም፣ አንዳንድ የሀገረ ስብከቱ የሥራ ክፍሎችና የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት፣ “ተጠሪነታችን ለፓትርያርኩ ነው” በሚል ከሕግና ሥርዓት ውጭ በመሆን፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሚሰጠውን አመራር ያለመቀበል አዝማሚያ እንደሚያሳዩና ይህም ለመልካም አስተዳደር ችግር፣ ለምዝበራና ለሌሎችም አግባብ ለሌላቸው ተግባሮች በር መክፈቱን ዘርዝሯል፡፡
በአጠቃላይ መዋቅርና አደረጃጀቱ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ተልእኮ የሚያሳካና ዓላማዎችንና ግቦችን ለማስፈጸም የሚያስችል እንዳልሆነ፤ በተለይም፣ ሥልጣን ሁሉ ተጠቃሎ በአንድ ቦታ ተከማችቶ መገኘትና የሥራና የሓላፊነት ክፍፍል አለመኖሩን፤ የሥራ አስፈጻሚው ተግባርና የዳኝነቱ ሥራ ተቀላቅሎ እንደሚሠራና ለአሠራር ሥርዓት ክፍተትና ለፍትሕ መዛባት ምክንያት እንደሆነ ያስረዳው ጥናቱ፤ ሕግን የማውጣት፣ ሕግን የማስፈጸምና ሕግን የመተርጎም የሥልጣን መርሖዎች፣ ከቋሚ ሲኖዶሱ ጀምሮ በየደረጃው ተለያይተውና ተመጣጥነው በአጥጋቢ ሁኔታ የሚዘረጉበት ተቋማዊ ሁኔታ ሊኖር እንደሚገባ ጠቁሟል፡፡ መዋቅሩንና አደረጃጀቱን ከላይ እስከ ታች መልሶ የማደራጀቱና የማስተካከሉ ተግባር፣ ስትራቴጂያዊና መሠረታዊ በሆነ መልክ መፈጸም እንዳለበትና በጉዳዩ ላይ ቁርጠኛ አቋም ሊያዝ እንደሚገባ ጥናቱ አስገንዝቧል፡፡
ሕጎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች ተሟልቶ አለመገኘትና ያሉትንም እንደየወቅቱ ሁኔታ እየታየ ማሻሻያ አለማድረግ፥ ለክፋትና ለተንኮል፣ ለግል ጥቅም ለተሰለፉ ወገኖች የተመቻቸ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ጥናቱ ጠቅሶ፤ የአሠራር ሥርዓቱን በአግባቡ ለማከናወን የሚያስችሉ ሕጎችና ደንቦች ያለመኖራቸውን በተጨማሪ መሠረታዊ መንሥኤነት አስቀምጧል፡፡
የበላይና ዋነኛ የሆነውና በሥራ ላይ የሚገኘው የ2007 ዓ.ም. ሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ እጥር ምጥር ብሎ በግልጽ አቀራረብ፣ ጠቅላላ ድንጋጌዎችን፣ መሠረታዊ መርሖዎችንና ፖሊሲዎችን ይዞ በኮንስቲቱሽን መልክ እንደገና ተስተካክሎ እንዲጻፍና በየጊዜው ሳይቀያየር ቋሚና ዘላቂ እንዲሆን፤ ቃለ ዓዋዲው፣ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ በመሆኑ እንደገና ተሻሽሎ ሕጉን መሠረት በማድረግ፣ ሰበካ ጉባኤ ነክ የሆነው ተግባር ብቻ በሚገለጽበት ሁኔታ ተስተካክሎ እንዲጻፍ ማድረግ እንደሚያስፈልግ በመፍትሔነት የጠቆመው ጥናቱ፣ በአዲሱ መዋቅር የሚደራጀው የሥራ አስፈጻሚው አካል ተግባርና ሓላፊነቱን በብቃት ለመወጣትና ተጠያቂነትን ለማስፈን የሚያስችሉ የተለያዩ የሥራ ማስፈጸሚያ ሕጎችና ደንቦች(ቃለ ዐዋዲዎች) ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን እያጣቀሱ መውጣት እንደሚኖርባቸው አመልክቷል፡፡
ከፍተኛ ኮሚቴው፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅር በሁለንተናዊ መልኩ መልሶ ለማደራጀትና ለማሻሻል ያስችላሉ ያላቸውን ሦስት የመዋቅር ለውጥ አማራጮችን ከማብራሪያዎቻቸው ጋራ በጥናቱ በማካተት ያቀረበ ሲሆን፤ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ፣ ቃለ ዓዋዲውና የሠራተኛ አስተዳደር ደንቡ፥ የመልካም አስተዳደርና የሥነ ምግባር ችግሮችን በመቅረፍ፣ ወጥ የሆነ የአሠራር ሥርዓት በመዘርጋት ዋነኛ ተልእኮዋን በብቃት ለመወጣት በሚያስችላት አኳኋን የሚሻሻሉበትን ይዘትና ሊይዟቸው የሚገቡ ዋና ዋና ሐሳቦችንም አመልክቷል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር እጅግ አሳሳቢና የለውጥ ሥራውም የሁሉንም ትብብርና ድጋፍ እንደሚጠይቅ ያስገነዘበው ከፍተኛ ኮሚቴው፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ችግሩን ለመፍታት ያሳየው ተነሣሽነትና ቁርጠኝነት ተገቢና ወቅታዊ መሆኑን ገልጿል፡፡
የአሁኑ የጥምር ኮሚቴው ጥናታዊ ሪፖርት፣ ቀደም ሲል በተለያዩ አካላት በቀረቡ ሰነዶች የተጠቆሙ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮችና መፍትሔዎች አሳሳቢነት በድጋሚ የተረጋገጡበት እንደሆነ የተናገሩ የቅዱስ ሲኖዶሱ ምንጮች፤ የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤው፣ በመጪው ሳምንት ረቡዕ በሚጀመረው ስብሰባው፣ በዋነኛ አጀንዳነት በመያዝ የለውጥ ሥራውን በባለቤትነት በማስተባበር መልክና ቅርጽ የሚያሲዝ የባለሞያ አካል ሊሠይም እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ምልአተ ጉባኤው፣ ከባለፈው የጥቅምት መደበኛ ስብሰባው የተላለፈውንና የአዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት በሚመለከተው አጀንዳ ዙሪያ ተነጋግሮ ውሳኔ ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡


 ቅዱስ ጊዮርጊስ በኢትዮጵያ የክለቦች ታሪክ ፈርቀዳጅነቱ በተለያዩ ሁኔታዎች ይጠቀሳል፡፡ 80ኛ ዓመቱን በማክበር ላይ የሚገኘው ክለቡን በብሄራዊና አህጉራዊ ደረጃ አዳዲስ ምእራፎችን እየከፈተ ጉዞውን ቀጥሏል፡፡ በአፍሪካ የክለቦች ውድድር ተሳትፎ 50ኛ ዓመቱን ሲይዝ  በ2017 ቶታል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ድልድል ገብቷል፡፡ ከደቡብ ፤ ከመካከለኛው እና ከሰሜን አፍሪካ ምርጥና የቀድሞ ሻምፒዮን ክለቦች ጋር የሚፋለምበት ደረጃ ላይ ነው፡፡
በ2017 ቶታል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ 16 ክለቦች መሳተፋቸው በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ይህን ለውጥ በመፍጠሩ አድናቆት አግኝቷል፡፡ በተለይ በክለቦች ደረጃ ጠንካራ የሊግ ውድድር ያላቸው እነ አልጄርያ፤ ዛምቢያ፤ ሱዳን፤ ኬንያና የመሳሰሉት፤ እንዲሁም በምስራቅ፤ በደቡብ እና በመካከለኛው አፍሪካ ዞኖች ያሉ ክለቦች በምድብ ፉክክር ተሳታፊ የሚሆኑበትን እድል ፈጥሯል፡፡ በሌላ በኩል ባለፉት የውድድር ዘመናት በምድብ ፉክክሩ የሚገቡት ክለቦች 5 አገራትን ብቻ በተደጋጋሚ የሚወከሉበትን ሁኔታም ቀይሮታል፡፡ ዘንድሮ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የ13 አገራት ክለቦች ተሳታፊ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ሊጉ የምድብ ፉክክር አዳዲስ ክለቦች ከተለያዩ አገራት በብዛት ያሳተፈ በመሆኑ በአፍሪካ ደረጃ  የሚያገኘውን ትኩረት ያሳድገዋል፡፡
በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በካይሮ ከተማ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለ2017 የካፍ ቶታል ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ የምድብ ድልድሎችን  አውጥቷል፡፡ ኢትዮጵያን በመወከል የምድብ ፉክክር ውስጥ የገባው ቅዱስ ጊዮርጊስ በምድብ 3 ከደቡብ አፍሪካው ሜመሎዲ ሰንዳውንስ፤ ከዲ.ሪ ኮንጎው ኤኤስ ቪታ ክለብ እና ከቱኒዚያው ኤስፔራንስ ዴቱኒስ ጋር ተመድቧል፡፡ የምድብ የመጀመርያ ጨዋታዎች ከ2 ሳምንት በኋላ የሚጀምሩ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሜዳው ውጭ ከደቡብ አፍሪካው ሜመሎዲ ሰንዳውንስ ጋር ይገኛል፡፡
በሌሎቹ ሶስት ምድቦች ከ1 ጊዜ በላይ የሻምፒዮናነት ድሎችን ያስመዘገቡት የሰሜን አፍሪካ ክለቦች ቀለል ያሉ ታጋጣሚዎችን አግኝተዋል፡፡ በምድብ 1 በ2007 እኤአ ላይ ሻምፒዮን የሆነው የቱኒዚያ ኤትዋል ደሳህል፤ የሱዳኖቹ አልሂላል እና አልሜሪክ እንዲሁም በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ በምድብ ማጣርያው ተሳታፊ የሚሆነው የሞዛምቢኩ ፌዮቬራዬ ዴማፑቶ ይገኛሉ፡፡ በምድብ 2 የአምስት ጊዜ ሻምፒዮኑ የግብፁ ዛማሌክ፤ በቅድመ ማጣርያ ሃያሉን ቲፒ ማዜምቤ ጥሎ ማለፍ የቻለው የዚምባቡዌው ካፕስ ዩናይትድ፤ የአልጄርያው ዩኤስኤም አልጀር እና በሜዳው የሚያደርጋቸውን ጨዋታዎች በቱኒዚያ የሚያደርገው የሊቢያው አልሃሊ ትሪፖሊ ተደልድለዋል፡፡ በምድብ 4 ደግሞ ለስምንት ጊዜያት የአፍሪካ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው የግብፁ ክለብ አልአሃሊ፤ ከሞሮኮው ዋይዳድ ካዛብላንካ፤ የካሜሮኑ ኮተን ስፖርት እንዲሁም የዛምቢያ ዛናኮ ዩናይትድ ተመድበዋል፡፡
ብራዚላውያኖቹ ከደቡብ አፍሪካ
ሜመሎዲ ሰንዳውንስ የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ነው፡፡ በ2016 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው በሚያስገርም አጋጣሚ ነበር፡፡ የዲ.ሪ ኮንጎው ክለብ ኤኤስ ቪታ ክለብ ተገቢ ያልሆነ ተጨዋች በማሰለፉ በቅጣት ከውድድሩ ውጭ ሲሆን ሜሞሎዲ ተክቶ በመግባት እስከ ዋንጫው ድል ተጉዟል፡፡ ሜሞሎዲ ሰንዳውንስን ማልያቸው ከብራዚል ብሄራዊ ቡድን ጋር ስለሚመሳሰል ብራዚላዊያኖቹ እያሉ ይጠሯቸዋል፡፡ ባፋና ባ ስታይል የሚሏቸውም አሉ፡፡ ከተመሰረተ 47 ዓመት የሆነው ክለቡ ስታድዬሙ በፕሪቶርያ የሚገኘውና 28ሺ ተመልካች የሚያስተናግደው ሎፍተስ ቬርስፊልድ ነው፡፡ ከ2016 ጀምሮ ማሊያው በናይኪ ስፖንሰር የሆነለትና፤ 3 የደቡብ አፍሪካ ግዙፍ ኩባንያዎች በአበይት ስፖንሰርነት የሚደግፉት ክለቡን በባለቤትነት የሚያስተዳድሩት ፓትሪስ ሞቴስፔ የተባሉ ባለሃብት ናቸው፡፡ ዋና አሰልጣኝ ደግሞ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድንን ሲያሰለጥኑ የነበሩት ፒትሶ ሞስማኔ ናቸው፡፡በ2016 የዓመቱ የካፍ ምርጥ ክለብ የተባለው ሜሞሎዲ የ2017 የአፍሪካ ሱፕር ካፕንም ተቀዳጅቷል፡፡ በሌላ በኩል ከ1996 እኤአ ወዲህ የደቡብ አፍሪካ አብሳ ሊግን 7 ጊዜ ያሸነፈ ሲሆን በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ባለፉት 10 ዓመታ 37 ጨዋታዎች አድርጎ በ37 ድል፤ በ16 አቻ እንዲሁም በ15 ሽንፈት ገጥሞታል፡፡
ጥቁር ዶልፊኖች ከመካከለኛው አፍሪካ
የዲሪ ኮንጎው ክለብ ኤኤስ ቪታ ክለብ በ1973 እኤአ ላይ የአፍሪካ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ ሲሆን  በቅፅል ስም ጥቁር ዶልፊኖች ብለው ይጠሯቸዋል፡፡ ከተመሰረተ 92 ዓመታትን ያስቆጠረው ይህ ክለብ 80ሺ ተመልካች የሚያስተናግደውን ስታድ ዴ ማርታየርስ በሜዳነት የሚጠቀም ሲሆን የክለቡ ፕሬዝዳንት ጋብሬል አሲሚ ይባላሉ፡፡
ደምና ወርቅ ከሰሜን አፍሪካ
የቱኒዚያው ምርጥ ክለብ በሙሉ ስሙ ኤስፔራንሴ ስፖርቲቭ ዴ ቱኒዝ ተብሎ ቢታወቅም ቅፅል ስማቸው ደምና ወርቅ የሚል ነው፡፡ ከተመሰረተ 98ኛ ዓመቱን የያዘው ክለቡ በቱኒስ ከተማ የሚገኘውና 60ሺ ተመልካች የሚያተናግደውን ኦሎምፒክ ዴ ራዴስ ስታድዬም ይጠቀማል፡፡ የእግር ኳስ ብቻ ሳይሆን፤ እጅ ኳስ፤ ቅርጫት ኳስ፤ መረብ ኳስ እና የራግቢ ቡድኖችን የሚያተዳድረው ክለቡን በሊቀመንበርነት የሚመሩት ሃመዲ ማዴስ ናቸው፡፡ ኤስፔራንስ የቱኒዚያን ሊግ ለ21 ጊዜ የቱኒዚያ ካፕን 15 ጊዜ ያሸነፈ ሲሆን የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግን በ1994 እና በ2011 እኤአ ከማሸነፉም በላይ ለ4 ጊዜያት በ2ኛ ደረጃ ጨርሷል፡፡ በ1998 እ.ኤ.አ ደግሞ የአፍሪካ ሱፕር ካፕን አሸንፎ ነበር፡፡
ፈረሰኞቹ ከምስራቅ አፍሪካ
የ2009 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግን እየመራ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ  ዓመታዊ በጀቱ እስከ 20 ሚሊዮን ብር ይደርሳል፡፡   ከደጋፊዎች መዋጮ፤ ከስፖንሰሮች እና ከአጋር ድርጅቶች ፤ ከሜዳ፤ ከስፖርት ማህበሩ ክበብ፤ ከልዩ ልዩ የስፖርት ቁሶች ሽያጭ ከሚሰበስባቸው ገቢዎች የሚገኝ ነው፡፡ በማልያው ስፖንሰርሺፕ በየዓመቱ እስከ 6 ሚሊዮን ብር እየተከፈለውም ነው፡፡ በክለቡ ዘንድሮ   የአባልነት መዋጮ የሚከፍሉ ደጋፊዎች ብዛት ከ14ሺ 700 በላይ ሲሆን በተለያዩ የጥራት ደረጃዎች የተሸጡት ማልያዎች ከ10ሺ በላይ ናቸው፡፡  
ጊዮርጊስ በአገር ውስጥ የክለብ ውድድሮች ከ80 በላይ ዋንጫዎች የሰበሰበ ሲሆን፤ የፕሪሚዬር ሊግ 30፤ የጥሎ ማለፍ 13፤ የአሸናፊዎች አሸናፊ 10 ዋንጫዎች ይገኙበታል፡፡ በሀገር ውስጥ ውድድር ባስመዘገባቸው ተደጋጋሚ ድሎች ምክንያት ከኢትዮጵያ ክለቦች በአህጉራዊ ውድድሮች ተሳትፎው ከ50 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ ከዘንድሮ በፊት በአህጉራዊ ውድድሮች የተሻለ ውጤት ያስመዘገበው በ1959 ዓ.ም በአፍሪካ ክለቦች ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ የገባበት እና በ2005 ዓ.ም በኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ስምንት ውስጥ የገባበት ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ከ1967 እኤአ ጀምሮ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ስር በሚካሄዱ ውድድሮች፤ ለ12 ጊዜያት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ፤ለ10 ጊዜያት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ካፕ፤ 1 ጊዜ በአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ፤ 1 ጊዜ በካፍ ካፕ እንዲሁም ለ3 ጊዜያት በካፍ የአሸናፊዎች አሸናፊ ውድድሮች  ነው፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ማጣርያዎች ላይ (ውድድሩ በካፍ አዲስ መዋቅር መካሄድ ከጀመረበት ከ1997 እኤአ ወዲህ  ማለት ነው፡፡) ከዘንድሮ በፊት ለ12 ጊዜያት በነበረው ተሳትፎ  በአጠቃላይ ውጤቱ 61ኛ ደረጃ ላይ ነበር፡፡ ለ8 ጊዜያት ቅድመ ማጣርያውን በማለፍ ለመጀመርያ ዙር ሲበቃ ለ4 ጊዜያት ከውድድሩ የተሰናበተው በቅድመ ማጣርያ ነበር፡፡
የአቶ አብነት ተስፋ እና የአቶ አርሰናል ማነቃቂያ
በሙሉ ስማቸው ዴቪድ ባሪ ዲን ተብለው ይጠራሉ፡፡ የ73 ዓመት አንጋፋ የእግር ኳስ ባለሙያ ሲሆኑ በሊድስ ዩኒቨርስቲ ኢኮኖሚክስ አጥንተዋል፡፡ በ1983 እኤአ ላይ ወደ አርሰናል ሲቀላቀሉ በክለቡ እስከ 292ሺ ፓውንድ ኢንቨስት በማድረግ  16 በመቶ የአክሲዮን ድርሻ ገዝተው ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ  በአርሰናል ክለብና በእንግሊዝ እግር ኳስ ማህበር ምክትል ሊቀመንበርነት ከ20 ዓመታት በላይ አገልግለዋል፡፡  በአርሰናል ክለብ ከፍተኛ ባለስልጣን ሆነው በቆዩባቸው ዓመታት በክለቡ በነበራቸው የአክሲዮን ባለድርሻነት ፤ የአሰልጣኝ ቅጥር እና የተጨዋቾች ግዢ፤ የስታድዬም ግንባታ እና ሌሎች እንቅስቃሴዎች  ጉልህ ሚናዎች በመጫወታቸው አቶ አርሰናል (Mr· Arsenal) እስከመባልም ደርሰዋል፡፡ በተለይም በአርሰናል ክለብ ዋና አሰልጣኝነት ሲሰሩ 21ኛ  ዓመታቸውን የያዙትን ፈረንሳዊ አርሴን ዌንገር በመቅጠር በክለቡ ታሪክ ጉልህ አስተዋፅኦ ለማበርከት መቻላቸው ይጠቀስላቸዋል፡፡  በ2007 ክለቡ የለቀቁት የነበራቸውን  የአክሲዮን ድርሻ በ25 ሚሊዮን ፓውንድ በመሸጥ ነበር፡፡    በሌላ በኩል በ1992 እኤአ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በአዲስ መልክ ተዋቅሮ፤ በትርፋማ አቅጣጫዎች እንዲንቀሳቀስ ካስቻሉ ባለሙያዎች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ  ናቸው፡፡ከወር በፊት  የቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ አብነት ገብረመስቀል ባደረጉት ልዩ ጥረት በሸራተን አዲስ በተዘጋጀ የግማሽ ቀን ሲምፖዚዬም ላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ለሚንቀሳቀሱ ባለድርሻ አካላት የማነቃቂያ ንግግር አቅርበው ነበር፡፡  በዓመት እስከ 4.8 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ስለሚሆንበት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መዋቅራዊ አደራጃጀትና የእድገት ሂደት ፤ የክለቦችና የደጋፊዎች እንቅስቃሴ፤ በቴሌቭዥን የስርጭት መብት፤ በፕሮፌሽናል ተጨዋቾች የዝውውር ገበያ ያሉትን ጠቃሚ ተመክሮዎች  አጭር መግለጫ የሰጡበት መድረክ ነበር፡፡ በኢትዮጵያም የክለብ እግር ኳስ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ተመክሮ እንዴት መተግበር እንደሚቻል  ያነቃቁበት መድረክ ነበር፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ፕሬዚዳንት የሆኑት አቶ አብነት ገ/መስቀል በ2017 የካፍ የክብር ሽልማት አግኝተዋል፡፡ ዴቪድ ባሪ ዲንን ወደ አዲስ አበባ የጋበዙት እሳቸው ነበሩ፡፡ በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ ለውጥ የሚፈጥሩ ተመሳሳይ መድረኮችን ወደፊትም በመፍጠር ለመስራት እንደሚፈልጉ ተናግረው ነበር፡፡ በሚቀጥሉት 5 ዓመታት የኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር በስፖንሰርሽፕ፣ በፕሮፌሽናል አደረጃጀት ትርፋማ እንዲሆን የሚያስችሉ የውይይት መድረኮችን ለመፍጠር ቃል ገብተው ነበር፡፡