Administrator

Administrator

    አገር በቀሉ በላይአብ ሞተርስ የኪያ ሞተርስ ኮርፖሬሽን ሞዴል የሆኑትን ሁለት አውቶሞቢሎች ሪዮና ፒካንቶ የተባሉትን በአገር ውስጥ ገጣጥሞ ለገበያ ማቅረቡን አስታወቀ፡፡
ከትናንት በስቲያ ማምሻውን በሸራተን አዲስ በተካሄደው መኪኖቹን የማስተዋወቅ ሥነ - ሥርዓት የበላይአብ ሞተርስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ፈቃዱ ግርማ፣ በአሁኑ ወቅት  “ታይገር ኖዝ” የተባሉትን ሁለት የኪያ ሞዴል መኪኖች፡- ሪዮና ፒካንቶ ገጣጥመው ለገበያ ማቅረባቸውን ጠቅሰው፤ በ2010 የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት ታዋቂ የሆኑትን ሴዳን የመኪና ሞዴል ማለትም ሴራቶ፣ ለስፖርት አገልግሎት የሚውሉና ዘርፈ ብዙ
አገልግሎት ያላቸውን መኪኖች ለማቅረብ ማቀዱን ገልጸዋል፡፡
ኪያ ሞተርስ ኮርፖሬሽን በአሜሪካ ቀዳሚ ከሆነው የመኪና አምራች ኩባንያ ከፎርድ ጋር በጋራ መሥራት ከጀመረ በኋላ፣ በዓመት 1.5 ሚሊዮን መኪኖችን እንደሚያመርት ጠቅሰው፣ ኪያ፣ በ8 አገሮች 13 የመኪና ማምረቻና መገጣጠሚያ፣  በ172 አገሮች መሸጫና አገልግሎት መስጫዎች ፣
ዓመታዊ ገቢው 14.6 ቢሊዮን ዶላርና 40,000 የሙሉ ሰዓት ተቀጣሪ ሠራተኞች እንዳሉትና የኪያ መኪኖች በ2013 “ኢንተርናሽናል ካር ኦፍ ይር አዋርድ” ማሸነፉን ተናግረዋል፡፡
ድርጅቱ በአሁኑ ወቅት በ150 ሚሊዮን ብር ገጣጥሞ ለገበያ ያቀረባቸው መኪኖች ለኢትዮጵያ መንገዶች ፋሽን ናቸው ያሉት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፣ መኪኖቹ ሰፊ የቀለም ምርጫ፣ ውበት፣ ጥንካሬ፣ ምቾት፣ በፈለጓቸው ጊዜ መገኘት የሚችሉ፣ በአውቶማቲክና በእጅ ማርሽ የሚሠሩ መሆናቸውን፣ የሚገጣጠሙት መኪኖች ለ150 የአንድ ፈረቃ ሰራተኞች የሥራ ዕድል መፍጠሩን፣ ፈረቃው ከአንድ በላይ ከሆነ የሰራተኞቹ ቁጥር ከዚህ እንደሚበልጥና እነዚህን መኪኖች የሚገዙ ሰዎች በአገር ውስጥ ከሚሸጡ ተመሳሳይ መኪኖች ጋር ሲነፃፀሩ ከ15-20 በመቶ ቅናሽ ያገኛሉ፤ ሌሎችም ጥቅም አሏቸው በማለት አብራርተዋል፡፡
በላይአብ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የ11 ወንድማማችና የአንድ እህት የቤተሰብ ቢዝነስ ሲሆን “በላይ አብ” የሚለው ስም ለሟች አባታቸው ለአቶ በላይ ሀብተ ጊዮርጊስ መታሰቢያ የተሰየመ ነው፡፡ ኢንቨስትመንት ግሩፑ፣ 11 ኩባንያዎች ሲኖሩት፣ አምስቱ ትላልቅ ኩባንያዎች፣ በላይአብ ኤሌክትሪክና ዳታ ኬብል፣ በላይአብ ሞተርስ፣ ጎልደን ቱሊፕ አዲስ አበባ ሆቴል፣ ሊኮን ኮንስትራክሽን ግሬድ BC-2 ኮንትራክተርና ሌዊስ
ኮንስትራክሽን ማቴሪያልስ ሳፕላይ ኢንተርፕራይዝ ናቸው፡፡
እነዚህ አምስቱ ኩባንያዎች የተመሰረቱበት ካፒታል 579 ሚሊዮን ብር ሲሆን በአሁኑ ወቅት አጠቃላይ ካፒታላቸው መስሪያ ካፒታላቸውን ጨምረ ከ1.1 ቢሊዮን ብር በላይ ሆኗል፡፡ ኢንተርፕራይዞቹ ከ1ሺ በላይ ለሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥረዋል፡፡ 

• በሥርዓተ ጥምቀት፣ ከካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጋራ ያደረገችው ስምምነት ሲኖዶሱን አወያየ
• “ኢትዮጵያውያን ከሊቃውንቶቻቸው ጳጳስ አይሹሙ” የሚለው ቀኖና፣ ከፍትሐ ነገሥቱ ይወጣል
• በግል አታሚዎች ስሕተት የተጨመረባቸው ፥ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት እንዲስተካከሉ ታዘዘ
• ስለ አቡነ ጳውሎስ እና ኮ/ል መንግሥቱ ኃ/ማርያም የሚያወራው ‘ተኣምረ ማርያም’ ይገኝበታል

በክርስትናው የነገረ መለኰት እና የምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ከግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋራ፣ የቆየ የታሪክ ግንኙነትና የዶግማ አንድነት ያላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በትምህርተ ሃይማኖት ረገድ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሁለቱ እኅትማማች አብያተ ክርስቲያናት መካከል እየታየ ነው ያለው ልዩነት እንዲመረመር፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አዘዘ፡፡
የስብሰባው ምንጮች እንደተናገሩት፣ ምልአተ ጉባኤው ትእዛዙን የሰጠው፣ ምሥጢረ ጥምቀትን በተመለከተ፣ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንና የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን፣ ሚያዝያ 20 ቀን 2009 ዓ.ም.፣ በካይሮ የተፈራሙትን የጋራ ስምምነት የቅርብ መነሻ በማድረግ በተካሔደ ውይይት ነው፡፡
የካቶሊኩ ፖፕ ፍራንሲስ በቅርቡ ግብጽን በጎበኙበት ወቅት፣ ከኮፕት ቤተ ክርስቲያን ፖፕና የእስክንድርያ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ጋራ የተወያዩ ሲሆን፤ ከተፈራረሙት ባለ12 አንቀጾች የጋራ ስምምነት ውስጥ፣ አንዱ የሌላውን ምእመን ጥምቀት ላለመድገም የተስማሙበት አቋም(shared baptism) እንደሚገኝበት ተገልጿል። በሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት፣ የሥርዓተ ጥምቀቱ አፈጻጸምና የሃይማኖት ምስክርነቱ፣ መሠረታዊ ልዩነት እንዳለው የገለጹ ምንጮች፤ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን አካሔድ፣ የነገረ መለኰትና የምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንድነት ባላቸውና ኦሪየንታል ተብለው በሚታወቁት፥ የኢትዮጵያ፣ የሶርያ፣ የአርመንና የሕንድ እኅትማማች አብያተ ክርስቲያናት ቅዱስ ሲኖዶሶች ያልተመከረበት እንደኾነ አስረድተዋል፡፡
በሥርዓተ ጥምቀት ላይ የሚፈጠረው ልዩነት፣ በሌሎቹ የምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በሚኖረው አንድነት ላይ ተጽዕኖ እንዳለው ምንጮቹ ጠቅሰው፥ በሥርዓተ ቊርባን፣ ከአዳማዊ የሃጢአት ውርስ አንጻር የድንግል ማርያም ቅድስና፣ የካህናቱ ሥነ ምግባር (ሲጋራ ማጤስ)፣ የመሳሰሉት ኻያ ያህል ልዩነቶች በውይይቱ ወቅት እንደተነሡ ከቀደሙት ታላላቅ አባቶች አስተምህሮ ጋራ ያላቸው መጣጣም ጥያቄ ማሥነሳቱን አመልክተዋል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ በየጊዜው በሚያካሒደው ስብሰባ፣ ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ጋራ በትብብር መሥራቱ እንዲጠናከር፣ በተለይም ከግብጽ ኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋራ ለቆየው ግንኙነት ትኩረት እንዲሰጠው ቢያሳስብም፣ በትምህርተ ሃይማኖት ረገድ ከጊዜ ወደ ጊዜ ከሚታዩት ተናጠላዊ አካሔዶች አንጻር ዶግማዊና ቀኖናዊ አንድነቱ እንዲመረመር ስምምነት ተደርሶበታል፤ የሊቃውንት ጉባኤውም፣ ልዩነቶቹን አጥንቶ ለቀጣዩ ዓመት የጥቅምት ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርብ መወሰኑን አስታውቀዋል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ምልአተ ጉባኤው፣ ግብጻውያን በፍትሐ ነገሥት ፍትሕ መንፈሳዊ በጣልቃ(ሥርዋጽ) የጨመሩት ነው የተባለው አንቀጽ በቀጣይ የመጽሐፉ ኅትመቶች እንዲቀር መወሰኑ ተገልጿል። “ኢትዮጵያውያን ከሊቃውንቶቻቸው ጳጳስ አይሹሙ” የሚለው ሥርዋጹ፣ በግብጾች
እንደሚነገረው፣ በኒቂያ ጉባኤ 42ኛ አንቀጽ ያልተወሰነ፣ ሐሰተኛ ቀኖና ነው፤ ተብሏል፡፡
በአራተኛው ክፍለ ዘመን፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ጥያቄና ፈቃድ በግብጽ ከተሾመው ቅዱስ ፍሬምናጦስ በኋላ እስከ 1951 ዓ.ም. ይሾሙ የነበሩት ጳጳሳት ግብጻውያን እንደነበሩ ያስታወሱት ምንጮቹ፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ከሥራቸው ለማድረግ ከአገራቸው ነገሥታት ጋራ መክረው ያስገቡት መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከራሷ ልጆች የራሷን ፓትርያርክና ጳጳሳት መሾም ከጀመረች ግማሽ ምእት ዓመት የተቆጠረ በመኾኑ፣ ሥርዋጹ፣ በቀጣይ ኅትመቶች እንዲቀር ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል። በስንክሳር የሚያዝያ 10 ቀን ንባብ፣ ከንጉሥ ሐርቤ ጋራ በተያያዘ ያለውም ያለውን ታሪክ፣ በተመሳሳይ መልኩ ከኅትመት እንዲወጣ መወሰኑ ታውቋል፡፡     
በሌላ በኩል፣ በግል አታሚዎች እየታተሙ በሚወጡ የጸሎትና የሥርዓት መጻሕፍት ውስጥ ተጨምረዋል የተባሉ ተኣምራት፣ አግባብ ያልኾኑ የሕዝቦች መጠሪያዎች የመሳሰሉት፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ውጭ የተፈጸሙና አስተምህሮዋን የሚፃረሩ እንደኾኑ ቅዱስ ሲኖዶሱ እንደመከረበት ተገልጿል፡፡ በግል አታሚዎቹ የቀድሞዎቹን ትክክለኛ ቅደጂዎች በሚያፋልስ መልኩ ለኅትመት የዋሉት፥ የስንክሳር፣ የራእየ
ማርያምና የተኣምረ ማርያም መጻሕፍት የተጠቀሱ ሲሆን፤ የቀድሞውን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስንና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያምን ከቀኖናዊ አሠራር ውጪ በማካተት የታተመው ‹ተአምረ ማርያም› በአስረጅነት ተነሥቷል፤ በሊቃውንት ጉባኤም ተጠንቶ እንዲቀርብ መወሰኑ ታውቋል፡፡


Saturday, 06 May 2017 10:38

የወር አበባ መዛባት...

 ባለፈው እትም ስለወር አበባ መዘግየት መምጣትና መቅረት በሚመለከት አንዳንድ ነጥቦችን አንስተን ከዶ/ር ሙስጠፋ ነጋሽ ያገኘነውን ማብራሪያ ለአንባቢ ማለታችን ይታወሳል። ከወር አበባ ጋር በተያያዘ ያለውን ጠቃሚ ነገር ዶ/ር ሙስጠፋ ነጋሽ በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ኮሌጅ መምህርና የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት የሆኑት ለዚህ እትም የሰጡትን ቁምነገር ታነቡ ዘንድ እነሆ ብለናል። ከ University of Maryland School of Medicine ድረገጽ ያኘነውን ቁምነገርም እናስነብባችሁዋለን።
የወር አበባ በተለይም ፍሰቱን ካልጠበቀ የሚያስትለው ችግር አለ።
የወር አበባ መጠን ከአስር እስከ ሰማንያ ሊትር በአማካይ ደግሞ ሰላላ ሚሊ ሊትር ነው። ከዚህ በተጨማሪም የሚፈሰው ደም የመርጋት ሁኔታ ሊታይበት አይገባም። ይህ ከሆነ ግን የወር አበባ መብዛቱን የሚያመላክት ነው። ስለዚህም ከዚህ ጋር ተያያዥ በሆነ ምክንያት፡-
የደም ማነስ እና ከደም ማነስ ጋር የተያያዙ ሌሎች ችግሮችንም ያስከትላል።
ልብ ድካምና ኢንፌክስን ለመሳሰሉት ሕመሞች ያጋልጣል።
የስነአእምሮአዊ ችግር ከወር አበባ ጊዜውን አለመጠበቅና የመጠን መብዛት ሊከሰት ይችላል። ለዚህም እንደ ምክንያት የሚቆጠረው አንዲት ሴት በአጠገብዋ ያለች ጉዋደኛ ወይንም እህትዋ የወር አበባዋ በትክክል የሚመጣና የሚሄድ ከሆነ እስዋ ግን እኔ ለምንድነው ይህ መዛባት የገጠመኝ በሚል ከመጨነቅ ሊከሰት ስለሚችል ነው። ስለ ዚህም ሐዘን፣ የስሜት መጎዳት፣ እንደድብርት የመሳሰሉት ችግሮችም ሊገጥሙአት ይችላሉ።
የወር አበባ መዛባት የሚያስከትለው ሌላው ችግር በተለይም በትዳር ላይ ላሉ ያልተጠ በቀ እርግዝና ነው። ከዚሀም የተነሳ ጽንሱን ወደማቋረጥ ስለሚሄዱ እና በተለያዩ ምክንያቶችም ለማህጸን ካንሰር የመጋለጥ እድሎችን ያስከትላል።
እንደ ዶ/ር ሙስጠፋ ነጋሽ ማብራሪያ ሴቶች የተለያዩ የእርግዝና መከላከያዎች በተለይም ፕሮጀ ስትሮን ያላቸው መከላከያዎችን ሲወስዱ የወር አበባ አይፈጠርም። በዚህም ምክንያት ብዙ ጊዜ እርግዝና ተፈጥሮ ይሆናል የሚል ስጋት በሴቶች ላይ ይስተዋላል። አንዳንዶች ደግሞ ደሜ ሆዴ ውስጥ እየተጠራቀመ ስለሆነ ሆዴን እየነፋኝ ነው የሚል ስጋት ይስተዋልባቸዋል። ነገር ግን ሁሉም ሰው ሊገነዘበው የሚገባው ነገር በመርፌ የሚወሰድ የእርግዝና መከላከያ የወርአበባ እንዳይፈጠር ማድረጉን ነው። ለዚህም ምክንያቱ አንዱን ሆርሞን ብቻ ስለሚይዝ ሲሆን በኪኒን መልክ የሚዘጋጁት ግን የወር አበባ በጊዜው እንዲመጣ የሚያስችሉ ሆነው የተዘጋጁ ናቸው። በእርግጥ በኪኒኒ መልክ የተዘጋጀ በመርፌ የሚሰጥ መከላከያ እንዳለ እሙን ነው። ስለዚህ የወር አበባ መጀመሪያ የመዛባትና መቅረት ችግሮች እስከ 49/አመት ባሉት እድሜ ውስጥ ከሆነ እርግዝና እና ከእርግዝና ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ችገግሮች መኖር ያለመኖራቸውን ማወቅ ተገቢ ይሆናል። በዚህ መልክ የሚከሰቱ ችግሮች ለሕይወት አስጊ ስለሚሆኑ እና ጊዜ ሊሰጣ ቸው ስለማይገባ በፍጥነት ወደሐኪም መሔድም ይመረጣል። ውርጃ የሚከሰት ከሆነ ኢንፌ ክሽን በመፍጠር ወደሰውነት ሊሰራጭ ከመቻሉም በላይ ማህጸንዋን ከጥቅም ውጭ ሊያደርግ ይችላል። ምናልባትም ከማህጸን ውጭ እርግዝና ከሆነ ከመጠን በላይ በሆድዋ ውስጥ ደም ስለሚፈስ ለሕይወት አስጊ ሊሆን ይችላል። በእርግጥ አንዳንድ ጊዜ የሚወሰዱ የእርግዝና መከላከያዎችም የወር አበባ መዛባቱን ሊያስከትሉ የሚችሉ ሲሆን ይህንን በሚመለከትም መድሀኒቱን ካዘዙ ባለሙያዎች ጋር መመካከር ያስፈልጋል።
የወር አበባ እርግዝና ሲኖር፣
ጡት በማጥባት ወቅት፣
በመርፌ መልክ የሚሰጡ የእርግዝና መከላከያዎች ሲወሰዱ ሊቋረጥ ይችላል።
ከላይ የተጠቀሱት ሁኔታዎች ተፈጥሮአዊ ሲሆኑ ተፈጥሮአዊ ያልሆነው ደግሞ፡-
እድሜው የወር አበባ መምጫ ሆኖ ሳለ ሳመጣ ሲቀር፣
ምንም የእርግዝና መከላከያ ሳይወሰድ፣
እርግዝና ሳይኖር፣
እድሜ ለወር አበባ መቋረጥ ሳይደርስ ከሆነ አሳሳቢ ይሆናል።
ስለዚህ አንዲት ልጅ ከ15-16/ ባለው እድሜዋ የወር አበባ ካላየች ወደሕክምና መሔድ ግድ ነው። የወር አበባ በትክክለኛው እድሜ ቢመጣም የመምጫ ጊዜውን የሚያዛባ ከሆነና የሚቋረጥ ከሆነም የህክምና ድጋፍ ያስፈልጋል።
በወር አበባ ምክንያት የሚመጣ ሕመምን በዘመናዊ ሕክምና ማስወገድ እንደሚቻል እና የተለያዩ የቤት ውስጥ እርዳታዎችም እንደሚያስወግዱት University of Maryland School of Medicine ድረገጽ ይገልጻል።
የመጀመሪያው የማህጸን አጥንት ተሸካሚ አጥንት ምርመራ ነው። ይህ የምርመራ ሂደትም ላፓራስኮፒ በሚባለው የምርመራ መሳሪያ የሚከወን ነው። ሌላው የህክምና ዘዴ የአልትራ ሳውንድ ምርመራ ነው። እንደዚሁም የደምና የሽንት ምርመራን በመውሰድ የተከሰተውን ችግር በዝርዝር ለማወቅ ይረዳል። የእርግዝና መከላከያ እንክብሎች ህመምን ለመቀነስ እና የተዛባ የወር አበባን ለማስተካከል ይረዳል ስለሚባል በሕክምናው ይታዘዛል። በሳይንሱ አለም ሌሎች የተለያዩ የህክምና ዘዴዎችም ስላሉ ችግሩ የገጠማቸው ሴቶች ወደሕክምናው አለም ጎራ እንዲሉ ይመከራል።
የወር አበባ መዛባትን በሚመለከት የተለያዩ የአመጋገብና የአኑዋኑዋር ምክሮችም ይለገሳሉ።
በካልሲየም የበለጸጉ ምግቦችን መመገብ ማለትም ቅጠላቅጠልና ጥራጥሬዎች እንዲሁም አትክልቶችን መመገብ ጠቃሚ መሆኑን ድረገጹ ያትታል።
ፍራፍሬዎች እንጆሪን እና ቲማቲምን ጨምሮ ባጠቃላይም ከሰውነት ውስጥ (Antioxidant) መመረዝን የሚያስወግዱ ምግቦችን መመገብ ጠቃሚ ነው።
በኢንደስትሪ ውስጥ ተሰርተው የታሸጉ እና እንደስንዴ ዳቦ፣ ፓስታ እና ስኩዋር የመሳሰሉትን ምግቦች ማስወገድ የወር አበባ መዛባት እንዳይኖር ያደርጋል።
ስጋን በሚመለከት የሚመከረው መጠኑ ትንሽ የሆነ ቀይ ስጋ እና ትንሽ ፋት ቅልቅል የሆነ ስጋን በመጠኑ መመገብን ይመክራል ድረገጹ።
ተጋግረው የታሸጉ ምግቦች እንደ ኩኪስ ኬኮች የተጠበሰ ድንች እና በኢንደስትሪ የተሰሩ ምግቦችን ማስወገድ ይጠቅማል።
በምግቦች ውስጥ የወይራ ዘይት፣ የአትክልት ዘይት የሆኑትን ለማብሰያነት መጠቀም ጠቃሚ ነው።
አልኮሆል እና ሲጋራ የሚጠቀሙ ከሆነ ማስወገድ ተገቢ ነው።
ከ6-8/ ብርጭቆ ውሀ በቀን መጠጣት ይመከራል።
በቀን እስከ 30/ደቂቃ የአካል አንቅስቃሴ ማድረግ ይመከራል።
ከዚህ ውጭ እንደከሞሜላ ያሉ ተፈጥሮአዊ የሆኑ ቅጠላ ቅጠሎች እንደሻይ አፍልቶ መጠጣትም ሊጠቅም ስለሚችል ከተለያዩ መረጃዎች በማገናዘብ እርግጠኛ የሆኑበትን ነገር መጠቀም ይመከራራል።
ከወር አበባ ጋር በተያያዘ አንዱ አስቸጋሪ ነገር የባህርይ መለዋወጥ ነው። ዶ/ር ሙስጠፋ ነጋሽ እንደሚሉት ሴቶች የወር አበባቸው ሊመጣ አካባቢ ባህሪያቸውን ብቻም ሳይሆን ሰውነታቸውም ጭምር ይለዋወጣል። የጡት ወጠርጠር ማለት፣ ጭንቀት፣ መነጫነጭ፣ ትውከት የመሳሰሉት ነገሮች ይከሰታሉ። ከዚህም በተጨማሪ የስሜት መለዋወጥ እና መረበሽ እንዲሁም የሆድ መክበድ ሊገጥማቸው ይችላል። የማህጸን ፈሳሽም በዛ ሊል ይችላል። በእነዚህ መሰል ምክንያቶች የተነሳ ትእግስትን የሚፈታተን ነገር ሊገጥማቸው ስለሚችል የባህርይ መለዋወጥ ነገር ሊታይ ይችላል። ከዚህ ውጭ ግን ሕመም የሚሆንበትም አጋጣሚ አለ። ሴትዋ ከስራራ እስከመ ቅረት ወይንም ወደሐኪም ቤት ሄዳ ሕክምና እስኪደረግላት ድረስ የሚያደርሳት ከሆነ ሕመም ስለሆነ በጣም አስቸጋሪ ነው። ስለዚህም አብረው የሚኖሩ ሰዎች የትዳር ጉዋደኛም ይሁን ቤተሰብ ይህንን መረዳትና ጊዜው እስኪያልፍ በትእግስት መጠበቅ ይኖርባቸዋል። ለዚህ ጉዳይ ምንም ግምት ሳይሰጡ ከሴትየዋ ጋር መጨቃጨቅ ወይንም ክብርን፣ ትኩረትን መንፈግ የበለጠ ስለሚያበሳጫት ሊጎዳት ይችላል። ይህ የገጠማት ሴት ደግሞ ምክንያቱን በመደበቅ ለመታገል መሞከር ሳይሆን ያለችበትን ወቅትና ሁኔታ በትክክል ማስረዳት መቻል አለባት። በግልጽ በመነጋገር ችግሩን መፍታት ይቻላል ይላሉ ዶ/ር ሙስጠፋ ነጋሽ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት እና መምህር።

 የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ2019 እኤአ ላይ ካሜሮን ለምታስተናግደው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የሚያደርገውን የምድብ ማጣርያ ከወር በኋላ ቢጀምርም፤ አስፈላጊውን የተሟላ ዝግጅት በተያዘው እቅድ መሰረት ለማከናወን አልቻለም። አዲሱ ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ለስፖርት አድማስ እንደገለፁት በመጀመሪያ ምርጫቸው ለብሔራዊ ቡድኑ 29 ተጨዋቾችን በመመልመልና የአንድ ወር የዝግጅት እቅዳቸውን ለፌደሬሽኑ ከሳምንት በፊት አቅርበው ነበር፡፡ ከኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ፤ ከጥሎ ማለፍ እና ከቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ በተያያዘ ባሉት የጨዋታ መደራረቦች ሳቢያ እቅዳቸውን ሊተገብሩ አልቻሉም፡፡ የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ባስተላለፈው ውሳኔ ግን ከጋና ጋር ከሚደረገው ጨዋታ በፊት ዋልያዎቹን ለ10 ቀናት ብቻ እንዲያዘጋጁ ወስኖባቸዋል፡፡ ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ለፌደሬሽኑ ያቀረቡትን የ1 ወር የዝግጅት እቅድ እንዳብራሩት፤ 3 የወዳጅነት ጨዋታዎችን ከከተማ ውጭ ለማድረግ፤ የተለያዩ የልምምድ መርሃ ግብሮችን ለመስራት፤ የተጨዋቾችን የጤና ሁኔታዎችና ወቅታዊ አቋም በመገንዘብ ቡድኑን ለማዋሃድና የመጨረሻ ቡድናቸውን ዝርዝር ለማሳወቅ ፍላጎት ነበራቸው፡፡ ይሁንና የክለቦች መልካም ፈቃደኝነት ባለመኖሩ የዝግጅት ጊዜው ከ1 ወር ወደ አስር ቀናት እንዲያጥር እንዲሁም የወዳጅነት ጨዋታዎች ብዛትም ከ3 ወደ አንድ እንዲቀነስ ግድ ሆኗል፡፡
ለ6 ወራት ያለአንዳች ውድድር ተበትነው የቆዩት  ዋልያዎቹ በአፍሪካ ዋንጫው የምድብ ማጣርያ በምድብ 6 ከጋና፤ ከኬንያና ከሴራሊዮን መደልደላቸው ይታወቃል፡፡ ከወር በኋላ የመጀመርያ ጨዋታቸውን  የሚያደርጉት ከሜዳ ውጭ ከጋና ብሄራዊ ቡድን ጋር ይሆናል፡፡ ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ለስፖርት አድማስ በሰጡት አስተያየት የብሄራዊ ቡድኑ ባለቤት ህዝቡ እና ሁላችን ነን ብለው፤ በቴክኒክ ኮሚቴ ፀድቆ የቀረበውን የ1 ወር የዝግጅት እቅዳቸውን የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ወደ 10 ቀናት ለማሳጠር መወሰኑን በመቃወም በከፍተኛ ደረጃ መከራከራቸውን አስገንዝበዋል፡፡ ፌደሬሽኑ፤ የክለብ አሰልጣኞች እና አመራሮች፤ ሚዲያ እና ህዝቡ ለብሄራዊ ቡድኑ የሚሰጠውን ትኩረት ለማሳደግ   በጋራ  እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ ያቀረቡት ዋና  አሰልጣኙ፤ የዝግጅት እቅዶች ተለዋዋጭ መሆን የለባቸውም ሲሉም ያሳስባሉ፡፡ ክለቦች በጠቅላላ ጉባኤ በጋራ የደረሱበት ስምምነት ላይም በድጋሚ ምክክር በማድረግ እንዲሰሩም ይመክራሉ፡፡
በሌላ በኩል ቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የሚያደርገው ተሳትፎ በተወሰነ መልኩ ጫና መፍጠሩ አይቀርም የሚሉት ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኮንጎው ክለብ ኤኤስ ቪታ ጋር በሜዳው የሚያደርገው ሁለተኛ ጨዋታም ከዋልያዎቹ የጨዋታ መርሃ ግብር የሚደራረብበት ሁኔታ እንደሚያስጨንቃቸውም ጠቁመዋል፡፡
የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያውን ከሜዳ ውጭ ከጋና ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ መጀመራቸው ፈታኝ እንደሚሆን ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ ሲያስገነዝቡ የ10 ቀናት ዝግጅቱ ሙሉና ውጤታማ ቡድን ለመገንባት እንደሚያስቸግራቸው አልሸሸጉም፡፡ በብሔራዊ ቡድኑ የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ አጀማመር ስኬታማ ለመሆን በተለዋጭ እቅዶች እየተንቀሳቀስኩ ነው ግን ብለዋል፡፡ በተለይ የጋና ብሄራዊ ቡድን በቅርብ ጊዜያት ያደረጋቸውን ሦስት ጨዋታዎች ቪዲዮ በጥልቀት እንደተመለከትን በተለያዩ የዓለም ሀገራት ያሉ የጋና ፕሮፌሽናል ተጫዋቾች እንቅስቃሴም ስከታተል ቆይቻለሁ ብሏል፡፡ ከምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታ ከመደረጉ 1 ሳምንት በፊት ከኡጋንዳ  ብሄራዊ ቡድን ጋር የሚያደርጉት የወዳጅነት ጨዋታ ቋሚ ተሰላፊዎቻቸውንና፤ አጠቃላይ የቡድኑን ስብስብ ለመለየት የምጠቀምበት ይሆናል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለአዲሱ ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ የብሄራዊ ቡድኑን ሙሉ ሃላፊነት  ካስረከባቸው  ሳምንታት አልፈዋል፡፡  በውል ስምምነቱ እንደተጠቀሰው የዋልያዎቹ ዋና አሰልጣኝ ሆነው ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት የሚሰሩ ሲሆን፤ በ2019 እኤአ ላይ ካሜሮን ለምታስተናግደው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ማብቃት እንዳለባቸው ተገልፆላቸዋል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለዋና አሰልጣኙ ውላቸው በስምምነት እስካልተቋረጠ ድረስም ከስልክ፣ መኪና እና ሹፌር እንዲሁም የጤና መድህን ወጭዎችና ሌሎች ጥቅማጥቅሞች ጋር በወር ያልተጣራ 100000 ብር ደመወዝ እንደሚከፍላቸው ይታወቃል፡፡ ከሳምንት በፊት የፌዴሬሽኑ ቴክኒክ ኮሚቴ እና ስራ አስፈፃሚው ባፀደቀላቸው መሰረት ዋና አሰልጣኙ ሁለት ረዳት አሰልጣኞች የቅዱስ ጊዮርጊሱ ምክትል አሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ እና የመከላከያ አሰልጣኝ በለጠ ገብረኪዳን ናቸው፡፡  ፀጋ ዘአብ የግብ ጠባቂዎች አሰልጣኝ ሆኖ ሲመደብ፣ ይስሃቅ ሽፈራው የብሄራዊ ቡድኑ ወጌሻ እንዲሁም ዶክተር አያሌው የቡድኑ ሃኪም ሆነው ይሰራሉ፡፡ የስነ ልቦና እና የስነ ምግብ ባለሙያዎችን የፌደሬሽኑ የህክምና ኮሚቴ ከስራ አስፈፃሚው ጋር በመመካከር የሚያሳውቁ ይሆናል፡፡
ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ትውልዳቸው በምዕራብ ሸዋ ዞን ኮደዱላ ቀበሌ ገበሬ ማህበር ሲሆን፤ ለበርካታ ዓመታት እግር ኳስን ተጫውተዋል፡፡ ላለፉት 24 ዓመታት በተለያዩ ክለቦች በአሰልጣኝነት ያገለገሉ ናቸው፡፡ በተለይ የኢትዮጵያ ባንኮች፣ መከላከያ፣ ሲዳማ ቡና እና አዳማ ከተማ ክለቦችን  በማሰልጠን  ሰፊ ልምድ ያካበቱ ሲሆን የፕሪሚዬር ሊጉን ዋንጫ ማንሳት ባይችሉም ጠንካራ ቡድን  በሚገነቡበት አሰራራቸው ይታወቃሉ፡፡ በ1995 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድንን በማሰልጠን የሰሩ ሲሆን ለሦስት ዓመት ከሉሲዎቹ ጋር ሲያሳልፉ ለሦስተኛ ጊዜ ለአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፉ በማድረግም ውጤታማ ነበሩ፡፡
ዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ከፌደሬሽኑ ጋር ውሉን በፈረሙበት ወቅት ለ32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማለፍ ብቻ ሳይሆን ሩብ ፍፃሜ መግባት ዕቅዳቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ በተለያየ ምክንያት ከብሄራዊ ቡድኑ ያገለሉ ተጫዋቾችንም ወደ ቡድኑ ሊመለሱ  እንደሚችሉም አስታውቀው ነበር፡፡ ይህን አስመልክቶ ዋና አሰልጣኙ ለስፖርት አድማስ በሰጡት አስተያየት ከቀድሞ ተጨዋቾች ወደ ብሄራዊ ቡድኑ እንዲመለስ በተለይ ጥረት ያደረጉት የቅዱስ ጊዮርጊሱን አዳነ ግርማ በማነጋገር ነበር፡፡ ‹‹አዳነን  ወደ ቡድኑ እንዲመለስ ስጠይቀው በቅርበት አግኝቼው ነው። ሁሌም ለአገሩ ለማገልገል ፍላጎት እንዳለው ገልፆልኝ በተለያዩ የግል ምክንያቶች  ግን ወደ ቡድኑ ለመመለስ እንደሚከብደው አስረድቶኛል፡፡ እኔም ሙሉ ለሙሉ አቋሙን ተረድቼ ውሳኔውን ተቀብያለሁ›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ለብሄራዊ ቡድን በመጀመርያ ምርጫ የጠሯቸውን ተጨዋቾች ስም ዝርዝር እስካሁን ያላሳወቁት ዋና አሰልጣኙ፤ በውጭ ካሉ ተጨዋቾች በተለይ በግብፅ የሚገኙት የአጥቂ መስመር ተሰላፊው ኡመድ ኡክሪና አማካዩ ሽመልስ በቀለ ለብሄራዊ በድኑ ለመሰለፍ መልካም ፈቃዳቸውንና ጉጉታቸውን መግለፃቸውንም ተናግረዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በ2019 እኤአ ካሜሮን ወደምታስተናግደው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በሚደረገው የምድብ ማጣርያ በምድብ ስድስት የሚገኙ ሌሎቹ ቡድኖች ወደ ካምፕ ገብተው በመሰባሰብ ባይሆንም በተለያያ መንገድ ዝግጅቶቻቸውን ከጀመሩ ሳምንታት ተቆጥረዋል። በተለይ ኬንያ ለምድብ ማጣርያው ከፍተኛ ትኩረት የሰጠች ሲሆን የመጀመርያውን የወዳጅነት ጨዋታ ከሳምንት በፊት ከማላዊ ብሄራዊ ቡድን  በናይሮቢ አድርጋ ያለምንም ግብ በአቻ ውጤት ተለያይተዋል፡፡ የሃራምቤ ኮከቦች የሚባለውን የኬንያ ብሄራዊ ቡድን በዋና አሰልጣኝነት የሚመሩት ስታንሊ አኩዋምቢ ናቸው፡፡ ሰሞኑን ለዴይሊ ኔሽን በሰጡት አስተያየት በአፍሪካ ዋንጫ እና የቻን ውድድር በሚኖራቸው ዝግጅቶች ስኬታማ መሆን የሚቻለው የፌደሬሽን እና የፕሪሚዬር ሊግ አስተዳደር ትብብርና ድጋፍ ሲሰጡ ነው ብለዋል፡፡ ለብሄራዊ ቡድኑ ጠንካራ እና የተሟላ ዝግጅት ሲባል የፕሪሚዬር ሊጉ አስተዳደር በጨዋታዎች መርሃ ግብር ላይ የተወሰኑ ሽግሽጎችን እንዲያደርግ የጠየቁት ስታንሊ አኩዋምቢ፤ ክለቦች ወሳኝ ተጨዋቾቻቸውን በአስፈላጊው ወቅት በመልቀቅ እንዲተባበበሩ እና በየወሩ ቢያንስ  የወዳጅነት ጨዋታ ፌደሬሽኑ እንዲያዘጋጅላቸው ጥሪ አቅርበዋል፡፡ በሌላ በኩል ከምድቡ ሰፊ የማለፍ እድል እንደያዘ የሚነገርለት የጋና ብሄራዊ ቡድን በዋና አሰልጣኝነት የሚመሩት ኩዋሲ አፒያህ ሲሆኑ ወደ ሃላፊነቱ የመጡት ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡ አሰልጣኙ የጋና ህዝብ በአፍሪካ ዋንጫ እና በዓለም ዋንጫ ማጣርያዎች ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን አምበሉ  አሰሞሃ ጊያንም ተመሳሳይ መልዕክት ነበረው፡፡ አሳሞሃ ጊያን ለጋና ክሮኒክል በቅርቡ በሰጠው አስተያየት በጋና ፕሪሚዬር ሊግ እና በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ያሉ ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች  ለብሄራዊ ቡድኑ ቁርጠኛ መሆን እንዳለባቸው መክሯል፡፡ ከ2012 እስከ 2014 የጋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የነበሩት ኩዋሲ አፕያህ በድጋሚ ጥቋቁር ክዋክብቶችን እንዲመሩ ሲመረጡ የሁለት ዓመት የቅጥር ኮንትራት  ተፈራመዋል፡፡ የጋና ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫው ሻምፒዮን እንዲያደርጉ እና ለ2018 የራሽያ ዓለም ዋንጫ እንዲያሳልፉ የጋና እግር ኳስ ፌደሬሽን ይፈልጋል፡፡

                 የምድብ 6 ጨዋታዎች

• ጁን 9 ፤ 2017 እኤአ ጋና ከኢትዮጵያ - ሴራሊዮን ከኬንያ
• ማርች 23፤ 2018 እኤአ ኢትዮጵያ ከሴራሊዮን - ኬንያ ከጋና
• ሴምፕተምበር 5 ፤ 2018 እኤአ ጋና ከሴራሊዮን - ኢትዮጵያ ከኬንያ
• ሴፕቴምበር 9፤ 2018 እኤአ ሴራሊዮን ከጋና - ኬንያ ከኢትዮጵያ
• ኦክቶበር 12 ፤ 2018 እኤአ ኢትዮጵያ ከጋና - ኬንያ ከሴራሊዮን
• ኖቬምበር 9፤ 2018 እኤአሴራሊዮን ከኢትዮጵያ - ጋና ከኬንያ

 የታንዛኒያ መንግስት በሃሰተኛና በተጭበረበሩ የትምህርት ማስረጃዎችና የኮሌጅ ሰርተፍኬቶች አማካይነት በተለያዩ የመንግስት የስራ መደቦች ላይ ተቀጥረው ሲሰሩ የተገኙ 9 ሺህ 900 የአገሪቱ ሰራተኞችን ከስራ ገበታቸው ማባረሩ ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆን ሙጉፋሊ ሙስናን ለመዋጋት በብሄራዊ ደረጃ ያወጁት ዘመቻ አካል በሆነው በዚህ እርምጃ፣ በመላ አገሪቱ በተከናወነ ምርመራ፣ በሃሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ተቀጥረው ሲሰሩ የተገኙት ከ9 ሺህ 900 በላይ የመንግስት ሰራተኞች በአስቸኳይ ከስራ እንደዲባረሩ መደረጋቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በተከናወነው የመንግስት ሰራተኞች የትምህርት ማስረጃ ማጣራት ስራ፣ የ1ሺህ 500 ያህል ሰራተኞች ትክክለኛ የትምህርት ማስረጃዎች በተጭበረበረ መልኩ እንደገና ተስተካክለው ለብዙ ሰራተኞች የትምህርት ማስረጃ ሆነው እንደቀረቡ መረጋገጡንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ባለፈው መጋቢት ወር ላይ በተከናወነ ተመሳሳይ ምርመራ፣ በስራ ገበታቸው ላይ ለሌሉ 20ሺ ገደማ ሰራተኞች ደመወዝ እንደሚከፈላቸውና በዚህም አገሪቱ በየአመቱ በአማካይ 82 ሚሊዮን ፓውንድ  እንደምታጣ መረጋገጡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

የአውሮፓ ህብረት፤ እንግሊዝ ከህብረቱ አባልነት ለመውጣት ያከናወነቺውን ህዝበ ውሳኔ ተፈጻሚ ለማድረግና ጠቅልላ ለመውጣት በቅድሚያ 100 ቢሊዮን ዩሮ እንድትከፍል የሚያስገድድ መመሪያ ሊያወጣ እየተዘጋጀ ነው የተባለ ሲሆን፣ የብሬግዚት ሚኒስትሩ አገራቸው የተባለውን ክፍያ እንደማትፈጽም አስታውቀዋል፡፡
ህብረቱ እንግሊዝን ይህን ያህል ገንዘብ ለማስከፈል ማቀዱን ፋይናንሺያል ታይምስ ጋዜጣ ሰሞኑን መዘገቡን ተከትሎ፣ ሚኒስትሩ ዴቪድ ዴቪስ እንግሊዝ ክፍያውን አትፈጽምም ሲሉ በይፋ ማስታወቃቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት ይህን ያህል ገንዘብ እንዲከፍል ከአውሮፓ ህብረት በይፋ የቀረበለት ጥያቄ እንደሌለ የጠቆሙት ሚኒስትሩ፣ የተባለውን ክፍያ እንድንከፍል የሚያስገድዱ ህጎች እንዳሉና እንደሌሉ በዝርዝር ከመወያየት በዘለለ 100 በሊዮን ዩሮ አንከፍልም ሲሉም አክለዋል፡፡  
ህብረቱ እንግሊዝን 100 ቢሊዮን ዩሮ ያህል ገንዘብ ለማስከፈል ያቀደው ከአባልነቷ በመውጣቷ ሳቢያ የሚከሰቱ ወጪዎችን ለማካካስ ነው መባሉን የጠቆመው ዘገባው፣ የገንዘብ ክፍያው እንዲፈጸም ጥያቄውን ያነሱት አገራትም ፈረንሳይና ጀርመን ሊሆኑ ይችላሉ መባሉንም ገልጧል፡፡

  የኡጋንዳ ፖሊስ ባለፈው ረቡዕ የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀንን ለማክበር በመዲናዋ ካምፓላ ወደሚገኙ ጎዳናዎች ከወጡ የአገሪቱ ጋዜጠኞች መካከል ስድስቱን ማሰሩን ኒውስዊክ ዘግቧል፡፡
የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀን የት ይከበር በሚለው ጉዳይ ላይ በኡጋንዳ የጋዜጠኞች ማህበር አመራሮች መካከል ልዩነት መፈጠሩን ተከትሎ፣ የተወሰኑ የማህበሩ አባላት ዕለቱን ለማክበር ወደ አደባባይ ወጥተው በአመራሮቻቸው ላይ ተቃውሟቸውን ባሰሙበት ወቅት የከተማዋ ፖሊስ “ሰልፉን ለማካሄድ ህጋዊ ፈቃድ አላገኛችሁም” በሚል ስድስት ያህል ጋዜጠኞችን ማሰሩን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የከተማዋ ፖሊስ በፕሬስ ነጻነት ቀን በጋዜጠኞች ላይ የወሰደው እርምጃ የመንግስት ባለስልጣናትን ማስቆጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለስልጣናቱ ባስተላለፉት ፈጣን ትዕዛዝ ጋዜጠኞቹ ክስ ሳይመሰረትባቸው በሰዓታት ልዩነት ከእስር እንዲለቀቁ መደረጉንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ባለፈው ሳምንት ባወጣው የ2017 የአለማችን አገራት የፕሬስ ነጻነት ደረጃ  መሰረት፤ ኡጋንዳ በፕሬስ ነጻነት ከአለማችን 180 አገራት 112ኛ ደረጃን መያዟንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

  በፌስቡክ የማህበራዊ ድረገጽ በኩል ጽንፈኝነትን የሚያስፋፉና አንባቢያንን የሚያሸብሩ መልዕክቶችን የሚያሰራጩ ተጠቃሚዎችን የሚያድኑና እርምጃ የሚወስዱ ተጨማሪ 3 ሺህ ተቆጣጣሪ ሰራተኞችን ቀጥሮ ሊያሰማራ እንደሆነ ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፌስቡክ ተጠቃሚዎችን ወደ ጽንፈኝነት የሚስቡና የፍርሃትና የመሸበር ስሜትን የሚፈጥሩ መልዕክቶችና ቪዲዮዎች በከፍተኛ ሁኔታ እየተበራከቱ መምጣታቸውን ተከትሎ፣ የኩባንያው መስራች ማርክ ዙከርበርግ ጉዳዩን ለመግታት በማሰብ፣ ተጨማሪ ተቆጣጣሪዎችን ቀጥሮ ወደ ስራ እንደሚያስገባ ባለፈው ረቡዕ አስታውቋል፡፡
ተጠቃሚዎች መሰል መልዕክቶችንና ቪዲዮዎችን በፌስቡክ ላይ ሲያገኙ በአፋጣኝ ለኩባንያው 4ሺህ 500 ያህል ተቆጣጣሪዎች ጥቆማ መስጠት የሚችሉበት አሰራር ተቀይሶ እየተሰራበት እንደሚገኝ የተነገረ ሲሆን ኩባንያው ድርጊቱን በፈጸሙ ተጠቃሚዎች ላይ አፋጣኝ እርምጃ እንደሚወስድም ተነግሯል፡፡
ፌስቡክ በየሳምንቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መሰል ጥቆማዎችና የቅሬታ መልዕክቶች እንደሚደርሱት የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ እነዚህን በርካታ ጉዳዮች አጣርቶ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት እንዲችል እስከ አመቱ መጨረሻ ድረስ ተጨማሪ 3 ሺህ ያህል ተቆጣጣሪዎችን ለመቅጠር ማቀዱንም ገልጧል፡፡

 አቶ ዳጂ ጃራ ኩምቢ በተባሉ ባለሀብት በአዳማ ከተማ ወንጂ መታጠፊያ ላይ የተሰራውና 55 ዘመናዊ የመኝታ ክፍሎች ያሉት ደንበል ቪው ኢንተርናሽናል ሆቴል ዛሬ ይመረቃል፡፡ ሆቴሉ ሁሉም ነገር የተሟሉለት ሱትስ፣ 2 ደሉክስ ቲውን፣ 21 ደሉክስ ስታንዳርድ፣ 13 ሲንግል ስታንዳርድና 12 ሲንግል ክፍሎች ሲኖሩት፣ ከ30 እስከ 300 ሰዎች ማስተናገድ የሚችሉ 4 አዳራሾች አሉት፡፡ ክፍሎቹ፣ ቲቪ፣ ስልክ፣ ጠረጴዛና ወንበር፣ ሶፋ፣ ሻወር፣ ነፃ ዋይፋይ … ያሉት ሲሆን እንግዶችን የሚያረካ አገልግሎትና መስተንግዶ ለመስጠት እየተጠባበቀ ነው ተብሏል፡፡

   ‹‹ለሠራተኞቻችን በምንሰጠው ልዩ ትኩረት እንለያለን››
                      
     በእንግዶች፣ በሠራተኞችና አብረውት በሚሰሩ ባለድርሻ አካላት ተመራጭ እንዲሆን በትጋት እንደሚሰራ የጠቆመው ሳፋሪ አዲስ ሆቴል፤ የዛሬ ሁለት ሳምንት በይፋ ሥራ እንደሚጀምር ተገልጿል።
የሳፋሪ አዲስ ሆቴል ልዩ አማካሪ አቶ ዜናዊ መስፍንና የሆቴሉ ማኔጅመንት አባላት ባለፈው ማክሰኞ በቦሌ መንገድ ከቴሌ ዝቅ ብሎ በሚገኘው የሆቴሉ አዳራሽ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ የሆቴሉ ዓላማ ልዩ አገልግሎት በመስጠት በሆቴል ኢንዱስትሪው ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረግና የአገሪቱን ቱሪዝም ገጽታ መቀየር ነው ብለዋል፡፡
በ1,3000 ስኩዌር ሜትር ላይ ያረፈው የዚህ ሆቴል ግንባታ 6 ዓመት እንደፈጀ የጠቀሱት የሆቴሉ ልዩ አማካሪ አቶ ዜናዊ፣ አሁን ዝግጅቱን አጠናቅቆ ግንቦት 5 በይፋ ስራ ይጀምራል ብለዋል፡፡
ሳፋሪ ማለት እንደ ወርቅ፣ አልማዝ፣ ፐርልና መሰል ማዕድናት የከበረ ድንጋይ ስያሜ ነው ያሉት ልዩ አማካሪው፤ ላለፉት 30 ዓመታት በወርቅና የከበሩ ድንጋዮች ንግድ ላይ ተሰማርተው የቆዩት የሆቴሉ ባለቤት አቶ ፍስሐ አባይ፣ ለሥራቸው ክብርና ማስታወሻ ይሆን ዘንድ ሆቴሉን ‹‹ሳፋሪ›› ብለው መሰየማቸውን ገልጸዋል፡፡
ሆቴሉ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ 64 ደሉክስ፣ 8 ባለ ሁለት አልጋ (ትዊንስ)፣ 26 ሱትና 24 ስታንዳርድ የመኝታ ክፍሎች ሲኖሩት፣ ረዥም ጊዜ የሚቆዩ እንግዶች፣ ምግባቸውን የሚያዘጋጁባቸው 8 አፓርትመንት ክፍሎች ከተሟላ የወጥ ቤት ዕቃዎች ጋር ተደራጅተው ይጠብቋቸዋል፡፡
2 ሬስቶራንቶችና 3 ባሮች ያሉት ይኼው ሆቴል፤ ከ20-50 ሰዎች ማስተናገድ የሚችሉ አራት አዳራሾች ያሉት ሲሆን በሆቴሉ ላረፉ እንግዶችና ለውጭ ተጠቃሚዎች የጂምናዚየምና የስፓ  (ስቲም፣ ሳውና፣ ጃኩዚ ማሳጅ) አገልግሎት በባለሙያ ይሰጣል፡፡  ለወንዶችና ለሴቶች የፀጉር ውበት፣ የእጅና የእግር ጥፍር ማስዋቢያ አገልግሎት እንደሚሰጥም ታውቋል፡፡
ሆቴሉ፣ 60 መኪኖችን ማቆም የሚችል ስፍራ ሲኖረው፤  ቦታው በሆቴሉ ለሚያርፉና ለውጭ እንግዶች ይበቃል ወይ? ተብለው የተጠየቁት አቶ ዘናዊ ሲመልሱ፤ ‹‹ሆቴሉ ቢዝነስ ስታይል ነው። በርካታ መኪና ማቆሚያ የሌላቸው የዚህ ዓይነት ሆቴሎች በአሜሪካም ሆነ በሌሎች አገራት በብዛት አሉ›› ብለዋል፡፡
በግንባታ ወቅት ለ700 ሰራተኞች የሥራ ዕድል እንደፈጠረ የጠቀሱት ልዩ አማካሪው፤ ‹‹ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር ከ200-230 ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል፤ ሳፋሪ አዲስ፤ ለሠራተኞቹ የላቀ ልዩ ትኩረት ይሠጣል›› ብለዋል፡፡
እኛን ልዩ ከሚያደርጉን ነገሮች አንዱ፣ ከእንግዳውም በላይ ለሰራተኞቻችን የምንሰጠው የቅድሚያ ትኩረት ነው፡፡ ምክንያቱም በማኔጅመንቱ አስተዳደር ደስተኛ ያልሆነ ሰራተኛ፤ እንግዶችን በጥሩ ሁኔታ አያስተናግድም፡፡ ስለዚህ ሠራተኞቹ፣ የባለቤትነት ስሜት ተሰምቷቸው፤ ‹‹ሆቴሉ የኛ ነው›› ብለው እንዲቀበሉ፣ ከደሞዝና ከደረጃ ዕድገት በተጨማሪ የተለያዩ ጥቅማ ጥቅሞችን ያገኛሉ፡፡ የስራ ላይና ከውጭ አገር ባለሙያ አስመጥተን ሥልጠና እንሰጣቸዋለን፡፡ በዚህ ዓይነት የሠራተኞችን ፍልሰት እንቀንሳለን ብለን እናምናለን›› ብለዋል- አቶ ዜናዊ፡፡
‹‹ከሠራተኞች 40 በመቶ ያህሉ ከዚህ በፊት ምንም ዓይነት የሆቴል ሥራ ልምድ የሌላቸውና እኛው እዚሁ ያሰለጠንናቸው ናቸው፡፡ የቀጠርናቸው ሰራተኞች ከትምህርና ከሥራ ልምድ ባሻገር ከ7 የሚበልጡ ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አቀላጥፈው የሚናገሩ ናቸው›› በማለት አስረድተዋል፡፡
ምናልባትም በአዲስ አበባ የመጀመሪያው እንደሆነ የሚነገርለት ግዙፍና እጅግ ዘመናዊ መሳሪያዎች የተገጠሙለት የላውንደሪ ክፍሉ፤ ለሠራተኞች ዩኒፎርም፤ ለእንግዶችና ለውጭ ተጠቃሚዎች አገልግሎት ይሰጣል ብለዋል፡፡