Administrator

Administrator

በአፍሪካ ቀንድ በአይነቱ የመጀመሪያው ነው ተብሏል
የኢትዮጵያ የንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የአሜሪካ የንግድ ምክርቤት አካል ከሆነው አለማቀፍ የግል ንግድ ተቋማት ማዕከል (CIPE) ጋር በመተባበር ያቋቋመውና በአፍሪካ ቀንድ በአይነቱ የመጀመሪያው እንደሆነ የተነገረለት የንግድ ስራ ስልጠና አካዳሚ ባለፈው ማክሰኞ ተመርቆ ተከፈተ፡፡
የኢትዮጵያ የንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን በአካዳሚው የምረቃ ስነስርዓት ላይ እንደተናገሩት፣ በአገሪቱ የንግድ ስራ የልህቀት ማዕከል በመሆን እንዲያገለግል ታስቦ በአዲስ አበባ የተገነባው የዚህ የንግድ ስራ ስልጠና አካዳሚ መከፈት፣ በአገሪቱ የግል ዘርፍ ላይ መነቃቃትን የሚፈጥር ነው፡፡
በአገሪቱ ያለው የግሉ ዘርፍ እንቅስቃሴ ከተለምዷዊ አስተሳሰቦችና አሰራሮች መላቀቅና በዘመናዊ የንግድ ስራ ንድፈ ሃሳቦችና አሰራሮች መመራት እንደሚኖርበት የገለጹት ወ/ሮ ሙሉ፣ አካዳሚው ለንግዱ ማህበረሰብ አባላትና ለሚመለከታቸው ድርጅቶች ሰራተኞች ተገቢውን ስልጠና በመስጠት፣ የግሉን ዘርፍ አቅም በማሳደግ ረገድ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት አስረድተዋል፡፡
ከምክር ቤቱ የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው፣ የስልጠና ማዕከሉ የኢትዮጵያ የንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤትንና  የአባል ድርጅቶችን የአመራርና የአስተዳደር ክህሎት የማጠናከርና ተቋማዊ አቅምን የመገንባት አላማ ያለው ነው፡፡ በንግዱ ዘርፍ በተሰማሩ ተቋማት መካከል ያለውን ግንኙነት፣ ትብብርና፣ ጥምረት ለማሳደግም ይሰራል ተብሏል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ከፍተኛ የህግ ባለሙያው ፕሮፌሰር ሞሃመድ ሃቢብ በበኩላቸው፣ መሰል አለማቀፍ ትብብር መፍጠር፣ ወቅቱን የጠበቀ የንግድ ስራ እውቀትን በማሰራጨት ረገድ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ጠቁመው፣ አካዳሚው መቋቋሙ በአገሪቱ ያለውን የግሉን ዘርፍ እንቅስቃሴ እንደሚያነቃቃና እድገቱን እንደሚያፋጥን  ተናግረዋል፡፡
የልህቀት ማዕከሉ መገንባቱና ተገቢውን ስልጠና መስጠቱ፣ የግሉ ዘርፍ በአገሪቱ ልማትና እድገት ላይ የሚጠበቅበትን የመሪነት ሚና እንዲጫወት የሚያስችል መነሳሳት እንደሚፈጥርም አክለው ገልጸዋል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በተከናወነው የአካዳሚው የምረቃ ስነስርዓት ላይ የመንግስት ተወካዮች፣ የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች፣ የአለማቀፍ የልማት ድርጅቶች ተወካዮች፣ የኢትዮጵያ የንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት አጋሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል፡፡
የኢትዮጵያ የንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት፣ ከ60 አመታት በላይ የአገሪቱን የንግድ ማህበረሰብ ማገዝ የሚያስችሉ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱ ተነግሯል፡፡

      በኢትዮጵያ የቴሌኮም ፕሮጀክቶች ላይ ላለፉት 12 ዓSqƒ ሲሰራ የቆየው ዜድቲኢ፣ አሁን በመካሄድ ላይ በሚገኘው የቴሌኮም ማስፋፊያ ፕሮጀክት 50 በመቶ ድርሻ መውሰዱ የሚታወቅ ሲሆን፤  በኤሌክትሪክ ሃይል ስርጭት፣ በትምህርት አቅርቦትና በከተማ አስተዳደር ዙሪያ ሶስት የቴክኖሎጂ ውጤቶቸን ለኢትዮጲያ ገበያ አስተዋወቀ፡፡
ፓወር ግሪድ፣ ኢለርኒንግ እና ስማርት ሲቲ በመባል የሚታወቁት እነዚህ ቴክኖሎጂዎች የተሣለጠ የከተማ አኗኗር ለመፍጠር የሚያስችሉና በከተማ አስተዳደር ውስጥ ወሳኝ የሚባሉትን መሰረታዊ መረጃዎች በማጠናቀር አመራራርን ዘመናዊ ለማድረግ የሚያግዙ ናቸው፡፡
የኢትዮጲያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት በተገኙበት ለሀገር ውስጥ ገበያ የተዋወቁት የቴክኖሎጂ ውጤቶች በፍጥነት እያደገች ባለችው ቻይና እና በአለም አቀፍ ደረጃ ተተግብረው ከፍተኛ ስኬት ያስመዘገቡ መሆናቸውን ዜድቲኢ ገልፆ፤ በአለም አቀፍ የቴክኖሎጂ አምራችነት ቀዳሚ ስፍራ ለማግኘት አስችለውኛል ብሏል፡፡
ስማርት ሲቲ የተሰኘው ቴክኖሎጂ የ2013 የአለም አቀፍ የሞባይል ቴክኖሎጂ የሽልማት አሸናፊ እንደሆነና በቤጂንግ ከተማ ተተግብሮ የአለም አቀፍን የፈጠራ ተሸላሚ ለመሆን እንደበቃ ኩባንያው ገልጿል፡፡  ኢለርኒግና ፓወር ግሪድ የተባሉት ቴክኖሎጂዎችም ከቻይና በተጨማሪ በሞሪሺየስ፣ ፓፓዋ ኒው ጊኒ፣ በአሜሪካ፣ በቬንዙዌላ እና በኬኒያ ተሞክረው ውጤታማ መሆናቸው ተነግሯል፡፡
በፍጥነት እያደጉ ባሉባት የኢትዮጵያ ከተሞች ውስጥ እነዚህ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተተግብረው ውጤታማ እንደሚሆኑ ዜድቲኢ ጠቅሶ፤ የኢትዮጵያ የህዝብ ብዛት በ2020 ወደ 120 ሚሊዮን ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅና ከዚህም ውስጥ 60 በመቶ ያህሉ በከተማ ይኖራል ተብሎ እንደሚገመት ገልጿል።

Monday, 31 March 2014 11:07

የጥንቱ አገረሸ

ሁሉን የሚችል ዳስ አንጣሎ፤ ገትሮ
ደልድሎ፤ አሳምሮ
ሊጡ ተቦካና እንጀራው ተጋግሮ
ለብሶ ተከምሮ፤
ጠጁ ተጣለና በጠላ ጉሮሮ
ሊወርድ ተደርድሮ፤
ወጡ በያይነቱ ባዋቂ ተሠርቶ፤
ቁርጡ ተሰናድቶ፤
ሰው ሁሉ ለመብላት፤ ለመጠጣት ጓጉቶ፤
ሲጠብቅ ሰንብቶ፤
አዝማሪው ለዘፈን ቆሞ ተዘጋጅቶ፤
ማሲንቆው ተቀኝቶ፤

ጨዋታ ፈረሰ!
ዳቦ ተቆረሰ!
ሙሽራው ጠፋና ሠርጉ ተበላሸ፤
የተጠራው ሸሸ፤
ጊዜ ከዳውና በጊዜው ላመሸ፤
ዳሱ ተረበሸ፤
የጥንቱ አገረሸ፡፡
(ከፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም
“ዛሬም እንጉርጉሮ” የተሰኘ የግጥም መድበል የተወሰደ)

የአሜሪካ መንግሥት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መርጦ ለመሸለም ጥሪ ማድረጉን የፓርቲው ልሳን ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ዘግቧል፡፡ በሌላ በኩል ከአሜሪካ ኤምባሲ በኩል የተገኙ መረጃዎች የሰማያዊ ፓርቲ መሪ የተመረጡት የአሜሪካ  ስቴት ዲፓርትመንት  በየዓመቱ ለሚያዘጋጀው የሊደርሺፕ ፕሮግራም እንጂ ለሽልማት አይደለም ይላሉ፡፡  የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው የፓርቲውን ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃልን በጉዳዩና ኤርፖርት ላይ በገጠማቸው ችግር ዙርያ አነጋግራቸዋለች፡፡

ወደ አሜሪካ ለመጓዝ ኤርፖርት ከገቡ በኋላ ችግር እንደገጠመዎት ሰምቻለሁ፡፡ ችግሩ ምን ነበር?
በአሜሪካ መንግስት ተጋብዤ ለሶስት ሳምንት የምቆይበት “ወጣት የአፍሪካ መሪዎች” የሚል ፕሮግራም ነበር፡፡ በሉፍታንዛ ነበረ የምሄደው። በኤርፖርት ውስጥ አስፈላጊውን ሂደት ሁሉ አልፌ የኢሚግሬሽንና ደህንነት ሰዎች ፎቶ ወስደው ፓስፖርቴን ተቀበሉኝና አንደኛው አለቆቹ ጋር ይዞኝ ሄደ፡፡ ለሶስት ሰዓት ያህል አንድ ክፍል ውስጥ አቆዩኝ፡፡ መጨረሻ ላይ ከፓስፖርቴ ውስጥ አንድ ገፅ ነቅለው አውጥተው … “አንድ ገፅ ወጥታለች” ብሎ ቀዶ አመጣልኝ … እቃዬ አውሮፕላኑ ውስጥ ገብቶ ነበር፤ እሱንም አወረዱት፡፡ ባለፈው ሰኞ ነበር አሜሪካ መገኘት የነበረብኝ፤ ለጊዜው ተስተጓጉሏል።
የአሜሪካ መንግስት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል እንደሸለማችሁ ባለፈው ሳምንት በፓርቲያችሁ ልሳን ላይ ተዘግቧል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ዕድሜው አጭር ከመሆኑ አንፃር ሽልማቱ ይገባናል ትላላችሁ?
ኢትዮጵያ ከዓለም የመጨረሻ ድሃ አገር ናት፡፡ አገሪቱን ከድህነት ለማውጣት የልጆቻችንን ዕድሜ የሚጠይቅ ተከታታይ ሥራ እና ትግል የሚያስፈልገው ነው፡፡ ሥራችንን የምትለኪው ግን በአንፃራዊነት ነው፡፡ ለምሳሌ ሰልፍ የሚባል ነገር ለስምንት አመት ኢትዮጵያ ውስጥ የማይታሰብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሁሉም ፓርቲዎች ሰልፍና የአደባባይ የፖለቲካ ስራን እንደ ባህል እየያዙትና፤ እየተነቃቁም ናቸው። የሌሎች ፓርቲ አመራሮች “ህዝቡ ፈርቷል፤ ሰልፍ አይወጣም፣ አይተባበረንም” በሚል ዝም ብለው የመግለጫ ስራ ነበር የሚሰሩት፡፡ አሁን  ነገሮች ተለውጠዋል፡፡ አዲሱ ትውልድ በፊት ተከታይ እንጂ የራሱ ሀሳብ ኖሮት የሚሳተፍ አልነበረም። በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ ግን ሌት ተቀን የሚተጉ ሰዎችን ታያለሽ… እስከመታሰርም ደርሰዋል፡፡ ይህም የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ የሚታየው የተፈጠረው የፖለቲካ መነቃቃትና ግንዛቤ ነው እንጂ የሀገራችንን ችግር ሰማያዊ ፓርቲ ፈትቶ ይጨርሰዋል ወይ ብትይ …. ትውልዱም የሚጨርሰው አይመስለኝም። ብዙ ተከታታይ ስራዎች ይጠይቃል፡፡ ከነበርንበት ጨለማ አንፃር ነው መታየት ያለበት፡፡ ቅንጅት በመፍረሱ ህዝቡ  ተስፋ ቆርጧል፡፡ ኢህአዴግ ጠቅላይ  በመሆኑና አፋኝ አዋጅ በመያዙ ዘላለማዊ ይመስል ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ያንን አስቸጋሪ ሁኔታ ወደ ይቻላል በማምጣትና መነቃቃት በመፍጠር የፖለቲካ ድባቡን ቀይሮታል፡፡ ይሄ ደግሞ ረጅም ጊዜንና ትልቅ ስራን የሚጠይቅ ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ግን በአጭር ጊዜ ይሄንን ማድረግ ችሏል፡፡ ከዚህ መንፈስ ነው የሚታየው እንጂ እኛ ብዙ ሰራን ብለን አንኩራራም፡፡ ገና ብዙ ስራ ነው የሚቀረን፤ ወደፊትም ብዙ እንሰራለን፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ አሁን በዘረዘሩልኝ ምክንያቶች በአሜሪካ መንግስት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል ሸልሞታል፤ ሽልማቱም ይገባናል እያሉኝ ነው?
አዎ .. በደንብ ተሸልመናል፡፡ ሽልማቱም ይገባናል፡፡ ሽልማቱ ይገባናል ስንል ግን አሜሪካኖች አይደሉም የሚሸልሙንና የሚያወድሱን፡፡ ግን በራሳቸው መመዘኛ እኛን መምረጣቸው መልካም ነገር ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የሚያድግ ፓርቲ ነው፡፡ በኢትዮጵያ 70 ከመቶ የሚሆነው ህዝብ ወጣት ነው፡፡ ወጣቱን ሊወክል የሚችል ፓርቲ ነው፡፡ አዲስ አስተሳሰብን እንደፈጠረ ሃይል፣ ሽልማትን አስበን አይደለም የምንሰራው፡፡ ከዚህ በላይ ለሃገራችን ብዙ መስራት ይጠበቅብናል፡፡
በየጊዜው የተለያዩ ፖለቲከኞች ለህዝብ የገቡትን ቃል ሳይፈጽሙ ሸርተት ይላሉ፡፡ ህዝቡን ከዚህ ዓይነቱ ጥርጣሬ እንዴት ማውጣት ይቻላል ይላሉ?
ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም፡፡ ከዚህ በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ በተደጋጋሚ ውጤት ያልመጣው የግለሰብ ፖለቲካ በመሆኑና ፖለቲካው በሰዎቹ ስብዕና ላይ በመመስረቱ ነበር፡፡ ይሄም ትግሉን ጎድቷል፡፡ ለዚህ መፍትሔው ትግሉን ህዝባዊ ማድረግና በአንድ ሰው ላይ አለመንጠልጠል ነው፡፡ ህዝቡ ፖለቲካውን የራሴ ነው ብሎ መያዝ አለበት፡፡ ግለሰቦች ሲሄዱ ሌሎች ይተካሉ፡፡
ኢትዮጵያ የወላድ መካን አይደለችም፤ ብዙ ልጆች አሏት፡፡ ፖለቲካውን የጋራ ካደረግነው የህዝቡ ስጋት ይቀንሳል፡፡ ፖለቲካ የዜግነት ጉዳይ ነው፤ ሁሉም መሳተፍ አለበት፡፡ ያ በሆነ ጊዜ ራሳቸውን ብቻ ለአገር ጠቃሚ አድርገው የሚያስቡ ሰዎች መመፃደቃቸውን ያቆማሉ፡፡ ያኔ መግነንም አምባገነንነትም ይጠፋል፡፡ ፓርቲውም ህዝባዊነት ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ልጆች የትኛውም ቦታ ላይ ተወዳድረውና ሰርተው መኖር የሚችሉ ናቸው፡፡ በዚህ በአሰልቺና በተጠላ ፖለቲካ ውስጥ የገቡት የአገር ፍቅር ስላላቸው ነው፡፡ የአገር ፍቅር ደግሞ ከየትኛውም ሽልማትና ሞገስ በላይ ነው፡፡   
ከወር በፊት ለፓርቲ ሥራ ወደ አሜሪካና አውሮፓ ተጉዘው ነበር፡፡ የተለያዩ ስብሰባዎችንም ከዳያስፖራው ጋር አድርጋችኋል፡፡ በዚህ ጉዞ ዋና ዓላማችሁ ምን ነበር?
ሁለት ወር ነው የቆየሁት፤ አውሮፓ አስራ አምስት ቀን፣ አሜሪካ 45 ቀን ያህል፡፡ አትላንታ፣ ሳንሆዜ፣ ቦስተን፣ ላስቬጋስ፣ ሎስአንጀለስ፣ ሲያትል… ነበርኩ። የመጀመሪያ ስብሰባዬ ዲሲ ነበር፡፡ የስብሰባው ዓላማ ሰማያዊ ፓርቲ የተመሰረተባቸውን መሰረታዊ አላማዎችና ምሰሶዎችን ማስተዋወቅ ነበር፡፡ እዚህም አብዛኛውን ቅዳሜና እሁድ ምሁራንን ቢሮዋችን ውስጥ እየጋበዝን በፀረ ሽብር ህጉ፣ በመሬት ፖሊሲ፣ በአጠቃላይ በኢኮኖሚ በታሪካችን ዙሪያ በመወያየት ሰማያዊ ፓርቲ ያለውን አቋም ለህዝብ በተደጋጋሚ ይገልጽ፣ ያስተምር ነበር፡፡ የአሜሪካና አውሮፓ ጉዞ ዓላማ፣ በውጭ ያለው ኢትዮጵያዊ ለሰማያዊ ፓርቲ ሀሳቦችና ፕሮግራሞች ድጋፍ እንዲሰጥና የትግል ስልቶቻችንንም ጭምር ለማስተዋወቅ ነበር፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ሀይል እንጂ ድርጅታዊ መዋቅር የለውም፤ የንቅናቄ ፓርቲ ነው፤ የበሰለ ፖለቲካ አያራምድም የሚል ትችት ይሰነዘርባችኋል? እርስዎ ምን ይላሉ?
የሞተን ፖለቲካ ልታነሺ የምትችይው፤ ህዝብ ሲከተልሽና መነቃቃትን መፍጠር የምትችይው የአገሪቱን ችግር በሚገባ መረዳት ሲቻል፣ ለዚያ ችግር መፍትሄ ሊሆን የሚችል ቀጥተኛ ፖሊሲ ሲኖር፣ ፖሊሲውን ለማስፈፀም ደግሞ ብቃት ያለው አመራር ሲኖር ነው ህዝቡ የሚነቃነቀው፡፡ በስልጣን ላይ የተቀመጡ ሰዎች ፖሊሲ አላቸው፤ ሰማያዊ ፓርቲዎች ግን ፖሊሲ የላቸውም ቢባል ለአመለካከት የማይመች ነው የሚሆነው፡፡ በመሰረቱ አንድ ሰው ሊነቃነቅ የሚችለው  የሚያምንበት ነገር ሲኖር ነው። መነቃነቅ ከተፈጠረ እምነት አለ፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎች በህብረት ለመስራት የትብብርና የውህደት እንቅስቃሴ ላይ ቢሆኑም ሰማያዊ ፓርቲ ለውህደት ዳተኝነት ይታይበታል የሚል ትችት ይሰነዘርበታል…
በኢትዮጵያ የ40 ዓመት የፖለቲካ ፓርቲዎች ታሪክ “ዛሬ ተዋህደው፤ ነገ ፈረሱ” ሲባል ነው የምናውቀው፡፡ ይሄ እንዲቀጥል አንፈልግም፡፡ ስለዚህም የውህደትንና የጥምረትን ነገር በጥንቃቄ መመርመር እንፈልጋለን፡፡ በሆይሆይታ የሚፈጠሩ ጥምረቶችና ውህደቶች ውጤቱ ሲያመጡ አልታየም። ለምሳሌ አንድነት ወደ መድረክ የገባው በጣም ፈጥኖ ስለነበር ራሱን ጎድቷል፡፡ እናም አንድነት ከመድረክ ታገደ ተባለ፡፡ ሰላሳ ሶስት ፓርቲዎች ተቋቁመው ምንም ነገር ሳይፈይዱ ነው የከሰሙት። በቅርቡ ደግሞ “አንድነትና መኢአድ ለውህደት እየተነጋገሩ ነው” ሲባል ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ተቋረጠ ተብሏል፡፡ እኛ ጥናት ሳይደረግ በፍጥነት ሮጠን ወደ ውህደት አንገባም፡፡ ወደ ፖለቲካው ያልገባ አዲሱ ትውልድ አለ፤ ፓርቲዎች አካባቢ ጊዜ ከምናጠፋ እዛ ላይ አተኩረን ህዝብ ውስጥ ብንሰራ ጉልበትም፣ ሀይልም፣ ዕውቀትም ገንዘብም አለ የሚል አቋም ይዘን ነው የምንንቀሳቀሰው፡፡ በመርህ ደረጃ ግን ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ለመስራት ሰማያዊ ፓርቲ ዝግጁ ነው፡፡
የምርጫ ስነ ምግባር ኮዱን አንፈርምም ብላችኋል፡፡ ለምንድነው ለመፈረም ያልፈለጋችሁት?
አንድ ህግ በሀገር ደረጃ ህግ ሆኖ ከወጣ በኋላ መፈረም አለመፈረም አስገዳጅ አይደለም፤ ትክክለኛም አሰራር አይደለም፡፡ ለምሳሌ የማናምንባቸው አዋጆች ሁሉ ወጥተዋል፡፡ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣ የመሬት ሊዝ አዋጅ፣ የሲቪክ ማህበራት ማደራጃ፣ የሚዲያና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ወጥተዋል፡፡ እነዚህን አዋጆች ሰማያዊ ፓርቲ አፋኝ አዋጆች ናቸው ብሎ ያምናል፡፡ ህግ ሆነው ከወጡ በኋላ ግን ህገመንግስታዊ በሆነ መንገድ እስከ ምንቀይራቸው ድረስ ለአዋጆቹ መገዛት ግዴታችን ነው፡፡ የስነ ምግባር ደንብና አዋጅ በፓርላማ ህግ ሆኖ ፀድቋል፤ ለእሱ ብቻ መፈረም አያስፈልግም። አዋጅ በወጣ ቁጥር እኮ አንፈርምም፡፡ አጀንዳ ሆኖም መቅረብ የለበትም፡፡ ኢህአዴግ ለድርድር እንቅፋት ለመፍጠር ሲፈልግ ያመጣው ነው፡፡

“አፉን ከወጋኸውማ አሰፋኸው!”
(የጐንቸ ኤትወኸተታ ወካዀንም ቢውሪ አንቃታ ባረም፣
አንቃሸታ ቦካዀ አቤተትዀንም) - የጉራጊኛ ተረት

በዩናይትድ ስቴትስ እንደቀልድ የሚወራ ዛሬ ተረት የሆነ አንድ ትርክት አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዝቅ ብሎ የህዝቡን የኑሮ ደረጃ ማየት ወሳኝ ነው በሚል እሳቤ፣ በመጀመሪያ የሴተኛ አዳሪዎችን ህይወት  ሊያዩ ሄዱ፡፡ ሦስት ዓይነት ደረጃ ያላቸው ሴቶችን አገኙ ይባላል፡፡
አንደኛ ደረጃ የምትባለዋ ባለ ወርቃማ ፀጉት ናት፡፡
ሁለተኛ ደረጃ የምትባለው ባለቀይ ፀጉር ናት፡፡
ሦስተኛ ደረጃ የምትባለው ባለጥቁር ፀጉር ናት፡፡ ይቺኛዋ የኑሮ ደረጃዋ የመጨረሻ ዝቅ ያለ ሴት ናት ማለት ነው። በመጀመሪያ አንደኛ ደረጃዋ ዘንድ ይሄዱና፤
“እኔ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነኝ፡፡ ከአንቺ ጋር አንድ ምሽት ማሳለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ምን ያህል ገንዘብ ትጠይቂኛለሽ?” አሏት፡፡
ባለ ወርቃማ ፀጉሯ ሴትም፤
“ሰላሳ ሺ ዶላር ይበቃኛል” አለቻቸው፡፡
“ጥሩ፤ እንግዲህ ዘወር ዘወር ብዬ ሌሎችን አጠያይቄ እመለሳለሁ” ብለው ወደ ሁለተኛ ደረጃዋ ባለ ቀይ ፀጉር ሴተኛ አዳሪ ይሄዳሉ፡፡
ለእሷም፤
“እኔ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነኝ፡፡ ከአንቺ ጋር አንድ ማታ ማሳለፍና ተዝናንቼ ለማደር ምን ያህል ገንዘብ ይፈጅብኝ ይሆን?” ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡
ባለ ቀይ ፀጉራ ሴትም፤
“ሃያ ሺህ ዶላር በቂ ነው ለእኔ” ትላቸዋለች፡፡
ፕሬዚዳንቱም፤
“እስቲ ዘወር ዘወር ብዬ የተሻለ ክፍያ አገኝ እንደሆነ አጠያይቄ እመለሳለሁ፡፡ ይሄ የመጨረሻ ዋጋ መሆኑ ነው አይደለም?”
“አዎን” አለቻቸው ሳታመነታ፡፡ በመጨረሻ ወደ ዝቅተኛዋ ባለጥቁር ፀጉር ሴት ዘንድ ይሄዱና፤
“እኔ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነኝ፡፡ ከአንቺ ጋር አንድ ቆንጆ ምሽት ለማሳለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ምን ያህል ገንዘብ እንደሚያስፈልገኝ ንገሪኝ፡፡ ታዲያ፤ ምንም ሳትፈሪ የሚያዋጣሽን ሀቀኛ የገንዘብ መጠን ነው የምትነግሪኝ እሺ?” አሏት፡፡
ባለ ጥቁር ፀጉርዋ ሴተኛ አዳሪም አውጥታ፣ አውርዳ የሚከተለውን መልስ ሰጠቻቸው፡፡
ስድስት ቅድመ - ሁኔታዎችን ካሟሉ ከእኔ ጋር በነፃ ለማደር ይችላሉ፡፡ ብላ ጀመረች፡፡
ፕሬዚዳንቱም በችኮላ፣
“ምን ምንድናቸው?” ብለው ጠየቋት፡፡ ባለ ጥቁር ፀጉሩዋ ሴትም፤
“አይቸኩሉ፤ ልነግርዎት ነው፡፡ ደግሞም እርሶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ እንደሚያስረዝሙት አላንዛዛውም፡፡”
1ኛ/ ቀሚሴን በጣም ከፍ የሚያደርጉት የሚያስከፍሉኝን ቀረጥ ያህል ለመሆን ከቻለ፤
2ኛ/ የውስጥ ሱሪዬን ዝቅ የሚያደርጉት የሰራተኛው ህዝብ ዝቅተኛ ደሞዝ ድረስ ከሆነ፤
3ኛ/ የሰውነትዎ ጥንካሬ እንደ ኑሮ የከበደ ከሆነ፣
4ኛ/ በዚሁ ከባድና ጠንካራ ሁኔታ እኔ ለዳቦ ስሰለፍ የምቆመውን ያህል ጊዜ፤ ጠንክረው የሚቆዩ ከሆነ፤
5ኛ/ እቅፍዎ ውስጥ ሲያስገቡኝ፤ ከምኖርበት በክረምት ብርድ የተሞላ ቤት የተሻለ የሚሞቀኝ ከሆነ
6ኛ/ የፍቅር ጨዋታዎ ህዝቡን የሚጫወቱበትን ዓይነት ከሆነ፤ ነው፡፡ ዕውነቴን ነው የምልዎት አምስት ሳንቲም ሳይከፍሉ ከእኔ ጋር በነፃ ማደር ይችላሉ” አለቻቸው፡፡
*     *      *
የህዝብን የኑሮ ደረጃ ዝቅ ብሎ ወርዶ የሚያይ መሪ፣ አለቃ፣ ኃላፊ ማግኘት መታደል ነው፡፡ ያስቀናል፡፡ የዋጋ መናርና የታክስ ማሻቀብ አንድን ማህበረሰብ የጦርነትን ያህል ያጠፋዋል፡፡ ለዚህ ነው መሪዎች ሁሉ የህዝባቸውን ኑሮ በቅርብ ያስተውሉ የሚባለው፡፡ ህዝብ የሀገር ሙቀት መለኪያ ነው፡፡ ህዝብ የሚከፍለው ግብር ከሚያገኘው አገልግሎት ጋር ካልተመጣጠነ የቀዘቀዘች አገር ውስጥ ነው የሚኖረው፡፡ ህዝብ ደሞዙ ከሚኖረው ኑሮ ጋር ካልተመጣጠነለት ኖረ አይባልም፡፡ ህዝብ ከዕለት ዕለት ህይወት እየከበደው ከሄደ ከሳቁ ምሬቱ፣ ከደስታው ሐዘኑ እየበረታ ሥርዓቱን፣ አገዛዙን፣ ገዢዎቹን፣ አስተዳዳሪዎቹን ይጠላል፡፡ ሀገሩም የእሱ አትመስለውም፡፡ ህዝብ መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎችን ለማግኘት ነግ-ሠርክ የሚሰለፍ ከሆነ፤ አልፎ ተርፎም ከናካቴው ዕጥረት የሚከሰትበት ሁኔታ ከመጣ፣ ብሶቱ ወሰን አይኖረውም፡፡ ህዝብ በመኖሪያ ቤት ችግር የሚሰቃይ ከሆነ መሰረታዊ የኑሮ አስፈላጊ ነገር ጎሎበታል ማለት ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ የሚከፋው ደግሞ ይህንን የሚገልፅበት መንገድ ካጣና በፍርሃት ተሸማቆ ከተቀመጠ ነው፡፡ “አዲስ ያይጥ - ወጥመድ በሰራህ ቁጥር” አዲስ አይጥ የምትወለድ ከሆነ፣ ወይ ወጥመዷ ላይ ወይ አጥማጁ ላይ ችግር አለ ማለት ነው” ይባላል፡፡ በሙስና የተሞላ ልማት ዘርዛራ ወንፊት ነው፡፡ ዕብቁንም፤ እንክርዳዱንም፤ እያሳለፈ፤ እያዩ እህል አለን እንደሚሉት አይነት የዋህነት ይሆናል፡፡ የዚህ ሁሉ መጨረሻው ድህነት ነው፡፡ ድህነት ሲመጣ ቃላት ይበዛል። ስብሰባ፣ ንግግር፣ የማይተገበር ቃል - መግባት እንደህይወት ይወሰዳል፡፡ እንደኑሮ ይለመዳል፡፡ “አንድ መንግሥት ከሌላ መንግሥት የሚማረው ጥበብ ከህዝብ ኪስ ገንዘብ አሟጥጦ መውሰድ ነው” ይለናል፤ አዳም ስሚዝ የጥንቱ የጠዋቱ የኢኮኖሚ ሊቅ፡፡  
አንድ የአሜሪካኖች አባባል አለ:- “በአንድ አገር ከዋናው ይልቅ ምክትሉ ነው ምርጥ ሥራ አለው የሚባለው፡፡ ምክንያቱም ትልቁ ሥራው ጠዋት ሲነሳ ‘ዋናው አለቃ ደህና አደሩ?’ ማለት ብቻ ነው!” ከዚህ ይሰውረን፡፡
ኑሮ እጅግ በከፋ ሁኔታ ላይ ሲገኝ፤ እንግሊዞች “ሶስት ትውልድ ሙሉ ሸሚዛችንን እንደጠቀለልን አለን” ይላሉ፡፡ ጣሊያኖች ደግሞ፤ “ከከዋክብት እስከ ጋጣ/በረት እየኖርን ነው” ይላሉ፡፡ ስፔይኖችም፤ “ሀብትን፤ የሌለው ይሠራዋል። ያለው ያላግባብ ይጫወትበታል” ይላሉ፡፡ ኢትዮጵያውያን፤ “ኑ እስኪለን መከራችንን እናያለን” ይላሉ፡፡ አምላክ አንደኛውን እስከሚጠራን ቀን ድረስ አበሳ ፍዳችንን እየቆጠርን ነው እንደማለት ነው!! ሁሉ የምሬት ቋንቋ አለው! ጊዜውና ደረጃው ይለያይ እንጂ ምሬቱ የሚፈታበትም መንገድ እንደዚያው ይለያያል፡፡ ማናቸውም ዕቅድና ስትራቴጂ ህዝብ ኑሮ ላይ ያነጣጠረ መሆን አለበት፡፡ ይሄ ማለት የእርስ በርስ ሙግትና የአዕምሮ አክሮባት ከመሥራት ይልቅ፤ የህዝቡስ ሁኔታ እንዴት ነው? ማለት ዋና ጉዳይ ነው፣ ማለት ነው፡፡ ለህዝብ ተብሎ፣ በህዝብ ስም የተቀረፀውንም አጀንዳ ለግል ጥቅም እንዳይውል ጠንክሮ መጠበቅ ይገባል፡፡
በሀገራችን “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” የተባለው ተረት ዕድሜው እጅግ ረጅም ነው፡፡ የሥርዓቶቻችንን ያህል አርጅቷል፡፡ በተግባር ሲተረጐም ግን ገና ዛሬ የተወለደ ነው የሚመስለው፡፡ በየቢሮው፣ በየማህበሩ፣ በየፓርቲው የምናየው ሀቅ ነው፡፡ “አዲስ እረኛ ከብት አያስተኛ”፣ “እከክልኝ ልከክልህም” አብሮ ሲተረት የኖረ ነው፡፡ እዚህ ላይ፤ ሁለት የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ሲቀያየሩ ሂያጁ ለመጪው ያለውን መጥቀስ መልካም አርአያነት ያለው ነው:-
“እኔ ይሄን ሥልጣን (ቢሮ) ለቅቄ ስወጣና ወደቤቴ ስሄድ፤ የተደሰትኩትን ያህል አንተ ወደዚህ ሥልጣን በመምጣትህ የምትደሰት ከሆነ፤ በዚች አገር የመጨረሻው ከፍተኛ ደስተኛ ሰው አንተ ነህ ማለት ነው!” (ይህን የተባሉት አብርሃም ሊንከን ናቸው) ይሄ መታደል ነው፡፡ በማናቸውም መንገድ ሥልጣን ላይ የሚወጣ ሰው፤ “ሥልጣን በሸተተው ማግስት አካሄዱ ሁሉ ይለዋወጣል፤ እንደድመት ኮርማ ይሆናል” ይባላል፡፡ ከዚህም ይሰውረን። አክብሮታችን ለመንበሩ እንጂ ለሰውዬው አይደለም፡፡ ዞሮ ዞሮ ህዝብን ማገልገያ መንበር መሆን አለበት፡፡ አንዱ ባለሥልጣን ሌላውን ባለሥልጣን የጐዳ መስሎት በሚሠነዝረው ጥቃት የዝቅተኛው ክፍል ህዝብ መጠቃቱ ትልቅ ጉዳት ነው፡፡ አፍ በሰፋ ቁጥር ተሳዳቢው ህዝብ ነው፡፡ የሚላክበት ህዝብ ነው፡፡ ጎረቤትም ቢቆስል ጦሱ ላገር ነው፡፡ የቆሰለ አውሬ ለያዥ ለገራዥ አስቸጋሪ ነው፡፡ ጣጣው ግን የህዝብ ነው፡፡   
ለዚህ ነው “ጅቡን የወጋኸው ምኑን ነው?” ቢሉት፤
“አፉን” አለ፡፡ “አፉን ከወጋኸውማ አሰፋኸው” የሚለው የጉራጊኛ ተረት ለማንም የማስጠንቀቂያ ደውል የሚሆነው!! \\\

  • “በመንገድ ላይ ለሚደርሱ አደጋዎች የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ተጠያቂ ነው”
  • “መንግሥትን በሰራው ጥፋት መክሰስ ህገ-መንግስታዊ መብት ነው” - የህግ ባለሙያ

ለአዛውንቱ አቶ ተስፋዬ ኪዳኔ መስከረም 10 ቀን 2006 ዓ.ም መልካም ቀን አልነበረም፡፡ ከመ/ቤታቸው ወጥተው ወደ ቤታቸው እያመሩ ነበር፡፡ ከ5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ወደ ጌጃ ሰፈር በሚወስደው መንገድ ኮንዶሚኒየም ቤቶች አካባቢ ሲደርሱ በፍፁም ያልጠበቁት አስደንጋጭ አደጋ አጋጠማቸው፡፡ መንገድ ዳር ከሚገኝ ጉድጓድ ውስጥ ገብተው እግራቸው ተሰበረ፡፡
ከድንጋጤ ጋር ሙሉ ኃይላቸውን አሰባስበው ባሰሙት የድረሱልኝ ጥሪ፣ የአካባቢው ሰዎችና የእሳት አደጋ ሰራተኞች ተረባርበው ከጉድጓዱ በማውጣት ወደ ባልቻ ሆስፒታል ለህክምና ወሰዷቸው፡፡ በሆስፒታሉ ለ20 ቀን ተኝተው ከ23 ሺህ ብር በላይ አውጥተው ቢታከሙም እንደተመኙት በፍጥነት ከጉዳታቸው አገግመው በእግራቸው ቆመው ለመሄድ አልቻሉም። ይኸውና ላለፉት 7 ወራት ከሰውና ከክራንች ድጋፍ መላቀቅ አቅቷቸዋል፡፡
አሁንም በተመላላሽ ህክምናቸውን እየተከታተሉ ሲሆን አቶ ተስፋዬ ለደረሰባቸው ጉዳት ኃላፊነት የሚወስድ አካል የትኛው እንደሆነ ባለማወቃቸው መብታቸውን ማስከበርና ካሳ ማግኘት እንዳልቻሉ ይናገራሉ። “መንገዱ ላይ የተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ ነው የገባሁት፣ ኃላፊነቱን መውሰድ የሚገባው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ነው የሚል እምነት አለኝ። ነገር ግን አንድ ሰው የዚህ ዓይነት አደጋ ሲደርስበት በየትኛው የህግ አግባብ፣ ማንን መክሰስና መጠየቅ እንዳለበት አላውቅም” ብለዋል፡፡
እንደ አቶ ተስፋዬ ሁሉ ባለፉት 6 ወራት መንገድ ዳር ተቆፍረው ባልተከደኑ ጉድጓዶችና በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ ኩሬዎች ውስጥ ገብተው 41 ሰዎች መሞታቸውን፣106 ሰዎች መቁሰላቸውን ከአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠሪያ ኤጀንሲ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ዓምና በግማሽ አመት ውስጥ 28 ሰዎች በተመሳሳይ አደጋ ሲሞቱ፣ 88 ሰዎች ቆስለዋል፡፡ ይህም ዘንድሮ የአደጋው መጠመን መጨመሩን ያመለክታል፡፡  
“በአዲስ አበባ መንገዶች ላይ በየአምስት ሜትሩ ጉድጓድ አለ፡፡ አብዛኞቹ ጉድጓዶቹ በአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ለፍሳሽ (ድሬኔጅ) መውረጃ የተቆፈሩ ናቸው፡፡ ለቴሌኮም፣ ለመብራት ኃይል ኬብሎችና ለመሰል አገልግሎት የሚቆፈሩም አሉ፡፡ ጉድጓዶቹ ትላልቅ ስለሆኑ ከሰው ቁመት በላይ እስከ 2 ሜትር ጥልቀት ያላቸው ናቸው” ይላሉ፤የአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠር የኮሙኒኬሽ ኦፊሰር አቶ ንጋቱ ማሞ፡፡
ጉድጓዶቹ፣ በተለያዩ ምክንያቶች ክፍት ሊሆኑ ይችላሉ ያሉት አቶ ንጋቱ፤ ሕገ-ወጦች ክዳኑ  ላይ ያለውን ፌሮና ሌሎች ነገሮች ወስደው ክፍት ይተዋቸዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የጉድጓዶቹ ባለቤት የሆኑ ድርጅት ሠራተኞች ለሥራ ይከፍቱትና ሳይዘጉ ይተዋቸዋል፡፡ ሁሉም ጉድጓዶች ያሉት መንገድ ላይ ነው፡፡ እነዚህ ጉድጓዶች ብዙውን ጊዜ ጉዳት የሚያደርሱት በክረምትና በጭለማ ነው፡፡ በክረምት ፍሳሹ ሞልቶ አስፋልቱን ስለሚያጥለቀልቀው ጉድጓድ መኖሩ አይታወቅም፡፡ በጭለማም አይታይም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ለመንገድ ግንባታ ጉድጓዶች ይቆፈራሉ፡፡ ጧት ሥራ ስትሄድ ያልነበረ ጉድጓድ፣ ማታ ስትመለስ ተቆፍሮ ይጠብቅሃል፡፡ በሥራ መግቢያና መውጫ ሰዓት ጉድጓድ ስለመኖሩ የማያውቅ እንግዳና ሌላውም ሰው ትራንስፖርት ለመያዝ ሲጋፋ ጉድጓዶቹ ውስጥ ወድቆ ሊጎዳ ይችላል፡፡
ይኼ በከተማው መኸልም የሚታይ ነው፡፡ ከመዲናዋ ወጣ ብለው በሚገኙ የልማት ማስፋፊያ አካባቢዎችም ለኢንቨስትመንት በማለት ንፋስ ስልክ ላፍቶ ወረዳ አንድና ሁለት፣ ቦሌ ቡልቡላ ወረዳ አንድ፣ ቦሌ ኤርፖርቶች ድርጅት ጀርባ፣ ኮልፌ ቀራንዮ ሚኪሌይላንድ አካባቢ፣ ሐና ማርያም፣ ገርጂ ጊዮርጊስ … አካባቢዎች ድንጋይና ማዕድን ለማውጣት ፈቃድ ወስደው የሚቆፍሩ አሉ። የሚፈልጉትን ነገር ካገኙ በኋላ ለቀው ሲሄዱ የቆፈሩትን ጉድጓድ ሳይከድኑት ክፍቱን ትተው ነው የሚሄዱት፡፡ ያ ቦታ ውሃ ይቋጥርና ኩሬ ይፈጥራል። እዚያ ውስጥ ዋና የማይችሉ ታዳጊዎችና ወጣቶች ገብተው ሲዋኙ ወይም ኮብልስቶን ጠራጊዎች የግል ንፅህና ለመጠበቅ ገብተው ሲታጠቡ ሰምጠው ይሞታሉ፡፡
ሰሞኑን እንኳ ሐና ማርያም አካባቢ ባለ ኩሬ ውስጥ አንድ የ10 ዓመት ታዳጊ ገብቶ ሬሳውን አውጥተናል፡፡ ኩሬው ብዙ ህይወት ነው የቀጠፈው። አቃቂ አካባቢ የውሃ ችግር ስላለ እዚያ አካባቢ ካለ ኩሬ ውሃ ለመቅዳት የሄደ የጋሪ ፈረስ  ከነጋሪው ኩሬው ውስጥ  ሰጥሞ ሞቶ አውጥተናል፡፡
ለእነዚህ አደጋዎች ተጠያቂዎቹ ድንጋይ ወይም ማዕድን ለማውጣት ቦታውን ቆፍረው ሲያበቁ ቦታውን ቀድሞ ወደነበረበት ሳይመልሱ ክፍቱን ትተው የሚሄዱ ድርጅቶችና አስፈጻሚ አካላት ናቸው፡፡ ቦታውን ለመቆፈር ከአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ፈቃድ ሲያወጡ፣ ሲበቃቸው መልሰው ለመክደን ግዴታ ይገባሉ፡፡ ባለስልጣን መ/ቤቱም “ቃላችሁን ባታከብሩ” ብሎ ጉድጓዱን መክደን የሚያስችል ከፍተኛ ገንዘብ በመያዣ ይቀበላል። ነገር ግን ድርጅቶቹ በቸልተኝነት ወይም በሌላ ምክንያት የቆፈሩትን ጉድጓድ ሳይዘጉ ቢሄዱ አይጠየቁም ወይም አስፈጻሚው አካል ተከታትሎ ለመያዣ በተቀበለው ገንዘብ ጉድጓዱ እንዲዘጋ አያደርግም፡፡ እኛ አገር ጥሩ ጥሩ ሕጎች አሉ፡፡ ነገር ግን ተከታትሎ የሚያስፈጽም አካል የለም፡፡
በዚህ የተነሳ ባለፉት 6 ወራት ውስጥ ብቻ 41 ሰዎች ባልተከደነ የመንገድ ጉድጓድና ኩሬ ውስጥ ገብተው ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ከ15 ቀን በፊት ሜክሲኮ ከፌዴራል ፖሊስ ዋና ጽ/ቤት ፊት ለፊት አንድ የ32 ዓመት ወጣት ለቀላል ባቡር መንገድ በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ ሞቷል፡፡ ጊዜው ትንሽ ቆየት ብሏል እንጂ አንድ ሰው በቀድሞው የአፍሪካ ኅብረት ድርጅት፣ በአሁኑ የአፍሪካ አንድነት አካባቢ ባለ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ 5 ቀን ከቆየ በኋላ እንዳጋጣሚ ሆኖ ከእነሕይወቱ ሊወጣ ችሏል፡፡ ያ ሰው ዕድለኛ ነው ማለት ይቻላል፡፡ አንዲት ልጅ በአጋጣሚ ከጉድጓድ ውስጥ ድምፅ ትሰማለች። ለማረጋገጥ ጠጋ ስትል ሰው አየች፡፡ ልጅቷ እዚህ (እሳት አደጋ) የሚሰራ ወንድም ስለነበራት፣ ደውላ ስላየችው ነገር ነገረችው፡፡ በአጋጣሚ ወንድምየው ዕረፍት ላይ ስለነበር፣ ደውሎ ነገረንና ሄደን አወጣነው፡፡ ያ ሰው አሁንም በሕይወት አለ፡፡ የሀይገር ሹፌር ሲሆን ትዳር መስርቶ እየኖረ ነው። ይኼ አደጋው ሲደርስ ዘመድ ወይም በአካባቢው የነበሩት ሰዎች ደውለውልን ያወጣናቸው ናቸው። ለእኛ ሳይደወል ዘመድ ወይም የአካባቢው ሰዎች ከጉድጓድ አውጥተው ወደ ቤትና ወደ ሐኪም ቤት የወሰዷቸው ወይም የቀበሯቸው በርካታ ናቸው፤ ቤት ይቁጠራቸው፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ ከአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ጋር ብዙ ጊዜ ተወያይተናል፡፡ እኔ ራሴ ከባለሥልጣኑ ኃላፊ ከኢንጂነር ፍቃዱ ኃይሌ ጋር ተነጋግሬአለሁ፡፡ ምንም መፍትሔ ያልተገኘለት ችግር ሆኖ ቆይቷል፡፡ ለልማት ተብሎ ተቆፍሮ በሚፈጠር ኩሬ ውስጥ በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ሰው ገብቶ ይሞታል፡፡ በዚህ የተነሳ በዜጎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ነው፡፡ እኛ ማድረግ የምንችለው ጉድጓድ ወይም ኩሬ ውስጥ ገብተው የሞቱትን ሬሳ አውጥተን ለፖሊስ ማስረከብ፣ አምቡላንስ ስላለን ተጎድተው በህይወት ያሉትን ህክምና ወደሚያገኙበት ማድረስ ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ ከኩሬ ውስጥ ሬሳ ስናወጣ በአካባቢው ላሉ ሰዎች ትምህርት እንሰጣለን፡፡ ነገር ግን እዋኛለሁ ብሎ ለሚሄድ ሰው ጠባቂ ማቆም አንችልም፡፡ ልማት ሲካሄድ ያለ ቁፋሮ ሊካሄድ አይችልም፡፡ ስለዚህ ጉድጓድ ሲፈጠር መከለል አለበት፡፡ በአካባቢው አደጋ መኖሩን የሚጠቁሙ ዓለም አቀፍ ምልክቶች ስላሉ፣ እነሱ ጉድጓዱ ጋ ከመድረሱ ከ5 ሜትር በፊት መተከል አለባቸው፡፡
ለምሽት ደግሞ አንፀባራቂ ምልክት ማኖር ያስፈልጋል፡፡ በኮንስትራክሽን ቦታዎች ብዙ ጊዜ አደጋ የሚደርሰው በዝቅተኛ ሰራተኞች ላይ ነው፡፡ ባለሙያዎቹማ አደጋ ሊኖር እንደሚችል ስለሚያውቁ ይጠነቀቃሉ፡፡ ስለዚህ ለአደጋ የተጋለጡትን ሰራተኞች ማስተማርና የአደጋ መከላከያ ቆብ እንዲደፉ፣ ቦት ጫማ እንዲያደርጉና ጓንት እንዲያጠልቁ … ማስገደድ ያስፈልጋል በማለት አቶ ንጋቱ አሳስበዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ የመስሪያ ቤታቸው አቋም ምን እንደሆነ የተጠየቁት የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ሥራ አስኪያጅ ኢ/ር ፍቃዱ ኃይሌ፣የሚያስተዳድሩት መስሪያ ቤት የከተማዋን መንገድ የሚሰራና የሚያስተዳድር እንደመሆኑ መሰል አደጋዎች ሲደርሱ ተጠያቂ የማይሆንበት ምክንያት እንደሌለ ይገልፃሉ፡፡
መንገድ ላይ ያሉ ጉዳዮችን እየተከታተለ መዝጋትና መድፈን የባለስልጣኑ ድርሻ ከመሆኑም በላይ ህብረተሰቡም ጥቆማ በመስጠት ሊተባበር ይገባል ያሉት ኢንጂነሩ፤ እስካሁን ወደ መስሪያቤታቸው “ጉዳት ደርሶብኛልና ካሳ ይገባኛል” የሚል አቤቱታ ይዞ የቀረበ ተጎጂ ባይኖርም እንዲህ ያለ አቤቱታ ከቀረበ መስሪያቤታቸው ኢንሹራንስ ገብቶም ቢሆን ማሳከም እንዳለበትና ተጠያቂ መሆን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
መንገድ ሲሰራ ከሰዎች ንክኪ ተከልሎ መሆን እንዳለበት የሚያስገነዝቡት ኢ/ር ፍቃዱ፤ ከዚህ አግባብ ውጪ የመንገድ ግንባታ ሲከናወን አደጋውን ያደረሰው ሥራ ተቋራጭ ከሆነ ባለስልጣኑ ተጠያቂ ይሆናል፡፡ አንዳንድ ተሽከርካሪዎች በእግረኛ መንገድ ላይ ወጥተው የፍሳሽ ማስተላለፊያ ቱቦ ክዳኖችን መስበራቸው ለጉድጓዶቹ መፈጠር መንስኤ ነው ያሉት ኃላፊው፤ በቀለበት መንገድ ላይ ያሉ የፍሳሽ ማስወገጃ ቱቦ የብረት ክዳኖችም በሌቦች መዘረፋቸው ለባለስልጣን መስሪያቤቱ ፈታኝ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ተሽከርካሪዎችና እግረኞች በጉድጓድ እየገቡ ከፍተኛ አደጋ እየደረሰባቸው እንደሚገኝ መረጃው አለን ያሉት ኢ/ር ፍቃዱ፤ ተጠያቂነትን የሚያሰፍን ጠንካራ የህግ አፈፃፀም ያስፈልጋል፤ ኅብረተሰቡም ጉድጓዶች ሲያጋጥሙት ለባለስልጣኑ መጠቆም አለበት ብለዋል፡፡
ችግሩን ለመቅረፍ የባለስልጣን መስሪያቤቱ ሰራተኞች የቱቦ ክዳኖችን ከፍተው ቆሻሻ ካፀዱ በኋላ በአፋጣኝ መልሰው እንዲደፍኑ፣ ኮንትራክተሮችም መንገድ ሲሰሩ ከልለው እንዲሰሩ ጥብቅ ትዕዛዝ እየተላለፈ መሆኑን ኢ/ሩ ገልፀዋል፡፡
ስሜ አይጠቀስ ያሉ አንድ የሕግ ባለሙያ፤ መንገድም ይሁን ህንፃ በአጠቃላይ የመሰረተ ልማት መዋቅር ሲሰራ በሰዎች ደህንነትና አካል ላይ ጉዳት በማያደርስ መልኩ መሆን እንዳለበት የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ እንደሚደነግግ ጠቅሰው፤ የግንባታ ስራው ተጠናቅቆ አገልግሎት በመስጠት ላይ ባለ መንገድ ላይ ለሚደርስ ጉዳት የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣንና የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን፣አደጋው የደረሰበት መንገድ ተጠቅሶ ክስ ሊቀርብባቸው ይችላል ብለዋል፡፡
በኮንስትራክሽን ሂደት ላይ ባለ መንገድ ውስጥ የደረሰ አደጋ ካጋጠመ ግን፣ ተጎጂው መንገዱን የሚያሠራውን ባለስልጣን መስሪያቤትና ሥራ ተቋራጩን በአንድነት በመጥቀስ ኃላፊነት ሊወስድ የሚገባውን አካል ፍ/ቤት ይወስንልኝ ብሎ ክስ ሊመሰርት እንደሚችል ባለሙያው አብራርተዋል። ይህ የክስ አቀራረብ ተመራጭ የሆነው፤ ሥራ ተቋራጩን መቆጣጠር ያለበት አሠሪው መስሪያ ቤት ስለሆነና በመካከላቸው ያለው ውል ስለማይታወቅ ነው ብለዋል፤ ባለሙያው፡፡
በእኛ ሀገር እንደ ልማድ ሆኖ መንገድ ሲሰራ የጥንቃቄ ምልክቶች እንደማይቀመጡ መታዘባቸውን የተናገሩት ባለሙያው፤ በአንዳንድ የሰለጠኑ ሀገሮች ከ5 ሜትር ርቀት ላይ ምልክቶችና አቅጣጫዎች እንደሚቀመጡ በመጠቆም በእኛም ሀገር ይህ አስገዳጅ ህግ ተፈፃሚ መደረግ አለበት ሲሉ ይመክራሉ፡፡ በቴሌ ኬብል ቀበራ ወቅት ጉድጓዶች ሳይከደኑ ከቀሩም የቴሌ መሆኑን በማረጋገጥ፣ አሊያም ፍ/ቤት ያጣራልኝ በማለት የመንገዶች ባለስልጣንና ቴሌን አጣምሮ ክስ መመስረት ይቻላል ብለዋል፡፡
በእኛ ሀገር የመንግሥት መስሪያ ቤቶችን በወንጀል መክሰስ (ኮርፖሬት ክሪሚናል ሊያቢሊቲ) በሚለው ፅንሰ ሐሳብ መነሻነት የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ እንደሚከለክል የጠቆሙት የህግ ባለሙያው፤ ተጎጂው የደረሰበትን የጉዳት መጠን ጠቅሶ “ልካስ ይገባኛል” ብሎ የፍትሐብሔር ክስ ማቅረብ ይችላል ብለዋል፡፡ “መንግሥትን ከስሼ ካሣ አገኛለሁ” የሚለው ሐሳብ በራሱ በኛ ሀገር ካለመለመዱም በላይ በፍ/ቤቶች የተንዛዛ አሰራር ምክንያት ተጎጂዎች መብታቸውን እንዳያስከብሩ ዳተኛ ያደርጋል ያሉት ባለሙያው፤ ይህ ባህል መቀረፍ እንዳለበትና ሰዎች ሕጉ የሰጣቸውን መብት እንዲያስከብሩ አሳስበዋል።  
በጉዳዩ ላይ የሚመለከታቸውን የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎት እና የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን መስሪያ ቤትን አስተያየት ለማካተት ያደረግነው ሙከራ ስልካቸው ባለመነሣቱ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡          

ቅሬታቸውን ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሓላፊዎች ገልጸዋል

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ በኾኑ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን እምነትና ሥርዐት እንዲማሩ፣ ዕውቀታቸውንና ገንዘባቸውን በማቀናጀት ሞያዊ ድጋፍ እንዲያበረክቱ በማስተባበር ላይ የሚገኘውን ማኅበረ ቅዱሳንን በአሸባሪነት በመፈረጅ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ አማካይነት ጠቅላላ ሀብቱና ንብረቱ የሚታገድበት ውሳኔ እንዲተላለፍ በመንግሥትም በኩል እርምትና ርምጃ እንዲወሰድበት የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የአድባራት አስተዳዳሪዎች መግለጫ አውጥተውበታል በተባለው ስብሰባ ጉዳይ ኹለት የቅ/ሲኖዶስ አባላት ለከፍተኛ የመንግሥት ሓላፊዎች ቅሬታቸውን ማሰማታቸው ተገለጸ፡፡
የቅ/ሲኖዶሱን ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሉቃስንና በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስና የጅማ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስን በስም የጠቀሱት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች፣ ሊቃነ ጳጳሳቱ ቅሬታቸውን ያቀረቡት ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሓላፊዎች እንደኾነ ቢገልጹም የሓላፊዎቹን ስም ከማሳወቅ ተቆጥበዋል።
ቤተ ክርስቲያኒቱ በፀረ ሙስናና በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ከመንግሥት ጋራ የተጠናከረ ሥራ ለመሥራት በቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መወሰኗን ሊቃነ ጳጳሳቱ አስታውሰው፣ በዚህም መሠረት ለሙስናና ብክነት የተጋለጡ አሠራሮችን ለማረምና ለማስተካከል ጥረት እያደረገች ቢኾንም ባለሥልጣናቱ ከማን ጋር መሥራት እንዳለባቸው በትክክል አለመለየታቸውንና ግንኙነቱም ሙሰኞችን በአይዟችኹ ባይነት የሚያበረታታ እንደኾነ መናገራቸው ተጠቅሷል፡፡
ሊቃነ ጳጳሳቱ ቅሬታቸውን በዚህ መልኩ ለባለሥልጣናቱ ለማቅረብ ያስገደዳቸው የአድባራት አስተዳዳሪዎቹ፣ ‹‹ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችን ለአድማ ያነሣሣል፤ በሀገርና በቤተ ክርስቲያን ላይ ሁከትና ሽብር እንዲፈጠርና ሰላም እንዲደፈርስ ያደርጋል›› ባሉት በማኅበረ ቅዱሳን ላይ የሚወሰደው አስተዳደራዊ ርምጃ በፀረ ሽብር ሕጉ መሠረት ተጠናክሮ እንዲቀጥል የጠየቁበት መግለጫቸው ነው፡፡
የመንግሥት የተለመደ እገዛ እንዳላቸው በአጽንዖት የጠቀሱት አስተዳዳሪዎቹ በዚሁ መግለጫቸው፣ መንግሥት በፀረ ሽብር ሕጉ ታሳቢነት ገለልተኛ ኦዲተር መድቦ በማኅበሩ ላይ የሀብትና ንብረት ቁጥጥር የማካሔድ ድጋፉ እንዳይለያቸው ያስተላለፉት ጥሪ በሌላቸው ሕጋዊነትና ውክልና የቀረበ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ በራስዋ መንገድ ማከናወን በሚገባት ተግባር ላይ አላስፈላጊ ጣልቃ ገብነትን የሚጋብዝና ለውጭ ተጽዕኖ አሳልፎ የሚሰጥ እንደኾነ ተመልክቷል፡፡
በመንበረ ፓትርያርኩ ከተገኙት የመንግሥት ሓላፊዎች ጋራ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ እንደተካሔደ በተገለጸው የኹለትዮሽ ውይይት፣ ማኅበረ ቅዱሳንን በመቃወም ሰበብ የወጣው የአስተዳዳሪዎቹ መግለጫ ዋነኛ ዓላማ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ ወስና የምታካሒደውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ሒደት መጋፋት ነው ተብሏል፡፡  መላውን የሀገረ ስብከቱን አድባራት አገልጋዮች  ለመወከል የማይበቁ ጥቂት ግለሰቦችን በመያዝ ይደረጋል የተባለው ይኸው እንቅስቃሴም ‹‹የት እንደሚያደርስ እናየዋለን›› የሚሉ ንግግሮች ጭምር ከሊቃነ ጳጳሳቱ የተሰሙበት እንደነበር ምንጮቹ አስታውቀዋል፤ ጉዳዩም በመጪው ግንቦት በሚካሔደው የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ዓቢይ መነጋገርያ መኾኑ እንደማይቀር ተጠቁሟል፡፡
ከሀገረ ስብከቱ አድባራት የተውጣጡ ናቸው የተባሉ አስተዳዳሪዎች ያደረጉት ስብሰባ፣ አስተባባሪዎቹ ከፓትርያርኩ ተሰጥቶናል ከሚሉት ፈቃድ በቀር በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስና በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ዘንድ በይፋ የታወቀና የተፈቀደ እንዳልነበረ ምንጮቹ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳንን በሁከትና ሽብር ለሚከሱ በቂ ሕጋዊነትና ውክልና የላቸውም ለተባሉ አካላት ፓትርያርኩ የሰጡትን የስብሰባ ፈቃድ፣ በቅርቡ ማኀበሩ አገር አቀፍ የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤ  እንዳያካሒድ ከተጣለበት እገዳ ጋር ያነፃፀሩ ታዛቢዎች፣ ሁኔታው የፓትርያርኩን ርምጃዎች መርሕ አልባነት የሚያጋልጥ ነው ይላሉ፡፡ ከዚህም ባሻገር መተዳደርያ ደንብ ያለውና ግልጽ ተልእኮ ይዞ የሚንቀሳቀሰው ማኅበር፣ህልውናና አገልግሎት በግልጽ አስተዳደራዊ ጫና ውስጥ መግባቱን  እንደሚያመለክት ታዛቢዎቹ ያምናሉ፡፡
ከመዋቅር፣ ከሀብትና ንብረት ቁጥጥር ጋራ በተያያዘ በማኅበሩ ላይ የሚቀርቡት ውንጀላዎች፣ በፀረ አክራሪነት ስም የሚናፈስበትን ፕሮፓጋንዳ በማጠናከር ፖሊቲካዊ ርምጃ እንዲወሰድበት ፍላጎት ያላቸውን አካላት ምኞት በጉልሕ እንደሚያሳይ አስረድተዋል፡፡ ማኅበሩ ሃይማኖቱን የሚጠብቅ፣ ቤተ ክርስቲያኑን የሚከባከብና ሀገሩን የሚወድ ብቁ ዜጋ ለማፍራት ያለውን ዓላማ የሚረዱ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ካህናት፣ ምእመናንና የመንግሥት አካላትም የተቃዋሚዎቹን አቋምና መግለጫ በጥንቃቄ እንዲመለከቱትም አሳስበዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቀኖናና ትውፊት ውጭ ነው በተባለ የሌላ እምነት አስተምህሮ የተነሳ  በኮሌጁ ደቀ መዛሙርት መካከልና በደቀ መዛሙርቱ ምክር ቤት አባላት ውስጥ ያለው ግንኙነት ውጥረት ውስጥ እንደገባ እየተገለጸ ነው፡፡
ከኮሌጁ ውጭ ከሚገኙና በቅ/ሲኖዶስ ከተወገዙ ግለሰቦችና ቡድኖች ጋር የዓላማና የጥቅም ግንኙነት መሥርተዋል በተባሉ ጥቂት ደቀ መዛሙርት አማካይነት በኮሌጁ ውስጥ ከመንጸባረቅ አልፎ እንደ ሰደድ እሳት እየተቀጣጠለ ነው የተባለው ይኸው አስተምህሮ፣ አስተዳደራዊ መፍትሔ እንዲበጅለት የደቀ መዛሙርቱ ምክር ቤት ጥር 5 ቀን 2006 ዓ.ም. ለኮሌጁ አስተዳደር ያቀረበው ጥያቄ እስከ አሁን ምላሽ አለማግኘቱ  ውጥረቱን የበለጠ እንዳባባሰው ለአዲስ አድማስ የደረሰው መረጃ አመልክቷል፡፡
የአስተምህሮው ውዝግብ አፋጣኝ መፍትሔ አለማግኘቱ ከደቀ መዛሙርቱ አልፎ የምክር ቤት አባላትን ለሁለት እንደከፈለ ተገልጧል፡፡ ኮሌጁንና ደቀ መዛሙርቱን በቅንነትና በትጋት ለማገልገል በደቀ መዛሙርቱ ጠቅላላ ጉባኤ የተመረጠውና ከፍተኛ ሓላፊነት የተጣለበት የደቀ መዛሙርቱ ምክር ቤት፣ ‹‹ከልማቱ ጥፋቱ አመዝኗል›› ያሉት ጸሐፊውና አንድ የአመራር አባሉም ራሳቸውን ማግለላቸው ታውቋል፡፡
‹‹ከቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖናና ትውፊት ውጭ የኾነ የኑፋቄ ትምህርት ሲዘራ ድምፀ ተዓቅቦ ከማድረግ ባሻገር ችግር አለባቸው ከሚባሉት ደቀ መዛሙርት ጎን ተሰልፈው ኮሌጁንም ኾነ ሓላፊነት የሰጠንን ደቀ መዝሙር በቅንነት እንዳናገለግል የአንዳንድ መማክርት አባላት ተግባር አውኮናል›› ያሉት ሁለቱ አባላት፤ በዚህ ሳምንት ለኮሌጁ ዋና ዲን ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ፣ ምክር ቤቱ የችግሩ ተባባሪ በመኾኑ ከሓላፊነቱ ታግዶ ጉዳዩ እንዲጣራና እምነታቸውና ሥነ ምግባራቸው በተመሰከረላቸው ደቀ መዛሙርት እንዲተካ ጠይቀዋል፡፡
‹‹የቤተ ክርስቲያንን እንጀራ እየበሉ፣ በጀቷን አውጥታ እያስተማረቻቸው የሌላ እምነት የሚያራምዱ›› ያሏቸውን ወገኖች አጥብቀው እንደሚቃወሙ የገለጹ የደቀ መዛሙርት ተወካዮች በበኩላቸው፣ ኮሌጁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖናና ትውፊት ለመጠበቅና ለማስፋፋት የቆመ  በመኾኑ አስተዳደሩ፣ በቃል፣ በድምፅና በጽሑፍ የሚቀርቡለትን ማስረጃዎች መርምሮ አስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጣቸው አሳስበዋል፡፡

          ለችግር የተጋለጡ ህፃናትን እና በለጋ እድሜያቸው ተደፍረው ወይም ተገደው የልጅ እናት የሆኑ ሴቶችን ለመርዳትና የተሻለ ህይወት እንዲኖራቸው ለማድረግ ታስቦ ከሁለት ዓመታት በፊት የተቋቋመው መሠረት የበጎ አድራጎት ድርጅት በድርጅቱ የበጎ ፍቃድ አገልጋዮች ተነሳሽነት “በጎ ፍቃደኝነት” የሚል መሪ ቃል ያነገበ ልዩ ገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ሊያካሂድ ነው፡፡
መጋቢት 21/2006 ዓ.ም በሐርመኒ ሆቴል በሚካሄደው በዚሁ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት፣ ባለሀብቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የድርጅቱ ድጋፍ ሰጪ አካላትና ሌሎች የድርጅቱ አጋሮች እንደሚገኙበት አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
“እኛው ለእኛው በእኛው” በሚል መሪ ቃል እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ የሚገኘው ይኸው ድርጅት ምንም አይነት ቋሚ የገቢ ምንጭ ሳይኖረው ጠንካራ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ የሚገኝ ሲሆን በአሁኑ ወቅት 280 ህፃናትንና 125 ሴቶችን በመርዳት ላይ የሚገኝ ድርጅት እንደሆነም ተገልጿል፡፡ ህብረተሰቡ የህፃናቱን እና የሴቶችን ህይወት ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ በሚደረገው እንቅስቃሴ ያለውን በመለገስ ሃላፊነቱን እንዲወጣ የድርጅቱ መስራች እና ዳይሬክተር ወ/ሮ መሰረት አዛገ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

       ከሁለት ዓመት በፊት የተጀመረው ለማረሚያ ቤቶች የሚውል መፃሕፍት ማሰባሰብ ዛሬ ይጀመራል፡፡ ለቀጣዮቹ 30 ቀናት በሚቆየው የመፃሕፍት ማሰባሰብ ሥራ መጽሐፍ መለገስ የሚፈልጉ ፈቃደኞች በተመረጡ ቦታዎች እንዲያስቀምጡ በጎ ፈቃደኛዋ ጥሪ አድርጋለ ች፡፡ ዋቢ ሸበሌ ሆቴል፣ ብሄራዊ ቴአትር ጀርባ የሚገኘው ጃፋር መጽሐፍ መደብር፣ ሜጋ መጽሐፍት መደብር ቢሮ እና ፒያሳ እናት ህንፃ ፊት ለፊት የሚገኘው አብዲ መጸሐፍ መደብር መጽሐፎቹን ለማስቀመጥ የተመረጡ ቦታዎች እንደሆኑ ነርስ ሊንዳ በቀለ ገልፃለች። በ2004 ዓ.ም ብሄራዊ ቴአትር መግቢያው መጽሐፍ የሆነ ፕሮግራም አዘጋጅታ ወደ ሶስት ሺህ ያህል መጽሐፍትን በመሰብሰብ ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንዳስገባች የገለፀችው በጎ ፈቃደኛዋ፤ በ2005 ዓ.ም ከኅብረተሰቡ ገንዘብ በማሰባሰብ ጋሞ አካባቢ ለሚገኙ የገጠር ት/ ቤቶች የመማሪያ መጽሐፍትን በቅናሽ በመግዛት ማስረከቧን ተናግራለች፡፡ ዘንድሮም በጎ ፈቃደኞች የሚለግሷቸውን መጸሐፍት ለቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እንደምታስረክብ ገልፃ፤ ሁሉም ሰው ካለው መጽሐፍ ላይ እንዲለግስ ጥሪ አቅርባለች፡፡ በጎ ፈቃደኛዋ በየዓመቱ የምታካሂደውን የመጽሐፍ ማሰባሰብ ሥራ “መጽሐፍት ለሁሉም በሁሉም ስፍራ” በሚል መርህ እንደምታከናውንም ጨምራ ገልፃለች፡፡

በኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር እና በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ትብብር የመፅሀፍ አውደርዕይ መዘጋጀቱን የደራሲያን ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ገ/ክርስቶስ ሃ/ሥላሴ አስታወቁ፡፡ አውደርዕዩ ከመጋቢት 15 እስከ 21/2006 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን ከዳግማዊ ምኒሊክ ት/ቤት ፊት ለፊት በሚገኘው ቦታ ላይ እንደሚካሄድም ተገልጿል፡፡ በአውደ ርዕዩ ላይ መጽሐፍት በታላቅ ቅናሽ ለሽያጭ እንደሚቀርቡ የተናገሩት ሥራ አስኪያጁ፤ የአውደርዕዩ መክፈቻ እለት ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት በብሄራዊ ሙዚየም አዳራሽ በርካታ ደራሲያንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት “በርናባስ” በተሰኘ ልብወለድ መጽሐፍ ላይ ሂሳዊ ውይይት ይካሄዳል ተብሏል።