Administrator

Administrator

በ5 አመት 30 ሺ ስደተኛ ቻይናዊያንን በነዋሪነት የተቀበለች ከተማ ተሸላሚ ሆናለች - 1.6 ሚ. ስደተኞች በከተማዋ ይኖራሉ
          ከተሞች ውስጥ በቋሚነት የሚኖሩ ቻይናዊያን ቢቆጠሩ ወደ 700 ሚሊዮን ገደማ ናቸው። የቻይና መንግስትና ገዢ ፓርቲ እንዲሁም ገለልተኛና ዓለማቀፍ ተቋማት በዚህ ያምናሉ። ነገር ግን፤ እዚያው በዚያው ሌላ ነገር ትሰማላችሁ። የከተማ ነዋሪዎች ቁጥር ወደ 440 ሚሊዮን ገደማ እንደሆነ በይፋ ይነገራል፤ ሪፖርት ይቀርባል። “በአንድ አፍ ሁለት ምላስ” አትሉም? የተሳሳተ ነገር የፃፍኩ እንዳይመስላችሁ። ነገሩ እውነት ነው። “በከተማ የሚኖሩ” እና “የከተማ ነዋሪዎች” ቁጥር እንዴት ይለያያል? የእንቆቅልሹ ፍቺ ይሄውላችሁ። 260 ሚሊዮኖቹ ስደተኞች ናቸው። ከሌላ አገር የመጡ አይደሉም። እዚያው አገራቸው ውስጥ ከገጠር ወደ ከተማ የገቡና በስደተኛነት የተመዘገቡ ቻይናዊያን ናቸው። ከተማ ውስጥ 20 አመት ቢያሳልፉ፣ ቤተሰብ ቢመሰርቱና እዚያው ከተማ ልጅ ቢወልዱ ለውጥ የለውም። “የከተማ ነዋሪ” የሚል እውቅና አያገኙም። ከነልጃቸው “ስደተኛ” በሚል መጠሪያ ነው የሚታወቁት። “ሁለተኛ ደረጃ ዜጎች” የሚል ስያሜም የተለመደ ነው - እዚያው በቻይና የሚዲያ ዘገባዎች ውስጥ ሳይቀር።
“የከተማ ነዋሪ” መሆንና “ስደተኛ” ተብሎ መኖር፣ ልዩነቱ የስያሜ ጉዳይ ብቻ አይደለም። በአንድ ከተማ ውስጥ እየኖሩ፣ በአንድ ፋብሪካ ውስጥ በተመሳሳይ ሙያና ብቃት የሚሰሩ ሁለት ቻይናዊያን እኩል ደሞዝ እንዳያገኙ የሚያደርግ ስርዓት ነው። ጡረታ ሲወጡ የሚያገኙት ክፍያም በ10 እጥፍ ይለያያል። በአጠቃላይ፤ በርካታ አመታትን ያስቆጠረው አድልዎ ከአፓርታይድ ጋር ይመሳሰላል - ባለፈው ሳምንት የወጣው ዘ ኢኮኖሚስት መፅሔት እንደገለፀው።
ነገርዬው፤ የ21ኛው ክፍለዘመን ታሪክ ስለማይመስል ግር ያሰኛል። ምናልባት፤ቻይናን እንደ ሁለት አገር ብንቆጥራት ሳይሻል አይቀርም። ታሪኩ የሚጀምረው፤ የዛሬ 55 ዓመት ነው። በብዙዎቹ ኮሙኒስት ፓርቲዎች ላይ እንደተለመደው፣ የቻይናው ኮሙኒስት ፓርቲ መሪ ማኦ ዜዱንግ ለከተሜነት ጥሩ ስሜት አልነበራቸውም። “ሰዎች በገፍ ከገጠር ወደ ከተማ እየፈለሱ ቀውስ ይፈጥራሉ” የሚለው ሰበብ ተጨመረበትና ቻይናዊያን የመኖሪያ አካባቢያቸውን እንዳይለውጡ የሚከለክል የቁጥጥር ስርዓት ተፈጠረ። በደርግ ዘመን ተጀምሮ ከነበረው ቁጥጥር ጋር ይመሳሰላል። ከቀበሌ “የይለፍ ወረቀት” እና “የመልቀቂያ ፈቃድ” ያላገኘ ሰው ከመኖሪያ አካባቢው መልቀቅ አይችልም ነበር። ያው፤ ኮሙኒስቶች፣ የሁሉንም ሰው ኑሮና ንብረት የመቆጣጠር ረሃብ አለባቸው - የስልጣን ጥም ልትሉት ትችላላችሁ። የቻይናው ቁጥጥር ፈፅሞ የማያፈናፍን መሆኑ ነው ልዩ የሚያደርገው።
የሆነ ሆኖ፤ማኦ ባወጡት ሕግ መሰረት የአገሬው ሰዎች በሁለት ጎራ ተከፍለው ተመዘገቡ - የከተማ እና የገጠር ነዋሪ (hukou) በሚል። “የከተማ ዜጋ እና የገጠር ዜጋ” ልንለውም እንችላለን። ለምን ብትሉ? በጣም አስቸጋሪ ነው። ከገጠር ነዋሪነት ወደ ከተማ ነዋሪነት መሸጋገር፤ ከአንድ የአፍሪካ አገር ተሟሙቶ የአሜሪካ ቪዛና የመኖሪያ ፈቃድ እንደማግኘትና ከዚያም ዜግነት እንደመለወጥ ነው። የገጠር ነዋሪ (ዜጋ) የነበረ፣ እድሜ ልኩን የገጠር ዜጋ እንደሆነ ይቀጥላል - ከነልጆቹ፣ ከነልጅ ልጆቹ።
አዋጁና ቁጥጥሩ ቀስ በቀስ እየላላ የመጣው፣ ከማኦ ህልፈት በኋላ በዴንግ ዚያዎፒንግ መሪነት ኮሙኒስት ፓርቲው የኢኮኖሚ ስርዓት ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ማድረግ ሲጀምር ነው። በማኦ ዘመን፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ በሙሉ በመንግስት ቁጥጥር ስር መግባቱ፣ ድህነት መባባሱና ረሃብ መከሰቱ አይገርምም። ሌሎች ኮሙኒስት አገራትም የሚጋሩት ታሪክ ነውና። አስገራሚው ነገር፤ የቻይና ኮሙኒስቶች ከድህነት ለመውጣት፣ መጠነኛ የካፒታሊዝም ወይም የነፃ ገበያ ስርዓት ተግባራዊ ለማድረግ መወሰናቸው ነው - የዛሬ 35 ዓመት ገደማ። “የጋራ መሬትና የጋራ ምርት” በሚል በግዴታ በማህበር ተደራጅተው በጋራ ሲደኸዩ የነበሩ ገበሬዎች፤ ማሳ ተከፋፍለው በግል እንዲያመርቱ ተፈቀደ። በከተማም፣ ንብረት ማፍራት፣ የንግድ ወይም የማምረቻ ቢዝነስ መክፈት ይቻላል ተባለ። ሃብት ማፍራትን እንደ ትልቅ ክህደትና ወንጀል ይቆጥር የነበረ ኮሙኒስት ፓርቲ፤ “ሃብታም መሆን ጀግንነት (ቅዱስነት) ነው - To be rich is Glorious” እያለ በባነርና በፖስተር፣ በሬድዮና በቲቪ ያስተምር ጀመር።
በተከፈተችው የነፃ ገበያ ጭላንጭል አማካኝነት፣ የሚታይ የሚጨበጥ ፍሬ ለማግኘት ጊዜ አልፈጀባቸውም። የአገሪቱ ኢኮኖሚ መሻሻል ጀመረ። የነፃ ገበያ ማሻሻያውም ቀስ በቀስ እየሰፋ፣ በአምስት አመታት ውስጥ ኢኮኖሚያቸው ወደ ፈጣን እድገት ተሸጋገረ። ከዚሁ ጋር አብሮ ነው፤ ታይቶ በማይታወቅ ፍጥነት የስራ እድል መስፋፋት የጀመረው - በከተሞች በተለይም በማምረቻ የኢንዱስትሪ ቢዝነሶች። ነገር ግን፤ ሰዎች ከገጠር ወደ ከተማ እንዳይፈልሱ የሚያግድ ሕግ ይዘው፣ በኢኮኖሚ እድገት መቀጠል አይችሉም። የግድ መለወጥ አለበት። ደግሞም ለውጠውታል።
በእርግጥ ህጉ አልተሻረም። ነገር ግን፤ ሕጉን የሚያላላ ዘዴ ተፈጠረ። ወደ ከተማ ሄደው ለመስራት የሚፈልጉ የገጠር ነዋሪዎች፣ በጊዜያዊነት የይለፍና የመኖሪያ ፈቃድ የሚያገኙበት ሰፊ እድል እንዲያገኙ ነው የተወሰነው። “የአገር ውስጥ የዲቪ ሎተሪ” በሉት። በስደት ጊዜያዊ ቪዛና ጊዜያዊ ግሪን ካርድ እንደማግኘት ነው። ጊዜያዊ ተብሎ የተጀመረው ስደት እየሰፋ ቀጠለ እንጂ አልቆመም - ከተማ የገቡት ስደተኞች ወደ አገር ቤት አልተመለሱም። ግን ደግሞ፣ ጊዜያዊ የመኖሪያ ፈቃዳቸው ወደ ሙሉ ዜግነት አልተለወጠም። 10 እና 20 ዓመት ቢያልፋቸውም፤ ቤተሰብ መስርተው ልጆችን ቢያፈሩም፤ የአገሪቱ ህግ “የከተማ ነዋሪ” በሚል ስያሜ አያውቃቸውም።
ሕይወታቸው ሲታይ፣ በከተማ ከ20 አመት በላይ የኖሩ ናቸው። በህጉ ሲታይ ደግሞ፣ ከነልጆቻቸው ስደተኛ “የገጠር ነዋሪ (ዜጋ)” ናቸው። ከጥቂቶች በስተቀር፣ የብዙዎቹ ስደተኞች እጣ ፋንታ ከዚህ የተለየ ባለመሆኑ፣ ዛሬ ቁጥራቸው 260 ሚሊዮን ደርሷል። በሌላ አነጋገር፣ በከተማ ከሚኖሩት ሰዎች መካከል፣ 37 በመቶ ያህሉ ስደተኛ ወይም ሁለተኛ ደረጃ ዜጎች ናቸው። ልጆቻቸው በመንግስት ትምህርት ቤት ወይም ዩኒቨርስቲ ውስጥ ማስመዝገብ አይፈቀድላቸውም። በመንግስት ሆስፒታል ውስጥ አገልግሎት ማግኘት አይችሉም። መኖሪያ ቤት ሽያጭና ኪራይ ላይ በመንግስት የሚመደቡ ድጎማዎችንም አያገኙም። በዚያ ላይ ከፍተኛ የጡረታ ክፍያ አድልዎ ይጠብቃቸዋል።ይህንን አድልዎ ለማስወገድ እየጣረ እንደሆነ፣ የቻይና መንግስት መግለፁ አልቀረም። ለበርካታ አመታት በከተማ የኖሩ “ስደተኞች”፣ ሙሉ“የከተማ ነዋሪነት”ን የሚቀዳጁበት ሂደት እንደተጀመረም ይገልፃል። ነገር ግን፤ ሂደቱ ገና ፈቅ አላለም። በአርአያነት የተሸለመችውን ከተማ መጥቀስ ይቻላል። ዞንግሹን ትባላለች። በከተማዋ ከሚኖሩ ሰዎች መካከል ግማሾቹ “ስደተኞች” ናቸው - 1.6 ሚሊዮን ያህል። ባለፉት አምስት አመታት ከእነዚህ ውስጥ “የከተማ ነዋሪነት”ን የተቀዳጁት 30ሺ ያህሉ ብቻ ናቸው። በከተማዋ ውስጥ ካሉት 200ሺ የስደተኛ ልጆች መካከልም በመንግስት ትምህርት ቤት እንዲመዘገቡ የተፈቀደላቸው ለ25ሺ ያህሉ ነው። የማኦ ቅርስ የኮሙኒዝም ውርስ የሆነው አድልዎ ገና አልተነካም ቢባል ይሻላል።

ሳውዲ ዓረቢያ በዚህ ወር 50 ስሞችን ጥቁር መዝገብ ውስጥ አስገባች
አንዳንድ መንግስታት፣ ይህንንም ከልክለው ያንንም አግደው ሲያበቁ የሚሰሩት ነገር እየጠፋባቸው የሚጨነቁ ይመስላሉ - የሚከለከል ነገር ቢጠፋ የስም አይነት ይከለክላሉ፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የአንዳንድ ወላጆች ነገረ ሥራ ከአብዮት አይተናነስም፡፡ በስዊድን አገር የልጃቸውን ስም ሲያስመዘግቡ፣ “Brfxxccxx” ብለው ነው የጀመሩት፡፡ የልጃቸው ስም ገና ተጽፎ አላለቀም፡፡ ከ40 በላይ ፊደሎችን የያዘ ስም ነው፡፡ የመጨረሻዎቹ ስምንት ፊደላት “Sqlbb11116” ይላል፡፡ በስንት መከራ ነው ለልጃቸው ሌላ ስም እንዲያወጡ የተደረጉት፡፡
በየአገሩ በልጆቹ ስም ላይ ለመጫወት ወይም ለመቀናጣት የሚሞክር ወላጅ እንደማይጠፋ በመጠቆም፣ ግሎባል ፖስት ዘገባውን ሲያቀርብ በኒውዝላንድ ሁለት ወላጆች ሊነበብ የማይችሉ ስሞችን እንዳስመዘገቡ ገልጿል፡፡
እንደ ገመድ የረዘሙ ስሞችን አልመረጡም፡፡ እጥር ምጥን ያሉ ስሞችን ነው ያስመዘገቡት፡፡ አንደኛው ወላጅ ለልጃቸው ስም ሲመርጡለት በአንድ ነጥብ ጨረሱት፡፡ አንዲት የነጥብ ምልክት ብቻ ነች የምትታየው - ሲመዘገብ በድምጽ ምን ተብሎ እንደሚጠራ እንጃ፡፡ ሌላኛው ወላጅም እንዲሁ የልጃቸውን ስም ሲያስመዘግቡ ትንጥዬ ጨረር መሰል ምልክት አስፍረዋል (*) በዚህም በዚያም ተብሎ የኋላ ኋላ ለልጆቻቸው ሌላ ስም ለመምረጥ ተስማምተዋል
እንዲህ አይነት ችግሮችን ለማስወገድ፤ በጃፓን፣ የልጆች ስም በቀላሉ በጽሑፍ የሚገለጽና የሚነበብ መሆን አለበት የሚል ህግ አለ፡፡ ተገቢ አይደሉም የሚባሉ ስሞችም ይከለክላሉ፡፡ ለምሳሌ “አኩማ” ብሎ ስም አይፈቀድም - ሰይጣን እንደማለት ነው፡፡
በጀርመን፣ የወንዶችን ስም ለሴት ወይም ደግሞ የሴቶችን ስም ለወንድ መጠቀም አይቻልም፡፡ ከዚህ በላይ፤ የወንድ ይሁን የሴት ተለይተው የማይታወቁ ስሞች ተቀባይነት አይኖራቸውም፡፡
አንዳንድ አገሮችማ የሚፈቀዱና የማይፈቀዱ የስም አይነቶችን እየዘረዘሩ አዋጅ አውጥተዋል፡፡ በክርስትና የሃይማኖት አክራሪነት በነበረበት ዘመን በፖርቱጋል የሚፈቀዱ ስሞች በሃይማኖታዊ መፃሕፍት ውስጥ የተጠቀሱ ስሞች ብቻ ነበሩ፡፡ በእስልምና የሃይማኖት አክራሪነትን የሚያራምዱ ሰዎች በመበርከታቸው ይመስላል፣ ማሌዢያ ከስምንት አመት በፊት አዲስ ህግ አውጥታለች፡፡ ልጆችን በእንስሳት፣ በነፍሳት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በቅጠላቅጠልና በቀለም አይነቶች መሰየም ይከለክላል ህጉ፡፡ ብርቱኳን፣ ሃረገወይን፣ አንበሴ፣ ነብሮ፣ ግራር ወይም ፅድ ብሎ መሰየም አይቻልም፡፡ በዚህ ወር በሳዑዲ አረቢያ በጥቁር መዝገብ ውስጥ እንዲካተቱ ከተደረጉት 50 ስሞች መካከል ገሚሶቹ የተወገዙት ከውጭ አገር የተወሰዱ ናቸው በሚል ምክንያት ነው - ሊንዳ እና አሊክ የመሳሰሉ ስሞች፡፡ የንጉሳዊውን ቤተሰብ ክብር ይዳፈራሉ ተብለው ከታገዱት ስሞች መካከል ደግሞ “ማሊካ” የሚል ይገኝበታል - እቴጌ ወይም ንግስት ማለት ነው፡፡ በሃይማኖት ሰበብ የተከለከሉም አሉ፡፡ ጅብሪል (ገብርኤል) ብለው ለልጅዎ ስም ማውጣት አይችሉም፡፡  

በታዋቂዋ የክራር ተጫዋችና ድምጻዊት በአስናቀች ወርቁ የህይወት ታሪክ ዙሪያ የሚያጠነጥነውና ‘አስኒ’ የሚል ርዕስ ያለው ዘጋቢ ፊልም፣ ከትናንት በስቲያ በኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ-አሜሪካ ጉዳዮች የሲኒማ ጥናቶችና የአፍሪካ ጥናቶች ፕሮግራም ኢንስቲቲዩት ለመጀመሪያ ጊዜ ለእይታ በቃ፡፡
ነዋሪነቷ በአሜሪካ በሆነው ራሄል ሳሙኤል ዳይሬክተርነት የተዘጋጀውና ሰርቶ ለማጠናቀቅ ከአራት አመታት በላይ የፈጀው ይህ ዘጋቢ ፊልም፣ የድምጻዊቷን የህይወትና የሙያ ጉዞ በጥልቀት የሚዳስስ እንደሆነ ታዲያስ መጽሄት ከኒውዮርክ ዘግቧል፡፡
‘አስኒ’ ዘጋቢ ፊልም፣ ከሶስት አመታት በፊት በ76 ዓመት ዕድሜዋ ከዚህ አለም በሞት የተለየችው ድምጻዊት አስናቀች ወርቁ፣ በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ የራሷን ደማቅ አሻራ ጥላ ያለፈች፣ በዘመኗ ለነበሩ ወጣት አርቲስቶች ፈር የቀደደችና፣ በትወናው መስክም ድንቅ ክህሎቷን ያሳየች ዘመን ተሻጋሪ አርቲስት መሆኗን የሚያሳይ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
የፊልሙ ዳይሬክተር ራሄል ሳሙኤል ከዚህ በፊትም በሳንፍራንሲስኮ ውስጥ በተከናወኑ ታላላቅ የማስታወቂያ ፕሮጀክቶች ላይ በተለያዩ ኤጀንሲዎች አማካይነት ስትሰራ የቆየች ሲሆን፣ ፊልሙን ኤዲት ያደረገውና በጋራ ፕሮዲዩስ ያደረገውም፣ በኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ ሞሬስ ካንባር የፊልምና የቴሌቪዥን ኢንስቲቲዩት ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆነው ኢትዮጵያዊው የማነ ደምሴ ነው፡፡

  የአድዋ ድልን 118ኛ ዓመት ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ “ዝክረ አድዋ” የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል የፊታችን ሰኞ ከ11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቴአትር እንደሚካሄድ “ኬር ኢቨንትስ እና ኮሙዩኒኬሽን” አስታወቀ፡፡ ፌስቲቫሉ ለሶስተኛ ጊዜ የሚካሄድ ሲሆን የዘንድሮው የአድዋ ድል 118ኛ ዓመትና የሚያዚያ 27 የአርበኞች ድል 74ኛ ዓመት በጥምረት እንደሚከበር ድርጅቱ ገልጿል፡፡ “ዓለምን ያስደነቀውን የያኔዎቹ ጀግኖች አባቶቻችንንና እናቶቻችንን አኩሪ ድል በቴአትር፣ በሽለላ፣ በውዝዋዜ፣ በፊልም፣ በፎቶና በውይይት እንድንዘክረው ወስነናል” ብሏል አዘጋጁ፡፡
በፌስቲቫሉ ላይ መገኘት የሚፈልጉ ሁሉ እንዲታደሙለትም ጥሪውን አስተላልፏል ኬር ኤቨንትስ እና ኮሙዩኒኬሽን፡፡     

“ሚኒልክና አድዋ” በተሰኘው የሬይሞንድ ጆናስ መጽሐፍ ላይ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ገለፀ፡፡
ውይይቱ ነገ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ መፅሐፍትና ቤተ - መዛግብት ኤጀንሲ የስብሰባ አዳራሽ እንደሚካሄድም ታውቋል፡፡ ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት  የታሪክ ምሁር የሆኑት አቶ ብርሃኑ ደቦጭ ሲሆኑ፤ በውይይቱ ላይ የንባብ ቤተሰቦች  እንዲሳተፉ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…ክረምቱም እየመጣ ነው…ብርድ ብርድ ሊለን ነው፡፡ ለነገሩ… አለ አይደል… ዘንድሮ ፀሀዩዋ በሙሉ አቅሟ ወጥታም ‘ብርድ፣ ብርድ’ ይለናል፡፡ ምን ይደረግ! ብዙ ነገሮች ስረ መሰረታቸው እየተናደ፣ የትናንት በጎ ነገሮች አፈር እየለበሱ፣ እንግዳ ሲመጣ እግር አጥቦ የማሳደር ወንድማማችነት ወደ ‘አፈ ታሪክነት’ እየተለወጠ…ምነው ብርድ፣ ብርድ አይለንሳ! ልክ ነዋ…ምቾት በሌለበት ብርድ ‘ሰተት’ ብሎ ነው የሚገባው!  
ሁሉ በሽተኛ ሁሉ ራሴን ባይ
በቤታችን ደህና መጥፋቱ ነው ወይ!
የሚሏት አሪፍ አባባል አለች፡፡ እናማ…አሁን፣ አሁን የምናያቸውና የምንሰማቸው ነገሮች አብዛኞቹ  “በቤታችን ደሀና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ናቸው፡፡ ከታች እስከ ላይ (ይቅርታ፣ ‘ከላይ እስከታች’ ለማለት ፈልጌ ነው፡) ነገሩ ሁሉ ግራ የተጋባ ሆኗል፡፡ በስርአት መመራት እየቀነሰ አብዛኛዎቹ ነገሮች የሚሆኑትም፣ የማይሆኑትም በእኛ በጎ ፈቃድ ብቻ ነው፡፡ ክፋቱ ደግሞ በጎ ፈቃድ የሚለው ነገር ከውስጣችን ሙልጭ ብሎ እየወጣ ነው፡፡ (በጎ ፈቃድ? የምን በጎ ፈቃድ!)  
እናማ…ህዝባችን የምድሩ ጉዳይ ግራ ሲገባው ቀን ከሌት እየጸለየ ነው፡፡ እባክህ ይቺን አገር ታደጋት እያለ ነው፡፡ “እባክህ እንዲህ የሚያናክስንን፣ የሚያቧጭረንን፣ ውሃና ዘይት ያደረገንን ጋኔን አሸቅንጥረህ ወርውርልን” እያለ ነው፡፡ ጋኔኑ ተሽቀንጥሮ እንዲወረውርልን ግን…ትንሽዬም ብትሆን የራሳችንን አስተዋጽኦ የምናደርግ ብዙ አይደለንም፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የፀሎት ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…ስኮትላንዳውያን ‘ገብጋባ’ ናቸው ይባላል፡፡ እናላችሁ… አንዱ ስኮትላንዳዊ ከባድ የገንዘብ ችግር ይገጥመዋል፡፡ በጣም ከመቸገሩ የተነሳም እግዚአብሔርን ለመጠየቅ ወሰነ፡፡ “እግዚአብሔር  እባክህ እርዳኝ፡፡ ሱቄ ተወሰደብኝ፡ ገንዝብ ካላገኘሁ ቤቴም ሊወሰድብኝ ነው፡፡  እባክህ ሎተሪ እንዲደርሰኝ አድርግልኝ፡፡” ያን ቀን ሎተሪውን ሌላ ሰው ያሸንፋል፡፡ በተከታዩ ሎተሪ መውጫ ቀን ስኮትላንዳዊው እንደገና ይጸልያል፡፡ “እግዚአብሔር  እባክህ እርዳኝ፡፡ ሱቄ ተወሰደብኝ፤ ቤቴ ተወሰደብኝ፣ ገንዝብ ካላገኘሁ መኪናዬም ሊወሰድብኝ ነው፡፡” አሁንም ለሌላ ሰው ይደርሳል፡፡ ስኮትላንዳዊው አሁንም እንደገና ይጸለያል፡፡ “እግዚአብሔር  እባክህ እርዳኝ፡፡ ሱቄ፣ ቤቴና መኪናዬም ተወሰዱብኝ፡፡ አሁን የምበላው እንኳን አጣሁ፡፡ ብዙ ጊዜ እርዳታ ጠይቄህ አላውቅም፡፡ ደግሞ ጥሩ አገልጋይህ ነኝ፡፡ እባክህ ሎተሪ እንዲደርሰኝ አድርግልኝ!” ይሄኔ ከሰማይ ከፍተኛ ብልጭታ ታየና እግዚአብሔር ምን ቢለው ጥሩ ነው…”መጀመሪያ የሎተሪ ትኬት ሳትገዛ እንዴት ብዬ ነው እንዲደርስህ የማደርገው!” አጅሬው ለካ ከገብጋባነቱ የተነሳ አንድም ቀን የሎተሪ ትኬት ሳይገዛ ነበር የሚጸልየው፡፡
እናላችሁ…አንዳንዴ ነገረ ሥራችንን ስታዩ የሎተሪ ትኬቱን ሳንገዛ “እባክህ፣ ሎተሪ እንዲወጣልኝ አድርግልኝ! አይነት ጸሎት መደጋገም ነው፡፡
ታዲያላችሁ…ቀን አልፎ ቀን ሲተካ ከተስፋ ሰጪ ነገሮች ሁሉ ተስፋ የሚያስቆርጡ ነገሮች ሲበዙ ግራ ይገባችኋል፡፡ ለምን ተስማምተን መኖር እንዳቃተን ግራ የሚገባ ነው፡፡ የምንለያይባቸው፣ የጎሪጥ የምንተያይባቸው ነገሮች መብዛታቸው ምክንያት ለመስጠት እንኳን አስቸጋሪ ነው፡፡ በአንድ በኩል ስለማይገባንና የያዘው አጀንዳ  ‘መርዝ ይሁን ማር’ ገና ባልለየት ‘ግሎባላይዜሽን’ እያወራን በቤታችን እንኳን ተስማማትን መኖር እያቃተን ነው፡፡ የምር እኮ መደማመጥ አልተቻለም፡፡ የምንናገራቸው ነገሮች እንደ አዳማጩ ፍላጎት እየተመተሩ ‘ጠብ አውርድ’ አይነት ነገሮች በየቦታው ታያላችሁ፡፡ የሚከፋፍሉን ነገሮች በብዙ ቁጥር ነገ ተነገ ወዲያ “ምነው ከሳ አልክብኝ!” ያልነው ወዳጃችን  “ከሳ አልክብኝ ያልከው በሽተኛ ነህ ለማለት ነው!” አይነት ‘ቅልጥ ያለ ጠብ’ ሊፈጥር ይችላል፡፡
አንዲት ወዳጄ የገጠማትን ስሙኝማ…ከአዲስ አበባ ወጣ ካለ ከተማ ብቅ ብላ በሚኒባስ ስትመለስ መኪናው ውስጥ ከተፈቀደው በላይ ትርፍ ሰዎች ይገባሉ፡፡ ሾፌርም ትራፊክ እንደሚከሰው ቢለማመን የሚሰማው ጠፋ፡፡ ወዳጄም ነገር ለማብረድ ብላ አንደኛውን ትርፍ የገባ ሰው “መኪናው ሙሉ ሰው ብቻ ነው የሚጭነው…” ብላ ሳትጨርስ ሰውየው ምን ቢል ጥሩ ነው…“እኔ ግማሽ ሰው ነኝ!” እና አልወርድም አለ፡፡ በዛ ቢበቃ ጥሩ ነበር፡፡ ለወዳጆቹ “ሙሉ ሰው አይደለህም አለችኝ…” ብሎ ነገሩ ሁሉ ድብልቅልቁ ወጣ፡፡ እንደምንም በአንዳንድ ሰዎች ጣልቃ ገብነት ወደ አዲስ አበባ ተመለሰች፡፡
አያችሁልኝ አይደል! እንዲሁ በትንሽ ትልቁ ጠብ፣ ጠብ ስለሚለን ነው እንጂ “መኪናው ትርፍ ሰው አይጭንም፣” ማለት “እኔ ግማሽ ሰው ነኝ!” ያሰኛል?
እናማ…“በቤታችን ደህና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡
ንግግሮች እንኳን እየተሰነጣጠቁ ባለበት ወቅት ነገ ከነገ ወዲያ ሰላምታችን እንኳን ተመንዝሮና ተመነዛዝሮ ‘አገር ቀውጢ’ ቢሆን ምን ይገርማል፡፡ በንጹህ ልቦና የተነገሩ ምንም ጉዳት የሌለባቸው አባባሎች ወደ ዘር፣ ኃይማኖት፣ ፖለቲካ ምናምን እየተመነዘሩ “እውነትም የተዘጋ አፍ ዝንብ አይገባበትም…” እንድንል እያደረጉን ነው፡፡
እናላችሁ…“በቤታችን ደሀና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡
ብዙ ቦታ በጎ መልስ የሚመልስ ማግኘት እያዳገተ ነው፡፡ ሁሉም ብሶቱን እናንተ ላይ ሊወጣ ነው የሚሞክረው፡፡ “ሻዩ ውሀ ውሀ ነው የሚለው” ስትሉ  “ሻይ ቅጠሉን እኛ አላመረትነውም…” የሚሉ አሳላፊዎች የበረከቱበት ዘመን ነው፡፡ በሳንቃ መወልወያና በእጅ መጥረጊያ ፎጣዎች መካካል ልዩነቱ ግራ ገብቷችሁ ስትጠይቁ ግልምጫ የምታኙበት ዘመን ነው፡፡
ገንዘባችሁን ከፍላችሁ ስለምትገዙት አገልግሎትና ምርት ጥራት አፍ አውጥቶ መጠየቅ ‘ድፍረት’ እየሆነ የመጣበት ዘመን ነው፡፡ በማስታወቂያዎች የምንሰማቸውና የምናያቸው ነገሮች ከዋናዎቹ ምርቶችና አገልግሎቶች ጋር አልገጥም እያሉን ግረ ተጋብተናል፡፡ ስሙኝማ…አንዳንዴ ሳስበው ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…የአማርኛ ቋንቋ ቅጽሎች በሙሉ ማስታወቂያዎች ላይ በገፍ እየገቡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ ለመዝገበ ቃላት እንኳን የሚበቁ ቅጽሎች እንዳናጣ! ቂ…ቂ…ቂ…
እናማ…“በቤታችን ደሀና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡
‘የእኛው ሰውዬ’  አንድ ጊዜ “ምን ሲሉት ፋንድያ ይላል…” ምናምን ብለው ሙልጭ አድርገው ልክ ልካችንን ነግረውን ነበር፡፡ ዘንድሮ ‘ፋንድያ’ ምናምን አይባል እንጂ ‘ወንበር’ ማለት ሰፊው ህዝብ ላይ ‘መነስነስ’ የሚመስላቸው መአት አሉ፡፡ እናማ…“በቤታችን ደህና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡የትራፊክ መብራት ጠብቆ ማሽከርከር የህግ ጉዳይ ሳይሆን የአሽከርካሪዎች ‘በጎ ፈቃድ’ ጉዳይ እየሆነ ነው፡፡
 በየዕለቱ ነገሬ ብላችሁ ካያችሁ መብራት ጥሰው ለማለፍ የሚሞክሩና የሚያልፉ አሽከርካሪዎች ብዛት ይገርረማችኋል፡፡ ኮሚክ እኮ ነው…በመኪና መሪ ጀርባ የተቀመጠ ሁሉ የቸኮለና ‘የተጣደፈ’ እሱ ብቻ ይመስል መብራት ሲጥስ፣ ጡሩምባውን ሲያምባርቅ…“ኧረ ሥነ ምግባር ምን ጉድጓድ ውስጥ ተወሸቅሽ!” ያሰኛችኋል!
እናማ…“በቤታችን ደህና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡ ከነቢይ መኮንን ግጥም የቀነጨብኳትን አንብቧትማ፡፡
አንዳንዴ
አንጎሌን እንደ ዣንጥላ አጥፌ
አገርን በወግ ሰልችቼ፣ ፍቅሯን ከልቤ አጠንፍፌ
ወደ እሷ የሚያደርሱኝን መንገዶች ሁሉ አጥሬ
    ሌላ ሌላ አገር አያለሁ፡፡
አገሬ ግን…እንደጌታ የስቅለት ቀን
በአራት አቅጣጫ ተወጥራ
እመስቀል ላይ ተቸንክራ
ጣሯን ቁልቁል በማሰማት
ነገዋን በእኔ ለማየት “ላማ ሰበቅታኒ?” አለችኝ “ለማን ተውከኝ በዚህ ሰዓት?”
አዎ…አገር “ላማ ሰበቅታኒ? ለማን ተዋችሁኝ በዚህ ሰዓት?” እያለች ነው— የሚሰሟት ጥቂት፣ ጆሯችን ላይ የተኛን መአት ሆንን እንጂ!
እናማ…“በቤታችን ደህና መጥፋቱ ነው ወይ!” የሚያሰኙ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!

           ከአምስት ወር በፊት ነበር “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” የተሰኘ አዲስ የጋዜጠኞች ማህበር የመመስረት እንቅስቃሴ የተጀመረው፡፡ በምስረታው ሂደት ግን ከነባሮቹ የጋዜጠኞች ማህበራት ጋር አይጥና ድመት ሆኖ ቆይቷል፡፡ የማህበሩ ስያሜ ለውዝግብ መነሻ በመሆን ተጠቅሷል፡፡ በዚህ ብቻ ግን አላበቃም፡፡ ነባሮቹ ማህበራት “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” ውስጥ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በአመራር ደረጃ ተቀምጠዋል ሲሉ መተቸት ያዙ፡፡ በውጭ ኃይሎች ይደገፋል ሲሉም የወነጀሉ ቢሆንም በተጨባጭ ማስረጃ ማሳየት ግን አልቻሉም፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች፤ አሁን እየተወገዙ ካሉት ዓለም አቀፍ የመብት ተቋማት መካከል ብዙዎቹ ከተለያዩ ማህበራትና ከመንግስት ጋር ሲሰሩ እንደነበር ተናግረዋል፡፡
የማህበራት ምዝገባ ኤጀንሲ ለአዲሱ ማህበር ዕውቅና እንደማይሰጥ ያስታወቀው ባለፈው ሳምንት ሲሆን “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” በሚል ተመሳሳይ ስም የተመሰረተ ማህበር እንዳለ ኤጀንሲው አስታውቋል፡፡
የማህበሩ ሊቀመንበር ጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ፤ እንደ ማህበር እውቅና እስከሚሰጠን ድረስ ተግባራችንን እንቀጥላለን ብለዋል፡፡ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የማህበሩ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በበኩላቸው፤ ጉዳዩን ለቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል፡፡ ነባሮቹ የጋዜጠኞች ማህበራት አዲሱ ማህበር ዕውቅና ለማግኘቱ እምብዛም የተከፉ አይመስሉም፡፡
“የማህበራትን መቋቋም እናበረታታለን ድጋፍም እናደርጋለን” ያሉት የኢብጋህ ሊቀመንበር አቶ አንተነህ አብርሃም፤ እውቅና የተከለከለው ማህበር ግን ለመቋቋም ሲሞክር ነባር ማህበራትን “የመንግስት አሽከሮች፣ ተለጣፊዎች በሚል ውግዘትና ስድብ መጀመሩን በበጎ አላየነውም ብለዋል፡፡ ቀደምት ማህበራትን አውግዘው መነሳታቸውም የእነሱን መቋቋም እንደ ስጋት እንድናየው አስገድዶናል የሚሉት ሊቀመንበሩ፤ “ማህበሩ በውጭ ሃይሎች ገንዘብ እየተደገፈ ነው” ለሚለው መከራከሪያችን ማስረጃ አለን ብለዋል፡፡ ማንነታቸውን አሁን መግለፅ ከማንፈልጋቸው የውጭ ተቋማት “ምርጫ መጥቷል፤ በዚህ ምርጫ ይሄን ስርአት ካልጣልነው ሌላ ምርጫ የለንም፤ ትብብር አድርጉልን” ተብለን ተጠይቀን ነበር የሚሉት አቶ አንተነህ፤ እኛ ይሄን ባናደርግ ሌላ ማህበር እንደሚያቋቁሙ፣ ለጋዜጦች ገንዘብ እየሰጡ እኛን የሚያብጠለጥሉ ፅሁፎችን እንደሚያፅፉ፣ ከዚያም እኛም እንደምንጠፋና የመንግስት ስርአትም እንደሚቀየር ነግረውናል፤ እንደተባለውም ከሁለት ሳምንት በኋላ ማህበር ተቋቋመ፤ በሂደትም ለእኛ የተነገሩን ነገሮች መፈፀም ጀመሩ ብለዋል፡፡ ይህን መረጃ በመንተራስ አስቀድመን ጋዜጠኞች እንዲጠነቀቁ ተናግረናል ያሉት ሊቀመንበሩ፤ “የበግ ለምድ ለብሰው ከመጡ ተኩላዎች ተጠንቀቁ ማለት ውንጀላ አይደለም” ብለዋል፡፡
ማህበሩ፤ “አርቲክል 19” ከተባለ የውጭ ድርጅት ጋር በመመሣጠር አባላቱን ለማሰልጠን ተንቀሳቅሷል የሚሉት አቶ አንተነህ፤ በኢትዮጵያ ህግ “አርቲክል 19” አገር ውስጥ ውስጥ መንቀሳቀስ አይችልም፣ በውጭ ዜጋ ገንዘብና ድገፍ የሚካሄድ የመብት ማስከበር እንቅስቃሴ በህግ የተከለከለ ነው ብለዋል፡፡ ተቋሙ የተለያዩ የስለላ ስራዎች እንደሚሰራ፣ የተለያዩ የአመፅና ህገ ወጥ ተግባራትን እንደሚያነሳሳ ስኖውደን (የሲአይኤ አባል የነበረው ግለሰብ) ማጋለጡን የጠቆሙት አቶ አንተነህ፤ አዲስ ለሚመሰረተው ማህበር አባላት “ሴፍቲ” እና “ሴኩሪቲ” ጉዳይ ላይ ድብቅ ስልጠና መስጠቱ ተገቢ አይደለም ባይ ናቸው፡፡ አሁን እያንዳንዱ ምን እንደሚሰራ በሚገባ ይታወቃል” ያሉት አስተያየት ሰጪው፤ “ማንም የፈለገውን ይበል፣ ከዚህ በኋላም ስለ ማህበሩም ሆነ ስለሌሎች የውጭ ተቋማት ለአባሎቻችን ግንዛቤ በመስጠት ግዴታችንን እንወጣለን” ብለዋል፡፡
የኢጋማ ሊቀመንበር አቶ መሰረት አታላይ በበኩላቸው፤ አዲስ ማህበር ማቋቋማቸው ላይ ምንም ተቃውሞ የለንም፤ ነገር ግን እኛን አውግዘው መነሳታቸው ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡ ለወደፊትም ቢሆን አፍራሽ ተልእኮ ላይ የተሰማራ ጋዜጠኛ እና ማህበር አንፈልግም ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ከዚህ በኋላ ከማህበሩ ጋር በተያያዘ መግለጫና ማብራሪያ ለመስጠት እንቸገራለን ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ነፃ ጋዜጠኞች ማህበር ሊቀመንበር አቶ ወንደወሰን መኮንንም፤ አዲሱ ማህበር ነባሮችን በማውገዝ መጀመሩ ተገቢ አልነበረም ባይ ናቸው፡፡ ማህበር መቋቋሙ የሚደገፍ ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ነገር ግን ጦርነት አውጆ መነሳት በስሜታዊነት ከመነዳት የዘለለ ፋይዳ የለውም ብለዋል፡፡ ማህበሩ ከውጭ ሃይሎች ጋር ተሣስሮ ለመስራት መሞከሩ በሃገር ህልውና ላይ አደጋ የሚጋርጥ ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ለውጭ ሃይሎች የሚንበረከክ ማህበር ማየት እንደማይፈልጉ ጠቁመው፤ ከአዲሱ ማህበር ጋር ምንም አይነት የጥቅም ግጭት እንደሌላቸውም ገልፀዋል፡፡ እንዲህ ያለ ውዝግብና ትርምን ውስጥ የዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀን በዛሬው ዕለት በአገራችን ይከበራል፡፡

ሰውየው ወደ አደን ሊወጣ እየተዘገጃጀ ነው፡፡ መሣሪያ ሲያዘጋጅ፣ ጥይት ሲቆጥር ጥሩሩን (የውጊያ ልብሱን) ሲያጠልቅ፤ ዝናሩን ሲታጠቅ፤ ከአፋፍ ሆኖ የሚያስተውለው ጎረቤቱ፤ “ምን ጉድ መጣ? መጠየቅ አለብኝ ብሎ ወደ ቁልቁል ወረደ፡፡
ታጣቂው ሲወጣ ጎረቤቱ አገኘው፡፡
“እንዴት አደርክ ወዳጄ!” አለ አዳኙ ሞቅ አድርጎ፡፡
“ደህና እግዚሃር ይመስገን! አንተስ እንዴት አድረሃል?”
“ወደ ደጋ ወጥቼ ሠርጉም፣ ልቅሶውም ተደባልቆብኝ፤ እሱን ተወጥቼ መምጣቴ ነው! አሁንኮ ካፋፍ ላይ ሆኜ ቁልቁል ሳስተውል ትጥቅህን ስታዘጋጅ አይቼህ ምን ገጥሞት ይሆን? ብዬ ነው ልጠይቅህ የመጣሁት?” አለው፡፡
“የለም፤ ወደ ጫካ ለአደን እየሄድኩ ነው፡፡”
“ምን ልታድን አስበህ ነው?”
“ነብር”
“ነብር?!” አለ ጎረቤት፤ በድንጋጤ፡፡
“ምነው ደነገጥክ?”
“ነብር አደገኛ ነዋ!”
“ቢሆንም ተዘጋጅቻለሁ፤ አሳድጄ እገድለዋለሁ!”
“ብትስተውኮ አለቀልህ ማለት ነው፡፡ እሺ ብትስተው ምን ይውጥሃል?”
“ከሳትኩማ ወዲያውኑ አቀባብዬ ደግሜ እተኩሳለሁ”
“ሁለተኛ ጊዜ ብትስተውስ?”
“ወዲያው ለሶስተኛ ጊዜ አቀባብዬ ግንባሩን እለዋለሁ!”
“ለሶስተኛ ጊዜ ብትስተውስ?”
“እህ! አንተ ከእኔ ነህ ወይስ ከነብሩ?!”
*      *      *
ነገርን ከአሉታዊ ገፁ አንፃር ብቻ ማየት እጅግ ጎጂ ባህል ነው! ለሀገር ዕድገት ስንል፡፡ ለሀሳብ ነፃነት ስንል፤ በምንደክምበት ረዥም መንገድ ከማን ጋር መጓዝ ተገቢ እንደሆነ ያልለየ ጋዜጠኛ ዓላማና ግቡ ጥያቄ ውስጥ የሚገባ ነው፡፡ ቢያንስ የቱ ድረስ ተራራውን አብረን እንጓዛለን ማለት ያባት ነው! የሀገር ጉዳይ ከፅሁፍና ከሀሳብ ነፃነት ተለይቶ አይታይም - ዲሞክራሲያዊ አካሄድ አለን የምንል ከሆነ፡፡ የህዝቡን መረጃ የማግኘት ነፃነት ሳናከብር ለሀገርና ለህዝብ ዲሞክራሲያዊ መብቶች እየታገልን ነው ብንል ቢያንስ ወይ ለበጣ ወይ የዋህነት ነው፡፡ ሳይማሩ ማስተማር ለአስተማሪውም ለተማሪውም ኪሳራ አለው፡፡ አመለካከትን ያዛባል፡፡ ጎዶሎ ዕውቀት ሊሆን ይችላል፡፡ የአላዋቂነትን ገደል ያሰፋል፡፡ ውጤቱም-ያልነቃ፣ የማይጠይቅ፣ ለለውጥ ያልተዘጋጀ ህዝብ ይዞ መኖር ይሆናል፡፡ ያ ደግሞ “ባለህበት ሃይ” ወይም “ቀይ ኋላ ዙር” የሚል የሰልፍ ህግ ከማክበር ያለፈ አገራዊ ፋይዳ የለውም፡፡ አርቀን እናስተውል፡፡ የዓለም ኢንፎርሜሽን ቀን፣ የዓለም ላብ አደሮች ቀን፣ የዓለም የሴቶች ቀን፣ የዓለም የጤና ቀን፣ የዓለም የእናቶች ቀን፣ የዓለም የህፃናት ቀን .. ዛሬም የዓለም የፕሬስ ቀን፤ እናከብራለን እንላለን፤ ሁሉም፤ ሀሳብን በነፃ ጋር ቅርብ ቁርኝት ያላቸው የራቁ ፅንሰ-ሀሳቦች ናቸው፡፡
እዚህ ላይ የፈረንሳይ ፈላስፋ ፒየር ጆሴፍ ፕሩዶንን ማስታወስ ተገቢ ሳይሆን አይቀርም፡- ብዙ ፈላስፎች ህዝብን ለመግዛት በሚፅፉበት ዘመን እሱ ህዝብ ሆነን ስለመገዛት ፅፏል፡- “መገዛት ማለት መታሰብ ማለት ነው፡፡ መታወስ ማለት ነው፡፡ መመዝገብ ማለት ነው፡፡ የመንግስት ቁጥጥር ውስጥ መግባት ማለት ነው፡፡ ተጠያቂ መሆን ማለት ነው፡፡ መለካት ማለት ነው፡፡ ተለይቶ መታየት ማለት ነው፡፡ በኦዲተር መታወቅ ማለት ነው፡፡ የፈጠራ መለያ ማግኘት ማለት ነው፡፡ የንግድ ፈቃድ ማግኘት ነው፡፡ ሥልጣን ማግኘት ነው፡፡ መካተት ነው፡፡ መቀጣት ነው፡፡ መታነፅ ነው፡፡ የእርማት መንገድ ላይ መቀመጥ ነው፡፡ መስተካከል ነው፡፡ ይህ ሁሉ እንግዲህ በየአንዳንዱ ክንዋኔ፣ በየአንዳንዱ ሽያጭና ግዢ እንዲሁም፣ በየአንዳንዱ እንቅስቃሴ ውስጥ የሚታይ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ መብትን መገፈፍ፣ የመናገር፣ የመፃፍ፣ የመሰብሰብ፣ የመደራጀትን ነፃነት ማጣት፣ አግባብ አይደለም፡፡ ዕውቅና ማጣት መገደብ፣ መገፋት፣ መጣል፣ መረጋገጥ፣ መወገር፣ ወዘተ በኃይል መገዛት ነው፡፡ ያ ደግሞ የዲሞክራሲን ሰፈር አያቅም፡፡
ተገዢዎች ጥበብ እንዳላቸው አንርሳ፡፡ ልምድ እንዳላቸው አንርሳ፡፡ ከትላንት ሊማሩ እንደሚችሉ አንርሳ፡፡ ህዝቦች፤ መማረር፣ መናደድ፣ ማዘን፣ ትተው፤ ዝም ሊሉ እንደሚችሉ አንርሳ፡፡ ዲሞክራሲ ሙልጭ እሚወጣው (Zero Sum) ይሄኔ ነው!
በንፁህ ልቦና የማይሰራ የፕሬስ ሰው ህዝብንም፣ ሙያውንም፣ እራሱንም ይጎዳል፡፡
የፕሬስ ሰው በመደለል አያምንም፡፡ ሥልጣንንም አይቋምጥም፡፡ የኢኮኖሚንም ሆነ የፖለቲካ ሥልጣን ሙሰኞች፤ ስለሐቀኛ ጋዜጠኛ ሲያስቡ የሚጨንቃቸው ለዚህ ነው!
“ተመስጌን ነው!
የእንግሊዝን ጋዜጠኛ
ጉቦ መስጫ፣ ማማለያ
ወይም እጁን መጠምዘዢያ
ቅንጣት ታህል ቦታ የለም!!
ያለጉቦ መስራቱንም
መመልከቻም፣ ጊዜ የለም
መገንዘቢያም፣ ወቅት አደለም!!
ተመስጌን ነው!”
    ይለናል ሐምበር ዎልፍ፤ ጣሊያን የተወለደው እንግሊዛዊ ገጣሚ፡፡
ፕሬስ አጋዤ ነው ብሎ የሚያምን መንግሥት ራሱን ማያ መስተዋት ያገኛል፡፡ ሆደ-ሰፊ አመለካከት፤ አዎንታዊና ገንቢ ምዛኔ ያለው ሥርዓት ጤናማ አገርን ያለመልማል፡፡
“በፕሬስ አትናደድ፡፡ አለበለዚያ አብዛኛው ሥራህ የህዝቡን የፖለቲካ ህይወት ካልገዛሁ ማለት ብቻ ይሆናል፡፡” (ክሪስታቤል ፓንክረስት) ያ ደግሞ የሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ጉዞን ያጨናግፋል፡፡ ጠብታዎችን በሙሉና በጥልቅ ዐይን ማየትና በጊዜ ቦታ ቦታ ማስያዝስ ከብዙ መጪ ጠንቀኛ ዥረቶች ይገላግለናል፡፡
ታሪክ ፀሀፊዎች፤ “በትክክለኛው የታሪክ ወገን መቆም፤ ከዛሬ ጎን ሳይቆሙ ሊደረግ ይችላልን?” በሚለው ጥያቄ ዙሪያ ብርቱ ሙግት ያቀርባሉ፡፡ ነፃ ጋዜጠኛ ግን ይህን ጥያቄ በአዎንታ አይመልሰውም፡፡ ይልቁንም፤ ተጨባጩ ዕውነት ባለበት ቦታ ሁሉ ጋዜጠኛ አለ፤ ይላል፡፡ ምነው ቢሉ፤ የአሜሪካው ፀሐፊና ጋዜጠኛ ሐንተር ቶምፕሰን ነገሩን እንዲህ ይደመድምልናል፡-
“እኔ በአለፉት አሥር ዓመታት የማውቀውን ዕውነት ሁሉ ብፅፍ ኖሮ እኔን ጨምሮ ከሪዮ እስከ ሲያትል ያለው 600 ያህል ህዝብ እስር ቤት ይበሰብስ ነበር፡፡ በጋዜጠኛነት ሙያ ውስጥ፤ ፍፁም ውድና የማይገኝ (rare) እንዲሁም አደገኛ ሸቀጥ (dangerous commodity) ፍፁም እውነት ነው፡፡” ይህ ማለት ግን አንፃራዊ እውነት፣ ተጨባጭ ሁኔታ ላይ የተመረኮዘ መረጃ የለም ማለት አይደለም፡፡ ከላይ ያልነውን ሁሉ ብለን ስናበቃ፤ ስለ ፕሬስና ፕሬስ ሰዎች ለመናገር፣ ከሌላ ዓላማና ግብ አኳያ የተዛባ፣ የተዛነፈ ወይም ፍፁም በሥሃ የተሞላ አመለካከት ይዞ መገኘት፤ “እቺ ጎንበስ ጎንበስ ሣር ፍለጋ ሳትሆን ዱባ ለመስረቅ ናት” ከማለት በቀር ምን ይባላል?!

Saturday, 03 May 2014 12:27

የወቅቱ መልዕክት

አልገልህምን ምን አመጣው?

አሳዳጅና ተሳዳጅ እየተሯሯጡ ነው፡፡ ተሳዳጅ በመሳደድ ስጋትም፣ በደመነብስም አንድ ረዥም ዛፍ ላይ ይወጣል፡፡ አሳዳጅ በእጁ ጦር ይዟልና ዛፉ ላይ መውጣት አልቻለም፡፡ ስለዚህ፤
“ና ውረድ፤ አልገልህም!” አለው፡፡
ዛፍ ላይ ያለው ተሳዳጅ፤
“ወዳጄ! ዝም ብለህ ና ውረድ አትለኝም ወይ? አልገልህምን ምን አመጣው?” አለው

የወቅቱ  ጥቅስ


ቃለ -  ምልልስ
ጋዜጠኛ - “ሚስተር ስታሊን ቢሞት በዓለም አቀፉ ጉዳይ ላይ ምን ለውጥ ይመጣ ይመስልሻል?”
የክሬምሊን ቃል - አቀባይ - “ይሄን ጥያቄ መጠየቅህ ለአንተ ለጠያቂው በጣም ጥሩ ነው፡፡ ለእኔ ለመላሹ ግን ጥበብ የጐደለው ጥያቄ ነው!”

43 ሚሊዮን ዶላር ፈጅቶባታል ተብሏል

          ግብጽ 43 ሚሊዮን ዶላር ያወጣችበትንና የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ የግንባታ ሂደት በአየር ላይ ሆኖ እየተከታተለ መረጃ የሚሰጣትን ወታደራዊ ሳተላይት ከሁለት ሳምንት በፊት ማምጠቋን በይፋ እንደገለፀች   አህራም ኦንላይን ዘገበ፡፡
ኢጂሳት የሚል ስያሜ የተሰጠው ሳተላይቱ፤ የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ቁመት፣ ውሃ የመያዝ አቅምና የሚለቀውን የውሃ መጠን የተመለከቱ መረጃዎችን እየተከታተለ የሚያቀርብ እንደሆነ የገለጹት የግብጽ ብሄራዊ የሪሞት ሴንሲንግና ስፔስ ሳይንስስ ባለስልጣን ምክትል ፕሬዚደንት አላ ኤልዲን ኤል ናህሪ፣ ሳተላይቱ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከሚከናወንበት አካባቢ በተጨማሪ፣ የአባይ ወንዝ በሚፈስባቸው የተለያዩ አካባቢዎች ላይ በማተኮር፣ ከፍተኛ የጥራት ደረጃ ያላቸው ጠቃሚ ፎቶግራፎችን እያነሳ እንደሚልክ  ሰሞኑን በካይሮ በተካሄደ ሴሚናር ላይ ተናግረዋል፡፡
ለሁለት ወራት ከሚቆይ የሙከራ ጊዜ በኋላ፣ በመጪው ሰኔ ወር አጋማሽ ላይ መደበኛ ስራውን ይጀምራል የተባለው  ሳተላይቱ፣ የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እየተከታተለ ለግብጽ ባለስልጣናት መረጃ ከማቀበል ባለፈ፤ የኮንጎ ወንዝን ተፋሰስ በመከተል በሚያነሳቸው ፎቶግራፎች፣ ወንዙን ከአባይ ጋር ለማገናኘት ታስቦ የተረቀቀውን የፕሮጀክት ሃሳብ ውጤታማነት በተመለከተ የራሱን ፍተሻ ያደርጋል ተብሏል፡፡ የግብጽ መንግስት ሳተላይቱ ከሚያቀርባቸው መረጃዎች የሚያገኘው ውጤት፣ ከኢትዮጵያ ጋር በግድቡ ዙሪያ የጀመረው ክርክር ተጠናክሮ እንዲገፋ እንደሚያደርገው ያምናል ያሉት አላ ኤልዲን ኤል ናህሪ፣ ግድቡን ከታለመለት የሃይል ማመንጨት ስራ ውጭ ለማዋል በኢትዮጵያ በኩል ማናቸውም አይነት እንቅስቃሴዎች ቢደረጉና ጉዳዩ ወደ አለማቀፍ ግልግል የሚያመራ ከሆነም፣ የግብጽ መንግስት ይሄንኑ የሳተላይት መረጃ ለክርክሩ የህግ ድጋፍ ለማግኘት እንደሚጠቀምበት አል አህራም ለተባለው  ጋዜጣ ተናግረዋል፡፡
አል አረቢያ ድረ-ገጽ በበኩሉ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ፣ ግብጽ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ ላይ የምታነሳቸውን ቅሬታዎች ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ለማቅረብ ከወሰነች፣ ኢትዮጵያ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ መሆኗን ባለፈው ሳምንት መናገራቸውን ዘግቧል፡፡
የግድቡ መገንባት የአባይን ወንዝ የውሃ መጠን በመቀነስ ተጎጂ ያደርገናል በሚል ተቃውሞአቸውን በተደጋጋሚ የገለፁት የግብጽ ባለስልጣናት፣ ሳተላይቱ የሚሰጣቸውን መረጃ መሰረት በማድረግ የሚደርሱበት ውጤት፣ በግድቡ ዙሪያ ከኢትዮጵያ ጋር በሚያደርጉት ክርክር ይዘውት የቆዩትን አቋም እንደሚያጠናክርላቸው ተስፋ ማድረጋቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡ የግብጽን ሳተላይት ማምጠቅ በተመለከተ፣ አንዳንድ ድረገጾች ቀደም ብለው መረጃ ያወጡ ቢሆንም፣ የአገሪቱ መንግስት ስለጉዳዩ ይፋዊ መግለጫ ሲሰጥና ድርጊቱን ሲያምን የአሁኑ የመጀመሪያው  ነው፡፡