Administrator

Administrator

 ወታደራዊው ሃይል ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ባካሄደው መፈንቅለ መንግስት ከስልጣን የወረዱትና በግዞት የቆዩት የቡርኪና ፋሶው የሽግግር መንግስት ፕሬዚዳንት ሚሼል ካፋንዶ ረቡዕ ዕለት ወደ ስልጣናቸው መመለሳቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ፕሬዚዳንት ሚሼል ካፋንዶ ወደስልጣናቸው መመለሳቸውን ይፋ ያደረጉት፣ የመፈንቅለ መንግስቱ መሪና ለአንድ ሳምንት በስልጣን ላይ የቆዩት የአገሪቱ መሪ  ጄኔራል ጊልበርት ዴንድሬ የስልጣን ሽግግሩን ለመታዘብ ወደ አገሪቱ በመግባት ላይ የነበሩ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት መሪዎችን ለመቀበል ወደ አውሮፕላን ማረፊያ ባመሩበት ወቅት ነው ብሏል ዘገባው፡፡
የምዕራብ አፍሪካ አገራት የኢኮኖሚ ማህበረሰብ ኢኮአስ በሽግግር መንግስቱና በወታደራዊው ሃይል መካከል የተፈጠረውን ግጭት በሰላማዊ ድርድር ለመፍታት ያስችላል በሚል ባቀረበው የድርድር ሃሳብ መሰረት፣ አገሪቱ ወደ ብጥብጥ እንዳትገባ የመፈንቅለ መንግስቱ መሪዎች ከቤተ መንግስቱ እንዲርቁ መደረጋቸውን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ኮፋንዶ ወደ ስልጣናቸው እንደተመለሱ ማወጃቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡በወታደራዊው ሃይልና መፈንቅለ መንግስቱን በተቃወሙ የአገሪቱ ዜጎች መካከል በተነሳው ግጭት ከ10 በላይ ሰዎች መሞታቸውንና ከ100 በላይ የሚሆኑ የአገሪቱ ዜጎችም መቁሰላቸው ተነግሯል፡፡
ባለፈው አመት ጥቅምት ወር ላይ በተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመጽ ከስልጣናቸው የወረዱትን የቀድሞውን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ብሌስ ኮምፓዎሬን ተክቶ መንበረ መንግስቱን የተረከበው የቡርኪና ፋሶ የሽግግር መንግስት፣ በመጪው ጥቅምት ወር በሚደረግ ምርጫ ስልጣኑን ለማስረከብ እቅድ እንደነበረውም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

    13.50 ዶላር የነበረው መድሃኒት፣ 750 ዶላር ገብቷል
    
   ኤችአይቪ ቫይረስ በደማቸው ውስጥ የሚገኝ ዜጎች በሚወስዱት መድሃኒት ላይ የ5,000% የዋጋ ጭማሪ ያደረገው የአሜሪካ መድሃኒት አምራች ኩባንያ፣ ከታማሚዎች፣ ከመብት ተሟጋች ቡድኖች፣ ከህክምና ማህበራት፣ ከፖለቲከኞችና ከማህበራዊ ድረገጽ ተጠቃሚዎች ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመውና ዋጋውን ለመቀነስ ማሰቡን እንደገለፀው ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ቱሪንግ ፋርማሲዩቲካልስ የተባለው የመድሃኒት አምራች ኩባንያ፤ ዳራፕሪም በመባል የሚታወቀውን የመድሃኒት ምርቱን የመሸጫ ዋጋ ከ13.50 ዶላር ወደ 750 ዶላር ማሳደጉን ማስታወቁን ተከትሎ ከታማሚዎችና ከተለያዩ አካላት ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመው የጠቆመው ዘገባው፣ የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚም የተወሰነ የዋጋ ቅናሽ ለማድረግ ማሰባቸውን እንደተናገሩ ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የዋጋ ጭማሪው ያስነሳውን ተቃውሞ ለማጣጣል የሞከሩት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ማርቲን ሸክሬሊ፣ ተቃውሞውን የሚሰነዝሩት ስለ መድሃኒት አምራች ኢንዱስትሪው አካሄድ በቂ ግንዛቤ የሌላቸው ሰዎች ናቸው፤ የዋጋ ጭማሪውን አድርገን የምናገኘውን ተጨማሪ ገንዘብ ሌሎች መድሃኒቶችን ለመፍጠር ለምናደርገው ምርምር ለማዋል ነበር ያሰብነው ብለዋል፡፡
ዋና ስራ አስፈጻሚው ማርቲን ሸክሬሊ በትዊተር ገጻቸው ላይ የተሰነዘረባቸውን ከፍተኛ ተቃውሞ ተከትሎ፣ ቱሪንግ ፋርማሲዩቲካልስ የተባለው ኩባንያቸው በቅርቡ ከህብረተሰቡ የመግዛት አቅም ጋር የሚመጣጠን የዋጋ ቅናሽ እንደሚደርግ ቢናገሩም፣ ምን ያህል የዋጋ ቅናሽ ለማድረግ እንደታሰበ በግልጽ አላሳወቁም፡፡
ኩባንያው ዳራፕሪም የተባለውንና የቶክሶፕላዝሞሲስ የፓራሳይት ኢንፌክሽንን በማከም ረገድ ፍቱን የሆነውን መድሃኒት አምርቶ የመሸጥ ፍቃድ ያገኘው በቅርቡ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ኤችአይቪ ኤድስን በመሳሰሉ በሽታዎች የተጠቁና በሽታን የመከላከል ተፈጥሯዊ አቅማቸው ደካማ የሆኑ ታማሚዎች መድሃኒቱን በስፋት እንደሚወስዱ ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜናም በማህበራዊ ድረ-ገጾች ላይ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የሚሰነዘሩ ሃሳቦችን መነሻ በማድረግ ቢቢሲ ባወጣው ዘገባ፣ በአሁኑ ወቅት በአገረ አሜሪካ አይንህን ለአፈር በመባልና በመጠላት ረገድ፣ የተጋነነ የዋጋ ጭማሪ ያደረገውን ኩባንያ የሚመሩት የ32 አመቱ ማርቲን ሸክሬሊ ቱሪንግ፣ ቀዳሚውን ስፍራ ሊይዙ እንደሚችሉ ጠቁሟል፡፡

    በስኳር በሽታ ሳቢያ የተጐዱ የልብ የደም ቱቦዎችና የሰውነታችን ውስጣዊ አካላቶች የአበባ ጐመን በመመገብ በፍጥነት እንዲጠገኑ ማድረግ እንደሚቻል በዘርፉ ጥናት ያደረጉ ባለሙያዎች ገለፁ፡፡
 በአሜሪካ ዋርዊክ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ባሉ ምሁራን የተደረገና በቅርቡ ይፋ የሆነ አንድ ጥናት እንዳመለከተው፤ በአበባ ጐመን ውስጥ የሚገኘውና ሰልፎራፔን የተሰኘው ንጥረ ነገር የደም ቱቦዎችን የሚጠብቁ ኢንዛይሞች በብዛት እንዲመረቱ ያደርጋል፡፡ ይህም በሴሎች ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሞሎኪውሎች ቁጥር እንዲቀነስ እንደሚያደርግ ባለሙያዎቹ ገልፀዋል፡፡ ከስኳር በሽታ ጋር ግንኙነት ያለውና Hyperglycemia በመባል የሚጠራው ከፍተኛ የጉሉኮስ መጠን በደም ስሮች ላይ የሚያስከትለውን ጉዳት በአበባ ጐመን ውስጥ የሚገኘው ሰልፎራፔን የተባለው ኢንዛይም እንደሚጠግነው መረጋገጡንም ምሁራኑ ተናግረዋል፡፡ የስኳር ህሙማን ከጤናማዎቹ በአምስት እጥፍ ለልብ በሽታዎች የተጋለጡ ናቸው፡፡ የስኳር ህመም በልብ ደም ስሮች ላይ በሚያስከትለው ጉዳት ሳቢያ ስትሮክና የልብ ድካም ይከሰታል፡፡

ለጤናዎ 10 ጠቃሚ ምግቦች
ፈረሰኛ ለስኳር ህሙማን ይመከራል
የምንመገባቸውን ምግቦች በማስተካከል ጤናችን የተጠበቀ ማድረግ እንደሚቻል የዘርፉ ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡ ቀጥሎ የተዘረዘሩት 10 የምግብ ዓይነቶች ሰውነታችን የበሽታ መከላከል አቅሙን እንዲጨምር በማድረግ፣ ጤናማና ደስተኛ ህይወት ለመምራት እንደሚያስችለን Changeone.com ከተሰኘው ድረ ገፅ ያገኘነው መረጀ ያመለክታል፡፡ እነዚህ ለጤናዎ ጠቃሚ የሆኑ አስር የምግብ አይነቶች የሚከተሉት ናቸው፡-
አሣ - ከእንስሳት የሚገኘውን ሥጋ የሚተካውና ጥሩ የፕሮቲን ምንጭ የሆነው አሣ Omega 3 ለተባለው ፋቲአሲድ ዋንኛ ምንጭ በመሆንም ይታወቃል፡፡ እነዚህ ፋቲአሲዶች የደም ቅዳዎቻችን ንፁህ እንዲሆኑ ያደርጋሉ፡፡ አሣ በተለይ ለስኳር ህሙማን ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው የምግብ አይነት ነው፡፡ የስኳር በሽተኞች አብዛኛውን ጊዜ (HDL) የተሰኘው ጠቃሚ ኮሌስትሮል እጥረት ይታይባቸዋል፡፡ Omega 3 ይህንን የኮሌስትሮል እጥረት በማስተካከል ይታወቃል፡፡
በሣምንት ቢያንስ ሁለት ቀን አሣን መመገብ ለጤና እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ሳልመን፣ ማካፌል እና ቱና የተባሉት የአሣ ዓይነቶች የፋቲ አሲዱ ዋንኛ መገኛዎች ናቸው፡፡
የዶሮ ስጋ
ፈረሰኛ የምንለው የዶሮ ብልት፤ ለስኳር ህሙማን እጅግ በጣም ተመራጭና ጠቃሚ የምግብ አይነት ነው፡፡ የዘርፉ ባለሙያዎች ፈረሰኛን “ተአምረኛው ምግብ” ሲሉ ይጠሩታል፡፡ ፈረሰኛ የሥጋ ምግቦች ከያዙት የስብና የኮሌስትሮል መጠን በእጅጉ ያነሰ ነው የያዘው፡፡ በ85 ግራም ፈረሰኛ ውስጥ 142 ካሎሪና 3 ግራም ስብ ብቻ ይገኛል፡፡
እርጐ
እርጐ በፕሮቲንና ክብደትን ለመቀነስ በሚረዳው ካልሲየም በተባለው ንጥረ ነገር የዳበረ ነው፡፡ በርካታ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት፤ በካልሲየም የዳበሩ ምግቦችን የሚመገቡ ሰዎች በቀላሉ ክብደታቸውን ለመቀነስ ይችላሉ፡፡ ደስተኛና ጤናማ ህይወት እንዲኖርዎ የእርጐ ወዳጅ ይሁኑ፡፡ ቁርስዎን ቅባት የሌለው እርጐ በመውሰድ ይጀምሩ፡፡
አትክልቶች
አትክልቶች በተፈጥሮአቸው ዝቅተኛ ካሎሪ ነው ያላቸው፡፡ በፋይበር (አስር) የበለፀጉም ናቸው፡፡ የምግብ ገበታዎን ለጤና ከፍተኛ ጠቀሜታ ባላቸው ንጥረ ነገሮች በዳበሩት አትክልቶች ሞሉት ማለት የደም ስኳር መጠንዎን ተቆጣጠሩ ማለት ነው፡፡
ፍራፍሬ
ፍራፍሬዎች የከፍተኛ ፋይበር ምንጭ ሲሆኑ ዝቅተኛ ስብና ዝቅተኛ ካሎሪን በመያዝም ይታወቃሉ፡፡ ፍራፍሬዎች ልባችንን፣ ዓይናችንንና ጥርሶቻችንን ከበሽታ በሚከላከሉ አንቲኦክሲደንቶች የበለፀጉ ናቸው፡፡ ፍራፍሬዎችን ከጭማቂው ይልቅ እንዳለ መመገብን ይምረጡ፡፡ በርካታ ለጤና ጠቃሚ የሆኑ ነገሮች በፍሬው ላይ ስለሚገኙና እነዚህ ጠቃሚ ነገሮች በሚጨመቅበት ወቅት ስለሚጠፉ ፍሬውን እንዳለ መመገቡ ጠቀሜታው ከፍ ያለ ይሆናል፡፡ ፍራፍሬዎች በተፈጥሮ ስኳርና ካሎሪ የበለፀጉ በመሆኑ በብዛት ከመመገብ መታቀብ ይኖርብናል፡፡
ለውዝ
ለውዝ የቫይታሚን E ዋንኛው ምንጭ ነው፡፡ ይህ ቫይታሚን በውስጡ የያዘው አንቲኦክሲደንት ሴሎችን በመጠበቅ የነርቭና የአይን ጉዳት እንዳይከሰት ያደርጋል፡፡ ለውዝ በበርካታ ጠቃሚ የስብ አይነቶች የተሞላ የምግብ አይነት ነው፡፡ እነዚህ ስቦች የልብ በሽታን በመከላከልና ኢንሱሊን ያለመቀበል ሂደትን በመቀነስም ይታወቃሉ፡፡ የደም ውስጥ የስኳር መጠንንም ለመቆጣጠር ያስችላሉ፡፡ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት፤ ለውዝን አዘውትሮ መመገብ ክብደትን ለመቀነስ ይረዳል፡፡ የስኳር ህመምተኛ ከሆኑ ግን ለውዝን አዘውትረው አይመገቡ፡፡
ቀረፋ
በምግብዎ ውስጥ ቀረፋን ጣል የሚያደርጉ ከሆነ፣ አስገራሚ በሆነ ሁኔታ የደምዎ የስኳር መጠን ቀንሶ ያገኙታል፡፡ በቀረፋ ውስጥ የሚገኙ ንጥረ ነገሮች ሰውነታችን ኢንሱሊንን በአግባቡ እንዲጠቀም ያደርጉታል፡፡ በስኳር ህሙማን ላይ የተደረገ ጥናት፤ ግማሽ ማንኪያ ቀረፋ በየዕለቱ የሚወስዱ ሰዎች የደም የስኳር መጠናቸው በአስገራሚ ሁኔታ ቀንሶ ተገኝቷል፡፡ የቀረፋን ዱቄት በዳቦ ወይንም በሌሎች ምግቦችዎ ውስጥ በመጨመር ይመገቡ፡፡ እንጨቱንም በሻይ መልክ እያፈሉ በመጠጣት ጤናዎን ይጠብቁ፡፡
ጥራጥሬ
የጥራጥሬ ምግቦች በፋይበር የበለፀጉ ናቸው፡፡ አዘውትረው ቢመገቧቸው ጤናዎን ለመጠበቅ በእጅጉ ይጠቅምዎታል፡፡
የወይራ ዘይት
የወይራ ዘይት በልብ በሽታ የመያዝ ዕድልን ይቀንሳል፡፡ የደም የስኳር መጠንን ያረጋጋል፡፡ ምግብዎን በወይራ ዘይት አብስሎ ሲመገቡ ራስዎን ከተለያዩ በሽታዎች ይታደጋሉ፡፡ ይሁን እንጂ የስኳር ታማሚ ከሆኑ፣ የወይራ ዘይትን አዘውትረው ከመመገብ ይቆጠቡ፡፡  

በአገራችን ከአምስት ህሙማን አንዱ መድሃኒቶችን በስህተት ይወስዳል
የሃኪሙን የእጅ ፅሁፍ ማንበብ የሚያዳግታቸው ፋርማሲስቶች በዝተዋል

በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በተደረገለት ሙሉ ምርመራ የጉበት ህመምተኛ መሆኑ ሲነገረው ድንጋጤው ልክ አልነበረውም፡፡ ህመሙ ዕለት ከዕለት እየተባባሰበት በመሄዱ ምክንያት ወደ ሆስፒታል ሄዶ ምርመራ ለማድረግ ሲወስን፣ ሃኪሙ ህመሙን አውቆለት ፈዋሽ መድሃኒት እንደሚያዝለት፣ ከበሽታውም እንደሚያገግም ጽኑ እምነት ነበረው፡፡
ከሃኪሙ የተፃፈለትን የመድሃኒት ማዘዣ ይዞ መድሃኒቱን ፍለጋ ወጣ፡፡ በከተማው ውስጥ ያሉ በርካታ መድሃኒት ቤቶችን ቢያስስም መድሃኒቱን ማግኘት አልቻለም፡፡ ቆይቶ ግን መድሃኒቱ በአንድ ፋርማሲ ውስጥ እንደሚገኝ ሰማ፡፡ ለመድሃኒቱ የተጠየቀውን ዋጋ ከፍሎ ገዛ፡፡ ችግሩ ግን ስለመድሃኒቱ አወሳሰድ ፋርማሲስቱ የነገረው ነገር አልነበረም፡፡ የገዛውን መድሃኒት ይዞ ወዳዘዘለት ሃኪም ሄደ፡፡ ሃኪሙ ዘንድ ቀርቦ መድሃኒቱን በብዙ ፍለጋ ማግኘቱን በመግለጽ፣ ስለአወሳሰዱ እንዲነግረው ጠየቀው፡፡ ሃኪሙ በጣም ተገርሞ፤
“ለመሆኑ መድሃኒቱ የተገዛው ከፋርማሲ ውስጥ ነው?” ጠየቀው
“አዎ” አለ ታካሚው፡፡
“ታዲያ እንዴት ፋርሚሲስቱ ስለአወሳሰዱ ሳይነግርህ ቀረ?” በማለት መድሃኒቱን ከነማዘዣው ከህመምተኛው ላይ ተቀብሎ አየው፡፡ ታካሚው በሃኪሙ ፊት ላይ ያየው ከፍተኛ ድንጋጤ እሱኑ ይበልጥ አስደነገጠው፡፡
“ችግር አለ?” ሲል ጠየቀው ሃኪሙን
“እርግጠኛ ነህ እኔ ላዘዝኩልህ የተሰጠህ መድሃኒት ይሄ ነው?” ሲል ጠየቀው ታማሚውን፡፡
“ጌታዬ 486 ብር የከፈልኩበት መድሃኒት እኮ ነው እንዴት ብዬ ከሌላ መድሃኒት ጋር እቀላቅለዋለሁ”
ለዚህ መድሃኒት መግዣ ያወጣውን 486 ብር ለማግኘት የተጋፈጠውን ውጣ ውረድ የሚያውቀው እሱ ብቻ ነው፡፡ ሃኪሙ በጣም አዘነ፡፡
ታካሚው ከፋርማሲ ገዝቶ ያመጣው መድሃኒት፤ ለማህፀን ህክምና የሚያገለግልና ለሴቶች ብቻ የሚታዘዝ ነበር፡፡ ሁኔታው እጅግ ቢያስደነግጠውም ለመድሃኒቱ ያወጣው ገንዘብ ኪሣራ ላይ ሊወድቅ መሆኑ ይበልጥ አበሳጨው፡፡ ወደ ፋርማሲው ሄዶ ስለጉዳዩ በመንገር፣ ገንዘቡን እንዲመልሱለት ለማድረግ መድሃኒቱን ተቀብሎ ወደዚያው አመራ፡፡ ፋርማሲው ውስጥ ላገኘው ሰውም ሁኔታውን አስረዳ፡፡ በወቅቱ የተገኘው ባለሙያ፤ ከሰውየው ላይ መድሃኒቱን ተቀብሎ አየው፡፡ ምናልባት የፋርማሲ ባለሙያው በስህተት ሰጥቶት ሊሆን እንደሚችል ነግሮ፣ በማዘዣው ላይ የተፃፈውን መድሃኒት ሊሰጠው እንደሚችል አግባባው፡፡ ይሁን እንጂ ይህኛውም ሰው በመድሃኒት ማዘዣው ላይ የተፃፈውን ጽሑፍ በአግባቡ በማንበብ ተገቢውን መድሃኒት ሊሰጠው አልቻለም፡፡ ይልቁንም “መድሃኒቱ እኛ ጋ የለም ሲል” ማዘዣውንና ታማሚው ቀደም ሲል የከፈለውን 486 ብር መልሶ በመስጠት አሰናበተው፡፡
ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝን ይህንን መረጃ ያገኘሁት ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ለህክምና መጥቶ ካገኘሁት አንድ ታካሚ ነው፡፡ ታካሚው ከሃኪሙ የተፃፈለትን መድሃኒት በሆስፒታሉ ቅጥር ግቢ ከሚገኘው የመድሃኒት መሸጫ ፋርማሲ ለማግኘት ባለመቻሉ ነበር መድሃኒቱን ፍለጋ ከተማውን ሲያስስ የከረመው፤ ይሁን እንጂ በአብዛኛው መድሃኒት ቤቶች ውስጥ መድሃኒቱን ለማግኘት አልቻለም፡፡ ከዚህ የከፋው ደግሞ ከበሽታው ጋር ፈጽሞ የማይገናኝና ምናልባትም ለከፋ ችግር ሊያጋልጠው የሚችል መድሃኒት ባለሙያ ነኝ ብሎ ከተቀመጠ የመድሃኒት ቤት ሰራተኛ መሰጠቱ ነው፡
ወደ ሆስፒታሉ ተመልሶ የመጣው ሃኪሙ መድሃኒቱን በሌላ መድሃኒት ቀይሮ እንዲፅፍለት ለመጠየቅ መሆኑን አጫውቶኛል፡፡ ለፍለጋው በተዘዋወረባቸው በርካታ መድሃኒት ቤቶች ውስጥ ያገኛቸው የፋርማሲ ባለሙያዎች፤ በማዘዣው ላይ የተፃፈው የሃኪሙ የእጅ ጽሑፍ ፈጽሞ የማይነበብ መሆኑንም ነግረውታል፡፡ ስለዚህም ሃኪሙ ሊነበብ በሚችል መልኩ ማዘዣውን እንዲፅፍለት እንደሚጠይቀውም ገልፆልኛል፡፡
አለም አቀፉ የጤና ድርጅት (WHO) ለፋርማሲ ሙያ በሰጠው ትርጓሜ፤ የፋርማሲ ባለሙያ ማለት፣ ከሃኪም በሚሰጠው ትዕዛዝና መመሪያ መሠረት፣ መድሃኒቶችን ለህሙማን ማደል፣ ስለመድሃኒቱ አወሳሰድ፣ መድሃኒቱ ስለሚኖረው የጐንዮሽ ጉዳትና ከመድሃኒቱ ጋር ሊወሰዱና ላይወሰዱ ስለሚችሉ ምግብና መጠጦች በግልጽ ለህመምተኛው የሚያሳውቅ ሰው ነው፡፡ የፋርማሲ ባለሙያው መድሃኒቶችን ለህሙማን ከማደል በዘለለ ከህሙማኑ ጋር ጥብቅ መግባባትን ማድረግ የሚችል መሆን ይኖርበታል፡፡ ባለሙያው ሁልጊዜም ከህመምተኛው ጀርባ ሆኖ ስለህመምተኛው የሚጨነቅና የሚያስብ ሰው ነው፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፋርማሲ ት/ቤት መምህር ዶክተር ተስፋዬ ታረቀኝ እንደሚናገሩት፤ “የፋርማሲ ሙያ እንደ ህክምና ሙያ ሁሉ ትልቅ ከበሬታ ሊሰጠው የሚገባና በአግባቡ የሰለጠነ የሰው ሃይልን የሚጠይቅ ነው፡፡ የፋርማሲ ባለሙያዎች ከህክምና ባለሙያዎች ጋር ጥብቅ ትስስር ሊኖራቸው ይገባል፡፡ የፋርማሲ ባለሙያ ማለት ከሃኪሙ በሚሰጠው ማዘዣ መሠረት ታማሚው መድሃኒቱን በአግባቡ መውሰድ እንዲችል ተገቢውን መመሪያ የሚያስተላልፍ ሙያተኛ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አሁን የሚታየው ነገር ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ታካሚው መድሃኒት ፍለጋ በሚሄድባቸው ፋርማሲዎች ውስጥ ያሉ ሰዎች ሙያውን በሚገባ ያውቁታል ለማለት ፈፅሞ አያስደፍርም፡፡ አንዳንድ ፋርማሲስቶች፤ የመድሃኒት ማዘዣዎች አልነበብ ሲላቸው፣ በደንበኞች ፊት ሃኪሞችን ከፍ ዝቅ አድርገው ሲሳደቡና ሲያዋርዱ ይታያል፡፡ ይህ ደግሞ ለሙያው የሚሰጠውን ግምት በእጅጉ የሚያወርድና በሃኪሙና በህመምተኛው መካከል መተማመን እንዳይኖር የሚያደርግ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የመድሃኒት ማዘዣዎችን በሚገባ አንብቦና ተረድቶ መድሃኒቶችን ለህሙማን የሚያድል የፋርማሲ ባለሙያ ማግኘቱ እጅግ አስቸጋሪ እየሆነ የመጣ ጉዳይ ነው”
በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በቅርቡ የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚያመለክተው፤ በኢትዮጵያ ውስጥ ከሃኪም መድሃኒት ከታዘዘላቸው ታካሚዎች ከአምስቱ አንዱ መድሃኒቶችን በስህተት ይወስዳል፡፡ ሃኪሞችን የፋርማሲ ባለሙያዎችን፣ ነርሶችንና ህሙማንን ያካተተው ጥናቱ፤ በመድሃኒት አስተዛዘዝ ዙሪያ ከባድ ችግር እየተከሰተ መሆኑን ይጠቁማል፡፡
አንዳንድ የጤና ባለሙያዎች የሚጽፉት የመድሃኒት ማዘዣ የማይነበብና የተሟላ መረጃ የሌለው ሲሆን የሃኪሙን የእጅ ጽሑፍ በሚገባ አንብቦና ተረድቶ ተገቢውን መድሃኒት ለህመመተኛው የሚሰጥ የፋርማሲ ባለሙያ ማግኘትም አስቸጋሪ ሆኗል፡፡
ህሙማኑም ስለታዘዘላቸው መድሃኒት አወሳሰድ ሃኪማቸውን አይጠይቁም፡፡ የፋርማሲ ባለሙያዎቹም፤ ለህሙማኑ መድሃኒቱን ሲሰጡ ስለአወሳሰዱ፣ ስለመድሃኒቱ ባህሪያትና ስለጐንዮሽ ጉዳቱ አይናገሩም፡፡
ይህ የሚያሳየው ደግሞ ህመምተኛው ስለሚወስደው መድሃኒት ምንነትና አወሳሰድ ሳያውቅ በስህተት መድሃኒቶችን ለመውሰድ መገደዱን ነው፡፡
በጥናቱ እንደተመለከተው፤ ብዙውን ጊዜ ህሙማን መድሃኒት ፍለጋ ከፋርማሲ ፋርማሲ የሚንከራተቱት መድሃኒቱ በፋርማሲው ሳይገኝ ቀርቶ ሳይሆን የፋርማሲ ባለሙያው ማዘዣውን አንብቦ መረዳት ባለመቻሉ ምክንያት መሆኑን አመላክቷል፡፡ ይህ ጉዳይ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባና ሁሉም ሙያተኞች የሙያውን ሥነምግባር አክብረው፣ ተገቢውን ህክምናና መድሃኒት ለህመምተኛው መስጠት እንዳለባቸው ይኸው ጥናት ይገልፃል፡፡
በሰለጠነው ዓለም የመድሃኒት ማዘዣዎች በዲጂታል ማሽኖች እየተተኩ ነው፡፡
ልክ እንደ ባንክ ኤቲኤም ማሽን፣ በደንበኞቹ በቀረበለት የመድሃኒት ማዘዣ መሠረት ትክክለኛውን መድሃኒት አውጥቶ ከነአወሳሰድ መመሪያው ለህሙማኑ መስጠት የሚችል መሣሪያ አገልግሎት ላይ ውሏል፡፡
መድሃኒቶች ከበሽታ በመፈወስ ነፍስን የመታደጋቸውን ያህል በአግባቡ ካልተያዙና አገልግሎት ላይ ካልዋሉ አጥፊ የመሆን ዕድላቸው ከፍተኛ መሆኑን መገንዘብ ይገባል፡፡ ስለዚህ ለህይወት ደህንነት የተሰራልን መድሃኒት አጥፊያችን እንዳይሆን፣ እራሳችንን ጨምሮ የሚመለከተው አካል ለጉዳዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡       

“ልጃገረዶች አግብተው እስኪያልቁ ድረስ እንኖራለን”

   በጎፋ ብሄረሰብ መስቀል የበአላት ሁሉ አውራ ነው፡፡ ለ7 ተከታታይ ቀናት የሚያከብሩት ልዩ በዓላቸው ነው፡፡ አሁን የሥራ ጊዜን እንዳይሻማ በሚል ተቀንሶ ነው እንጂ ድሮ ለ15 ቀናት ነበር የመስቀል በዓል የሚከበረው፡፡
የዘንድሮ አከባበር ግን የተለየ ነው፡፡ ጐፋዎች የመስቀል በአልን ለመጀመሪያ ጊዜ በአደባባይ ተሰባስበው በተለያዩ ባህላዊ ስርአቶች በመናገሻቸው በሳውላ ከተማ እያከበሩ ይገኛሉ፡፡ “ማስቃላ ዮ!” (እንኳን ለመስቀል በአል አደረሰን) ሰሞነኛ የሠላምታና የመመራረቂያ ቋንቋቸው ነው፡
ብሄረሰቡ በአሉን መቼ ማክበር እንደጀመረ የሚጠቁም አረጋጋጭ ማስረጃዎች ባይኖሩም በአካባቢው ከ100 ዓመታት ቀደም ብሎ (ክርስትና ከመስፋፋቱ በፊት) ከአሁኑ አከባበር ጋር ተመሳሳይነት ባለው መልኩ በመስከረም ወር ይከናወን እንደነበር የሀገር ሽማግሌዎችና የመስቀል በአል አከባበርን ያጠኑ ምሁራን ይናገራሉ፡፡ ክርስትና ከመጣ በኋላ ይበልጥ የሀይማኖት ይዘቱንም የባህል ትውፊቱንም አስማምቶ ማክበር እንደተጀመረም ይገለፃል፡፡
ወርሃ መስከረም ወይም በብሄረሰቡ አጠራር ጉስታማ፤ የጭፈራና የደስታ ወር ነው - ለጎፋዎች፡፡ የእድሜ ባለፀጋዎች ልጆቻቸውን የሚመርቁበት፣ ወጣቶች እጮኛ የሚመርጡበት፣ በብሄረሰቡ ተወዳጅ የሆኑት “ግሶሌ”፣ “ሄራሶ”፣ “ጋዜ”፣ “ባራንቼ”፣ “ሆሴ” … የመሳሰሉት ባህላዊ ዜማዎች ጐልተውና ደምቀው የሚዜሙበት የፌሽታ ወቅት ነው - መስከረም፡፡
በአሉን ለመታደም ከአዲስ አበባ በ516 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ ወደምትገኘው ሳውላ ባቀናንበት ወቅትም እነዚህ የወርሃ መስከረም የደስታ ዜማዎች የበአሉ ማድመቂያ ሆነው ሰንብተዋል፡፡
ጎፋዎች የመስቀል በአልን ለመቀበል ቅድመ ዝግጅት የሚያደርጉት ከመስከረም 1 ጀምሮ ነው፡፡ ለተከታታይ 15 ቀናት እያንዳንዱ አባወራ የቤት እንስሳቱ እንዳይራቡበት ለ7 ተከታታይ ቀናት የሚበቃ መኖ ያዘጋጃል፡፡ ሴቶች ለበአሉ ባህላዊ ምግብና መጠጥ በማዘጋጀት ሥራ ይጠመዳሉ፡፡ የደመራው እለት እየተቃረበ ሲመጣም ወንዶች ለደመራ የሚሆነውን የተመረጠ “ግን ግና” የተባለ እንጨት መርጠው ያዘጋጃሉ፡፡ ህፃናት ልጆች ከብቶቻቸውን እያገዱ “መስቀል እንኳን መጣህልን፣ የኛ ደስታ፣ የኛ መዝናኛ መስቀል እንኳን መጣህልን፡
ሎያ ባይ ሎያ ባይ
ሎያ ባይ ማስቃላ ባይ
ማስቃላ ኡፋይስ ባይ
ሙሰ ሀሹ ባይ”… እያሉ በደስታ ያዜማሉ፡፡
አባወራዎች የደረሰ አዝመራ በደቦ ይሰበስባሉ፣ ያልደረሰውን ያርማሉ፣ ለእርድ የሚሆን በሬ ይገዛሉ፡፡ የመስከረም ወር ለጎፋዎች ሀብታም ከድሃ እኩል የሚሆኑበት ነው፡፡ “ጉስታ ጉስቴስ ጊታ ጊቴኤስ” ይባላል፤ ወሩ ላለው ይጨምራል፣ ለድሃውም ይሞላለታል ተብሎ ይታሰባል፡፡ በዚህም ሁሉም ለበአሉ የሚያደርጉት ዝግጅት እኩልነትን መርህ ያደረገ ይሆናል፡፡
የጎፋዎች ደመራ
መስከረም 16 የደመራ ቀን ነው፡፡ ለደመራ የሚተከለው ለቤት መስሪያ የሚውል ረጅም ቀጥ ያለ እንጨት ነው፡፡ በደመራው ጫፍ አደይ አበባ ይታሰራል፤ ይህም ተስፋን አመላካች ነው፡፡ የችቦ አስተሳሰርና የደመራው አቆራረጥ፣ የቤተሰቡን ቁጥርና እድሜ ከግምት ውስጥ ያስገባ ነው፡፡ በረጅሙ ደመራ ዙሪያ የሚቀመጡት ጨፈቃዎች (ሶልዜ ይሉታል) በቤተሰቡ አባላት የእድሜ ደረጃ ቁመታቸው ተመጥኖ ይዘጋጃል፡፡ ረጅሙ ለአባወራው፣ ቀጥሎ ያሉት ከታላቅ እስከ ታናሽ ወንድ ልጆች እንዲይዙት ይደረጋል፡፡ የደመራ እንጨት በማስቀመጡ ስነስርአት ላይ ሴቶች ፈፅሞ አይሳተፉም፡፡ ሴቶች ከደመራው በኋላ የሚበላ ገንፎና የሚጠጣ ነገር ያሰናዳሉ፡፡
ወንዶቹ በእድሜ ደረጃቸው የያዙትን ጨፈቃ፣ በረጅሙ ምሰሶ ዙሪያ ለማስቀመጥ ሶስት ጊዜ “መስቀላ ዮ! ዮ! ዮ!…” እያሉ ይዞራሉ፡፡ ይህም ሁሉ ነገር የሚፀናው በ3 ነው ከሚል የብሄረሰቡ እምነት የመነጨ ነው ይላሉ አቶ በላይ፡፡ ሽማግሌ እንኳ ሲመረጥ ወይ ሶስት ወይ 5 አሊያም 7 ነው የሚሆነው፤ ምክንያቱም በውሳኔዎች የድምፅ ብልጫ እንዲፈጠር ነው፡፡
ለደመራው ረጅምና ዝንፍ ያላለ ቀጥ ያለ እንጨት የሚመረጥበት ምክንያትም ልጆች በአስተሳሰብና በአመለካከት ጤናማ ሆነው እንዲያድጉ፣ ዘመኑ የሰላምና የስኬት እንዲሆን በመመኘት ነው፡፡ በመስቀል በአል በምንም አይነት መንገድ ጠማማ እንጨት ከደመራው ጋ አይቀላቀልም፡፡
ለዓይን ያዝ ሲያደርግ የቤቱ አባወራ (አባወራው በህይወት ከሌለ) የቤቱ ታላቅ ልጅ፣ ሁሉንም ችቦዎች ይዞ ለገንፎ ማብሰያ ከሚነደው እሳት ስር በመለኮስ፣ የቤቱን ምሰሶ በመዞር፣ የከብቶች ጋጣና በሩን በተለኮሰው እሳት እየነካካ፣ “መስቀላ ዩ! ዮ! ዮ!” እየተባለ ወደ ደጅ ይወጣል፡፡ አባት መጀመሪያ ችቦውን ከደመራው ካቀጣጠለ በኋላ ልጆች እንደየቅደም ተከተላቸው ባህላዊ ጨዋታዎችን እየተጫወቱ ችቧቸውን ያለኳኩሳሉ፡፡
በሚነደው ደመራ ዙሪያም “መስቀላ ዮ! ዳናው ዳና አልባ ዙማዳን ዳና” (መስቀል እንኳን መጣህልን … በአካባቢው እንደሚገኘው አልባ ዙማ ተራራ ገና ረጅም ዘመን እንኖራለን) “ከንቲ ሻላዳን ዳና” (በአካባቢው እንደሚገኘው ክንቲ ሻላዳ አለት ገና እንኖራለን) እያሉ ያዜማሉ፡፡ ዜማው በዚህ አያበቃም፤ “ሀረይ ካጨ ከሳናዳን፣ ገላኦ ገል ውራናስ ዳና” (አህያ ቀንድ እስኪያበቅል…. ልጃገረዶች አግብተው እስኪያልቁ ድረስ እንኖራለን) እያሉ እርስ በእርስ ይሸካከማሉ፡፡ ተቃቅፈው በመጨፈርም የእርስ በርስ ፍቅራቸውን ይገልፃሉ፡፡
በደመራ ሀዘን (ለቅሶ) የለም
የደመራ እለት የሞተ ሰው ካለ አይለቀስም፡፡ ከደመራ በኋላ የሀዘን ማስረሻ ጭፈራ እየተጨፈረ፣ ለቀስተኛው በራፍ ላይ ይዞራል፡፡ ከእንግዲህ ሀዘን የለም ይባላል፡፡ ሟች በመስቀል እሳት ተበልቷል (ማስቃላ ታማን ሜቴትስ) ይባላል፡፡ ለቀስተኞች ለቅሶውን አቁመው፣ “መስቀላ ዮ! ዮ” እያሉ ወደ ተጀመረው የመስቀል በአል ይመለሳሉ፡፡ ለበአሉ የተዘጋጀው ሰንጋም በ17 በዋናው በአል እለት ይታረዳል፡፡ ለ7 ቀናት ያህልም መከበሩን ይቀጥላል፡፡ (ድሮ ለ15 ቀናት ነበር የሚከበረው)
ሳምንቱን ሙሉም ስጋና በቅቤ የተዘጋጀ ገንፎ ብቻ እየተበላ፣ ቦርዴና ሌሎች መጠጦች እየተጠጡ ይሰነበታል፡፡ ከብቶችም የተዘጋጀላቸውን መኖ ይመገባሉ፡፡ አባወራዎች በበአሉ መዳረሻም ሆነ እስከ በአሉ ፍጻሜ ድረስ ከቀዬው መራቅ የለባቸውም፡፡
በመጨረሻም ደማቅ የመስቀል አሸኛኘት ስነ ስርአት “ሆሴ” እና “ጋዜ” በተባሉ ጭፈራዎች ደምቆ ይከናወናል፤ “ሰሮ ያራደሳ ሰሮ ረባ” (መስቀል በደህና መጥተህልናል በደህና ሂድ) ተብሎም ይመረቃል፡፡ “ሆሴ ማስቃላ ላይታን ሳሮያ!” (መስቀል ደህና ሁን! በዓመቱ ደህና ተመለስ) እየተባለ በአሉ ይሸኛል፡፡ ከዚያን ቀን በኋላ ስለመስቀል አይወራም፡፡
በአሉን ምክንያት አድርገው ከሚከናወኑ ተግባራት አንዱ ጎረምሶች የወደፊት ውሃ አጣጫቸውን የሚመርጡበት ሥነ ስርአት ነው፡፡ ልክ በሌላው የኢትዮጵያ ክፍል ለጥምቀት በአል እንደሚደረገው መተጫጨቱ የሚፈፀመው በሎሚ ነው፡፡ በጭፈራ ወቅት ወንዱ የበሰለ ባለቢጫ ቀለም ሎሚ ልቡ ለከጀላት ልጃገረድ ይሰጣል፡፡ ሴቶችም መልስ የሚሰጡት በሎሚ ነው፡፡ ሶስት አይነት ሎሚ ያዘጋጃሉ፡፡ እንስቷ፤ የጠየቃትን ወንድ የማትፈልገው ከሆነ ያልበሰለውን ትሰጠዋለች፣ ልቧ ከጅሎት ትንሽ ጊዜ እንዲጠብቃት ከፈለገች እንደ መብሰል ያለውን ሎሚ ትሰጣለች፤ ሙሉ በሙሉ የምትፈልገው ከሆነ ደግሞ የበሰለውን ሎሚ ከጡቶቿ መሃል አውጥታ ትሰጠዋለች፡፡ የበሰለ ሎሚ ያገኘ ወንድ፣ ከዚያን ቀን ጀምሮ የሰርግ ዝግጅት ማድረግ ይጀምራል፡፡ ጥንዶቹ እንደ ምርጫቸው በጥቅምት ወይም በጥር ይጋባሉ፡፡
ጥቂት ስለጎፋዎች
የጎፋ ብሄረሰብ በደቡብ ክልል ከአዲስ አበባ 516 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በጋሞ ጎፋ ዞን በደንባ ጎፋ ወረዳ ውስጥ ከሚገኙ 5 ነባር ብሄረሰቦች አንዱ መሆኑን በብሄረሰቡ ላይ የቀረቡ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ ብሄረሰቡ ከሚኒልክ ዘመን ጀምሮ ከነባሩ የማዕከላዊ መንግስት አስተዳደር ጋር የነበረው ግንኙነት ጥብቅ እንደነበርም ይነገራል፡፡ በተለይ በአድዋ ጦርነት ጊዜ ጎፋዎች የፈፀሙት ጀግንነት በአፄ ምኒልክ ዘንድ ሞገስን አግኝቶ ነበር፡፡ የጣሊያንን ቅኝ ገዢ ኃይል አድዋ ላይ ለማስቆም በተደረገው የሞት ሽረት ተጋድሎ፣ ጎፋዎች ስንቅና የጦር መሳሪያ በማቀበል ለመላው ጥቁር ህዝብ ኩራት ለሆነው የአድዋ ድል ጉልህ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፡፡
ለዚህም ተጋድሏቸው መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በአዲስ አበባ በስማቸው ቦታ ተሰይሞላቸዋል፡፡ የጎፋ ሰፈር፡፡
ወደ ሻሸመኔ አካባቢ የሚገኘው የጎፋ በር እየተባለ የሚጠራ ስፍራም በጦርነቱ ወቅት የብሄረሰቡ ተወላጆች ሰፍረውባቸው የነበረ ሲሆን ስያሜውን ያገኙት በዳግማዊ ምኒልክ በጎፈቃድ እንደሆነ ታሪክ ይጠቁማል፡፡
ጎፋዎች ቀደምት አባቶቻቸው ቅኝ ገዢውን የጣሊያን ጦር በመስዋዕትነት ለመመከታቸው ማስታወሻ ይሆን ዘንድም በሚለብሱት ባህላዊ ልብስ ላይ (2020 ይሉታል) ባለቀይ ቀለም ጥለትን ይጠቀማሉ፡፡
ባህላዊ አልባሳቶቻቸው ሲዘጋጅም ምንም ይሁን ምን ቀይ ቀለም ከላይ ተደርጎ ነጭና አረንጓዴ እንዲከተሉት ይደረጋል፡፡ ነጩ ሠላምን፣ አረንጓዴው የብሄረሰቡን አምራችነትና የአካባቢውን አረንጓዴ ተፈጥሯዊ አቀማመጥ እንደሚወክል የብሔረሰቡ ተወላጆች ይናገራሉ፡
“መስቀላ ዮ! መልካም የመስቀል በዓል!”
“አህያ ቀንድ እስኪያበቅል ድረስ እንኖራለን!”
“ልጃገረዶች አግብተው እስኪያልቁ ድረስ እንኖራለን!”

ደንበኞች በሞባይል ቁጥራቸው ሂሳብ መክፈት ይችላሉ

    አንበሳ ባንክ ቤልካሽ ቴክኖሎጂ ሶሉሺንስ ከተባለ ድርጅት ጋር በመሆን በሱቆችና መደብሮች ገንዘብን በሞባይል ለማዘዋወር የሚያስችል አዲስ ቴክኖሎጂ ሥራ ላይ አዋለ፡፡
የባንኩና የቤልካሽ ቴክኖሎጂ ሶሉሺንስ የሥራ ኃላፊዎች ሰሞኑን በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ ደንበኞች በሚቀርባቸውና ለሸመታ በሚዘዋወሩባቸው ሱቆች የሞባይል ስልካቸውን በመጠቀም የገንዘብ ዝውውር እንዲያደርጉ፣ ገንዘብ እንዲልኩና እንዲቀበሉ፣ በሱቆቹ ገንዘብ (ተቀማጭ) ገቢ እንዲያደርጉ፣ ክፍያዎችን እንዲፈጽሙ የሚያደርግ የሄሎካሽ አሠራር ተግባራዊ ማድረግ ጀምረዋል፡፡ ደንበኞች በሞባይል ቁጥራቸው የባንክ አካውንት መክፈት የሚችሉበት አዲስ አሠራር  መጀመሩን የተናገሩት የሥራ ኃላፊዎቹ፤ ደንበኛው በሚሰጠው የግል የሚስጢር ቁጥር ገንዘቡን ማስቀመጥ፣ ማዘዋወርና መላክ እንደሚችልም ተናግረዋል፡፡ እስከአሁን 200 ወኪሎች ወደተግባር መግባታቸውን የተናገሩት ኃላፊዎቹ፤ በቀጣይ አድማሳቸውን በማስፋት፣ በሁሉም የአገሪቱ ክልሎች አገልግሎታቸውን ለማዳረስ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡
አንበሳ ባንክ ባለፈው ዓመት ካፒታሉን 6.2 ቢሊዮን ብር ያደረሰ ሲሆን 510 ሚሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል አለው፡፡
ቤልካሽ ቴክኖሎጂ ሶሉሽንስ አዳዲስ የፋይናንስ ሥራ አገልግሎቶቹን ለህብረተሰቡ በማስተዋወቅ ላይ የሚገኝ ሲሆን እስከአሁን ሄሎ ዶክተር፣ ሄሎ ካሽ፣ ሄሎ ሎየር እና ሄሎ ሥራ የተባሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በሥራ ላይ አውሏል፡፡

Saturday, 26 September 2015 08:22

ለአዲስ አድማስ አዘጋጅ

     ባለፈው ቅዳሜ በወጣው የአዲስ አድማስ ዕትም ላይ፤ አደዳ ኃይለ ሥላሴ፤ “በአብነት ስሜ ላይ ለተሰነዘሩ ትችቶች የተሰጠ ምላሽ” በሚል ርዕስ የጻፉትን አነበብኩ። ደግሜም አነበብኩት። በዚሁ ጋዜጣ ላይ ወሪሳ ስለተባለው የአለማየሁ ገላጋይ መጽሐፍ አብነት ስሜ ባቀረቡት ሂሳዊ ጽሁፍ ላይ ለተሰጠ አስተያየት ምላሽ  ነው።
አንድ በ1960 ገደማ የደረሰብኝን ገጠመኝ አስታወሰኝ። በወቅቱ ዩኒቨርስቲ የህግ ተማሪ ነበርኩ። በአማርኛ ጋዜጦች በተለይ በ “አዲስ ዘመን” ሳምንታዊ አምድም ነበረኝ። አንዴ ለዚያ አምድ ያዘጋጀሁት ጽሁፍ አይወጣም ተብሎ ታገደ። አጋጁ ብላታ ወልደ ጊዮርጊስ ነበሩ። የማስታውቂያ ሚኒስቴር ምክትል ሚኒስቴርና የሳንሱር ሐላፊም ነበሩ። ከኔ ጋር ተቀራርብናል። አንድ ቀን ጠየኳቸው፤
 “ብላታ ይኸ የዘመኑ ሰው ብዙ እርስዎ ባልነበሩበት የተለያዩ ጉዳዮች ላይ ሊጽፍ ይችላል። አንዴት ለክተው ነው ያልፋል ይወድቃል የሚሉት?” አልኳቸው።
መለሱልኝ፤“ልጄ ሙት ቀላል ነው!” አሉኝ በጥሞና፤ “እኔ ካልገባኝና ካልተረዳሁት አያልፋትም!”
 ይህ የአደዳ ጽሁፍ ያንን አስታወሰኝ። መልእክቱ ካልገባን ካልተረዳን፥ (ሁሉንም ልናውቅና ልንረዳ አንችልምና)  ዞር- ዞር ብሎ መጠየቅና ማፈላለግ ነው። ካፈላለጉት ምንጩ (ጮቹ) እዚያው አሉልን። ሊገመት በሚችለው ምክንያት ሁሉ ብላታን እንዲያ አላልኩም። ልላቸው ተገቢም አልመሰለኝም።
ለምንናገረው፤ለምንጽፈው ሐላፊነትና ተጠያቂነት ለጀማው አንባቢ አለብን። ከሁሉም  በላይ ግን ተጠያቂነቱ ለራሳችን  መሆን   አለበት። ለራሳችን ታማኝ ከሆንን ለጀማውም ታማኝነቱ ከዚያ ይፈልቃል።  የሐምሌትን  በተዘዋዋሪ መንገድ መጥቀስ መሞክሬ ነው፡-
“This above all: to thine own self be true,
And it must follow, as the night the day,
Thou canst not then be false to any man.”
ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን እንዴት እንደተረጎመው በቃሌ ማስታወስ አልቻልኩም። በሒስና ኂስ መካከል ያለውንም ልዩነት ተማርኩ። እንደኔ  እንደኔ፣ ይህ የአደዳ ጽሁፍ አልፎ አልፎ ደጋግሞ ቢወጣ ጥሩ ይመስለኛል። “ጠንቀቅ ነው ደጉ!”  የሚል ይመስለኛል። ቀይ መብራት እንዳንጥስ ደውል ሆኖ ሊያገልግል የሚችል ይመስለኛል። እኔኑ ጨምሮ!
ከአክብሮት ጋር
አሰፋ ጫቦ
Corpus Christi Texas USA

    ከዕለታት አንድ ቀን ሚያሚ ለሚባለው ጋዜጣ፣ የቀብር ሥነስርዓት ክፍል ስልክ ተደወለ አሉ፡፡
ደዋይዋ ሴት ናት፡፡
“የአንድን ሰው የህይወት ታሪክ በመቃብሩ ላይ ፅፎ ለመቅረፅ ምን ያህል ይፈጃል?” አለች ሴትዮዋ፡፡
የጋዜጣው ሠራተኛ በትህትና፤
“ለአንድ ቃል አምስት ዶላር ያስፈልጋል እመቤት”
“ጥሩ” አለችና ሴትዮዋ ከጥቂት ጊዜ እረፍት በኋላ፤
“እርሳስ ይዘሃል?”
“አዎን እመቤት”
“ወረቀትስ ከአጠገብህ አለ?”
“አዎን እመቤት”
“እሺ እንግዲያው የምታፅፊለትን ቃል ልምረጥ”
“መልካም”
“እንግዲያው የእኔ እመቤት፤ ቦጋለ ሞቷል” ብለህ ፃፍ፡፡
“ይኸው ነው? በቃ?” አለ ፀሐፊው ባለማመን፡፡
“አዎን ይሄው ነው” አለች ሴትዮዋ
“እመቤቴ በስህተት አንድ ቁም ነገር ሳልነግርዎ ዘንግቻለሁ”
“ምንድን ነው የዘነጋኸው?”
“ከአምስት ቃላት በታች መናገር ክልክል ነው፡፡ አምስት ወይም ከአምስት በላይ መጠየቅ ነበረብዎ”
“እሺ፤ ጥቂት ደቂቃ እንዳስብ ፍቀድልኝ” ብላ ፍቃዱን ጠየቀች፡፡”
ጥቂት ደቂቃ አሰበችና
“እሺ እርሳስና ወረቀት ይዘሃል?”
“አዎን፤ እመቤት፤ ይዣለሁ!”
“እንግዲያው ፃፍ”
“እሺ እመቤት”
“እንግዲያው ቦጋለ ሞቷል - የሚሸጥ ካዲላኩ መኪናው እንዳለ አለ - አሁንም አልተሸጠም” ብለህ አክልበት አለችው፡፡
*   *   *
እንደሁኔታው ተስተካክሎ ቀዳዳዎችን መጠቀም አስተዋይነት ነው፡፡ መንገዶች ሁሉ በአንድ በኩል ብቻ ነው የሚሄዱት ብሎ ግትር አለመሆን ታላቅነት ነው!
ዕውቀት እያነሰ በመጣ ቁጥር ሐሜትና ስለሰው መተቸት እጅግ የሚዘወተር ነገር እየሆነ ይመጣል፡፡ በዚህም ሳቢያ ችግርን በመላ ከመፍታት ይልቅ ከአፍ አፍ ማዛመት ዋና ሥራ እየሆነ ይሄዳል፡፡
“በነገር በተተበተበ ማህበረሰብ ውስጥ ለብልሆች ስድቦች የጋራ ይደረጋሉ፡፡ ሐሜትንም ከሰው ሰው ይለዋወጡታል፡፡ (insults are shared and gossip is exchange) ይሄ የሆነበት ምክንያት ሐሜትን ማዛመት ከመቅለሉም የበለጠ አዝናኝና አስደሳች በመሆኑ ሲሆን፣ መቼም ቢሆን መቼ የሌሎችን ስህተት መለየትና ታርጋ መስጠት የራስን ህፀፅ ከማየት የቀለለ በመሆኑ ነው” ይሉናል ፀሐፍት፡፡
በየጊዜው ስለሚዲያዎች ክፉ ክፉው ይወሳል፡፡ ሚዲያዎች እንደአስፈሪ ጠላቶች መታየታቸው በየትኛውም ሥርዓት የሚከሰት ጉዳይ ነው፡፡ ያለነገር አይደለም፡፡ መረጃዎች ህብረተሰብን ያነቃሉ፡፡ የአስተሳሰብ ለውጥ ሊያመጡ ይችላሉ፡፡ ይህ ግን በአዎንታዊም በአሉታዊም ውጤት ሊፈረጅ ይችላል፡፡
“ፈላጭ - ቆራጭ መንግሥታት ሁነኛ ጫና በግል ሚዲያዎች ላይ ማሳረፋቸው የአጋጣሚ ጉዳይ አይደለም፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት የህዝብ ፍላጐት ብዙውን ጊዜ የሚቀሰቀሰው በድራማዊ ክስተቶችና ስማቸው በገነነ የተከበሩ ሰዎች እንዲሁም ሚዲያውን እንደራሳቸው ቤት ርስተ - ጉልት ባደረጉ ግለሰቦች ነው ይለናል - ዳንኤል ካህኔማን (Thinking, Fast and Slow)”
የአዕምሮአችንን ውሱንነት መዘንጋት የሚከሰተው እናውቃለን ብለን ባመንበት ነገር ያለን ለከት የለሽ በራስ መተማመን እና የድንቁርናችንን ሙሉ ገጽታ ለመረዳት ብቃት ማጣት እንዲሁም የምንኖርበትን ዓለም በጥርጣሬ መሞላት ልብ አለማለት ነው! በመጨረሻ የአገራችን የኢኮኖሚ ጣጣ ዛሬም መንገድም ኖሮ፣ አበባም ኖሮ፣ ባቡርም ኖሮ፤ ምን ሆነ? የሚለው ነው፡፡ ሙሰኛና ሙሰኛ ጀርባቸውን በሚተሻሹበት አገር ልማት ይኖራል ወይ? የሚለው ጥያቄ መልሱ አንድና አንድ ነው
ሹም ለሹም ይጐራረሳሉ፤
ድሃ ለድሃ ይላቀሳሉ!!
የልማት መርሀ - ግብር ሙስናን አይሽረውም እንደማለት ነው!!

“ከ100% በላይ ተጠናቋል” … ምን ማለት ነው?

    አንድ ወዳጄ ሰሞኑን ስልክ ደወለልኝና፤ “ፋብሪካው ከ100% በላይ ተጠናቋል ይባላል ወይ?” አለኝ፤ የመገረም ቅላፄ በሚያስተጋባ ድምፅ፡፡
“ምን ማለት ነው? እንዴት?” አልኩት፤ በመገረም ሳይሆን ግራ በመጋባት፡፡
“የሆነ ዜና ላይ ሰምቼው እኮ ነው … የሶላር ማምረቻ ምናምን መሰለኝ”
እኔ ከመናገሬ በፊት ሌላ አስገራሚ መረጃ አከለልኝ፡፡
“ደሞ እኮ ገና ሥራ አልጀመረም!”
“ምኑ ነው ታዲያ ከ100% በላይ ተጠናቋል የተባለው?”
ለአፍታ ያህል በጥልቅ ሀሳብ ውስጥ ሰጠምኩ፡፡
“ግን የት ነው የሰማኸው…. ከየትኛው ሚዲያ?” ከጥልቅ ሃሳብ ውስጥ መንጥቆ ያወጣኝ ከአንደበቴ ያፈተለከው የራሴ ጥያቄ ነበር፡፡ ወዳጄ መለሰልኝ፡፡
“ከመንግስት ሚዲያ ነው … ኢዜአ ወይም ኤፍ ኤም …” (ያው የመንግስት ሚዲያ የመንግስት ነው ብሎ መለሰኝ!)
እኔ የምላችሁ ግን …  “ፋብሪካው ከ100% በላይ ተጠናቋል” ሲባል… እውነት ምን ማለት ነው? ኢህአዴግ ስንት በታማበት የግንቦቱ ምርጫ እንኳን ከ100 ፐርሰንት በላይ ውጤት አምጥቷል አልተባለም! (ቦርዱማ 100% የተባለውንም አስተባብሏል!)
አሁን እኔ ለማወቅ የጓጓሁት ምን መሰላችሁ? ፋብሪካ ወይም ኮሌጅ አሊያም ሆስፒታል… ከ100% በላይ ተጠናቋል ሲባል… ምን እንደሚመስል ነው፡፡
እውነቴን እኮ ነው የምላችሁ … ከ100% በላይ የተጠናቀቀ ምንም ነገር ገጥሞኝ አያውቅም፡፡ ቆይ ግን? በምርጫስ ቢሆን … እገሌ ፓርቲ ከ100% በላይ በሆነ ድምፅ (ከየት መጥቶ?) አሸነፈ ይባላል እንዴ? (እዚህም ባይሆን እነ ሰሜን ኮሪጠ አካባቢ!) እኔ እንግዲህ ከወዳጄ መረጃ የተረዳሁት ምን መሰላችሁ? ከ100% በላይ ተጠናቋል ከተባለ፣ (ጦቢያ ምድር ማለቴ ነው!) “ሥራ አልጀመረም” ማለት ነው፡፡ (በምን ቋንቋ እንዳትሉኝ!)
መቼም ይሄን ዜና ያጠናቀረው ጋዜጠኛ፣ ቢያንስ “ቅጥ አምባሩ የጠፋ ዘገባ” በሚል ዘርፍ ዕውቅና ሊሰጠው ይገባል፡፡ ለነገሩ እንዲህ አይነት ልማታዊ ጋዜጠኞች በሽበሽ ናቸው፡፡ ለምሳሌ የEBC ጋዜጠኞች፤ የመንግስትን የልማት ስራዎች ወይም ስኬቶች ያለ ቅጥ በማጋነን፣ በመለጠጥና በማስፋት … ማንም የሚያህላቸው እንደሌለ በአስር ጣቴ ልፈርምላችሁ እችላለሁ፡፡ (ኧረ ኢህአዴግም ይፈርምላቸዋል!) እኔ የምለው ግን… “የግነት ጋዜጠኝነት” የሚባል ኮርስ አለ እንዴ? የኢህአዴግ ካድሬዎች እንዲህ ያለውን የ“ልማታዊ ጋዜጠኞች” ግነት፣ ለልማት ካላቸው ውስጣዊ መነሳሳትና መቆርቆር የመነጨ ነው … በሚል ሊገመግሙት ይችላሉ፡፡ ግምገማቸው ትክክል ነው … አይደለም የሚለውን ለመወሰን ግን አስቸጋሪ ነው፡፡ (“ውስጣዊ መነሳሳት” እና “መቆርቆር” የሚሉት ሃሳቦች መለኪያቸው ምንድን ነው?)
በነገራችን ላይ በየዓመቱ መስቀል ሲመጣ ትዝ የሚለኝ ... EBC ለበዓሉ ከመጡ የውጭ ቱሪስቶች ጋር የሚያደርገው ኢንተርቪውና ከዚያ ውስጥ የሚሰራው ግነት የበዛበት ዜና ነው፡፡ ይሄ እንኳን ዓላማው የአገር ገፅ ግንባታ በመሆኑ ችግር የለውም፡፡ ግን እኮ ዓላማው እንደተባለው ከሆነ፣ መቅረብ ያለበት ለኛ ሳይሆን ለውጭ ሰዎች ወይም ለኢትዮጵያ ዳያስፖራዎች ነበር፡፡ (እኛማ አረረም መረረም እየኖርነው ነው!)
ወደ “ልማታዊነት” ጉዳይ ልመልሳችሁ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በየሚዲያው ተከታትላችሁልኝ ከሆነ … ከመንግስት ባለስልጣናት እስከ ወረዳ አስተዳደር፣ ከከፍተኛ ባለሀብት እስከ ጥቃቅንና አነስተኛ ነጋዴዎች … ወዘተ ድረስ ምንም ሲናገሩ “… ልማታዊነት” የምትለዋን ቃል በግድ መደንገር አለባችሁ የተባሉ ይመስላሉ፡፡ “ልማታዊነት” ቃሉን ደጋግሞ በመጥራት ብቻ የሚመጣ ከመሰላቸው ቀለጡ፡፡ (አስማት እኮ አይደለም!)
እውነቱን ለመናገር ይሄ አካሄድ ግን ጤናማ አይደለም፡፡ ልማታዊ የመንግስት አመራሮችንም ሆነ ልማታዊ ባለሀብቶችን ፈፅሞ አይፈጥርልንም (ልማታዊ ደስኳሪዎችን እንጂ!)
ከዚያ ዘለል ካለም እንደ EBC ጋዜጠኞች ያሉ “የልማት ተቆርቋሪዎችን” ይፈጥርልን ይሆናል፡፡ ችግሩ ግን በአሁኑ ዘመን ጦቢያ የሚያስፈልጋት … በተግባር የሚሰራላት እንጂ የሚደሰኩርላት አሊያም የሚቆረቆርላት አይደለም፡፡ ልማታዊ ለመሆን ካድሬ መሆን አያስፈልግም (ለነገሩ ካድሬ ልማታዊ ሆኖ አያውቅም!) ልማታዊነት እኮ በተሰማራንበት ዘርፍ ውጤታማ ስራ ማከናወን ነው፡፡ ኪሳራ ሳይሆን ትርፍ ማስመዝገብ፡፡ ከመንግስትም ሆነ ከህዝብ የተሰጠንን ኃላፊነት በብቃት መወጣት ነው - ልማታዊነት!!
የተሰጣቸውን ትልቅ ኃላፊነት ሳይወጡ ቀርተው፤ “ልማቱ ወደፊት እንዲገሰግስ አስበን፣ ልማቱ እንዳይደናቀፍ ሰግተን፣ ልማቱ እንዳይቋረጥ ጓጉተን … ወዘተ” ሰበብ ድርደራ አያዋጣም፡፡
እንደውም ከተቻለ ከካድሬ በቀር ሌላው የመንግስት አገልጋይና ሹመኛ ሁሉ “ልማታዊ” የሚለውን ቃል ያለቦታው እንዳይደነጉር መመሪያ ቢጤ ቢወጣ ሸጋ ነበር፡፡ (በልማታዊነት ስም ሆድ አባብቶ ኃላፊነትን መሸሽ ተለምዷል!)
እናላችሁ … ሁሉም በተሰማራበት ሙያና በተሰጠው ኃላፊነት ቢለካ ነው የሚበጀው  “ልማታዊ …” የሚለውን ቃል በየንግግሩ መሃል በመሸጎጥ፣ እርስ በርስ መሸዋወድ ይብቃን! “ልማታዊ ነኝ” ያለ ሁሉ፤ ልማታዊነቱን በስራው ፍሬ፣ በውጤቱ ያስመዝን፡፡ ያኔ “ሀቀኛው ልማታዊ” እና “ሃሳዊው ልማታዊ” በግልፅ ይለያል፡፡ (ልማታዊነትን በመደስኮር የለማ አገር አላየንም!)
 ፖለቲካዊ ወጌን ከመቋጨቴ በፊት ሰሞኑን ለተለያዩ ሚዲያዎች ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የፀረሙስና ኮሚሽነሩ አቶ ዓሊ ሱሌይማን፤ ለአንድ ጥያቄ የሰጡትን ምላሽ እስቲ እንቆዝምበት፡፡
ከጋዜጠኛ የቀረበላቸው ጥያቄ እንዲህ ይላል፡- “ፀረሙስና ኮሚሽን፤ በከፍተኛ ባለስልጣናትና ባለሀብቶች ከሚፈፀሙ ሙስናዎች ይልቅ በትንንሽ ሙስናዎች ላይ የሚያተኩረው በፍራቻ የተነሳ ነው እንዴ?”
እሳቸውም እንዲህ ሲሉ መለሱ፤ “ሰው ይፈራል ባይባልም፣ የምንፈራበትም የማንፈራበትም ጉዳይ አለ፡፡ ትልቁ ነገር ግን ፍርሃቱ የግል ጉዳይ አይደለም፡፡ ልማት እንዳይደናቀፍ በመስጋት ነው፡፡ ልማቱን ላለማደናቀፍ በማለት ትንሹን ነገር አስበን፣ ትልቁ ነገር እንዳይሰናከል የምናደርገው ነገር ሊኖር ይችላል፡፡ በተረፈ ግን በራሳችን እንዲህ ብናደርግ እንዲህ ይመጣብናል የምንለው ነገር የለም፡፡”
እንዴ… ከዚህ በላይ ምን ይምጣ?! በትልቅ ስጋት … በከባድ ፍርሃት … እንዳሉ ያስታውቃሉ እኮ (ግን ያው ለልማቱ ሲሉ ነው!) “ልማቱ እንዳይደናቀፍ…” እየተባለ በሚደረገውም በማይደረገውም የተነሳ … አገሪቷ እንዳትደናቀፍ ሰጋሁ፡፡ (እንዴት አልሰጋ?!)
እኔ የምላችሁ… ቆይ ግን ልማት ምንድን ነው? ልማትና ሙስናስ? ትላልቆቹ ሙሰኞች በህግ ሲጠየቁ እንዴት ነው ልማቱ የሚደናቀፈው? ቁንጮዎቹ ሙሰኞች ይሄን ያህል አስፈሪ ሆነዋል ማለት ነው? በቁጥርስ ስንት ይሆናሉ? በመቶኛ ሲሰሉስ? ግን ግን እንዲህ የሚያስፈሩ እስኪሆኑ ድረስ ለምን ተጠበቁ? መቼ ነው “ልማቱ እንዳይደናቀፍ …” ከሚል ስጋት የምንወጣው?
ምናልባት እንዲህ ጉዳዩን እየበታተንን ስንፈትሸው አንዳች መላ፣ አንዳች ዘዴ ብልጭ ይልልን ይሆናል፡፡
በዚህ አንገብጋቢ ጉዳይ ላይ ጭንቅ ጥብብ ለማለት፣ የግድ የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር መሆን አይጠበቅብንም፡፡ ኢትዮጵያዊ መሆን ብቻ በቂ ነው፡፡ እናም እሳቸውንም ቢሆን ከሸክሙን እናግዛቸው (ለብቻቸውማ እዳ የለባቸውም!) መልካም ደመራ! መልካም መስቀል!

Saturday, 26 September 2015 08:01

የኪነት ጥግ

(ስለፊልም ስክሪፕት)
- ከጥሩ የፊልም ፅሁፍ መጥፎ
ፊልም መስራት እችላለሁ፤
ከቀሽም የፊልም ፅሁፍ ግን አሪፍ
ፊልም መስራት አልችልም፡፡
ጆርጅ ክሉኒ
አንድን ፊልም እሰራለሁ ወይም
አልሰራም ብዬ እንድወስን
የሚያደርገኝ የፊልም ፅሁፉ
አይደለም፡፡
ዣን ሉዊስ ትሪንቲኞንት
- አሁን አሁን የታሸገበትን ፖስታ
በማየት ብቻ የፊልም ፅሁፉ
አሪፍ መሆንና አለመሆኑን ማወቅ
እችላለሁ፡፡
ፒተር ኦ‘ቱሌ
- የፊልም ፅሁፍ ከማንበቤ
በፊት ምንም አይነት ውል
አልፈራረምም፡፡ ጥሩ ከሆነ
ደግሞ የ20 ዶላርም ይሁን የ1 ሚ.
ዶላር እሰራዋለሁ፡፡
ማርቲን ፍሪማን
- ልክ እንደ ፊልም ፅሁፍ ሁሉ፣
ለራስህ የቢዝነስ ዕቅድ ሊኖርህ
ይገባል፡፡
ፕሬይቲ ዚንታ
- ፀሐፊ ነኝ አልወጣኝም፤ በፊልም
ውስጥ ግን ለረዥም ጊዜ
ቆይቻለሁ፤ እናም የፊልም ፅሁፍ
መፃፍ እችላለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡
ቤኒቺዮ ዴልቶሮ
- ፊልም ለመስራት ከመወሰኔ
በፊት እናቴ ሁል ጊዜ የፊልም
ፅሁፉን ታነበዋለች፡፡
ቼሎ ግሬስ ሞርቴዝ
- መፅሀፍ በእጄ መያዝ እወዳለሁ፡
፡ አንድ ሰው የፊልም ፅሁፍ
ሲልክልኝ ታትሞ እንዲሰጠኝ
እጠይቃለሁ፡፡
ማርዮ ካንቶኔ
- ሊፃፍ ወይም ሊታሰብ የሚችል
ከሆነ፤ ፊልምም መሆን ይችላል፡፡
ስታንሌይ ኩብሪክ
- ከተሰሩት ማናቸውም ፊልሞች
ላይ እሰርቃለሁ፡፡
ኳንቲን ታራንቲኖ
- ዘይቤ (style) ማለት፤ ሁሉንም
ዘይቤዎች መርሳት ነው፡፡
ጄሌስ ሬናርድ
- ሁልጊዜም ፊልም ሰሪ የመሆን
ፍላጎት ነበረኝ፤ የመጀመሪያ
ፊልሜን እስክሰራ ድረስ ግን
ምስጢር አድርጌ አቆይቸዋለሁ፡
አንግሊ