Administrator

Administrator

    በላይ አብ ሞተርስ ከሁዋዌ ቴክኖሎጂስ ኢትዮጵያ ጋር ባደረገው የመኪና ሊዝ ስምምነት መሰረት፤ ዛሬ 36 ፒክ አፕ የመስክ ተሽከርካሪዎችን በማቅረብ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡
የኮርፖሬት የመኪና ኪራይ አገልግሎት በመጀመር በላይ አብ የመጀመሪያው እንደሆነ የጠቀሱት የድርጅቱ ኃላፊ፤ በተለያየ ምክንያት በራሳቸው ትራንስፖርት ከመጠቀም ይልቅ አገልግሎቱን ከአጭር ሳምንት እስከ ብዙ ወራት ለሚፈልጉ የመሰረተ ልማት ግንባታ፣ የመስክ ጥናትና ምርምር ለሚያከናውኑ ተቋማት፣ የኢንቨስትመንት ቅኝት ወይም ጥናት ለሚያካሂዱ ባለሀብቶች፣ ለሕዝብ ቆጠራና ምርጫ … እንደሚሰጥ አስታውቀዋል፡፡
የመኪናዎቹ አሽክርካሪዎች የበላይ አብ ሞተርስ ቅጥረኞች ሲሆኑ ተግባር ተኮር ስልጠና የተሰጣቸው፣ መኪኖቹም የደህንነትና የስምሪት ክትትልና ቁጥጥር ለማድረግ እንዲቻል ሲም ካርድና ጂፒኤስ ኤስ የተገጠመላቸው እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በሀገራችን የተንቀሳቃሽ ኔትወርክ ደረጃን ለማሻሻልና ለማሳደግ የሚሰራው ሁዋዌ ቴክኖሎጂስ ኢትዮጵያ፤ ከበላይ አብ ሞተርስ ጋር በገባው የሦስት ዓመት ውል መሰረት ፒክ አፕ መኪኖቹን በአዲስ አበባና በክልሎች ለትራንስፖርት አገልግሎት ይጠቀማል፡፡    
በላይ አብሞተርስ FAW  አውቶሞቢሎች ZNA ፒክአፕና ስቴሺንዋገን፣ አውቶቡሶችና ሞተር ሳይክሎችን አዳማ በሚገኘው የመኪና መገጣጠሚያ እየሠራ ሲሆን ባለሁለት ባለ አንድ ጋቢና ፒክ አፕ፣ ቀላል የጭነት መኪኖችን፣ ሚኒባስ፣ ከ22-45 መቀመጫ ያላቸውን ባሶች፣ ሎደሮች፣ ኤክስቫተሮች፣ ዶዘሮች፣ ግሬደሮች፣ ሮለሮችና የእርሻ መሳሪያዎችን ከውጭ ያስገባል፡፡

በርእስነት ያስቀመጥነው አባባል የዚህ አስተያየት አቅራቢ ነው፡፡ ይድረስ ለላንቺና ላንተ አምድ ዝግጅት ብለው ያደረሱን አስተያየት ከዚህ የሚከተለው ነው፡፡
“ቅዳሜ መጋቢት 2 ቀን 2009 ዓ.ም. በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ‘በህብረተሰብ’ አምድ ላይ ‘ፅንስ ማስወረድ ጥርስ የመንቀል ያህል ቀሏል’ በሚል ርዕስ ስለፅንስ ማቋረጥ ፅሁፍ መውጣቱ ይታወሳል፡፡ ፅሁፉ ጥንቃቄ የጐደለውን የፅንስ ማቋረጥ በመከላከል ረገድ ያለውን ሁኔታና መሻሻል ያለበትን ጉዳይ አስነብቧል፡፡ የጽሁፉ ርእስ አመራረጥም ምንጭ ካደረጋቸው ሰዎች የተገኘ ለመሆኑ በተለያየ መንገድ ተገልጾአል፡፡ ነገር ግን ምንጮች ያሉት አባባል  መነፃፀር የሌለባቸውን ጉዳዮች ያነጻጸረ ነው፡፡ በመሰረቱ ፅንስ ማቋረጥና ጥርስ ማስነቀል ለየቅል ስለሆኑ በምንም መመዘኛ የሚነፃፀሩ ጉዳዮች አይደሉም። በሙያነታቸው አንዳቸው ከሌላኛው የማይበልጡ ወይም የማያንሱ የተከበሩ ሙያዎች ናቸው፡፡ በሕክምናው ዘርፍ ሁለቱም የየራሳቸው የሆነ የሙያና የአሠራርና የአገልግሎት አሰጣጥ ጥበብ ያላቸው ናቸው፡፡ የፅንስ ማቋረጥ አገልግሎት የራሱ የሆነ የሰለጠነ ባለሙያና ደረጃውን የጠበቀ የሕክምና ተቋምና የአገልግሎት መስጫ መሣሪያዎችና መድሃኒቶች ያስፈልጉታል፡፡ ጥርስ ማስነቀልም በመጣጥፉ ውስጥ እንደቀረበው ቀላልና በዘፈቀደ የሚከናወን ሳይሆን ልክ እንደ ፅንስ ማቋረጡ የራሱ ባለሙያና ግብአቶች የሚያስፈልጉትና በጥንቃቄ የሚካሄድ መሆኑን አንባቢ ልብ ሊለው ይገባል። ይህንኑ የብዙቼንን ችግር የጥቂቶች እንደሆነ በማስመሰል ዘግናኝና ሰቅጣጭ በሆኑ ቃላትና አገላለጾች ማቅረብ ችግሩንም ሆነ የችግሩ ተጠቂዎችን አሳንሶ ወደማየት ሊያመራ ይችላል። ለምሣሌ አገልግሎቱን የሚሰጠውን ተቋም ‘ቤቢ ስቶፕስ’ የአገልግሎቱ ፈላጊዎችን ደግሞ ‘ነጠላ ዜማዋን ከምትለቅ ብናስፈነጥረው አይሻላት አገልግሎት ሰጪዎችንና ተቀባዮችን አውራጆችና አስወራጆች’ ብሎ ማቅረብ ለድርጊቱ ዝቅተኛ ግምት የተሰጠው ያስመስላል፡፡ በዚህ እትም እንደተገለጸው በደላሎች አገናኝነት የጽንስ ማቋረጥን ተግባር ዛሬም በየመንደሩ የሚፈጽሙ ሰዎች ካሉ ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡና ምስክርነቱን የሚሰጡላቸው ሰዎችም ይልቁንም ጉዳዩን ወደ ህግ አቅርበው እርምጃ እንዲወሰድ ቢያደርጉ የዜግነት ድርሻቸውን የሚወጡ ይመስለኛል፡፡ ያልተፈለገ እርግዝና ተከሰተ ብለው ባልተጠበቀ መንገድ ጽንሱን ለማቋረጥ የሚሄዱ ካሉ... እነሱም ቢሆኑ በህግ በተደገፈ በባለሙያና በጤና ተቋም ደህንነቱ የተጠበቀ ያውም በነጻ ጽንስን ማቋረጥ ስለሚችሉ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ መጣል እንደሌለባቸው አስተያየን እለግሳለሁ፡፡ የላንቺና ላንተ አምድ አዘጋጆች በዚሁ አጋጣሚ በአሁኑ ወቅት የጽንስ ማቋረጥ ሂደት ምን እንደሚመስል ባለሙያ አነጋግራችሁ ብታስነብቡን ጥሩ ይመስለኛል፡፡
        ቤተልሔም ተሾመ
የዚህ አምድ አዘጋጅ በደረሳት ጥቆማ መሰረት በአሁኑ ወቅት በጽንስ ማቋረጥ ዙሪያ ያሉት እውነታዎች ምን ይመስላሉ? ስትል በአይፓስ ኢትዮጵያ ዶ/ር አብዩት በላይን እና አቶ ደረጀ ወንድሙን አነጋግራለች፡፡ ዶ/ር አብዮት በላይ በአይፓስ ኢትጵያ ከፍተኛ ጤና አማካሪ ሲሆኑ አቶ ደረጀ ወንድሙ ደግሞ በዚሁ መስሪያ ቤት የፖሊሲ አማካሪ ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ በየዓመቱ ይፀንሳሉ ተብለው ከሚገመቱ ሴቶች መካከል 38 ከመቶ ያህሉ ሳያቅዱ ወይም ያለፍላጐታቸው እንደሚፀንሱ በአለን ጉት ማኸር ኢንስቲትዩትና አጋሮቹ እ.ኤ.አ. 2014/ በፅንስ ማቋረጥ ላይ የተካሄደ አንድ አገር አቀፍ ጥናት አመልክቷል፡፡ በዕድሜ ከ15 እስከ 49 ዓመት ከሆኑ 1000/ ሴቶች መካከልም 28ቱ ፅንስ ለማቋረጥ እንደሚገደዱ ይሄው ጥናት አስረድቷል፡፡ በጥናቱ መሠረት በአገሪቱ የሚገኙ የመንግሥት ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች እያንዳንዳቸው በዓመት በአማካይ 345/ ያህል ደህንነቱ ባልተጠበቀ መንገድ ፅንስ ለማቋረጥ ሞክረው ለድህረ ውርጃ ህክምና የመጡ ሴቶችን ያስተናግዳሉ፡፡ በተለይም በጠና ታመው ለድህረ-ውርጃ ህክምና ወደ ጤና ተቋማት ከሚሄዱ 100000/ ሴቶች መካከል 628ቱ እንደሚሞቱ ጥናቱ አሳይቷል፡፡ በኢትዮጵያ ለሴቶች ሞት ምክንያት ከሚሆኑት ዋና ምክንያቶች መካከል ጥንቃቄ የጐደለው ፅንስ ማቋረጥ አንዱ ነው፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት ከእርግዝናና ከወሊድ ጋር የተያያዙ የሴቶችን ህመምና ሞት ለመቀነስ የተሻሻሉና ፅንስ ማቋረጥን የሚመለከቱ የወንጀል ሕጉ ድንጋጌዎችን አዛብቶ ማቅረብም ተገቢ አይደለም፡፡ ለምሣሌ አስተያየት ሰጪዋ በተገለጸው እትም ላይ በተጠቀሰው ፅሁፍ የመጨረሻ አንቀጽ ውስጥ ‘አንዲት ሴት ውርጃን መፈፀም የምትችልባቸውን ምክንያቶች ያሰፈረው ሕጉ ሴቲቱ ውርጃ ለመፈፀም የምትፈልግበትን ምክንያት እንድትገልጽ አትገደድም ሲል ውርጃን በግልፅ መፍቀዱንም መከልከሉንም የማያሳይ አንቀጽ አክሎበቭል’ የሚለው አገላለጽ ብዥታን ይፈጥራል፡፡
መንግሥት ከወሊድና ከእርግዝና ጋር የተያያዙ የእናቶችን ሕመምና ሞት ለመቀነስ በኢትዮጵያ የወንጀል ሕጉ ውስጥ ፅንስ ማቋረጥን የተመለከቱ ድንጋጌዎች በ1997 ዓ.ም. እንዲሻሻሉ አድርጓል፡፡ ይህንንም ተከትሎ በ1998 ዓ.ም. በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ዝርዝር የቴክኒክና የአፈፃፀም መመሪያ ወጥቶ ተግባራዊ በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡ የፅንስ ማቋረጥ ሕጉን ማሻሻል ያስፈለገበት ዋነኛው ዓላማ ጥንቃቄ በጐደለው የፅንስ ማቋረጥ የተነሳ የሚደርሰውን አላስፈላጊ የእናቶችን ህመምና ሞት ለመቀነስ ሲሆን በተጨማሪም የሚከተሉትን ምክንያቶች ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ነው፡፡ እነሱም በርካታ ሴቶች በቤተሰብ ዕቅድ መረጃና አገልግሎት ባለማግኘት ላልተፈለገ እርግዝና የሚጋለጡ በመሆኑ ፅንስ ማቋረጥን በሕግ መከልከል ጥንቃቄ የጐደለውን ፅንስ ማቋረጥ የሚያባብስ በመሆኑ ፅንስ ማቋረጥን ለመቀነስ መፍትሄውበሕግ መከልከል ሳይሆን ሴቶችና ወንዶች ስለአካላቸው ተገቢ ግንዛቤ እንዲያገኙ ማድረግ እና የቤተሰብ ዕቅድ ፕሮግራምን ማስፋፋት መሆኑን በመገንዘብና ጥንቃቄ የጐደለውን ፅንስ ማቋረጥ ለማከም የሚወጣው ወጪ በሴቷም ሆነ በጤና ተቋማት ላይ ጫና የሚያሳድር መሆኑን በመገንዘብ ነው፡፡
ስለ ተዋልዶ ጤና የተሟላ መረጃ የሌላቸውና አስተማማኝ የእርግዝና መከላከያ የማያገኙ ሴቶች ላልታቀደ እርግዝና የመጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ፅንስ ማቋረጥ በሕግ ቢፈቀድም ባይፈቀድም ፅንስ ለማቋረጥ የወሰኑ ሴቶች ያጋጠማቸውን ያልቭቀደ እርግዝና ከማቋረጥ ወደኋላ አይሉም፡፡ የእርግዝና መከላከያ ዘዴዎች በማይኖሩበት ወይም በመከላከያዎቹ መጠቀም በህዝቡ አመለካከት የማይደገፍ ከሆነ ወሊድን ለማዘግየት ወይም ለመከላከል የሚፈልጉ ሴቶች ፅንስ ማቋረጥን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚፈጽሙ ጥናቶች ያመለክቭሉ፡፡ በሌላ በኩል ፅንስ ማቋረጥ በከፍተኛ ደረጃ ይፈፀምባቸው የነበሩ ያደጉ አገሮች የእርግዝና መከላከያ በማስፋፋታቸውና በተሳካ ሁኔቭ ሥራ ላይ በማዋላቸው ፅንስ ማቋረጥ እየቀነሰ መምጣቱን ከጥናቶች መገንዘብ ተችሏል። በመሆኑም ፅንስ ማቋረጥን በሕግ መፍቀድና አገልግሎቱን ተደራሽ ማድረግ ሴቶች ፅንስ በማቋረጥ እንዲተማመኑና እንደወሊድ መቆጣጠሪያ እንዲጠቀሙበት ሊያደርግ አይችልም፡፡ ፅንስ ማቋረጥን ለመከላከል መፍትሄው በሕግ መከልከል ሳይሆን ሴቶችና ወንዶች ስለአካላቶቻቸው በደንብ እንዲገነዘቡ ማድረግና የእርግዝና መከላከያ ዘዴዎችን በማስፋፋት ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል ነው፡፡ ሴቶች የእርግዝና መከላከያን በአጥጋቢ ሁኔቭ በሚጠቀሙበት ጊዜ የፅንስ ማቋረጥ ክስተት ይቀንሳል፡፡
በአንዳንድ አገሮች ፅንስ ማቋረጥ ሕጋዊ መደረጉን ተከትሎ የፅንስ ማቋረጥ ክስተት የጨመረ መስሎ እንደሚታይ የሚጠቁሙ አሃዛዊ መረጃዎች አሉ፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው ድርጊቱ ጨምሮ ሳይሆን ቀደም ሲል በሕገወጥ መንገድና በድብቅ ሲሠራ የቆየው የፅንስ ማቋረጥ ተግባር በህጋዊ መንገድ በግልጽ መከናወን በመጀመሩና ሳይደበቅ ሪፖርት በመደረጉ ነው፡፡
ሴቶች ያልተፈለገ እርግዝና ሲገጥማቸውና ፅንስ ለማቋረጥ ሲወስኑ ደህንነቱ የተጠበቀ ሕጋዊ የፅንስ ማቋረጥ አገልግሎት ካላገኙ ደህንነቱ ባልተጠበቀ ሁኔታ ምርጫቸውን ለመፈጸም ይገደዳሉ፡፡ በመሆኑም ፅንስ ማቋረጥን በሕግ ባልገደቡ አገሮች የክስተቱ መጠን በአነስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ድርጊቱን በሕግ በከለከሉ በማደግ ላይ በሚገኙ አገሮች ደግሞ ከፍተኛ የሆነ ጥንቃቄ የጐደለው የፅንስ ማቋረጥ ተግባር እንደሚካሄድ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ በተጨማሪም የፅንስ ማቋረጥ ዕድልን በሕግ በፈቀዱ አገሮች ውስጥ ጥንቃቄ በጐደለው የፅንስ ማቋረጥ ምክንያት የሚሞቱ ሴቶችን ቁጥር ለመቀነስ አስችሏል። በዚህ ረገድ የአገራችን ኢትዮጵያ ልምድ ተጠቃሽ ነው፡፡ ለምሣሌ ያህልም ከጤና ጥበቃ በተገኘ መረጃ መሠረት በ1998 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ጥንቃቄ በጐደለው ፅንስ ማቋረጥ ምክንያት የሚሞቱ ሴቶች ቁጥር 32 በመቶ የነበረ ሲሆን ሕጉ ከተሻሻለ ከ10 ዓመት በኋላ ግን ይህ አሃዝ ወደ 10 በመቶ ዝቅ ብሏል፡፡
የጤና ጥበቃ የአፈፃፀም መመሪያው የጤና ባለሙያው በቅን ልቦናው ሙያውን ተግባራዊ እንዲያደርግ ሰፊ ሥልጣን የሰጠው እንደማንኛውም ሌላ ህመም ሲሆን የግል አመለካከቱ ሳያግደው ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት የመስጠት ግዴታ እንዳለበት ያመለክታል እንጂ ሴቶች ስለጠየቁ ብቻ አገልግሎቱን ያገኛሉ ማለት አይደለም፡፡ ሕጉ በመደፈር ወይም ከቤተዘመድ ጋር በተደረገ ግንኙነት ለተከሰተ ፅንስ ማስረጃን ለማቅረብ በሚወስደው ጊዜ መራዘም ምክንያት ሴቶች ጥንቃቄ በጐደለው መንገድ ውስብስብ ወደሆነ የጤና ችግር ውስጥ እንዳይገቡ በማሰብ በተለየ ሁኔታ እንዲታይ አድርጓል። ይኸውም በመደፈር ወይም ከዘመድ ጋር በተፈፀመ የግብረ-ስጋ ግንኙነት አረገዝኩ ያለች ሴት የደፋሪውን ወይም የዘመዷን ማንነት ለመግለጽ እንደማትገደድ በሕጉ መብት ተሰጥቷታል። በተመሳሳይ ሁኔ ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች ለሆናቸው ወጣት ሴቶች የዕድሜያቸው ትክክለኛነት የሚገልጽ ማስረጃ ለማቅረብ እንደማይገደዱ በሕጉ ተመልክቷል፡፡

የስኮትላንድ ፓርላማ አገሪቱ ከብሪታኒያ ለመገንጠል የሚያስችላትን ህዝበ ውሳኔ በድጋሚ ለማድረግ የያዘቺውን አዲስ ሃሳብ ባለፈው ማክሰኞ በአብላጫ ድምጽ መደገፉን ተከትሎ፣ የእንግሊዝ መንግስት የመገንጠል ዕቅዱን እንደማይቀበለው ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
አገሪቱ ከብሪታንያ ለመገንጠል የሚያስችላትን ህዝበ ውሳኔ በመጪው አመት መጨረሻ ለማከናወን የሚያስችላትን ፈቃድ ከእንግሊዝ ለማግኘት ማሰቧን የስኮትላንድ ተቀዳሚ ሚኒስትር ኒኮላ ስተርጂን የገለጹ ሲሆን የእንግሊዝ መንግስት ግን በዚህ እቅድ ዙሪያ እንደማይደራደር አስታውቋል፡፡
የስኮትላንድ ፓርላማ ለሁለተኛ ጊዜ የመገንጠል ህዝበ ውሳኔ ይደረግ በሚለው የሚኒስትሯ ሃሳብ ላይ ባለፈው ማክሰኞ በሰጠው የድምጽ አሰጣጥ ስነስርዓት፣ ሃሳቡን 69 ለ59 በሆነ አብላጫ ድምጽ ቢያሳልፈውም የእንግሊዟ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ ግን፣ ዕቅዱን እንደማይቀበሉትና ድርድር እንደማያደርጉበት አስታውቀዋል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት ቃል አቀባይ፤ “የመንግስት የወቅቱ ዋነኛ ትኩረት አገሪቱ ከአውሮፓ ህብረት አባልነቷ ለመውጣት የጀመረቺው እንቅስቃሴ ነው፤ የስኮትላንድ የመገንጠል ጥያቄ የወቅቱ የመንግስታችን አጀንዳ አይደለም” ማለታቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡ የስኮትላንድ ህዝብ እንግሊዝ ከአውሮፓ ጋር የሚኖራትን ቀጣይ ግንኙነት በተመለከተ ወሳኝ የሆኑ መረጃዎችን ባላገኘበት ሁኔታ ይህንን እጅግ ቁልፍ ውሳኔ እንዲያሳልፍ መጠየቅ ፍትሃዊ አይደለም ሲሉም አክለዋል፡፡
ስኮትላንድ በ2014 ከብሪታኒያ ለመገንጠል ያካሄደቺው ህዝበ ውሳኔ የብዙኃኑን ድጋፍ ባለማግኘቱ አገሪቱ ሳትገነጠል መቅረቷ ይታወሳል፡፡

የአውሮፓ ህብረት በቀድሞው የሊቢያ ፕሬዚዳንት ሙአመር ጋዳፊ ሴት ልጅ አይሻ ጋዳፊ ላይ ጥሎት የቆየውን ማዕቀብ እንዲያነሳ በፍርድ ቤት ውሳኔ መሰጠቱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ህብረቱ እ.ኤ.አ በ2011 አይሻን ጨምሮ በተወሰኑ ሊቢያውያን ላይ የጉዞ ማዕቀብና ሃብታቸው እንዳይንቀሳቀስ የሚያስችል ትዕዛዝ ማስተላለፉን ያስታወሰው ዘገባው፤ ከ3 አመታት በኋላ የሌሎቹ ማዕቀብ ሲነሳ የአይሻ በዚያው መቀጠሉንና ማዕቀቡ ይነሳልኝ ስትል ያቀረበቺው ጥያቄ ተቀባይነት ሳያገኝ መቅረቱን ገልጧል፡፡
አይሻ በቅርቡ በፍርድ ቤት በመሰረተቺው ክስ፤ አባቷ ከሞቱና አገዛዛቸው ካከተመ በኋላ በእሷ ላይ የተጣለው ማዕቀብ አለመነሳቱ አግባብ አለመሆኑን በመግለጽ የተከራከረች ሲሆን ፍርድ ቤቱም አቤቱታዋ አግባብነት ያለው መሆኑን በመጥቀስ ማዕቀቡ እንዲነሳላት ወስኗል፡፡ የአውሮፓ ህብረት መንግስታትም ለፍርድ ቤት ክርክር የወጣውን ወጪ እንዲሸፍኑ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
አይሻ እና ሌሎች የተወሰኑ የጋዳፊ ቤተሰቦች እ.ኤ.አ ከ2013 አንስቶ በኦማን በጥገኝነት እየኖሩ እንደሚገኙም ዘገባው አስታውሷል፡፡

በጋና 208 የመንግስት መኪኖች የገቡበት ሳይታወቅ ጠፍተው መቅረታቸው መረጋገጡን ተከትሎ የአገሪቱ መንግስት ከአሁን በኋላ ለሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችና ለባለስልጣናት አገልግሎት የሚሰጡ አዳዲስ መኪኖች እንዳይገዙና አሮጌዎቹ ጥቅም መስጠታቸውን እንዲቀጥሉ መወሰኑን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር የወጣባቸው ቪ ኤይት እና ፕራዶ የመሳሰሉ ውድ መኪኖች የውሃ ሽታ ሆነው መቅረታቸውን ተከትሎ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ናና አኩፎ አዶ ባስተላለፉት ውሳኔ፣ የህዝብ ሃብት እየባከነ በመሆኑ ከአሁን በኋላ ላልተወሰነ ጊዜ ለመንግስት መስሪያ ቤቶች አገልግሎት የሚሰጡ አዳዲስ መኪኖች አይገዙም ብለዋል፡፡
ስልጣኑን የለቀቀው መንግስት 707 የመንግስት መኪኖችን ለአዲሱ የአገሪቱ መንግስት ማስረከቡን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአዶ መንግስት ስልጣን መያዙን ተከትሎ በተደረገ የሃብት ቆጠራ 234 መኪኖች መጥፋታቸው መረጋገጡንና የተወሰኑት በፍለጋ ሲገኙ የተቀሩት 208 መኪኖች ግን አሁንም ድረስ እምጥ ይግቡ ስምጥ ሳይታወቅ የውሃ ሽታ ሆነው መቅረታቸውን ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ፖሊስና ጉምሩክን ጨምሮ ከተለያዩ መስሪያ ቤቶች የተውጣጡ ግለሰቦችን በአባልነት የያዘ ልዩ ግብረ ሃይል አዋቅሮ የጠፉትን መኪኖች የማፈላለግና ከጉዳዩ ጋር ንክኪ ያላቸውን የቀድሞም ሆነ የአሁኑ የጋና መንግስት ባለስልጣናትን በቁጥጥር ስር አውሎ፣ ለህግ ለማቅረብ እየሰራ እንደሚገኝም ዘገባው ገልጧል፡፡

ካርሎስ ቀበሮው በሚል ቅጽል ስሙ የሚታወቀውና ከአለማችን ቀንደኛ ገዳዮች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ኢሊች ራሚሬዝ ሳንቼዝ፣ ከ43 አመታት በፊት በፓሪስ በሚገኝ የገበያ ማዕከል በፈጸመው አሰቃቂ የግድያ ወንጀል ባለፈው ማክሰኞ ለ3ኛ ጊዜ የዕድሜ ልክ እስራት ቅጣት እንደተጣለበት አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1974 የተከሰተውንና 2 ሰዎች ለሞት፣ 34 ሰዎች ደግሞ ለመቁሰል አደጋ የተዳረጉበትን የቦምብ ጥቃት ፈጽሟል በሚል ክስ ተመስርቶበት ፓሪስ በሚገኝ ፍርድ ቤት የቀረበውና ድርጊቱን አልፈጸምኩም ብሎ የተከራከረው ካርሎስ፤ በተከሰሰበት ወንጀል ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ተጨማሪ የዕድሜ ልክ እስራት እንደተፈረደበት ዘገባው ገልጧል፡፡
ካርሎስ ችሎቱ ከመሰየሙ ከሰዓታት በፊት፣ “ይህ እጅግ የሚገርምና ከአራት አስርት አመታት በፊት ተፈጸመ በተባለ ወንጀል ላይ የሚከናወን ወለፈንዲ የሆነ የፍርድ ሂደት ነው” በማለት ችሎቱን ያጣጣለ ቢሆንም፣ የዕድሜ ልክ እስራት ፍርዱ መወሰኑንና ይህን ተከትሎም ጠበቆቹ ውሳኔውን በመቃወም ይግባኝ እንደሚጠይቁ ማስታወቃቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ከ23 አመታት በፊት በፈረንሳይ ልዩ ሃይል ክትትል በካርቱም በቁጥጥር ስር የዋለው ቬንዙዋላዊው አደገኛ ገዳይ ካርሎስ በ1970 ዎቹ እና 80 ዎቹ በፈጸማቸውና ባስፈጸማቸው በርካታ የግድያ ወንጀሎች ለሁለት ጊዚያት የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት ከዚያ ጊዜ አንስቶ በፈረንሳይ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ የ67 አመቱ ካርሎስ፣ ከሳምንታት በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት ሙያህ ምንድን ነው በሚል ከችሎቱ ለቀረበለት ጥያቄ፣ “ብቁ አብዮተኛ” ሲል ምላሽ የሰጠ ሲሆን ዕድሜውን ሲጠየቅም፣ “17 ነው፤ ደስ ካላችሁ 50 አመት ጨምሩበት” ሲል ማላገጡን ዘገባው አስታውሷል፡፡

ውይይት ይደረጋል
እናት የማስታወቂያ ድርጅት፣ የጀርመን የባህል ማዕከልና ወመዘክር በትብብር በሚያዘጋጁት የንባብ ፕሮግራም ነገ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ‹‹ቤት ያጣው ቤተኛ››የተሰኘው የዮናስ ጎርፌ መፅሀፍ ላይ በወመዘክር አዳራሽ ውይይት ይካሄዳል፡፡ በዕለቱ የውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርበው የሙዚቃ ባለሙያው ሰርፀፍሬ ስብሀት እንደሆነ የገለፀው እናት የማስታወቂያ ድርጅት ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ጋብዟል፡፡

በምስክር ጌታነው ሚዲያና ፕሮሞሽን የተዘጋጀውና “የማንነት ዜማ” የተሰኘው የኪነ ጥበብ ምሽት የፊታችን ማክሰኞ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በብሔራዊ ቴአትር ይካሄዳል፡፡ በምሽቱ የበገና ድርደራ፣ የዋሽንት፣ የክራር፣ የመሰንቆና የመለከት ጨዋታዎች ለታዳሚ እንደሚቀርብም አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡ በዚህ ምሽት ዲያቆን ዳንኤል ክብረትና መጋቢ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ ወግና ዲስኩር የሚያቀርቡ ሲሆን ገጣሚ ነቢይ መኮንን ወግ ያቀርባል ተብሏል፡፡ በዚህ የባህል፣ የትውፊትና የጥበብ ምሽት ላይ ፍላጎት ያለው እንዲታደም አዘጋጁ ጋብዟል፡፡

በ2016 የኖቤል ሽልማት በስነጽሁፍ ዘርፍ አሸናፊ የሆነውና ስራ ስለበዛብኝ ሽልማቱን ለመቀበል አልችልም በማለት በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ሳይገኝ የቀረው አሜሪካዊው ድምጻዊና የሙዚቃ ግጥም ደራሲ ቦብ ዲላን፣ ከወራት ማንገራገር በኋላ ሰሞኑን ሽልማቱን ለመቀበል መስማማቱ ተዘግቧል፡፡
ባልተለመደ ሁኔታ ስለ ሽልማቱ ምንም አይነት አስተያየት ሳይሰጥ በመቆየቱና ሽልማቱን ባለመቀበሉ ብዙዎችን ሲያነጋግር የቆየው ቦብ ዲላን፤ አሸናፊነቱ በይፋ ከታወጀ ከአምስት ወራት በኋላ ስቶክሆልም ወደሚገኘው የኖቤል ተቋም በማምራት ሽልማቱን ለመቀበል መወሰኑን ቢቢሲ ገልጧል፡፡
የ75 አመቱ ቦብ ዳይላን በመጪዎቹ ጥቂት ቀናት ውስጥ በስቶክሆልም ሁለት የሙዚቃ ኮንሰርቶችን እንደሚያቀርብ የጠቆመው ዘገባው፣ እግረ መንገዱን  የ900 ሺህ ዶላር ሽልማቱን ይቀበላል ተብሏል፡፡
በተቋሙ ህግ መሰረት የኖቤል ተሸላሚ የሆነ ሰው በአንድ ዩኒቨርሲቲ በእንግድነት ተጋብዞ ትምህርት ካልሰጠ የሽልማት ገንዘቡን እንደማያገኝ ያመለከተው  ዘገባው፤ ዲላን ግን በአካል ተገኝቶ ለማስተማር እንደማይችል ጠቁሙ ይሄም ሆኖ ግን ትምህርቱን በቪዲዮ ቀርጾ ለማስተላለፍ ማቀዱን ገልጧል፡፡
ዲላን በኖቤል የስነጽሁፍ ዘርፍ ተሸላሚ በመሆን የመጀመሪያው አሜሪካዊ የዘፈን ግጥም ደራሲ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ በ1993 በስነጽሁፍ ዘርፍ ከተሸለመው የረጅም ልቦለድ ደራሲው ቶኒ ሞሪሰን በመቀጠል በዘርፉ ለሽልማት የበቃ አሜሪካዊ መሆኑንም አስታውሷል፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን፤ አመሻሹ ላይ አንድ የተራበ ተኩላ የሚበላ ነገር ባገኝ ብሎ ከቦታ ቦታ ሲዘዋወር፣ ድንገት አንድ ግቢ ውስጥ የህፃን ልጅ ድምፅ ይሰማል፡፡ ግራ ቀኝ ቃኝቶ ማንም በአካባቢው እንደሌለና እንደማይታይ አረጋግጦ፤ ቀስ ብሎ ኮሽታ ሳያሰማ ወደ ግቢው ይገባል፡፡ ወደ መስኮቱ ተጠጋና ከቤት ውስጥ የሚሰማውን ድምፅ በጥሞና ማዳመጥ ይጀምራል፡፡
ህፃኑ አሁንም እያለቀሰ ነው፡፡ እናትየው ልታባብለው ትሞክራለች፡፡
‹‹ማሙሽዬ ዝም በል፤ ነገ የማረግልህን አታውቅም፡፡ ከረሜላ፣ ብስኩት፣ እገዛልሀለሁ፡፡ ግን ማልቀስህን ካቆምክ ነው፡፡ እሺ?›› ማሙሽ አልተበገረም፡፡ ብስኩቱም ከረሜላውም ሊያማልለው አልቻለም፡፡
እናት ትዕግሥቷን ጨረሰችና፤
‹‹እንግዲህ ዋ! ውጪ ላለው ተኩላ ነው የምወረውርህ!›› አለችው፡፡
ተኩላ ይሄን ሲሰማ ልቡ ጮቤ ረገጠች፡፡
‹‹አሃ ልጁን ሊወረውሩልኝ ነው፡፡ እራቴን የምበላው ላገኝ ነው ማለት ነው!›› አለ፡፡ በፀጥታ መጠበቁን ቀጠለ፡፡
መስኮቱ ሥር ሆኖ ኮሽ ባለ ቁጥር እየቋመጠ ቀና ይላል፡፡ ምንም የለም፡፡ በጊዜ ለማይለካ ጊዜ በረሀብና በጉምዥት እያዛጋ ጠበቀ፡፡ ልጁ አልተወረወረለትም፡፡
እየመሸ ሲሄድ ልጁ እየተረጋጋላት ሲመጣ፤ እናትየዋ፤
‹‹ጎበዝ የኔ ልጅ!! ያ ተኩላ ቢመጣ በጭራሽ ልጄን አልሰጠውም፡፡ አንተ ፀባይ ያለህ ቆንጅዬ ልጅ ነህ፡፡ በል እንዲሞቅህ ቢጃማህን ድርብርብ አድርገህ አልጋህ ውስጥ ግባና ለጥ በል፡፡ እሺ የእኔ ቆንጆ?››
ልጁም፤
‹‹እሺ እማዬ ለጥ እላለሁ!›› አለና ተኛ፡፡ ተኩላው በጣም ተናደደ፡፡
‹‹በጣም የሚያሳዝነው እነዚህ ሰዎች ቃላቸውን ይጠብቃሉ ብዬ ልቤን ማውለቄ! ከእንግዲህ የዚያ ቤት ሰዎች የሚናገሩትን አንድም ቃል አላምንም!›› ብሎ ግቢውን ለቅቆ ወጣ!
*   *   *
ተጨባጭና ላም አለኝ በሰማይ ተስፋን መለየት፣ ካሮትና ዱላን ማወቅ፣ ዋናና አቋራጭ መንገድን ልብ ማለት ዋና ነገር ነው፡፡ አገኛለሁ ተብለው የሚጠበቁና የማይጠበቁ ነገሮችን ለይቶ ማወቅ ብልህነት ነው፡፡ ሰጪዎች በዋዛ የማይለቋቸው፣ ተቀባዮች ሲመኙዋቸው የሚኖሩ አያሌ ጉዳዮች እንዳሉ አለመርሳት ነው፡፡ ልጅ ራበኝ ብሎ ማልቀሱ፣ የፈለገውን ካልሰጣችሁኝ ብሎ ማልቀሱ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ እናት ማባበሏና እንዲተኛ ማድረጓ ግን የእናትነት ኃላፊነትና ፍቅር ነው፡፡ ህዝብ የሚጠይቃቸው ነገሮች አያሌ ናቸው፡፡ አንዳንዴ አልቅሶ ይጠይቃል፡፡ አንዳንዴ ጮኾ ይጠይቃል። አንዳንዴ በምሬት ይጠይቃል፡፡ ሁሉንም ጥያቄዎች እንደየጠባያቸው መልስ መስጠት ተገቢ ነው፡፡ የራሱና ራሱ ነጥቆ የሚወስዳቸው እንደ ሰብዓዊ መብቶችና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ያሉ ቁልፍ ነገሮች መኖራቸውን ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ ህዝቡ ራሱም የሚያውቀው ጉዳይ ነው፡፡ የእኔ ነው የሚለውንና ጎደለብኝ የሚለውን ለይቶ ማወቁ ነው ጥያቄዎችን እንዲያነሳ የሚያደርገው፡፡ ለዚህ ደግሞ የሲቪክ ተቋማት፣ የሙያ ተቋማት፣ ፓርቲዎች፤ አጋዥ ኃይላት ናቸው፡፡ እነሱም ቢሆኑ በወግ በወግ ሆነው፣ “ጋን በጠጠር ይደገፋል” የሚሉና በጥበባዊ ስልት የህዝብ ጥያቄ እንዲመለስ ተግተው የሚረዱ መሆን አለባቸው፡፡
መግባባትን፣ መቻቻልን፣ ዕርቅን፣ ትዕግሥትን፣ የጊዜ አጠቃቀምን ማወቅ አለባቸው፡፡ በመንግሥት በኩል ህዝብ ምሬት ደረጃ እስኪደርስ፣ የኑሮ ውድነቱ አንገፈገፈኝ እስኪል፣ ቸል ብሎ ማየት ነባራዊና ህሊናዊ ሁኔታዎችን አለመገንዘብ ነው፡፡ ሁኔታዎችን አለመገንዘብ ኋላ ተጠያቂነትን እንደሚያስከትልና ዋጋም እንደሚያስከፍል ልብ ማለት የልባሞች ክህሎት ነው፡፡
በሀገራችን ውስጥ የምናካሂዳቸው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ አብዮቶች የተሣሠሩ ካልሆኑ ዋጋ አይኖራቸውም፡፡ እንደገና ይበተናሉና፡፡ የሁሉም ግብ አገርን ማዘመን ነው፡፡ ይህም የህዝብ ህይወት የተሻለ እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡
ዳንኤል ለርነር የተባለ ፀሐፊ፤ ስለ ዝመና ሲናገር፤ “ዝመና እጅግ መልከ - ብዙ ሂደት ሲሆን በሁሉም የሰው ልጅ ሀሳብና እንቅስቃሴ ውስጥ ያለና ተጠቃሽ ነው፡፡ ዋና ዋናዎቹ ፍሬ ጉዳዮቹ፡- ከተማዊነትን ማበልፀግ (urbanization) ኢንዱስትሪያዊነት፣ ዓለማዊ ይዞታን ማሳደግ፣ ዲሞክራሲን ማስፋፋት፣ ትምህርትን ማራባትና የሚዲያ ተሳትፎን ማጎልበት ሲሆኑ፤ ቁም ነገሩ ግን ሁሉም የሚያድጉት ከተጣመሩና ከተሳሰሩ መሆኑ ላይ ነው” ይለናል፡፡ ዝምድናቸውና ሰምሮ - ተጓዥነታቸውን በትጋት መከታተል ያሻል፡፡
የእነዚህን ፍሬ ጉዳዮች ዕድገት ማረጋገጥ የሚቻለው ደግሞ ህዝብን አምኖ የህዝብን ተሳትፎ በእያንዳንዳቸው ውስጥ በአስተማማኝ መንገድ ማሳየት ሲቻል ነው፡፡ እንደ ድሮው ዘመን ፖለቲካዊ ንትርክ፤ “ሥርዝ ያንተ፣ ድልዝ የእኔ፣ እመጫት የእሷ፤ ሆያ - ሆዬ የሰፊው ህዝብ!” ብለን የምናልፈው ነገር አይደለም፡፡ ህዝብን ሳይዙ ጉዞ “እንሥራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” እንደሚባለው ዓይነት ነው። በየዘመኑ በተደጋጋሚ “ህዝብን ማገልገል” ፣ “ህዝባዊነት”፣ “ህዝባዊ ተሳትፎ”፣ “ዲሞክራሲያዊ አሳታፊነት”፣ “አረንጓዴ ዘመቻ”፣ “የኢኮኖሚ አብዮት”፣ “የባህል አብዮት” ወዘተ … ሲባል እንሰማለን። የዚህ ሁሉ መቋጫ ግን አንድ ጥያቄ ነው፡፡ “በተግባር አለ ወይ? አፍአዊ ነው ልባዊ?” የሚለው ነው። የሀገራችን ዕውነታ አብዛኛውን ጊዜ አሉታዊ መልስ እንዳለው ነው የሚያመላክተን፡፡ ወረቀት ላይ እንጂ መሬት ላይ የለም፡፡ ለምን ተብሎ ሲጠየቅ፤ በርካታ ምክኖችን መደርደር ቢቻልም አንዱ ዐቢይ ምክን ሐቀኛ ተግባሪ መጥፋቱ ነው! የወሬ ሰው መብዛቱ ነው፡፡ ለታይታና ለአደባባይ እይታ አለሁ አለሁ ባዩ መበርከቱ ነው! ደስኳሪው ከአንድ ቦይ እንደሚፈስ ውሃ የሚለፈለፍ ንግግር ሚዲያውን መሙላቱ ነው! ሁሉን መነካካት፣ ስለ ሁሉም ማውራት፤ በተጨባጭ  ምንም ፍሬ አለመያዝ… እየተለመደ መጥቷል፡፡ የለብ - ለብ ፖለቲካ፣ የለብ ለብ ኢኮኖሚ፣ የለብ ለብ ቢሮክራሲያዊ ዘመቻ ተጠናውቶናል፡፡ “ተሸክመዋል እንዳይባል በብብታቸው፣ ፈጭተዋል እንዳይባል ግማሽ ቁና” የሚለው ተረት የሚያስረዳን ይሄንኑ ነው!