Administrator

Administrator

  ትውልደ ኢትዮጵያዊው አቤል ተስፋዬ 6ኛ ደረጃን ይዟል

     ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤ የ2017 የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ 100 ዝነኞችን ዝርዝር ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ አምና በ22ኛነት ደረጃ ላይ የነበረው ታዋቂው ድምጻዊ ሻን ዲዲ ኮምብስ፣ ባለፉት 12 ወራት፣ የ130 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት ዘንድሮ የአንደኛነት ደረጃን ይዟል፡፡
ባለፈው አመት በ34ኛ ደረጃ ላይ የነበረቺው ታዋቂዋ ድምጻዊት ቢዮንሴ ኖውልስ፣ ዘንድሮ 105 ሚሊዮን ዶላር በማፍራት  የሁለተኛነት ደረጃን ስትይዝ፣ በአመቱ በድምሩ 95 ሚሊዮን ዶላር ያፈራቺው እንግሊዛዊቷ የ”ሃሪ ፖተር” መጽሃፍት ደራሲ ጄ ኬ ሮውሊንግ በበኩሏ የሶስተኛነቱን ደረጃ ይዛለች፡፡
ካናዳዊው የሂፕ ሆፕ አቀንቃኝ ድሬክ በ94 ሚሊዮን ዶላር፣ የአለማችን የወቅቱ የእግር ኳስ ኮከብ ክርስቲያኖ ሮናልዶ በ93 ሚሊዮን ዶላር አራተኛና አምስተኛ ደረጃን የያዙ ሲሆን፣ በአለም የሙዚቃ መድረክ እጅግ ደምቆ የወጣው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ በበኩሉ፤ በአመቱ 92 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት የአለማችን ስድስተኛው ከፍተኛ ተከፋይ ሆኗል፡፡
ሙዚቀኞች፣ የፊልም ተዋንያን፣ ስፖርተኞች፣ ደራሲያንና በሌሎች መስኮች አለማቀፍ ዕውቅናን ያተረፉ ዝነኞች  በተካተቱበት በዘንድሮው የፎርብስ መጽሄት የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ 100 ዝነኞች ዝርዝር ውስጥ፣ 16 ሴቶች ብቻ እንደተካተቱ የጠቆመው ፎርብስ፤ ከፍተኛውን ገቢ ያገኘቺው ቢዮንሴ ኖውልስ መሆኗንም አመልክቷል፡፡
በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት የአመቱ የአለማችን ዝነኞች ባለፉት 12 ወራት ያፈሩት ሃብት በድምሩ ከግብር በፊት 5.15 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስም ፎርብስ አስታውቋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ሳኡዲን በመካከለኛው ምስራቅና በምዕራቡ አለም ሽብር ወንጅለዋል

    የኢራኑ የሃይማኖት መሪ አያቶላህ አሊ ሃሚኒ፤”አሸባሪውን ቡድን አይሲስን የፈጠረቺው አሜሪካ ናት፤ አይሲስንና ሌሎች አሸባሪዎችን እየተዋጋሁ ነው የምትለውም ውሸቷን ነው” ሲሉ መናገራቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
አሜሪካ አይሲስንና አሸባሪዎችን እየተዋጋሁ ነው በማለት የምታሰራጨው መረጃ ከእውነት የራቀ ነው ያሉት አያቶላህ አሊ ካሚኒ፤ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት አለመረጋጋት እንዲፈጠር አድርጋለች በማለትም አሜሪካን ወቅሰዋል፡፡
“የአሜሪካ መንግስት ኢራን ራሷን የቻለች አገር ሆና እንዳትቀጥል ይፈልጋል፤ በሁለቱ አገራት መካከል የተከሰቱት አብዛኞቹ ችግሮችም መፍትሄ የማይገኝላቸው ናቸው” ሲሉ ሰሞኑን ከኢራን ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ባደረጉት ስብሰባ መናገራቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
የኢራኑ የሃይማኖት መሪ አያቶላህ አሊ ሃሚኒ፤ አሜሪካና ወዳጇ የሆነቺው ሳኡዲ አረቢያ አይሲስን ጨምሮ በኢራን የሽብር ጥቃት በመፈጸም የሚታወቁ ሌሎች አሸባሪ ቡድኖችን በገንዘብ ይደግፋሉ ሲሉም ወቅሰዋል፡፡  በተያያዘ ዜና ደግሞ፣ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ ጃቫድ ዛሪፍ፤ ሳኡዲ አረቢያ በመካከለኛው ምስራቅና በምዕራቡ አለም እየተፈጸሙ ለሚገኙ የሽብር ጥቃቶች ድጋፍ ትሰጣለች በሚል መውቀሳቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። እ.ኤ.አ በ1979 የተከሰተውን የኢራን እስላማዊ አብዮት ተከትሎ፣ ሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ማቋረጣቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ፕሬዚዳንት ትራምፕም ስልጣን ከያዙ ጀምሮ ባሉት ጊዜያት የኦባማ አስተዳደር ከኢራን ጋር የተቋረጠውን ግንኙነት ለማደስ የጀመረውን እንቅስቃሴ እንደሚያቋርጡ በተደጋጋሚ ሲናገሩ መደመጣቸውን ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ በእስራኤል ባደረጉት ጉብኝት፣ “ኢራን ሽብርተኞችን በገንዘብና በስልጠና መደገፏን ልታቆም ይገባል” ሲሉ መናገራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ኤርትራና ጅቡቲ እነ ሳኡዲን መደገፋቸው ሳያስቆጣት አልቀረም ሞሮኮና ኢራን ለኳታር የምግብ እርዳታ ልከዋል

     ኤርትራና ጅቡቲ በመካከለኛው ምስራቅ በተቀሰቀሰውና ከሰሞኑ ተባብሶ አገራትን ለሁለት በከፈለው የኳታር ጉዳይ፣ ከሳኡዲ አረቢያና አጋሮቿ ጎን እንደሚቆሙ ማስታወቃቸውን ተከትሎ፣ ኳታር በሁለቱ አገራት መካከል ግጭት በፈጠረው አካባቢ አስፍራቸው የነበሩ የሰላም አስከባሪ ወታደሮቿን ማስወጣቷ ተዘግቧል፡፡
ኤርትራና ጅቡቲ ከሰሞኑ ባወጡት መግለጫ፤ ኳታርን የሽብርተኝነት አጋር በሚል ካገለሉት የእነ ሳኡዲ አረቢያ ቡድን ጎን እንደሚቆሙ በይፋ ማስታወቃቸው የኳታርን መንግስት ሳያስከፋው እንዳልቀረና አገራቱ በይገባኛል ሲጋጩበት ከነበረው የድንበር አካባቢ የሰላም አስከባሪ ወታደሮቹን ለማስወጣት እንደገፋፋው ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የኳታር መንግስት የሰላም አስከባሪ ወታደሮቹን ከአካባቢው ማስወጣቱን ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ ቢያስታውቅም፣ ውሳኔውን ለማስተላለፍ የገፋፋውን ምክንያትም ሆነ ያስወጣቸውን ወታደሮቹን ብዛት በተመለከተ ግልጽ መረጃ አለመስጠቱን ዘገባው ገልጧል፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 ኤርትራና ጅቡቲ በሚያዋስናቸው ድንበር ላይ በሚገኝ አንድ ስፍራ ላይ የይገባኛል ጥያቄ በማንሳት ግጭት ውስጥ መግባታቸውን ያስታወሰው ሮይተርስ፤ የድንበር ውዝግቡ ወደ ግጭት ማምራቱን ተከትሎ፣ ኳታር የሰላም አስከባሪ ወታደሮቿን በአካባቢው ማስፈሯን ገልጾ፣ አገራቱ በሰሞኑ ውዝግብ ከእነ ሳኡዲ ጎን መቆማቸው ኳታርን ለእዚህ ውሳኔ እንደገፋፋት ጠቁሟል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ሞሮኮና ኢራን ሽብርተኝነትንና አሸባሪ ቡድኖችን ትደግፋለች በሚል ከተለያዩ አገራት ውግዘት ወደገጠማትንና ከፍተኛ የምግብ እጥረት ወደሚያሰጋት ኳታር የምግብ እርዳታ መላካቸውን አስታውቀዋል፡፡ የሞሮኮ መንግስት ለኳታር የምግብ እህል በአውሮፕላን መላኩን ባለፈው ረቡዕ ያስታወቀ ሲሆን፣ ጉዳዩ ከሰብዓዊ ድጋፍ እንጂ ከፖለቲካ ጋር እንዳይገናኝብኝ ሲል የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አበክሮ ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡ ኢራንም በተመሳሳይ ሁኔታ በአራት የጭነት አውሮፕላኖች የምግብ እህል ወደ ኳታር መላኳን ያስታወቀች ሲሆን፣ በቀጣይም በየዕለቱ 100 ቶን ፍራፍሬና አትክልት ወደ ኳታር ለመላክ ማቀዷን ዘ ኢንዲፔንደንት ጠቁሟል፡፡
የኳታር የፋይናንስ ሚኒስትር ባለፈው ሰኞ በሰጡት መግለጫ፤ የአለማችን እጅግ ሃብታም አገር የሆነቺው ኳታር ከውግዘቱ ጋር ተያይዞ ሊገጥማት የሚችለውን ቀውስ በብቃት መቋቋም የሚያስችላት በቂ ሃብት አላት ሲሉ መናገራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
 ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ በኳታርና በጎረቤት አገራት መካከል የተፈጠረው ችግር፣ የየአገራቱ ዜጎች የሰብዓዊ መብቶች እንዲጣሱ በር የሚከፍት መሆኑን በመጠቆም፣ ሁሉም አገራት የዜጎችን መብት ላለመጣስ እንዲጥሩ፣ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነር፣ ዛኢድ ራድ አል ሁሴን ባለፈው ረቡዕ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስና ባህሬን፤ ለኳታር ያላቸውን ሃዘኔታ ገልጸዋል ባሏቸው ሰዎች ላይ “የእስርና የገንዘብ ቅጣት እንጥላለን” የሚል ዛቻ እየሰነዘሩ ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ይህም የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመሆኑ አገራቱ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

  ጊዜው ያለፈበት ክሎሪንና ፍሌቨር ለጁስ ምርት ይውላል 20 ዓመት ያለፋቸው የሳሙና ኬሚካሎች ተገኝተዋል
    ምርቶቹ የሚሸጡት ከመዲናዋ በራቁ አካባቢዎች ነው ሠራተኛን መስደብ፣ ማዋረድና ማሸማቀቅ የተለመደ ነው
           ከጋዜጣው ሪፖርተር

       በሰበታ ከተማ የሚገኘው ፓስፊክ ኢንዱስትሪ ኃ.የተ.የግል ማህበር፤ አቶ መፍቱህ አብዱልጋፋር በተባሉ ባለሀብት ባለቤትነት የሚመራ ፋብሪካ ነው። ፓስፊክ ኢንዱስትሪ፤ ሦስት የተለያዩ ምርቶችን እያመረተ ለገበያ ያቀርባል - ‹‹ማሩቲ፣ ዊኒስታርና ክላሲክ›› የተባለ የልብስ ሳሙና፣ ‹‹ፕሮሚስ›› የተባለ የታሸገ ውሃ እና “ማርች ኦሬንጅና ማርች ማንጎ” የተባሉ ጁሶች ናቸው። ምርቶቹ በሙሉ የሚሸጡት ግን ከአዲስ አበባ በራቁ ክልሎች መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡  
ከድርጅቱ በቅርቡ የተባረሩ ሠራተኞች ለአዲስ አድማስ በዝርዝር እንደገለጹት፤ ”ሦስቱም ምርቶች የሚሠሩት ጊዜያቸው ባለፈ (ኤክስፓየር ባደረገ) ጥሬ ዕቃ ነው፡፡ ስለዚህ በአዲስ አበባና አካባቢው ለገበያ አይቀርቡም፤ ራቅ ወዳሉ የክፍለ ሀገር ከተሞች ተወስደው ነው የሚሸጡት”
ሠራተኞች አይበረክትለትም እየተባለ በሚነገርለት ፓስፊክ ኢንዱስትሪ፤ ጊዜያቸው ያለፈባቸው ኬሚካሎችና ሌሎች ጥሬ ዕቃዎች ለምርት እንደሚውሉ በቅርቡ ከድርጅቱ የለቀቁና የተባረሩ ሰራተኞች አጋልጠዋል፡፡ በአንድ ጊዜ ስቶር ሱፐር ቫይዘርም፣ ካሸርም፣ ፐርሶኔልም፣ ነዳጅ ቀጂም ሆና ትሰራ እንደነበር የገለጸችው የቀድሞ ሠራተኛ፤ በተቀጠረች በአንድ ወር ከ15 ቀኗ መባረሯን ትናገራለች፡፡ በዚህች አጭር ቆይታዋ ግን ጊዜያቸው ያለፈባቸው ጥሬ እቃዎች በፋብሪካው ውስጥ መኖራቸውን ብቻ ሳይሆን ለጁስና ለታሸገ ውሃ ምርት ጥቅም ላይ ይውሉ እንደነበር ማረጋገጧን ጠቁማለች፡፡  
“እዚህ ግቢ ውስጥ የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈ (ኤክስፓየር ያደረገ) ክሎሪን አለ፡፡ መጋዘኑን የምናውቀው ሁለት ሰው ብቻ ነን፣ እኔና የሚደባልቀው (ሚክስ የሚያደርገው) ልጅ ብቻ። ለረዥም ጊዜ በመቆየቱ ጊዜው ያለፈበትን ይህን ክሎሪን፤ ለውሃም ለጁሱም ምርት ይጠቀሙበታል። አንድ ቀን ወደ ክሎሪኑ ጠጋ ስል ሽታው አልተመቸኝም፡፡ ልጁን፤ እስቲ ይህን ክሎሪን አውጣልኝና የመጠቀሚያ ጊዜውን ልየው አልኩት፤ አወጣልኝና አየሁት፡፡ በ2012 ኤክስፓየር ያደርጋል- ይላል፤ አሁን 2017 ነው፤ ኤክስፓየር ካደረገ 5 ዓመት አልፎታል ማለት ነው፡፡”
በዚሁ የመጠቀሚያ ጊዜው ባለፈበት ክሎሪን የተነሳም ከባለቤቱ ጋር ፍጥጫ ውስጥ እንደገባችና እውነቱን ፊት ለፊት እንደነገረቻቸው ይህችው የቀድሞ ሰራተኛ ለአዲስ አድማስ አስረድታለች - የተለወጠ ነገር ባይኖርም፡፡
“የፋብሪካው ሰራተኞች ውሃ ከሚመረትበት ክፍል መጥተው፤ ክሎሪን ስጪን አሉኝ፤ አልሰጥም አልኳቸው፡፡ ለባለቤቱ ነገሩት፤ ስልክ ደውሎ ጮኸብኝ፡፡ ‹‹ያለመስጠት የእኔ ኃላፊነት ነው፤ መጥተህ አነጋግረኝ›› አልኩት፤ መጣ ‹‹ይህን ውሃ‘ኮ የሚጠቀሙት ሕፃናት ሊሆኑ ይችላሉ፤ ምናልባትም ያንተም ልጆች ሊጠቀሙበት ይችሉ ይሆናል፤ ከ5 ዓመት በፊት ኤክስፓየር ያደረገ ክሎሪን እንዴት ትጠቀማለህ?!” አልኩት፤ ‹‹በቃ ነገ ወደ ታች ግቢ ይጫናል›› ብሎኝ ሄደ፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ ወር ቆይቼ ነው የወጣሁት፤ እስከዚያ ጊዜ ድረስ  ታች  ወደተባለው ግቢ አልተጫነም፤ አሁንም እየተጠቀሙበት ሊሆን ይችላል” ስትል ጥርጣሬዋንና ግምቷን ተንፍሳለች፡፡
“የዛገ ዕቃ፤ ለምግብ ቀርቶ ለመለዋወጫ መጠቀም ክልክል ነው፤ በዚህ ድርጅት ውስጥ የሚጠቀሙት መለዋወጫ በሙሉ የዛገ ነው፡፡” ያለችው የድርጅቱ የቀድሞ ሰራተኛ፤ በጁስ ምርት ውስጥ የሚጨመረው ፍሌቨርም ጊዜው ያለፈበት መሆኑን እንዴት እንደደረሰችበት ለአዲስ አድማስ ጠቁማለች፡፡
“ፍሌቨሩ ከየት አገር እንደሚመጣ በፍፁም አናውቅም፤ ፍሌቨሩን ሌሊት መጥቶ የሚጨምረው ራሱ ነው፤ ቀምማችሁ ጠብቁኝ የሚል ትዕዛዝ ይሰጣል፤ ተቀምሞ፣ ስኳር ተደርጎበት ይጠብቀዋል፤ ሌሊት መጥቶ ፍሌቨሩን ጨምሮ፣ ያመጣበትን መያዣ ዕቃ ይዞ ይሄዳል። ይህን የጁስ አሠራር ማንም ሠራተኛ እንዳያይ የተደረገበት ምሥጢር ምንድን ነው? አንድ ቀን በአጋጣሚ ፍሌቨሩ የመጣበትን ዕቃ አግኝቼ ሳይ፣ ፍሌቨሩ ራሱ ኤክስፓየር ያደረገ መሆኑን ተረዳሁ”  
የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበትን ክሎሪን ባጋለጠችበት ጊዜ፤ ም/ሥራ አስኪያጁ አቶ ሸረፋ ከማል ‹‹ይሄ አንቺን አይመለከትሽም፤ ከእሱ ጋር መጋፈጥ ማለት ከግድግዳ ጋር መጋጨት ነው›› ሲል ሊያስፈራራት እንደሞከረ አስታውሳ፤ እሷም በበኩሏ፤ ‹ይቅርታ አድርግልኝ! እኔ ፈሪ ትውልድ አይደለሁም›› በማለት እንደመለሰች ተናግራለች፡፡
ድርጅቱ በአጠቃላይ ከባድ ችግሮች አሉበት ያለችው ደግሞ የ”ፕሮሚስ ውሃ” የፋይናንስ ሰራተኛ በመሆን ለ10 ወራት ገደማ ከሰራች በኋላ፣ ባለቤቱና ም/ሥራ አስኪያጁ ከባድ ዕዳ ፈጥረው፣ በዋስትና ያስያዘችውን የአሮጊት እናቷን መኖርያ ቤት እንዳያሸጧት ፈርታ፣ ሥራዋን በገዛ ፍቃዷ የለቀቀችው የድርጅቱ የቀድሞ ሠራተኛ ናት፡፡ ድርጅቱ ለጁስና የታሸገ ውሃ ምርት የሚጠቀምባቸውን ጊዜ ያለፈባቸው ጥሬ ዕቃዎች በዝርዝር ታውቃለች፡፡ እንደውም በቆጠራ ወቅት የአገልግሎት ጊዜ ያለፈባቸው ፍሌቨሮችና ስታርቾች አግኝተው፣ ለአስተዳደሩ ሪፖርት ማድረጋቸውን ጠቁማለች፡፡   
“እኔ በዚያ ድርጅት የሠራሁት 10 ወር ያህል ነው፡፡ በመጨረሻ ልወጣ አካባቢ ንብረት ቆጠራ ገብቼ ነበር፡፡ እንዳየሁት ከሆነ፣ የሚመረተው ውሃም ሆነ ጁስ በትክክል ችግር አለበት፡፡ የንብረት ቆጠራውን ያደረግነው እኔና የአስተዳደር ሠራተኛው ነበርን፡፡ ለምሳሌ፣ የሳሙና ኬሚካል የሚቀመጥበት ክፍል ውስጥ 20 ዓመት ያለፋቸው ኬሚካሎች፣ ኤክስፓየር ያደረጉ 40 ጀሪካን የጁስ ፍሌቨርና ስታርቶች አግኝተናል፡፡ እኔና የአስተዳደር ሰራተኛው፤ ጊዜያቸው ያለፈባቸው ጥሬ ዕቃዎች በሙሉ መወገድ አለባቸው ብለን የጻፍነው ደብዳቤ በእጄ ይገኛል”
አዲስ አበባ አፍንጫ ስር በሰበታ ከተማ እንዲህ ያለ የህብረተሰቡን ጤና የሚጎዳ፣  የተቀነባበረ ሕገ-ወጥ ተግባር ሲፈፀም፣ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ተቆጣጣሪ አካላት እንዴት ሳይደርሱበት ቀሩ? ማሰኘቱ አይቀርም፡፡ ሠራተኞች እንደሚናገሩት፤ የመንግስት ተቆጣጣሪ አካላት በየጊዜው ይመጣሉ ግን እንዴት እንደሆነ አይታወቅም፤ ሰውየው ‹‹ውሃ አድርጎ” አሳምኖ ይመልሳቸዋል፡፡
በካሸርነትና በስቶር ሱፐርቫይዘርነት የሰራችው የቀድሞ የድርጅቱ ተቀጣሪ፤ ‹‹እሱ እጁ ረዥም ነው፤ በትክክለኛ መንገድ 300 ሺህ ብር ከሚከፍል በሕገ-ወጥ መንገድ 3 ሚሊዮን ብር ቢያወጣ ይቀለዋል›› ብላለች፡፡
በፋብሪካ የሚመረት የምግብ ሸቀጥ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፤ ነገር ግን ድርጅቱ ከእንደዚህ ዓይነቱ ሥልጣኔም ሆነ የሠራተኞች ደህንነት አጠባበቅ ጉዳዮች ጋር አይተዋወቅም ብላለች- የቀድሞ የድርጅቱ ሠራተኛ፡፡
“በዚህ ፋብሪካ የሚሠሩ ልጆች ጓንት አይጠቀሙም፤ አይሰጣቸውማ! በክሎሪንና በሶዳ ዕቃ ያጥባሉ፤ በዚያው እጃቸው ጁስ ምርት ውስጥ ይገባሉ፡፡ ክሎሪንና ሶዳው ወደፊት፣ በእጃቸው ላይ በሽታ ሊያስከትልባቸው ይችላል፡፡ የመቶ ብር ጓንት ገዝቶ ቢሰጣቸው ምን ችግር አለበት? የሚገርምህ ነገር እኔ ነኝ በመቶ ብር ጓንት ገዝቼ የሰጠኋቸው። ይህንን ያደረኩበት ምክንያት እህቶቼ ናቸው ብዬ ነው፤ ችግር ነው እዚያ ቦታ የጣላቸው”
“ላቦራቶሪውም ራሱ ብዙ ችግሮች አሉበት” ትላለች - ይህቺው ሠራተኛ፡፡ እዚያ የሚሠሩ ሠራተኞችም ችግሩን እንደሚያውቁት ትናገራለች።
“ነገር ግን እየፈሩ አይናገሩም፡፡ አንዳንዶቹ የቤተሰብ አስተዳዳሪዎች ናቸው፤ ሌሎች ደግሞ የዕለት ጉርስ ማግኛቸው ስለሆነ ‹‹ነገ ብባረርስ?›› በማለት ስህተቱን ለመናገር ይፈራሉ፡፡ ይህን ሕገ-ወጥ አሠራር፣ የሠራተኞችን ጭቆናና ግፍ፤ መንግሥት በጥንቃቄ ቢከታተለው በጣም ደስ ይለኛል፡፡” ስትል አስተያየቷን ሰንዝራለች፡፡
“እውነቴን ነው የምለው እዚያ ግቢ ስገባ ኢትዮጵያ ውስጥ ሳይሆን አረብ አገር ወይም ሌላ የባርነት ሥርዓት የተንሰራፋበት አገር ያለሁ ነው የሚመስለኝ፡፡ ሽንት ቤት እንድትሄድ አይፈቀድልህም፣ ስልክ ተደውሎልህ ማንሳት አትችልም፡፡ ጧት ገብተህ እንደተዘጋብህ ትውላለህ። ሁለተኛው ጓንታናሞ ያለው ፓሲፊክ ኢንዱስትሪ ግቢ ነው፡፡ አንድ ጸሐፊ አለች፤ የኩላሊት በሽተኛ ስለሆነች ሐኪሟ ብዙ ውሃ ጠጪ ብሏታል፡፡ ብዙ ውሃ ስለምትጠጣና ሽንቷ ቶሎ ቶሎ ስለሚመጣባት ሽንት ቤት ትመላለሳለች። ‹‹አንቺ ለሽንትሽ ጊዜ የለሽም እንዴ?›› ተብላለች። ይህን ያህል ሰብአዊ መብት የሚጣስበትና ሕግ የሌለበት ድርጅት ነው።” ብላለች - ሠራተኛዋ፡፡
ስድስት ወር ያገለገለው የድርጅቱ ሰራተኛ የተባረረበት ምክንያት ይገርማል፡፡ ‹‹የድርጅቱ ባለቤት፣ ሥራ አስኪያጅ፣ አስተዳደር… ሁሉም ነገር ባለቤቱ ራሱ ነው›› ይላል - ሠራተኛው፡፡
‹‹ድርጅቱ ከፍተኛ ግብር ከፋይ ነው፡፡ በሥራዬ አጋጣሚ 224 ሺህ ብር ዕዳ አለባችሁ›› የሚል ደብዳቤ  ደረሰኝና ያንን ደብዳቤ ለባለቤቱ ሰጠሁ። ባለቤቱም “አንተን እዚህ ውስጥ ምን አገባህ? ለምንድነው ያመጣኻው?” በማለት ፀብ ተፈጠረ፡፡ የሰራሁበትን ደሞዝና አበል ሳይከፍለኝ ውጣ ብሎ ሰድቦ አባረረኝ›› ብሏል፡፡
ይኸው ሠራተኛ፤ ሌሎች ውሃ አምራች ድርጅቶች በቲቪ፣ በሬዲዮና በጋዜጣ ሲያስተዋውቁ አይቶ ‹‹እኛስ ፕሮሚስን ለምን አናስተዋውቅም?›› የሚል ሃሳብ ያቀርባል፡፡ ባለቤቱ ‹‹ዝም ብለህ ተቀመጥ፤ ይኼ አይሠራም፤ የማያገባህ ነገር ውስጥ አትግባ›› በማለት እንዳሸማቀቁት ተናግሯል፡፡  
የድርጅቱ ሌላው ችግር፣ ሠራተኛ ሲቀጥር ውል አይዋዋልም፡፡ ይሄ ደግሞ ሠራተኞች መብታቸውን እንዳይጠይቁ፣ የሰብአዊ መብት ረገጣ እንዲደርስባቸው እንዳደረጋቸው ተናግረዋል - የድርጅቱ ሠራተኞች፡፡ በሆነው ባልሆነው የሰራተኛውን ክብር አዋርዶ ከሥራ ማባረር፣ ደሞዝ መቆራረጥና ከእነአካቴው መከልከልም ለፓስፊክ ኢንዱስትሪ በጣም የተለመደ ተግባር መሆኑን ሠራተኞች ጠቁመዋል፡፡   
“ውል ስንጠይቅ፤ እኛ ሥራችሁ ላይ ገደብ (ሊሚት) እንዲኖርባችሁ አንፈልግም፤ ይላሉ። ነገር ግን እነሱ በፈለጉት ጊዜ ተነስተው፤ ‹‹ሥራህን ልቀቅ፣ ተባረሃል›› እያሉ ለአንዳንዶች ደብዳቤ ይሰጣሉ፡፡ ብዙዎች ግን ‹‹ዓይንህን እንዳላየው፤ ከነገ ጀምሮ እዚህ ግቢ እንዳትመጣ፤ ምንም መሥራት አትችልም አቅም የለህም፣…›› በማለት ባለቤቱ ሠራተኛውን አዋርዶ ያባርራል። አንድ ሠራተኛ 30 ቀን ሰርቶ ደሞዝ ሲወጣ ቀርቶ፣ በሁለተኛው ቀን ቢመጣ፣ ወር ሙሉ የሠራበት ደሞዙ አይከፈለውም፡፡ ‹‹ደሞዛቸው እንዳይከፈል››፣ “የዚህ ቀን ደሞዛቸው ይቆረጥ” የሚል የመከልከያ ደብዳቤ ለፋይናንስ ይጻፋል፤ በዚህ ዓይነት ደሞዛቸው ሳይከፈል ተመላሽ የሆነባቸው ብዙ ሠራተኞች አሉ”
የክፍለ ሀገር የሳሙና ሽያጭ ሠራተኛው ደግሞ 8 ወር ሰርቶ መባረሩን ተናግሯል፡፡ ‹‹ሰራተኛ ሲባረር ቀርቶ ሲቀጠርም ደብዳቤ አይሰጠውም። ‹አንተ ሌባ ነህ፤ ግቢዬን ለቀህ ውጣልኝ› ነው የሚባለው። የዚህ ዓይነት ስድብና አባባል በተደጋጋሚ ስሰማ ቆይቼ በመጨረሻም በእኔ ላይ ደረሰ፤ ሠራተኛ በግፍ የሚባረርበት መ/ቤት ፓሲፊክ ኢንዱስት ነው›› ብሏል፡፡
“አንድ ሰራተኛ በድርጅቱ ቆየ ቢባል 3 ወር ነው። እኔ 8 ወር ሰርቼ ነው የወጣሁት፤ የሚያውቁኝ ጓደኞቼ ይህን ያህል መቆየቴን ሲሰሙ ይገረማሉ። የባለቤቱ ሰላይ (ጆሮ ጠቢ ነህ) የሚሉኝም አሉ። እኔ የምሸጠው ሳሙና ማሩቲ ክላሲክ ይባላል። ሳሙናው ገበያ ላይ ካሉትና በትልቅነቱ ምርጥ ከሚባሉት አንዱ ነው። ዋጋውም በጣም ርካሽ ነው፡፡ ስለዚህ ገበያውም ውስጥ ገብቷል፡፡ የሚሸጠው ደግሞ ከአዲስ አበባ  ርቀው በሚገኙት  እንደ ሻሸመኔ፣ ዲላ፣ ይርጋጨፌ፣ ጂማ፣ አጋሮ፣ ጌራ፣… በተባሉ ራቅ ራቅ ባሉ የገክልል ከተሞች ነው፡፡ ነጋዴዎቹን ‹‹ይህ ሳሙና ተወዳጅ የሆነው ለምንድነው?›› በማለት ጠይቄአቸው ነበር፡፡ የሰጡኝ መልስ፤ የኅብረተሰቡ የኢኮኖሚ አቅም ዝቅተኛ ስለሆነ ዋጋው ረከስ ያለ ምርት ስለሚመርጡ ነው እንጂ የጥራት ደረጃው ዝቅተኛ እንደሆነ እናውቃለን፤ ብለውኛል፡፡ እኔም አገልግሎት ጊዜው ባለፈ ጥሬ ዕቃ ስለሚሰራ ጥራቱን የጠበቀ እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡” ብሏል የቀድሞው የሽያጭ ሠራተኛ፡፡
የፓሲፊክ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ መፍቱህ አብዱልጋፋር በበኩላቸው፤ ድርጅቱ የአገልግሎት ጊዜው ባለፈበት ጥሬ ዕቃ ይጠቀማል የሚለውን የሠራተኞች ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ ‹‹ይኼ‘ኮ የሀገር ሀብት ነው፤ ለ30 ዓመት የሰራ ፋብሪካ እንዴት እንዲህ ያደርጋል? በፍፁም ከእውነት የራቀ ነው››
የድርጅቱ ሠራተኞች ተፈፅሞብናል የሚሉትን በደል በተመለከተም ተጠይቀው ሲመልሱ፤ ‹‹ሰራተኛው ላይም ምንም በደል አይፈጸምም፤ ሰራተኛ ሲያጠፋ ከመቶ አንድ ሊኖር ይችላል እንጂ በማንም ላብ ላይ በደል አይፈጸምም፡፡ ደሞዙን ከአንድ ዳቦ ወደ ሁለት ዳቦ ለማሳደግ ከመጣር በስተቀር በሰራተኛው ላይ የሚደረግ ጭቆና የለም›› ብለዋል፡፡  

 ከአንድ አመት በፊት በቀዳማዊት እመቤት ሮማን ተስፋዬ፤ የመሰረት ድንጋይ የተቀመጠለትና በቅርቡ ግንባታው የተጠናቀቀው ‹‹ግሪን ላይት አውቶሜካኒክ” የስልጠና ማዕከል ረቡዕ ረፋድ ላይ በይፋ ተመረቀ፡፡ በኪያ ሞተርስና በኮሪያን ኢንተርናሽናል ኮኦፕሬቲቭ ኤጀንሲ (KOICA) ወጪው ተሸፍኖ፣ በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የተገነባው ይሄው ማዕከል፤ ባለ 4 ወለል ህንፃ ሲሆን ኢትዮጵያዊያንን ወጣቶች በአውቶሜካኒክ ስልጠና ወስደው ባለሙያ የሚሆኑበት ነው ተብሏል፡፡
ህንፃው ለአውቶ ሜካኔክና ለእጅ ስራ ሙያ ስልጠና የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችን ያሟላ ሲሆን በቀጣይም በተጨማሪ ቁሳቁሶች ተደራጅቶ በአጠቃላይ ለ615 ወጣት ወንዶችና ሴቶች ስልጠና ይዘጋጃል ተብሏል፡፡ በቀጣዩ ግንቦት ስልጠና መስጠት ይጀምራል የተባለው ማዕከሉ፤ የህንፃውን ግንባታ ጨምሮ ለአምስት ዓመት የሚቆይ ፕሮጀክት ሲሆን 220 ወጣቶችን በአውቶ ሜካኒክ፣ 395ቱን ደግሞ በእጅ ስራ ሙያ አሰልጥኖ፣ ራሳቸውን እንዲችሉ የማድረግ እቅድ ይዟል፡፡ ማዕከሉ የራሱ የአስተዳደር ቁመናና ስርዓተ ትምህርት እየተቀረፀለት እንደሆነም ተገልጿል፡፡
ስድስት የመማሪያ ክፍሎች፣ ሶስት ወርክሾፖች፣ አምስት ቢሮዎች፣ አምስት የእቃ ማከማቻ ክፍሎች፣ ሁለት የመምህራን ቢሮዎች፣ አንድ የICT ክፍል፣ አንድ ቤተ መፅሀፍት፣ አንድ ጋራዥና አንድ ላውንጅ አሟልቶ የያዘም ነው ተብሏል ህንፃው፡፡ በዚህ ማዕከል በአውቶ ሞቲቭ ኢንጂን በሌቭል 1 እና በሌቭል 2 በፓወር ትሬይንም እንዲሁ በሌቭል 1እና ሁለት ስልጠና የሚሰጠው ማዕከሉ በቀጣዩ ግንቦት በሁለት ዙር ስልጠና ለመስጠት ሰልጣኞችን መመዝገቡን አስታውቋል፡፡
በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የወርልድ ቪዥን ካንትሪ ዳይሬክተር ኤድዋርድ ብራውን ባደረጉት ንግግር፤ “ካንትሪ ዳይሬክተር ሆኜ ከተሾምኩ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የጎበኘሁት ትልቅ ፕሮጀክት በመሆኑ ለእኔ ትልቅ በዓል ነው” ብለዋል። ሌላው በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ በእንግድነት የተገኙት የአዲስ አበባ ቴክኒክ፣ ሙያና ትምህርት ስልጠና ኤጀንሲ ዳይሬክተር አቶ ዘሩ ስሙር፤ ኮሪያና ኢትዮጵያ ባላቸው ታሪካዊ ግንኙነት በእጅጉ ኢትዮጵያን እየደገፉ መሆኑን ጠቁመው መንግስት በቴክኒክና ስልጠና በርካቶችን ተጠቃሚ እያደረገ ቢሆንም ሁሉንም ስለማያዳርስ እንዲህ አይነት ድርጅቶች የሚያደርጉት ድጋፍ ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ የኮሪያ አምባሳደር በኢትዮጵያ ሚስተር ሙን ሁዋን ኪም ኢትዮጵያ ለኮሪያ ባለውለታ በመሆኗ ይህን ውለታ ለመመለስ ብዙ ምክንያቶችን እንፈልጋለን፤ ይሄም ፕሮጀክት ውለታ ለመመለስ አንዱ መንገድ ነው ብለዋል፡፡ ማዕከሉ ለሚያከናውነው የ5 ዓመት ፕሮጀክት፤ የ2.5 ሚ ዶላር (57.8) በጀት ተይዞለታል ተብሏል፡፡

 አዲስ አልበሙን አስተዋወቀ

     በኢትዮጵያ ሙዚቃ ወርቃማ ዘመን ለ25 ዓመታት በልዩ ብቃት ዘመን ተሻጋሪ የሙዚቃ ስራዎችን ለአድማጮች ያቀረበው ከያኒ ግርማ በየነ ባለፈው ማክሰኞ በብሔራዊ ቴአትር ከ ‹‹አካሌ ውቤ›› ባንድ ጋር ያቀረበው ኮንሰርት አስደሳችና አዝናኝ እንደነበር ታዳሚያን ገለፁ፡፡ ድምፃዊ፣ የሙዚቃ ቀማሪና አቀናባሪ እንዲሁም የፒያኖ ተጫዋች የሆነውና ለረጅም አመታት በአሜሪካ በስደት የቆየው አንጋፋው ከያኒ፤ ከሙዚቃው ተራርቆ የከረመ ሲሆን ወደ ሙዚቃው የተመለሰው ከሁለት ዓመት ወዲህ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በታዋቂው የሙዚቃ ሰው ፍራንሲስ ፋልሴቶ አነሳሽነት በግንቦት 2016 ፓሪስ በሚገኘው ‹‹ላ ኤሪ ቴጅ›› የተባለ ስቱዲዮ ግርማ በየነ ‹‹አካሌ ውቤ›› ከተሰኘው የኢትዮ ጃዝ ሙዚቃ ቡድን ጋር ‹‹ኢትዮፒክስ 30 ሚስቴክስ ኦን ፐርፐዝ›› የተሰኘውንና 14 ዘፈኖችን ያካተተው አልበሙን ያሳተመ ሲሆን፣ ባለፈው ማክሰኞ ያቀረበው ኮንሰርትም ይህንኑ አልበም ለማስተዋወቅ ያለመ እንደነበር ታውቋል፡፡ ለአርቲስቱ የመጀመሪያው ሙሉ አልበሙ ነው ተብሏል፡፡ ግርማ አልበሙን ለማስተዋወቅ ባዘጋጀው ኮንሰርት፤ ከ‹‹አካሌ ውቤ›› ባንድ ጋር አስደናቂ ትርኢት ያሳዩ ሲሆን በተለይ ግርማ በድምፅ ብቻ ሳይሆን በፒያኖ ችሎታውም ብዙዎችን አስደንቋል፡፡ አርቲስቱ በ1960ዎቹ፣ ከ60 በላይ የሙዚቃ ቅንብሮችን የሰራ ሲሆን ግሩም የግጥምና ዜማ ደራሲም ጭምር እንደነበር ይነገርለታል፡፡ በብሔራዊ ትያትር ቤት ባቀረበው ኮንሰርት ‹‹እንከን የሌለሽ››፣ ‹‹ካንቺ ወዲያ ሴት አላምንም››፣ ‹‹ፍቅር እንደክራር››፣ ‹‹ፅጌረዳ››፣ ‹‹መስሎን ነበር››፣ ‹‹ሙዚቃዊ ስልት›› የተሰኙትን ጨምሮ በርካታ ስራዎቹን በመጫወት አድናቆት የተቸረው ሲሆን ‹‹የድምፁ አለማርጀት›› ለብዙዎች መነጋገሪያ ሆኖ አምሽቷል፡፡ በኮንሰርቱ ላይ ስለፍቅር አብዝቶ የሰበከው ድምፃዊው፤ ከኢትዮጵያ ሴት ድምፃዊያን ሄለን በርኼ በተለይ ‹‹አታስፈራራኝ›› ለሚለው ዘፈኗ ያለውን አድናቆት በአደባባይ ገልጿል፡፡
ግርማ በየነ ከዚህ ቀደም ‹‹ዘራፍ››፣ ‹‹ጋይድ ቱ ሚዩዚክ ኦፍ ኢትዮጵያ››፣ እ.ኤ.አ በ2004 ‹‹በወርልድ ሚዩዚክ ጌት ወርክ›› አሳታሚነት ‹‹ኢትዮፒክስ ቁጥር 8››፣ ‹‹ስዊን ጊንግ አዲስ››፣ በቡዳ ሚዩዚክ አሳታሚነት ደግሞ ‹‹ኢትዮፒክስ 22›› በተሰኙ አልበሞች ላይ ተሳትፏል፡፡ አርቲስት ግርማን ያጀበው ‹‹አካሌ ውቤ›› የኢትዮ ጃዝ ሙዚቃ ቡድን፤ በፈረንሳይ ሙዚቀኞች የተደራጀ ሲሆን ከ74 በላይ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በዓለም ዙሪያ ማቅረቡ ታውቋል፡፡ ከወራት በፊትም በፈረንሣይ ከታዋቂው የፒያኖ ተጫዋች ሀይሉ መርጊያ ጋር በ ‹‹ስቱዲዩ ዴላ ኤል ሚቴጅ›› ታላቅ የሙዚቃ ዝግጅት ማቅረባቸው ተጠቁሟል፡፡

 እኻ ቲያፈኳን ኧኳዳር አት ኧደንግር ባነ ባረም) የቤተ ጉራጌ ተረት
ከኤዞፕ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይለናል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ሰው ክፉኛ ይታመምና ቤቱ ይተኛል፡፡ የመንደሩ ሰው ሁሉ የሚበላም የሚጠጣም እያመጣ በየተራ ይጠይቀዋል፡፡
“አቶ እገሌ” ይላል ጠያቂ
“አቤት” ይላል ተጠያቂ
“ዛሬስ እንዴት ነህ?”
“ከትላንቱ ይሻለኛል”
“ሐኪም ዘንድ ሄደህ ነበር?”
“አልሄድኩም”
“ታዲያ ከትላንቱ እንደተሻለህ በምን አወቅህ?”
“የታመምኩት እኔ አይደለሁ፡፡ ሰውነቴ ይነገርኛልኮ”
“ደህና እንኳን ለዚህ አበቃህ!”
ጠያቂዎቹ ተሽሎታል ብለው ሰውየውን ለመጠየቅ መምጣታቸውን ያቆማሉ፡፡ ሰውዬው ግን ካልጋው አልተነሳም፡፡ “እስቲ እንሂድና እንየው፡፡ ይሄ ሰው ለምን አልተነሳም” ብለው ቤቱ ቢሄዱ እዚያው እንደተኛ አገኙት፡፡
“አያ እገሌ” ይላል ጠያቂ
“አቤት” ይላል ተጠያቂ
“ዛሬስ እንዴት ነህ፡፡ እኛ’ኮ ተሽሎኛል ስትል፣ ትነሳለህ ብለን ነው የቀረነው፡፡ ዛሬ እንዴት ነህ?”
“ከትላንቱ ይሻለኛል”
“ባለፈውም ዛሬ እንዴት ነህ ስንልህ ከትላንቱ ይሻለኛል ብለኸን ነበር፡፡ እንዴት ነው ነገሩ?”
“እዚህ አገር ከትላንቱ ይሻለኛል የማይል ማን አለ?”
“እንደዚህ ከሆነ ሐኪም ቢያይህ ነው የሚሻለው” ብለው ሐኪም ይጠሩለታል፡፡ መድኃኒት አዞለት ይሄዳል፡፡ መድኃኒቱን ይወስዳል፡፡
በነጋታው ሐኪሙ ይመጣል፡፡
ሐኪሙ - “እንዴት ነህ?” ይለዋል፡፡
በሽተኛው - “ደህና ነኝ ዶክተር፡፡ ግን በጣም ያልበኛል”
ሐኪሙ - “ይሄ በጣም ጥሩ ምልክት ነው” ይለውና ይሄዳል፡፡
በሚቀጥለው ሐኪሙ ይመጣል፡፡
“እህስ አሁንስ እንዴት ነህ?” ይለዋል፡፡
በሽተኛው - “ተሽሎኛል፡፡ ግን እዚህ መገጣጠሚያዬ ላይ ይቆረጥመኛል፡፡ ያንቀጠቅጠኛል፡፡ ከዚያ ሰውነቴ በሙሉ በረዶ ይሆናል፡፡”
ሐኪሙ - “ይሄም በጣም ጥሩ ምልክት ነው” ብሎት ይሄዳል፡፡
ሐኪሙ ሌላ ቀን ይመጣል፡፡
“እህ ዛሬስ እንዴት ነህ?” ይለዋል በሽተኛውን
በሽተኛው - “ደህና ነኝ ግን አሁን ደግሞ ኃይለኛ ትኩሳት ለቆብኛል” ብሎ ይመልሳል፡፡
ሐኪሙም - “ኦ ይሄም በጣም ጥሩ ምልክት ነው፡፡ በጣም እየተሻለህ ነው ማለት ነው” ብሎት ይሄዳል፡፡
ከሠፈሩ ሰው አንዱና ወዳጁ የሆነው ሰው ከህክምናው በኋላ ምን ለውጥ እንዳመጣ ሊጠይቀው ይመጣል፡፡
ጠያቂ - “እሺ አያ እገሌ፡፡ ሐኪሙ ካየህ በኋላ እንዴት ሆንክ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
በሽተኛውም - “ወዳጄ አያድርስብህ፡፡ “በጣም ጥሩ ምልክት” ሊገለኝ ነው!”
***
እየተሻለኝ ነው እያለ ከሚሞት፣ “በጣም ጥሩ ምልክት ነው” እያለ ከሚገድል ይሰውረን፡፡ ‹‹ደግ ደጉን ማውራት የተሻለ ዓለም ለማየት ይጠቅማል›› የሚለው ብሂል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ እየከፋ ያለን ጉዳይ እየተሻሻለ ነው ማለት ግን እያወቁ ማለቅ ዓይነት ነው፡፡ ‹‹ዕውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር ››ለአገርና ህዝብ ይበጃል እንጂ ጐጂ አይደም፡፡ “የማይሰጋ ተስፋ የሌለው ሰው ነው” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ “አይመጣምን ትተሽ ይመጣልን ጨምሪበት” የሚሉት ነው አበሾች፡፡ በየኑሮ መስኩ ያለውን ህመም፣ በየሙያ መስኩ ያለውን ተወሳክ፣ በየፖለቲካ መስኩ ያለውን ወረርሽኝ በጊዜ መመርመር ዋና ነገር ነው፡፡ እኛ የወደድነውን እያጐላን በየሚዲያው ብንለፍፍ ለሀገርና ለህዝብ ፋይዳ ያለው ላይሆን ይችላል፡፡
አንድ ፀሐፊ ስለጋዜጠኝነት ሲጽፍ “ዋናው የሙያው ቁልፍ - ነገር…
አስፈላጊውን ነገር ተወዳጅ እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡ እኛ ግን የወደድነውን፤ አስፈላጊ ፋይዳ እንዲኖረው የማድረግ አደገኛ ተግባር ላይ ነን (Make the important interesting but we are in a danger of making the interesting important) ያለውን በፖለቲካም፣ በኢኮኖሚም፣ በማህበራዊ ዘርፍም መንዝረን ብናየው ይጠቅመናል፡፡
ዕውነትን መናገር በሽታን ከመደበቅ ያድናል፡፡ ሳይሻለን ተሻለን፣ ሳንድን ድነናል ከማለት ያድነናል፡፡ ከትላንት የተማርን ከማስመሰል ያወጣናል፡፡ ሰፈር - ሙሉ ሰው ከማሳሳት ያተርፈናል፡፡
በየዘመኑ ነባራዊ ዕውነታን ለራስ በሚያመች መልኩ በመቅረጽ ‹ዕውነቱ ይሄ ነው› እያሉ ለማሳመን መጣር የተለመደ ዘዴ ነው፡፡ ላንዳንዶች የአገዛዝ መላ ነው፡፡ ላንዳንዶች ከጣር ማምለጫ ነው፡፡ ኒክ ዴቪስ የተባለው ፀሐፊ ዕውነት እንዳንናገር የሚያደርጉን ሦስቱ ገዳይ ድክመቶች (1) የምንመርጣቸው ርዕሰ ጉዳዮች ዕውነታውን በመሠረታዊ መንገድ የሚያፋልሱት እንዲሆኑ በማድረግ ዋናውን ጭብጥ ማሳት፤
2) በተደጋጋሚ የምንጠቀምባቸውን ኢተአማኒ፣ አንዳንዴም ፈጽሞ ውሸት፣ የሆኑ ጭብጦች ደጋግመን በመጠቀም ዕውነተኛ ማስረጃዎች እንዲመስሉ ማድረግ፤
3) ከአካባቢው ህብረተሰብ መካከል ኃይለኛ ጉልበት ያላቸውን ወገኖች የሚያደምቁ ዕሴቶችን የማያቋርጥ አሻራ እንዲኖራቸው ፖለቲካዊና ሞራላዊ ውትወታን ማብዛት፤
ናቸው፤ ይለናል፡፡
ስለ ዛሬ ጤንነታችን ስንጠየቅ፣ ስለትናንት በሽታ ብናወራ የምናገኘው ጠቀሜታ ራስ ተኮር እርካታ ካልሆነ በቀር፣ ደርዝ ያለው ነገር አገር አንጀት ላይ ጠብ አያደርግም፡፡
ራሳችንን ከዛሬ ሥራችን፣ ከዛሬ ትልማችን፣ ከዛሬ ዕውቀታችን፣ ከዛሬ ውጤታችን ጋር እናመዛዝን፡፡ ህዝብ እየወደደኝ ነው እየሸሸኝ፣ እየሰለቸኝ ነው እየረካብኝ፣ የተናገርኩት እንደ ‹‹ቡመራንግ›› ተመልሶ እኔኑ እየወጋኝ ነውን? ዕውነተኛ ደጋፊ እያፈራሁ ነውን? ዕውነተኛ ተቃዋሚ አለኝ?
ኢንፎርሜሽን የሥልጣኔ መሠረት የሆነበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ኢንፎርሜሽን የሚደብቅ በሽታውን ከደበቀው ሰው አይለይም፡፡
ሌላው ዓለም ዛሬ፤ የህዝብ ግንኙነት ሠራተኞች የዜና ምንጭ ሊሆኑ እንደማይችሉ፣ የመረጃ ፍሰትን እንደሚያደናቅፉ እየተሟገተ መሆኑን አንርሳ፡፡
“የህዝብ ግንኙነት ዲሞክራሲ” (ኤሮን ዴቪስ) በተባለው መጽሐፍ ከጥናት የተገኙ ድምዳሜዎችን እንዲህ ያስቀምጣቸዋል:- “ለሚዲያ ከሚሰጡ መረጃዎች ተለይቶ የሚደበቅ አንድ መረጃ ሁሌ ይኖራል፡፡ በብዙ ድርጅቶች ውስጥ ያሉት የህዝብ ግንኙነት ሠራተኞች ግማሹ ወይም አብዛኛው ሥራቸው፤ ጋዜጠኞች መረጃ እንዳያገኙ ማድረግ ነው፡፡ አንዳንዴም ያለውን እንደሌለ ማድረግ፣ ስለ ድርጅቱ ክፉ ክፉ ወሬ ካለ ጨርሶ መደምሰስ (መሸምጠጥ) ነው ሥራቸው፡፡” ቢሮዎች፣ የቢሮ መሪዎችና ሠራተኞች፤ የፖለቲካ ሰዎች፤ ለኢንፎርሜሽን፣ ኢንፎርሜሽን ቢሉም ለዕውነተኛ ኢንፎርሚሽን፤ በራቸው ክፍት ሊሆን ይገባል፡፡ ልባቸውም እንደዚያው፡፡
ቼስተርተን የተባለው ፀሐፊ ያለውን ነገር ከልባችን ባናወጣው መልካም ነው፡፡
“እራት ላይ የሚቀርብ ሙዚቃ፤ ምግብ አብሳዩንም፣ ሙዚቀኛውንም እንደመስደብ ነው፡፡”
ባንድ ጊዜ ሁለት ተበዳይ ከሚኖርበት ሥርዓት ይሰውረን፡፡ ያም ምግቡ ሳይጣጣምለት፣ ያም ሙዚቃው ሳይሰማለት፣ መቅረቱ የሙያ ብክነት ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን፤ ከምግቡም ከጥበቡም ያልሆነው የግብር ታዳሚ ህዝብ ያሳዝናል፡፡ ይህንን ልብ ያላለ ታዳሚ ሁለተዜ ጥፋት ላይ ወደቀ ማለት ነው፡፡ ሙዚቀኛ ሳይሰማ እየተሰማሁ ነው ካለ፣ ምግብ አብሳዩ ህዝቡ እየበላ ነው ካለ፣ ታዳሚው ሙዚቃ እየሰማሁ፣ ምግብ እየበላሁ ካለ ተያይዘው ጠፍተዋል፡፡ እየታመመ ተሻለኝ፣ እየተቸገረ ኖርኩኝ የሚል “ሸማኔ ውሃ ሙላት ሲወስደው እስካሁን አንድ እወረውር ነበር አለ” እንደተባለው መሆኑ ነው፡፡ ከ20ኛ ፎቅ ላይ እየወደቀ ሳለ 8ኛ ፎቅ ያሉ ሰዎች እንዴት ነህ? ቢሉት፤ “እስካሁን ደህና ነኝ” አለ እንደተባለው ሩሲያዊ ብናስበውም ያስኬደናል፡፡ “እንዳካሄድ” አደል መንገዱ ሁሉ!

 “ህጋዊዎቹ ባልተለዩበት የሚደረግ ድርድር የህገ መንግስት ጥሠት ያስከትላል”

      የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ህጋዊ መሰፈርት አሟልተው እየተንቀሣቀሱ ነው ያላቸውን 5 ሃገር አቀፍ ፓርቲዎች ማንነት በዝርዝር እንዲያሣውቅ መኢአድ እና ሠማያዊ በደብዳቤ ጠይቀዋል፡፡
ቦርዱ ግንቦት 17 ቀን 2009 ዓ.ም ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ባቀረበው ሪፖርቱ፤ በሃገር አቀፍ ደረጃ ከሚንቀሳቀሱ 22 ፓርቲዎችና በክልል ከሚንቀሳቀሱ 40 ፓርቲዎች መካከል በተሻሻለው የፖለቲካ ፓርቲዎች አዋጅ መሠረት፤ ህጋዊ መስፈርት ያሟሉት 5 ሃገር አቀፍና 5 ክልላዊ ፓርቲዎች ብቻ መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡
ሆኖም ቦርዱ የትኞቹ ፓርቲዎች ህጋዊነቱን እንዳሟሉና እንዳላሟሉ በዝርዝር የገለፀው ነገር የለም፡፡
ይሄን ተከትሎ ሠማያዊ እና መኢአድ፤ የትኞቹ ፓርቲዎች ህጋዊ እንደሆኑ አለማሣወቁ በወደፊት እንቅስቃሴያችን ላይ አሣሣቢ ችግር ይፈጥርብናል” በሚል ቦርዱ ማብራሪያ እንዲሠጣቸው የጠየቀ ሲሆን፤ ህጋዊዎቹ ህጋዊ ካልሆኑት ሣይለዩ ከገዥ ፓርቲ ጋር የሚደረገው ድርድርም ትርጉም እንደሌለው መኢአድ ለአደራዳሪ ቦርድ ፅ/ቤትና ለምርጫ ቦርድ በላከው ደብዳቤ አስታውቋል፡፡
“ህጋዊ መስፈርት አሟልተው ካልተገኙ ፓርቲዎች ጋር ለድርድር መቀመጥ የህገ መንግስት ጥሠት የሚያስከትልና የህዝብን ጥያቄ የሚያዳፍን በመሆኑ በአፋጣኝ ምርጫ ቦርድ ማብሪያ እንዲሠጥበት መኢአድ በደብዳቤው ጠይቋል፡፡
ማብራሪያው ባልተሠጠበትና ህጋዊች ተለይተው ባልተገለፁበት ሁኔታ ድርድሩን ማካሄድ እንደማይቻልም መኢአድ አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሠጥ ላለፉት ሁለት ሣምንታት ያደረግነው ተደጋጋሚ ጥረት ሊሳካልን አልቻለም፡፡

 1700 ስደተኞች በ20 ዩኒቨርሲቲዎች በነፃ እየተማሩ ነው

     ከ850 ሺህ በላይ የተለያዩ ሀገራት ስደተኞችን ማስተናገዷ ያስመሰገናት ኢትዮጵያ፤ የዘንድሮውን የዓለም የስደተኞች ቀን በዓል የተመድ የስደተኞች ኮሚሽነር በተገኙበት የፊታችን ማክሰኞ በጋምቤላ ታስተናግዳለች ተብሏል፡፡ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ስደተኛ በማስተናገድ ከአፍሪካ ቀዳሚ የሆነችው ኢትዮጵያ፤ በስድስት የሀገሪቱ ክልሎች 27 የስደተኛ መጠለያዎችን አቋቁማ ማስተናገዷ እውቅና ተሰቶት “we
stand together with refugees” በሚል መሪ ቃል የሚከበረውን በዓል እንድታስተናግድ እድል ማግኘቷን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጿል፡፡
“ስደተኞች እንደሀገሬው ዜጎች የሚኖሩባት ሀገር ነች ኢትዮጵያ” ያለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤ በ20 ዩኒቨርሲቲዎች ለ1700 ስደተኞች ነፃ የትምህርት እድል ተሰጥቷቸው በመማር ላይ መሆናቸውንም አስታውቋል፡፡ ኢትዮጵያ በአሉን እንድታዘጋጅ የተመረጠችው በአለም አቀፍ ደረጃ ከስደት ጋር ተያይዘው እየተከሰቱ ባሉ ችግሮች መፍትሄ ዙሪያ ኃላፊነት በመሸከም ችግሩን ለማጋራት ባሳየችው ቁርጠኝነት ነው ተብሏል፡፡

     5G የቴሌኮም አገልግሎት አቀርባለሁ ብሏል

      የቻይናው የቴሌኮም ኩባንያ ዜድቲኢ በኢትዮጵያ፤ የቴሌኮም ምርምርና ፈጠራ ማዕከል ለማቋቋም የሚያስችለውን ስምምነት ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር መፈራረሙን አስታወቀ። በኢትዮጵያም ሆነ በአፍሪካ የመጀመሪያው ነው የተባለው የቴሌኮም ቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከሉ፤ አዳዲስ የቴሌኮሚኒኬሽንና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አማራጮችን እዚሁ ሀገር ቤት በመፍጠር ለተጠቃሚዎች ያቀርባል ተብሏል፡፡
የምርምርና ፈጠራ ተግባር ከሚያከናውንባቸው ዘርፎች መካከልም በገመድ አልባ ኢንተርኔትና የስልክ ግንኙነቶች፣ የኔትዎርክ ሽፋንና ጥራትን የሚያሻሽሉ ቴክኖሎጂዎች ምርምርና ፈጠራ እንዲሁም በሀገሪቱ የተዘረጋውን የቴሌኮም መዋቅር የሚያሻሽሉ ቴክኖሎጂዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ከሀገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ማዕከሎች ጋር ተቀናጅቶ ይሰራል የተባለውና በ3 ሺህ ስኩየር ሜትር ቦታ ላይ የሚያርፈው የፈጠራ ማዕከሉ፤ ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካ የሚተርፍ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ያፈልቃል ተብሏል፡፡ በተመሳሳይ ኩባንያው የ5ኛው ትውልድ (5G) የቴሌኮም አገልግሎትን በኢትዮጵያ ለማቅረብና ለማስፋፋት እቅድ እንዳለው ተገልጿል፡፡