Administrator

Administrator

የቀድሞው የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አብዲ መሐመድ ኡመር (አብዲ ኢሌ) ከእስር መፈታታቸው ተሰማ፡፡

ከስድስት ዓመት በፊት ነሐሴ 21 ቀን 2010 ዓ.ም. አዲስ አበባ ውስጥ በቁጥጥር ስር የዋሉትና እስካሁን በእስር ላይ የቆዩት አቶ አብዲ መሐመድ ኡመር፤ ከእስር የተለቀቁት ዐቃቤ ሕግ ክሱን በማንሳቱ መሆኑን ጠበቃቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል፡፡

ጠበቃና የሕግ አማካሪ አቶ  እስክንድር ገዛኸኝ እንደተናገሩት፤ የቀድሞው የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ክሳቸው ተነስቶ የተለቀቁት በዛሬው ዕለት  መጋቢት 5 ቀን 2016 ዓ.ም. መሆኑ ታውቋል።

ከአቶ አብዲ በተጨማሪም በተመሳሳይ በእሳቸው የክስ መዝገብ ጉዳያቸው ሲታይ የነበሩ የሌሎችም ተከሳሾች ክስ ተቋርጦ መለቀቃቸውን ጠበቃው ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ጠበቃና የሕግ አማካሪው እንደሚሉት፣ ዐቃቤ ሕግ ባለው ሥልጣን መሠረት የክስ ማቋረጫውን ለፍርድ ቤቱ አቅርቦ፣ አቶ አብዲ ከመፈታታቸው ውጪ ለጊዜው የደረሳቸው ዝርዝር ማብራሪያ እንደሌለ ለቢቢሲ ገልጸዋል።

“አሁን ማረጋገጥ የምችለው አቶ አብዲ ዛሬ ሐሙስ ከሰዓት በኋላ ከማረሚያ ቤት መፈታታቸውን እንጂ ዐቃቤ ሕግ ስላቀረበው ጥያቄ የደረሰን ነገር የለም” ሲሉ  የቀድሞው የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ከእስር መውጣታቸውን ጠበቃቸው ተናግረዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው ከዓመታት በፊት ጀምሮ የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ሆነው ሲመሩ የነበሩት አቶ አብዲ፣ በክልሉ ውስጥ ከተፈጸሙ በርካታ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች፣ ግድያዎችና የመንግሥት ሀብት ብክነት ጋር ስማቸው ሲነሳ ቆይቷል።
 
በቀድሞው ርዕሰ መስተዳደር ላይ ከቀረቡባቸው ክሶች መካከልም በ2010 ሰኔ እና ሐምሌ ወራት ውስጥ “በሶማሌ ክልል የእርስ በርስ ግጭት እንዲፈጠር ለማድረግ በማሰብ ‘ሄጎ’ በሚል ስያሜ የሚታወቅ ወጣቶች ቡድን አደራጅተዋል” የሚል ይገኝበታል።

በወቅቱ በሶማሌ ክልል ዋና ከተማ ጂግጂጋ በተፈጸመ ጥቃት በርካታ ሰዎች መገደላቸው፣ እንዲሁም ንብረትና አብያተ ክርስቲያናት ላይ ጉዳት መድረሱ ይታወቃል።

ኢትዮ - ሮቦ ሮቦቲክስ፤ በነገው ዕለት ሐሙስ፣ የ2024 የአፍሪካ ሮቦቲክስ ቻምፒዮንሺፕ ውድድሩን በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል የሚጀምር ሲሆን፤ ቅዳሜ መጋቢት 7 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ ለማወቅ ተችሏል፡፡ መርሃ ግብሩ  በአዲስ አበባ ለሁለተኛ ጊዜ የሚካሄድ ዓመታዊ የሮቦቲክስ ወድድር መሆኑን የኢትዮ-ሮቦ ሮቦቲክስ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰናይ መኮንን ገልጸዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ  በነገው ዕለት የሚጀመረውን የሮቦቲክስ ውድድር አስመልክቶ ከማዕከሉ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ  አቶ ሰናይ መኮንን ጋር አጭር ቆይታ አድርጓል፡፡ እነሆ፡-

****

እስቲ ታዳጊዎች ባለፉት 6 ወራት በናንተ ማዕከል ውስጥ ስለወሰዱት የሮቦቲክስ ሥልጠና አብራሩልኝ?

ታዳጊዎች ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ፕሮግራሚንግ፣ ዲዛይኒንግ እና ኢንጅነሪንግ ላይ ያተኮረ የሮቦቲክስ ስልጠናዎችን ወስደዋል፡፡ የመማር በተግባር መርህ ተከትለው በመስራት ለቬክስ ሮቦቲክስ ውድድር ተዘጋጅተዋል፡፡

ልጆቹ ከዚህ ሥልጠና በተጨባጭ የሚያተርፉት ምንድን ነው? በህይወታቸው ላይ ምን ይጨምራሉ?

በእነዚህ ጊዜያት የኢንጅነሪንግ ፣ የዲዛይኒንግ እና  የፕሮግራሚንግ ክህሎቶቻቸውን አሻሽለዋል፡፡ የራሳቸውን አዲስ ነገር የመፍጠርና የመሞከር እድል አግኝተዋል፡፡ በመጪው የዲጂታል ዘመን ውስጥ ብቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው ያደርጋቸዋል፡፡
ባለፈው ጥር ወር በቻይና በተካሄደ ውድድር ላይ ተሳትፋችሁ ተመልሳችኋል? ውድድሩ ምን ይመስል ነበር? ውጤቱስ? በመሰል ዓለማቀፍ  ውድድሮች ላይ መሳተፍ ፋይዳው ምንድን ነው? የኛ ልጆች ከቻይናዎቹ አቻዎቻቸው ጋር ሲወዳደሩ ምን ደረጃ ላይ ነው ያሉት?

ባለፈው ጊዜ በቻይና በነበረን ውድድር አበረታች ውጤት አይተናል፡፡ ለብዙ ተወዳዳሪዎች የመጀመሪያ ስለነበር፣ ከዚህ በኋላ በሌሎች አለም አቀፍ ውድድሮች ማለትም በአሜሪካና በካናዳ ለሚጠብቃቸው መሰል ውድድር የበለጠ ዝግጁ እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል ፡፡ ቻይናውያን እጅግ በጣም ከፍተኛ ዝግጅት አላቸው፤ በተለይም በትምህርት ካሪኩለማቸው ሮቦቲክስ እና ፕሮግራሚንግ የተካተተ ስለሆነ፤ ከኢትዮጵያውያን የበለጠ ውጤት በማምጣት በውድድሩ ላይ አንደኛ በመሆን አጠናቀዋል፡፡

እስቲ  ነገ ሐሙስ በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ስለሚጀመረው  የ2024 የአፍሪካ ሮቦቲክስ ቻምፒዮንሺፕ በጥቂቱ ይንገሩኝ? በውድድሩ ሌሎች አፍሪካውያን ይሳተፋሉ እንዴ?

በነገው እለት በኢሊሌ ሆቴል የሚደረገው የአፍሪካን ሮቦቲክስ ቻምፒዮንሺፕ በአዲስ አበባ ለሁለተኛ ጊዜ የሚዘጋጅ አመታዊ የሮቦቲክስ ውድድር ሲሆን፤ በዚህ  ውድድር የተወሰኑ እዚሁ አዲስ አበባ የሚኖሩ አፍሪካውያን ተማሪዎች ይሳተፋሉ፡፡ ውድድሩን ይበልጥ ሌሎች አፍሪካዊ ተማሪዎች የሚሳተፉበት ለማድረግ ጠንክረን እየሰራን ነው፡፡

ኢትዮ - ሮብ ሮቦቲክስ ከተከፈተ ምን ያህል ጊዜ ሆነው? እስካሁን ምን ያህል ተማሪዎች አስመርቃችኋል?

አፍሪካን ሮቦቲክስ ቻምፒዮንሺፕ ያልነው፣ ሮቦቲክስ ስንጀምር በአፍሪካ የመጀመሪያዎች እኛ በመሆናችን ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃ የሚሆነው ደግሞ በ2011 ዓ.ም  እኛ ከብዙ አለም አቀፍ የሮቦቲክስ ኩባንያዎች  ጋር  ስንፈራረም፣ ሌሎች  የአፍሪካ አገራት  ቀድመው አልተፈራረሙም ነበር፡፡ ሁለተኛ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መቀመጫ አገር ከመሆንዋ አንጻር ለዚህ ውድድር ከሌላ አገር የበለጠ ተመራጭ ያደርጋታል፡፡

እናንተ ዘንድ  በሮቦቲክስ ሰልጥነው ትልቅ ቦታ የደረሱ ኢትዮጵያውያን  አሉ?

በ2011 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስልጠና  ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ  ወደ አሜሪካና ካናዳ ሄደው ስኮላርሺፕ ያገኙና ከፍተኛ ውጤት በማምጣት እየተማሩ ያሉ፣ ከ100 በላይ ተማሪዎች በተለያዩ ጊዜያት አገራቸውን አስተዋውቀዋል፡፡ ለወደፊት ትምህርታቸውን ጨርሰው ወደ ስራ አለም ሲገቡ የምናያቸው ይሆናል፡፡ አሁን በስራ ላይ ካሉት ውስጥ  ሳሙኤል አርአያ በኦንላይን ስራ የሚጠቀስ ጎበዝ ልጅ ነው፡፡

ከሮቦቲክስ ሥልጠና ሌላ ቋንቋም ታስተምራላችሁ አይደል?

የቋንቋና የሰልፍ ዲስፕሊን ኮርስም ለህጻናት እንሰጣለን፡፡ በቋንቋ ስልጠናችን ለተማሪዎች ለየት ባለ ሪድ ኤንድ ቴል ፕሮግራማችን፣ ልዩ ልዩ በልምምድ ላይ ያተኮረ  ስልጠና እንሰጣለን፡፡

ኦቪድ ሪልእስቴት፤ “አንድ ቀን፣ አንድ ህልም፣ አንድ ዕድል” በሚል መሪ ቃል በትላንትናው ዕለት ከጠዋቱ 4 ሰዓት እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት በስካይላይት ሆቴል፣ ለአንድ ቀን ብቻ የሚቆይ ልዩ የቤቶች ሽያጭ በታላቅ ቅናሽ (40 %) ያከናወነ ሲሆን፤ በዚህም የሽያጭ መርሃ ግብር አብዛኞቹ ቤቶች ተሸጠው መጠናቀቃቸው ታውቋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክቶች ቀርጾ ወደ ሥራ መግባቱን ያስታወቀው ኦቪድ ሪልእስቴት፤ እነዚህ ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች ልማት ፕሮጀክቶች በ4 ምድብና ሳይቶች መካተታቸውን አስታውቋል፡፡

በትላንትናው ዕለት ለህዝብ የቀረበው አንደኛው ፕሮጀክት ጫካ መኖሪያ ቤት ሲሆን፤ ይህ ፕሮጀክት በአዲስ አበባ ጫካዎች ውስጥ በግንባታ ላይ የሚገኙ 1900 የተንጣለሉ ቤቶች ባለ1፣ ባለ 2 እና ባለ 3 መኝታ አፓርትመንቶችን የያዘ ሲሆን፤ ፕሮጀክቱ 9 ሄክታር በሚሸፍን ሰፊ የከተማው አረንጓዴ መስክ ላይ የሚለማ ነው ተብሏል፡፡

ሁለተኛው ሐረር ሆራይዘን ፕሮጀክት ሲሆን፤ ባለ 2 እና 3 መኝታ ቤት ዘመናዊ አፓርትመንቶችን የያዘ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ከአዲስ አበባ 8 ኪ.ሜ ርቀት ላይ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡

ሦስተኛው ኪንግስ ታወር ሲሆን፤ ባለ1፣ ባለ2፣ ባለ3፣ እና ባለ4 መኝታ አፓርትመንቶችን ይዟል፡፡  ኪንግስ ታወር ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን ያካተቱ 1740 ሰፋፊ መኖሪያዎችን ያካተተ መሆኑ ታውቋል፡፡

አራተኛው አፍሪካን ሃይትስ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ባለ1፣ ባለ2፣ ባለ3፣ እና ባለ4 መኝታ አፓርትመንቶችን ጨምሮ 324 ቤቶችን ያካተተ ነው ተብሏል፡፡

ኦቪድ ግሩፕ በሥሩ በተለያዩ የንግድ ዘርፎች ላይ የተሰማሩ በርካታ ድርጅቶችን ያቀፈ የኮርፖሬት ሆልዲንግ ነው፡፡
ኦቪድ ሪልእስቴት ለአንድ ቀን ባዘጋጀው ልዩ የቤቶች ሽያጭ
ፕሮግራም ላይ  ያቀረባቸው  ቤቶች በሙሉ መሸጣቸውን ገለፀ

ኦቪድ ሪልእስቴት፤ “አንድ ቀን፣ አንድ ህልም፣ አንድ ዕድል” በሚል መሪ ቃል በትላንትናው ዕለት ከጠዋቱ 4 ሰዓት እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት በስካይላይት ሆቴል፣ ለአንድ ቀን ብቻ የሚቆይ ልዩ የቤቶች ሽያጭ በታላቅ ቅናሽ (40 %) ያከናወነ ሲሆን፤ በዚህም የሽያጭ መርሃ ግብር አብዛኞቹ ቤቶች ተሸጠው መጠናቀቃቸው ታውቋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክቶች ቀርጾ ወደ ሥራ መግባቱን ያስታወቀው ኦቪድ ሪልእስቴት፤ እነዚህ ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች ልማት ፕሮጀክቶች በ4 ምድብና ሳይቶች መካተታቸውን አስታውቋል፡፡

በትላንትናው ዕለት ለህዝብ የቀረበው አንደኛው ፕሮጀክት ጫካ መኖሪያ ቤት ሲሆን፤ ይህ ፕሮጀክት በአዲስ አበባ ጫካዎች ውስጥ በግንባታ ላይ የሚገኙ 1900 የተንጣለሉ ቤቶች ባለ1፣ ባለ 2 እና ባለ 3 መኝታ አፓርትመንቶችን የያዘ ሲሆን፤ ፕሮጀክቱ 9 ሄክታር በሚሸፍን ሰፊ የከተማው አረንጓዴ መስክ ላይ የሚለማ ነው ተብሏል፡፡

ሁለተኛው ሐረር ሆራይዘን ፕሮጀክት ሲሆን፤ ባለ 2 እና 3 መኝታ ቤት ዘመናዊ አፓርትመንቶችን የያዘ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ከአዲስ አበባ 8 ኪ.ሜ ርቀት ላይ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡

ሦስተኛው ኪንግስ ታወር ሲሆን፤ ባለ1፣ ባለ2፣ ባለ3፣ እና ባለ4 መኝታ አፓርትመንቶችን ይዟል፡፡  ኪንግስ ታወር ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን ያካተቱ 1740 ሰፋፊ መኖሪያዎችን ያካተተ መሆኑ ታውቋል፡፡

አራተኛው አፍሪካን ሃይትስ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ባለ1፣ ባለ2፣ ባለ3፣ እና ባለ4 መኝታ አፓርትመንቶችን ጨምሮ 324 ቤቶችን ያካተተ ነው ተብሏል፡፡

ኦቪድ ግሩፕ በሥሩ በተለያዩ የንግድ ዘርፎች ላይ የተሰማሩ በርካታ ድርጅቶችን ያቀፈ የኮርፖሬት ሆልዲንግ ነው፡፡

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት  ሲሰሩ የነበሩ የቀድሞ ባልደረቦች ማህበራቸውን ወይም ‹‹አፊክሰን››  የመሰረቱበትን  25ኛ  ዓመት ክብረ በአል  ቅዳሜ የካቲት 30 ቀን 2016 ዓ.ም  ከጠዋቱ 3 ሰአት ጀምሮ በኢሲኤ አዳራሽ አክብረዋል፡፡

ፕሬዚዳንት  ሳህለወርቅ ዘውዴ  የአፊክስ የክብር አባል ሲሆኑ፤ ሌሎችም በአለም አቀፍ ደረጃ ሀገራቸውን ያስጠሩ ኢትዮጵያውያንም  የዚህ ማህበር አባላት ናቸው፡፡
 
አፊክስ ፣ በዋነኛነት የአባላቱን ጥቅምና መብት  ማስጠበቅን ቀዳሚ አላማው አድርጎ የተመሰረተ  ሲሆን፤ ከ586 በላይ አባላትም አሉት፡፡

 ከልዩ ልዩ አለም አቀፍ ተቋማት ጡረታ በወጡ ባለሙያዎች የተመሰረተው ይህ ማህበር  25ኛ አመቱን በድምቀት ሲያከብር፤ ከፍተኛ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሥራ ኃላፊዎች ታድመዋል፡፡ የእለቱ የክብር እንግዳ ሚስተር ሪሚዝ አልካባሮቭ፣ የተባበሩት መንግስታት ኤጀንሲዎችን በመወከል ንግግር አድርገዋል ።

ማህበሩን ከመሰረቱት መካከል ለረጅም አመት በፕሬዚዳንት ያገለገሉት  አቶ ተድላ ተሾመ በእለቱ የታደሙ ሲሆን፤ እርሳቸውም በዩኤንዲፒ ከ20 አመት በላይ  በከፍተኛ  ኃላፊነት አገልግለዋል፡፡

በዚህ ክብረ በአል ላይ ዶ/ር አፈወርቅ አየለ የኦፊክስ ፕሬዚዳንት የእለቱን መልእክት አሰምተዋል፡፡   ልዩ ልዩ ኪነጥበባዊ መሰናዶዎችና  የኦፊክስን የ25 አመት ጉዞ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም በተወዳጅ ሚድያና ኮሚኒኬሽን አማካይነት ቀርቧል፡፡

ኦፊክስ  የአባላቱን ጥቅም ሊነካ የሚችል  የመመሪያ ለውጥ በተባበሩት መንግስታት  ድርጅት ውስጥ ቢከሰት ለውጡን  ለአባላቱ ያሳውቃል፡፡ በስራ ላይ እየተሳተፉ ያሉ አባላት  ልምድና እውቀት በሰፊው ያካበቱ በመሆኑም ይህን የተቀደሰ አላማ ከግብ ለማድረስ ሌት ተቀን የሚታትሩ ባለሙያዎችም  ናቸው፡፡

ማህበሩ ሲመሰረት አንስቶ፣ ከጡረታ መስሪያ ቤት ዘንድ ውሳኔ የሚጠብቅ ጉዳይ ያላቸውን አባላት  በፍጥነት ውሳኔ እንዲገኝላቸው አድርጓል፡፡ በሥራ ላይ የሚገኙት ደግሞ  ጡረታ ከመውጣታቸው አስቀድሞ  ስለጡረታ ክፍያቸው እንዲሁም ስለ ጤና ጥበቃ መድን ቅድመ ዝግጅት  እንዲያደርጉ  አፊክስ እገዛውን በተሟላ መንገድ ሲሰጥ መቆየቱን ለመረዳት ተችሏል፡፡

የተባበሩት መንግስታት የቀድሞ ዓለምአቀፍ  ሠራተኞች ማህበር  ወይም አፊክስ ለጠቅላላ ጉባኤው ተጠሪ የሆኑ የቦርድ አባላት ያሉት ሲሆን፤ የማህበሩም ጽ/ቤት በኢሲኤ ግቢ ውስጥ ነው የሚገኘው፡፡

ያለ ማሲያዣ ለወጣቶችና ስራ ፈጣሪዎች ገንዘብ ማበደር የሚያስችል አማራጭን ይዤ መጥቻለሁ ያለው ከፍታ ማይክሮ ፋይናንስ በትላንትናው ዕለት በይፋ ተመርቋል።

የከፍታ ማይክሮ ፋይናንስ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ነፃነት ደነቀ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ መስፈርቶችን በሟሟላት ሙሉ እውቅና እና ፍቃድ በመያዝ ወደ ስራ መግባቱን ያስረዱ ሲሆን፤ በዘርፉ አዲስ እንደሚቀላቀል ተቋም የተለያዩ አማራጮችን በመያዝ መምጣታቸውን ነው ያብራሩት።

ከእነዚህም መካከል ወጣቶችና ስራ ፈጣሪዎችን ለማበረታታት እንዲቻል በሚል መርህ የስራ ፈጠራ ሃሳቦቹን አዋጭነት በማጥናት ያለ ማሲያዣ ስራ መጀመር የሚችሉበት የብድር አማራጭ አንዱ መሆኑን ገልፀዋል።

ይህ የብድር አማራጭ በማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት ደረጃ ያልተለመደ ነው ያሉት የቦርድ ሰብሳቢው፤ ከፍታ ማይክሮ ፋይናንስ  ወጣቶችና ሴቶች ላይ ትኩረት አድርጎ የሚሰራ ተቋም በመሆን መምጣቱን አብራርተዋል።

ከወጣቶችና ስራ ፈጣሪዎች በተጨማሪ በገጠሪቱ የሃገሪቱ ክፍሎች የሚገኙና የፋይናንስ ተደራሽነት በሌላቸው አካባቢዎች ላይም ማተኮር ሌላኛው የተቋሙ አገልግሎት መሆኑን አክለዋል።

የከፍታ ማይክሮ ፋይናንስ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አቶ ሞገስ ታመነ በበኩላቸው፤ ተቋሙ አገልግሎት መስጠት ከመጀመሩ በፊት በሃገሪቱ አሉ ከሚባሉ እንደ አዋሽ ባንክ፣  ዳሽን ባንክ፣ አቢሲኒያ ባንክ፣  እንዲሁም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ  ከመሰሉ ተቋማት ጋር በጥምረት ለመስራት የሚያስችል የመግባቢያ ሰነድ መፈራረሙን አንስተዋል።

ከፍታ ማይክሮ ፋይናንስ ሴቶችን ፣ ወጣቶችንና ስራ ፈጣሪዎችን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ እንደሚያተኩር የጠቆሙት  ስራ አስፈፃሚው፤ የቁጠባ ባህልን የሚያጎለብቱ በግልና በቡድን ለሚመጡም የተለያዩ አማራጮችን ይዘን መጥተናል ነው ያሉት።

አቶ ሞገስ አክለውም፤ በዝቅተኛ ኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ አምራች  ዜጎችና ተቋማት የቁጠባና የብድር አገልግሎት ማቅረብ እንዲሁም  አካታችና ሁሉን አቀፍ የፋይናስ ስነ ምህዳር መፍጠር የሚሉት የትኩረት አቅጣጫዎቻችን ናቸው ብለዋል።

ከፍታ ማይክሮ ፋይናንስ በ170 አባላት አማካኝነት በ24.5 ሚሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታልና በ89.4 ሚሊዮን ብር የተፈረመ ካፒታል ወደ ስራ የገባ ተቋም ነው።

 በብሔራዊ ባንክ መረጃ መሰረት፤ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጰያ  ወደ 50 የሚጠጉ የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት ይገኛሉ፡፡

Monday, 11 March 2024 10:32

ያ ዕለት ይናፍቀኛል !

“የዘመናት መድረክ ላይ ረዥሙን የታሪክ ጉዞ ተጉዘው ለሰው ልጆች ተስፋንና ጥበብን ይዘው ለትውልድ በመተላለፍ እንደ ውርስ የተሰጡ ቅርሶች መጻሕፍት ናቸው”  ሻምበል አፈወርቅ ዮሐንስ።
ስለ መጻሕፍት፣ ስለ ንባብ አዲሱ ባህላችን  ላወጋችሁ ነው። መጻሕፍትን በመላው አገራችን አዳርሰው የንባብ ባህልን የህዝብ ቋሚ ባህል  ለማድረግ፣ የኢትዮጵያ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ  በአያሌው እየተንቀሳቀሰ ነው። በዚህም እንቅስቃሴው 337916  መጻሕፍትን፣ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ ለ590 ተቋማት ሰጥቷል። ተቋማቱ  ዩኒቨርሲቲዎች ፣ የህዝብ ቤተ መጻሕፍት፣ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችና ማረምያ ቤቶች ናቸው። መጻሕፍትም እንዴት መነበብ እንዳለባቸው ደራሲያንን ፣ ገጣሚያንን፣ የዩኒቨርስቲ መምህራንን በመጋበዝ፣ ለታዳሚዎች ልምዳቸውን እንዲያጋሩ ያደርጋል። በየክልሉ ለሚገኙ የህዝብ ቤተ መጻሕፍት ሰራተኞች ሙያዊ ስልጠና ይሰጣል። በመዲናችን ለሚገኙ መጻሕፍት ነጋዴዎች ትራንስፖርት በማመቻቸት፣ በተጋባዝዋ ከተማ የመጻሕፍት አውደ ርእይ ያዘጋጃል። በዚህም ከየከተሞቹ ባህል፣ ስፖርት ቢሮ ጋር በመቀናጀት ህዝብ አውደ ርእዩ ላይ እንዲሳተፍ ያደርጋል።
ኤጀንሲው ወሳኝ የሆኑ ዶክሜንቶችን ኦርጂናሌውን ፣ አልያም ፎቶ ኮፒዎች በማቅረብ የራሱን የዘመናት እንቅስቃሴዎች በአውደ ርእዩ ላይ ያቀርባል። በቅርቡ በአርባምንጭ ከታዩ ዶክሜንቶች መካከል አቶ ታደሰ ታቼ የተባሉ አርቆ አሳቢ ከ70 አመታት በፊት፣ በ1946 ዓ.ም በወቅቱ አገሪቱን ሲመራ ለነበረው መንግስት የጻፉት ደብዳቤ ለትእይንት ቀርቦ ነበር ፡፡ አቶ ታደሰ፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አምስት ፣ አምስት ብር ቢያዋጣ እንዴት የአባይን ወንዝ መገደብ እንደሚቻል ይገልጹና፣ እርሳቸው ይህንኑ መዋጮ በወር 5 ብር በአመት 200 ብር ለመለገስ ቃል ይገባሉ። ይህ ሃሳብ ይሆን ለእነ አቶ መለስ ዜናዊ፣ ከሰባ አመታት በኋላ የህዳሴውን ግድብ መሰረት ለመጣል ያስቻላቸው ? ስል አውጠንጥኛለሁ።
 እዚያው በጉባኤው ላይ የከተሞቹ ከፍተኛ ሀላፊዎች፣ ታዳሚዎች በተገኙበት ትዕይንቱ ይጎበኛል። የከተማዋ ነዋሪዎች ይታደማሉ። በዚህም የማንበብ ፍቅር ያላቸው በደስታ የፈለጉትንና ገበያው ያቀረበላቸውን መጻሕፍት ሲሸምቱ ይስተዋላሉ።  
በቅርቡ በአገራችን “ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል!” የሚሉት ብሂል በተደጋጋሚ በመገናኛ ብዙሃን ይደመጣል። አባባሉ ሊያከራክር ቢችልም ከማንበብ የተሻለ ሰውን ሙሉ ሊያድርገው የሚችል ሙያ የለም ማለት እንችላለን። አዎን ልጆቻችንን ዩኒቨርስቲ ልከን የአንድ ሙያ ባለቤት ማድረግ እንችላለን። የህክምና ዶክተሮች ፣ ኢንጂነሮች ፣ ኢኮኖሚስቶች ወዘተ ማድረግ ይቻላል። ዓለምን በምልአት እንዲያዩዋት ግን መጻሕፍት ማንበብን ልንጨምርበት ይገባል። በዚህ ጉዳይ ላይ በእንድ ወቅት ከዶክተር ተወልደ ብርሃን ጋር ስንጨዋወት፤ “ማንኛውም ሰው የራሱ የእኔ የሚለው  ሙያ ሊኖረው ይገባል። በሙያው ላይ ዓለምን በምልአት ለማየት ታሪክንና ሥነ ጹሑፍን ሙያው ላይ ማከል አለበት። ይህንን ካደረገ ሥነ ጹሑፍ የወደፊቱን ሲያመላክቱት ፣ ታሪክ ደግሞ በሙያው ላይ ባለፈው ዘመን ምን እንደተሰራ ያሳውቁታል” ብሎኛል።
የኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት እና ቤተ መዛግብት እንድታደም ጠርቶኝ በድሬዳዋ ፣ አርባምንጭ ፣ ወላይታ ሶዶ፣ዱራሜ እና ዲላ ከተሞች  ላይ ተገኝቼ፣ የመጻሕፍት ንባብ ልምዴን ለታዳሚው አጋርቻለሁ። በዚህም የሚገርመኝ አይነት ገጠመኞችም በህይወቴ ውስጥ ተከስተዋል። ከማስታውሰው አንዱ  ድሬዳዋ ማረሚያ ቤቶች ተገኝቼ ልምዴን ያጋራሁበት እለት ነው። በእለቱ አንድ ታራሚ በእርማቱ ወቅት ምን ማድረግ እንዳለበት፣ ጊዜውን እንዴት መጠቀም እንደሚገባው ካነበብኩት እንዳጋራ ጥናቴ  እዚህ ላይ እንዳተኩር አቶ ያሬድ ተፈራ ነገረኝ። አቶ ያሬድ፣ ከቤተ መዛግብቱ ከፍተኛ ሀላፊዎች መካከል አንዱ ነው። እኔም ህይወቱ በእስር ቤት 100% የተቀየረ አንባቢ የማስታውሰው ማልኮም ኤክስን ነው።(1925 - 1965)  ኤክስ ጥቁር አሜሪካዊ ነው፣ ትምህርቱን ከዝቅተኛ ክፍል ነው ያቋረጠው። ዘመኑ በፈጠረበት ተጽእኖ አስፈሪ ወመኔ ሆነ። አንድ በታደለበት ቀን እስር ቤት ገባ። ያቺ ቀን ዳግም ልደቱ ሆነች ፣ ያቺን እለት ቢያልፋት ኖሮ በቀጣዩ ቀን ሟች ነበር። ምክንያቱም አንድ ነጭ ሰውዬ ሚስቴን አባልጎብኛል ብሎ ሊገድለው እርሱ በታሰረ የእለቱ እለት ጠመንጃ ገዝቶ ነበር። ኤክስ በእለቱ በመታሰሩ ሟችና ገዳይ ሳይገናኙ ቀረ። ከዚያ በኋላ የማልኮም ኤክስ ህይወት በእስር ቤት በመጻሕፍት ንባብ ታንጻ መቶ በመቶ ተቀየረች። ይህንን ላወጋቸው እራሴን አዘጋጀሁ ፤ አንድ ቅር ያለኝ ነገር ይህ ታሪክ የአንድ ሩቅ አገር የሚገኝ ጥቁር ልጅ ታሪክ ቢሆንም፣ ለአበሻ ምናብ ይርቅ ይሆን?  እያልኩኝ በቅጡ አውጠነጠንኩ። እንደ መታደል የዚህ እለት የኢትዮጵያ ህዝባዊ ደሞክራሲያዊ ሪፕብሊክ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ጓድ ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ ተጋባዥ ስለነበሩ ጎን ለጎን ስንቀመጥ፣ ከቁም እንቅልፌ ባነንኩ። ማውራት ያለብኝ ስለ ማልኮም ኤክስ ሳይሆን ስለ ጓድ  ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ ነው አልኩኝ። ልብ አድርጉልኝ፤ እኒህ ሰው በኢህዲሪ ዘመን ከፍተኛ ባለሥልጣን ነበሩ። ስርአቱ ሲፈርስ በእነ መንግስቱ ኃይለማሪያም ፋይል በተመሰረተባቸው ክስ የመጀመሪያ ተከሳሽ ናቸው። የክስ ሂደቱን እንደማስታውሰው  ሞት ተፈረደባቸው ፣ በሂደት ወደ ዕድሜ ይፍታህ ተቃለለላቸው፡፡ ከሁለት አስርት አመታት በኋላ በምህረት ተለቀቁ። ይህንን የመሰለ ጮማ ወሬ እንደዋዛ ካለፍኩት ድንቅ የመድረክ ሰው አይደለም አልኩት ለራሴ። አቶ ያሬድንም ሆነ ጓድ ፍቅረ ሥላሴን ሳላስፈቅድ ለታራሚው እጥር ምጥን ያለች አይን ገላጭ ንግግር አደረኩ። ንግግሬን ስቋጭ ሞቅ ያለ ጭብጨባ ተከተልኝ።
አልዋሽም፤ የጓድ ፍቅረ ሥላሴ ጽናታቸውን ከልብ አደንቃለሁ። ፌዎዶር  ዶስቶዬቭስኪ የተባለ አንጋፋ ሩሲያዊ ደራሲ፣ ደራሲ ለመሆን ለሚሹ ወገኖች ተጠይቆ ሲናገር፤ “ሞት ይፈረድብህ፤ በዚህ ስትጨነቅ በእድሜ ይፍታህ ይቃለልልህ ፣ ይህም ሲያስጨንቅህ በነፃ  ትለቀቃለህ፤ የዚያን ጊዜ ደራሲ ትሆናለህ” ይላል። ይህንን መራር  መንገድ ጓድ ፍቅረ ሥላሴ በጽናት ሲያልፉበት ባይ ነው ማድነቄ። ከዚያ በኋላ በእኔ እና በፍቅረ ሥላሴ መካከል ወዳጅነታችን ስር ሰዶ አዲስ አበባ ተገናኝተን መጻሕፍት ተቻችረናል። አገር ውስጥ እስካሁን ያልተነበበው መጽሐፋቸው ፤”እኔና አብዮቱ” እጄ ላይ አለ። ሌሎች የተጠናቀቁ ሥራዎች እንዳላቸው አውግተውኛል።  አንድ ቀን ያነበብኩላቸውን እዳስሰዋለሁ።
እንዲህ እይነቱ ጉዞ በተጋባዥ እንግዶች የሚወደድ ነው። እኔ ከተጋበዝኩ ስለምጓጓ እነማን አብረውን እንደሚጓዙ አስቀድሜ እጠይቃለሁ። አንዳንዴ የተነፋፈቅን ወዳጆች የምንገናኝበት ጊዜ አለ። አዲስ አበባ እንደሁ የምታገናኘን ቀብር ላይ ነው። “ተዋናይ እገሌ አረፈ!” ከተባለ ቀብር ላይ እንገናኛለን።
 ስለዚህ በህይወት ተገናኝቶ  እንዲህ አይነቱ አጋጣሚ ላይ መገናኘት  በጣም ተወዳጅ ነው።
የቀድሞው የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሥነ ጽሁፍ መምህር የነበረው መሰረት አበጀ፣ ዲላ እንግዳ ሆነን ሄደን የሆድ የሆዳችንን ስንጨዋወት፣ የካቲት ወር የተወለደበት ቀን እንደሆን ነገረን። የሚገርመው ወጣቶቹ ይህንን መረጃ ወደ ተግባር ቀይረው ምሽቱን 60ኛ ዓመት የልደት በዓሉን አከበርንለት። እርሱም በወጣቶቹ ድርጊት ልቡ ተነክቶ  ይህንን የመከባበርና የመዋደድ ባህልን  መጪው ትውልድ ላይ ማስታዋሉ እንዳስደሰትው አወጋን።
ዲላ ዩኒቨርስቲ ለወጣቶች የንባብ ልምዱን ሲያጋራ፣ የመግለጽ አቅሙ፣ የመመሰጥ ባህሪው ፣ ልክ እንደ ተዋጣላት ተዋናይ መድረክ ጠቦት ያደረገው ገላጻ ግሩም ነበር፡፡ ከእኔ ጋር በግል ስንጨዋወት፤ “ይህ የኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት እና ቤተ መዛግብት የሚሰራው ሥራ እጅግ የሚያስመሰግነው ነው። ቢያድለን ይህንን ተግባር መከወን ያለባቸው ትምህርት ሚኒስቴር እና ዩኒቨርስቲዎቹ ነበሩ፡፡ አልሆነም። አሁን ልብ ብዬ ሳስተውል ማንበብ በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ሞቷል። ኤጀንሲው ለመጻሕፍት ንባብ ዳግማዊ ትንሳኤ እያደረገለት  ነው። ደሞ እየተዋጣላቸው ነው። ታያለህ፤ ህዝቡ ተማሪው በታላቅ ፍቅር ሲቀበላቸው?! ሥራውም ግዴታቸውም ነው።እነርሱም ደስ ብሏቸው እየተወጡት ነው” ያለኝን አልዘነጋውም። መምህር መሰረት አበጀ ዘንድሮ የ62 ዓመት ጎልማሳ ነው ።
ለዲላ ከተማ ነዋሪዎች ንግግር እንዳደርግ የተመረጥኩት እኔ ነበርኩ። የጌዲዮ ህዝብ ከምግብ ሥጋ እንደሚወድ አውቃለሁ። በርካታ አዝናኝ ቀልዶች ተነግረውበታል፡፡ የተወሰኑትን አውቃቸዋለሁ። በነገራችን ላይ ሥጋ መብላት በመላው ህዝባችን እንደሚወደድ አውቃለሁ። የጌዲዮ ከሁላችንም ይልቃል ለማለት ነው። የቆየ ቢሆንም አንድ ጥናት ሲገልጽ፤ አመታዊ ፍጆታችን 6% ነው።አምሮታችን 94% መሆኑ ነው። በአለማችን ከፍተኛ ሥጋ ተመጋቢ ህዝብ፣ የቻይና ህዝብ ነው። የአመት ፍጆታቸው 60% ነው።
ወደ ጌዲዮ እንመለስ፡፡ አንዷን ቀልድ እነሆ። ዲላ ከተማ ውስጥ  ከሰአት በኋላ ሙቀት ያይላል። አንዱ  ብልሁ አስተማሪ ጥቁር ሰሌዳው ላይ በቅጡ የተቀለበ ሰንጋ ሳለ እና አንዴ በደንብ አጨብጭቦ ተማሪዎቹ ትኩረት እንደሰጡት፤ “ልጆች ከሻኛ ላይ ልቁረጥ? ወይንስ ከሽንጥ ላይ ?!” አሉዋቸው።
ልጆቹን በታላቅ ጉጉት፣ የአምሮት ምራቅ አፋቸውን እየሞላው፤ “ ከሻኛ ቁረጥ ፣ ከሽንጥ ቁረጥ ! “ እያሉ እንደ ምርጫቸው ተንጫጩ ። መምህሩም ተማሪዎች እስኪነቁ እንጫጩዋቸው። ከልብ መንቃታቸውን ካስተዋሉ በኋላ ወደ እለታዊ ትምህርት ገቡ። እኔም ወጌን በስጋ ወግ አሟሟቅሁት። ወዳጆቼም ሆኑ የቤተ መዛግብቱ ሀላፊዎች፣ ታዳሚው ህዝብ  “ምን ሊያወራ ነው ?” በሚል ስሜት ተደንቀው ሲከታተሉኝ አስታውሳለሁ። እኔም ሥጋ በበላ አንጀት ትንሽ መጻሕፍት ማንበቡ፣ አስተዋይና አርቆ አሳቢ እንደሚያደርግ፣ ጭብጤን ሳስይዝ፣ ሞቅ ያለ የጭብጨባ ሽልማት ተቸረኝ፡፡
ድሬዳዋ ፣እርባምንጭ፣ ጬንቻና ዲላ ማረሚያ ቤቶች የተለያዩ ገጠመኞች አሉን። የዲላው ልብ የሚነካ ነበር። የማረሚያ ቤቱ ከፍተኛ ሀላፊ ኮማንደር እንስት ናቸው። በሁለት ነገር አስታውሳቸዋለሁ። አንደኛ ከልክ በላይ ግዙፍ ቁመናቸው ሲሆን ፣ ሁለተኛው ልብ የሚነካው ንግግራቸው ትውስ ይለኛል፡፡ “ማረሚያ ቤታችንን የእውነት ማረሚያ እንዲሆን መጥታችሁ አስተዋፅኦ ስላደረጋችሁልን ከልብ አመሰግናለሁ። ሌሎች አካላት ህግን ከማስከበር ውጪ እንዴት ሊያስቡን አልቻሉም ? እናንተ በራሳችሁ ፍቃድ  ስላሰባችሁን ከልብ! ከልብ! እናመሰግናችኋለን !” አሉ ፤ትክዝ ብለው።የጬንቻው ማረሚያ ቤት የሚደንቅ ነው። እንግዳ አቀባበሉን ብሔራዊ በአል ነበር ያደረጉት።ታራሚዎቹ የክት ልብሳቸውን ለብሰው  ደማቅና ውብ በሆነ ስሜት፤ “እንኳን ደህና መጣችሁ!”ብለው ተቀበሉን። በቆይታ አስተዳደሩም በአገር አቀፍ ደረጃ የተሸለመ የማረሚያ ቤቶቻችን አምባሳደር እንደሆነ ተገንዝበናል፡፡ ረዳት ኮሚሽነር አጥናፉ አሰፋ ቦቃ ለማንም የማይከብዱ ድንቅ መኮንን ናቸው። ከባልደረቦቻቸው ጋር ባደረጉት ድንቅ አመራር፣ ጬንቻ ማረሚያ ተቋም የድንቅ ዜጎች መፈጠሪያ ማእከል አድረገውታል። አብረውኝ ከተጓዙ ጓደኞቼ ጋር ስንጨዋወት፤ “ይህ ማረሚያ ቤት ጬንቻ እንደ እንዱ የቱሪስት መስህብ ልትጠቀምበት ይገባል“ ማለታቸውን አስታውሳለሁ። በርግጥም የሚጎበኝ ተቋም ነው።ጬንቻ የታዋቂው ፖለቲከኛና ደራሲ አሰፋ ጫቦ የትውልድ ስፍራ ነች። አሰፋ በአንደበቱ ም በብእሩም አንስቶ አይጠግባትም። ይህንን የሚያውቁት የፖለቲካ ተጻራሪዎቹ፣ ጬንቻን በዘመኑ ከጣሩት ልማት ተቋዳሽ ሳያደርጓት አለፉ። የማጣጣል ብእር ተስፋዬ ገብረአብም፣ በጬንቻ ላይ መዞባታል። የሚገርመው አሰፋም አርፎ የፖለቲካ ድርጅትም ታሪክ ከሆነ በኋላ፣ ዘንድሮ ተነቃቅታ በዘመንዋ የአስፓልት መንገድ ለመስራት ተፍተፍ ስትል አስተዋልኳት። የመንግስትም ሆነ የግል ባንኮች ተከትፈውባት፣ ሞቅ ደመቅ እያለች ነው። “አንድን የስድስት አመት ህጻን ያሰብከውን ጉዳይ ለማብራራት ካልቻልክ  ጉዳዩን አንተም አላወቅኸውም “ ይላል አልበርታይን አነስታይን። ንባብን ለመጀመሪ ደረጃ ተማሪዎች በጣም አቅልለን ማቅረብ። ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ትንሽ ከፍ አድርጎ መግለጽ ፣ ጥልቀቱን ጨምሮ ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ማውሳት በሂደት እየበሰልንበት መጣን ።
መሥሪያ ቤቱ የሁሉንም ደራሲዎች ሥራ ሸምቶ፣ ተረታ ተረቱን ለአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ፣ የጠቅላላ እውቀቱን ለመምህራኑ ሸምቶ ሰጥቷል። ለሁለተኛ ደረጃና ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ከልብ ወለዱም፣ ከግጥሙም  ከፍልስፍናውም  እያደረገ ሲለግስ የአይን ምስክሮች ነን።
ሌላው አስተዋጽኦ ለገጠር ቤተ መጻሕፍት የሚያደርገው ልግስና የሚደነቅ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ጋሞ ውስጥ ኤዞ በተባለ ገጠር ውስጥ በዶክተር ታደሰ ወልዴ ስም በተሰየመው ቤተ መጻሕፍት ምረቃ ላይ ተገኝቼ በጉዳዩ ላይ ከእንድ ወዳጄ ጋር ስናወጋ፤ “በህይወት ዘመናቸው መጽሐፍ ምን እንደሆን አይተው የማያውቁ ወገኖቻችን እንዳሉ ታውቃለህ ?!” ሲል ያነሳልኝ ጥያቄ የማልዘነጋው ነው። ከአመታት በፊት ገጠር ውስጥ አንድ ማለዳ እለት መደብ ላይ ጋደም ብዬ አንድ መጽሐፍ አነባለሁ ። ይህንን ልብ ብላ ታስተውል የነበረች አዛውንቷ አክስቴ፣ ወ/ሮ ወዘንቴ ወጋ፤ “ ምንድነው የያዝከው ?” አለቺኝ። መጽሐፍ እንደሆነ ነገርኳት። መጽሐፍ ምን እንደሆነ ጠየቀችኝ ፤ዝግ ባለ ሁኔታ መጽሐፍ ምን እንደሆነ አስረዳኋትና ከልብ ተደነቀች ። በወቅቱ 100 አመት ይሞላት ነበር ። በዚህ አንድ ምእተ ዓመት ባስቆጠረ እድሜዋ፣ መጽሐፍ ስትመለከት ይህ  የመጀመሪያዋ ነበር።
በዚህ ነው የኢትዮጵያ ቤተ መዛግብት እና ቤተ መጻሕፍት ጥበቡን አይቶ የማያውቅ እንዲያውቀው ፣ ያወቀው ከህጻናት እስከ አዋቂው  እንዲፈትሽና ውስጡን እንዲያይ የሚያደርገውን ጥረት ይበል ልለው የወደደድኩት፡፡
ይህ ከላይ በቁጥር ያሰፈርኩት መረጃ ኤጀንሲው ከ2011 ዓ.ም እስከ 2015 ዓ.ም ያከናወነው ሲሆን፤ 2016 ዓ.ም የመጀመሪያ መንፈቅ አመት ተካቶበታል፡፡ ኤጀንሲው 82 ዓመታት ባስቆጠረ የስራ ልምዱ፣ አገልግሎቱ በአዲስ አበባና አካባቢው ነበር። ባለፉት አምስት አመታት በኢትዮጵያ ቆዳ ስፋት ልክ ባደረገው ጥረት፤ “ የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል” እንዲሉት እየሆነ ነው።
ተቋሙ፤የኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት እና ቤተ መዛግብት ወመዘክር በሚል ስያሜ በ1934 ዓም የተመሰረተ ነው። ወደ ኋላ ሄዶ በማንበብ ባህሪዬ እንደመረመርኩት፤ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ለወመዘክር የተለያዩ መንግስታትም ሆነ ትቋማት መጻሕፍት በልግስና ሲቸሩ፣ ንጉሰ ነገስቱ በአካል ተገኝተው መቀበላቸውን ማንበቤን አስታውሳለሁ። በዚህም በበርካታ የዓለም ቋንቋዎች አያሌ የመጻሕፍት ክምችት እንደሚኖረው እገምታለሁ። እራሳቸው አፄ ኃይለ ሥላሴ በቤተ መጻሕፍቱ በመገኘት እንደሚያነቡና በወቅቱ ከነበሩ ምሁራን ጋር በነጻነት ሲወያዩ ማየቱን ወዳጄ ኃይለ መለኮት መዋዕል አጫውቶኛል። ይህ ታላቅ የጥበብ ቤት ሲጠራኝ  በታላቅ ደስታ ነው  ከጎናቸው  የምቆመው። ይህን የተቀደሰ እንቅስቃሴያቸውን አብዝቼ ስለምወደውም  የሚጠሩኝን  ቀን እናፍቃለሁ፡፡
***
ከአዘጋጁ፡-
 ደራሲና ጋዜጠኛ ዘነበ ወላ ከ6 በላይ መጻሕፍትን ለንባብ አብቅቷል፡፡ ከጥበባዊና ወጋዊ ጸሃፊነቱ ባሻገርም የህይወት ታሪኮችን (ባዮግራፊስ) በመጻፍም ይታወቃል፡፡ ዘነበ ወላ አርታኢም ነው፡፡ ደራሲውን በኢሜይል አድራሻው፡ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል፡፡

ዱሮ ኪዩባን ከባቲስታን አምባገነናዊ አገዛዝ ነፃ ለማውጣት እነ ካስትሮና እነ ቼጉቬራ የትጥቅ ትግል ላይ በነበሩበት ዘመን (እ.ኤ.አ በ1950ዎቹ በ1990ዎቹ ውስጥ ) ይነገር የነበረ አንድ ወግ ነበር። አሁን ወደ አፈ-ታሪክነት ሳይለወጥ አልቀረም። የጥንት ተማሪዎች።
“ፋኖ ተሰማራ ፋኖ ተሰማ
እንደ ሆቺሚኒ እንደ ቼጉቬራ” ኢያሱ ይዘምሩለት የነበረ እንቅስቃሴ ማለት ነው።
ወጉ እንዲህ ነው።
 የኪውባው መሪ የነበሩት ፊደል ካስትሮ፣ የባቲስታን አገዛዝ ሊዋጋ ኃይል ሊያደራጅ ወደ ሜክሲኮ ይሄዳል። እዚያም አርጀንቲና የተወለደውንና ኋላ የኪውባ አብዮተኛ የሆነውን ቼ ጉ ቬራን ያገኛል። ሁለቱ ከአንድ ጠንካራ የኪውባ ተዋጊ ወታደር ጋር ጫካ ውስጥ ይመሽጋሉ። የትጥቅ ትግሉን በማፋፋም ላይ ናቸው። ከድጡ ወደ ማጡ እንዲሉ ከስፔይን ተገላግሎ በአሜሪካ እጅ መውደቅን ለመታገል እየጣሩ ነው።
የአሜሪካ መንግስት አሻንጉሊት የነበረው የባቲስታ ፉልጂኒቺዮ ጦር እጅግ አድርጎ እየበረታ፣ በአንጻሩ የታጋቾቹ ጦር እየተመናመነ ምን ማድረግ እንዳለባቸው  በጨነቃቸው ሰዓት ካስትሮ አንድ ሃሳብ አመጣ ይባላል።
“እንግዲህ ጓዶች ትግሉ እየመረረ፣ የጠላት ኃይል እያየለ እየመጣ ነው። ዕውነተኛ ታጋይነታችን፣ ቆራጥነታችን፣ ለነጻነታችን ከልብ የመቆማችን እውነተኛነት የሚለይበት ሰዓት ደርሷል። ስለዚህ ቃል እንግባ?”
“ምን የሚባል ቃል?” አለ ቼ።
“ምናልባት የጠላት ኃይል ከባድ ጥቃት አድርሶ ድንገት በእጁ ካስገባን፣ የሚያደርስብን ቅጣት፣ እኛ በሱ ላይ ያደረስንበትን ጥቃት ያህል ነው። ያው በእኛ ላይ ያለውን የጥላቻውን መጠን ያህል መሆኑ መቼም ጥርጥር የለውም። ባቲስታ ዓይኑን ካጠፋኸው ዓይንህን ያጠፋሃል። በጥይት ከቆላኀው በጥይት ይቆላሃል። እንዲያውም በዕጥፍ-ድርብ አብዝቶ፣ አንዱን በሺ መንዝሮ ነው ዋጋህን የሚሰጥህ። ስለዚህ ሁላችንም ለዓላማችን ስንል እኩል ጥቃት ማድረሳችን ከሆነ ብቻ ነው። አለበለዚያ ግን ከኛ መካከል ትንሽ ቅጣት የተቀጣ ሰው ዓላማችንን ክዷል ማለት ነው። ስለዚህ ዓላማችንን ላንክድ እንማማል።” ቼጉቬራም፣ ጠንካራው ታጋይም፣ በሃሳቡ ተስማሙ። ተማማሉ።ካስትሮ እንደፈራው ሦስቱም ተዋጊዎች ጠላት እጅ ወደቁ።
ከዚያም ለፍርድ ቀረቡ። ተፈረደባቸው። እንደየጥፋታቸው በቁማቸው እንዲቀበሩ ተወሰነ።አቀነባበራቸው የሚከተለውን ዓይነት ሆነ።
ቼ ጉቬራ ጨርሶ አይታይም። ካስትሮ ጉልበቱ ድረስ ብቻ ነው የተቀበረው። ጠንካራው ተዋጊ ወታደር ግን እደረቱ ድረስ መሬት ተቀብሯል። ይሄ ወታደር የካስትሮን እጉልበቱ ድረስ ብቻ መቀበር ባየ ጊዜ እንዲህ ሲል ወቀሰው።
”ካስትሮ ተማምለን ነበር። ከዳኸኝ። እኔን ደረቴ ድረስ ቀበሩኝ። አንተን ጉልበትህ ድረስ። የእኔን ያህል ጥቃት አላደረስክባቸውም ማለት ነው። ከሀዲ ነህ!”
ካስትሮም እንዲህ ሲል መለሰ!
“የለም የለም! አትሳት ጓድ። ጉልበት ድረስ ብቻ ወደ መሬት የገባሁበትን ምክንያት አላወቅህም። የቆምኩት!ኮ ቼ ጉቬራ ጭንቅላት ላይ ነው።
***
የራሳቸው ጭንቅላት የሌላቸው መሪዎች፣አለቆች፣ ኃላፊዎች በሌሎች ጭንቅላት መኖራቸው የተለመደ ነገር ነው። ሆኖም ውሎ ሲያድር የሌሎቹ ጭንቅላት፣ የሌሎቹ ስም፣ የሌሎቹ ታሪክ ለመኖሪያነት የሚያገለግበት ጊዜ ያልፍና ሁልህም በየራስህ ጭንቅላት ኑር የተባለ እለት የሚይዙት የሚጨብጡት የሚጠፋባቸው አያሌ ይሆናሉ። “አፍረው የተውት፣ ፈርተው የተውት ይመስለዋል” እንዲሉ፣  ለጊዜው የሚመጻደቅ ይኖራል። ቀኑ የደረሰ ጊዜ ግን ሁሉም ወደ ተገቢ ቦታው፣ ወደ ተገቢ ዕሴቱ የሚሄድበት፣ ተፈረካከሰ ያለውም ወደሚበታተንበት አቅጣጫ መጓዙ አይቀሬ ይሆናል።
አምባገነንነት ከልሂቅ እስከ ደቂቅ መከሰቻው ብዙ ነው። የየሰፈሩ ጌታ አለ እንደማለት ነው።
 የመሪ ጌታ አለ፣ የገንዘብ አለ። አምባገነንነትን አስመልክቶ ብሪታኒያዊው ባለሃብትና ታዋቂው ሰው ሪቻርድ ብራንሰን፤ “እኔ በጥሩ አምባገነንነት አምናለሁ። ዋናው ነገር አምባገነኑ እኔ ራሴ መሆን አለብኝ።” ብሏል። አምባገነኑ እኔ መሆን አለብኝ ብለው በይፋ የሚናገሩ አምባገነኖች ብዙ አይደሉም። በየውስጠ-ልቡናቸው የመጨቆን፣ የመግፋት፣ የማፈን፣ የማን-አለብኝ ባህሪ ያላቸው ሙልሙል አምባገነኖች ብቅ ብቅ በሚሉበት ጊዜ አገር ተኮነነች ማለት ነው። ሀሳዊ-ዴሞክራት የማታለያ ስብከትን (Demagogue) ያበዛል። ስሜታዊነትን ከምክንያታዊነት ያስቀድማል። በትንሽ ነገር ኩፍ ይላል-ገፁ ይለዋወጣል።
 ለማገዱ፣ ለማገቱ፣ ለማሰሩ፣ ለመግደሉ ወዘተ ሁሉ ምክንያት ይሰጣል። በየትኛውም ደረጃ ይሄን ባህሪ ይዞ የሚገኝ እሱ አምባገነን ነው። ከእንዲህ ያለው ይሰውረን ዘንድ ነው “ዕውነተኛ ዲሞክራሲ ሆይ፤ ከእኛ አትራቂ” እያልን የምንጸልየው። “የመናገር የመጻፍና ሃሳብን የመግለጽ ነጻነት ሆይ፣ ከእኛ አትራቂ” እያልን ሱባዔ የምንገባው ለዚህ ነው። ጉባዔ ሲያቅት ሱባኤ እንዲሉ።ሁሉን በእርጋታ፣ ሁሉን በትዕግስት መከወን፣ የብልህነትና የብስልነት ምልክት ነው ይላሉ። “ተመልሰህ ለምታፍሰው፣ ቸኩለህ አታፍስሰው” ነው ነገሩ። ቸኩሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ፣ ቸኩሎ መውቀስ ቸኩሎ ማወደስ፣ ቸኩሎ መራገም ከንቱ ሆኖ ሳለ፣ ኃይለኛ አለቆችና መሪዎች የዕለት መፈክራቸው ያደርጉታል። ይህ አገርን አያሳድግም። ህዝብን ነፃ አያደርግም። ጥንቃቄ ያሻዋል።ለህዝብ ተቆርቋሪ፣ ለሀገር አሳቢ የሚመስሉ በርካታ ግለሰቦች፣ ቡድኖችም ሆኑ መንግሥታት፣ እንደሚኖሩ አለመርሳት ተገቢ ነው። በርካታ ሃሳዊ-መሢሃን እንዳሉ ልብ ማለት ያስፈልጋል።
 የበግ ለምድ የለበሰ ቀበሮ ብቻ ሳይሆን፣ የቀበሮ ቆዳ የሚለብስ በግም እንደማይጠፋ ማወቅ ደግ ነው። ከነጋ ለማጨብጨብ ከመሸ ለመሳደብ የማይተኙ በርካታ የአለቃ ሚዜና አጃቢዎች “ሽቶው ውሃ ነው”  እስኪባሉ አንደኛ ማዕረግ ቦታ ሊቀመጡ ይችላሉ። የዛሬ ዕድሜ ግን በውሃ መስላ ሻማ ናት።
በሀገርና ህዝብ ጉዳይ የቲዮሪ አንጓች፣
የፖሊሲ መካሪ፣ የህግ አማካሪ፣ የቅርብ ተጠሪ፣ የሩቅ ተጧሪ የሆኑ ሰዎች፣ ቡድኖች፣  ፓርቲዎች፣ ሀገሮች ፍሬያቸው ብስል መስሎ ጥሬ፣ ምክራቸው አዛኝ መስሎ ገዳይ ከሆነ፣ “የሚስቴን ወገብ ይዞ የሚጨፍር ሚዜዬ አይደለም” የሚል ህዝብ እንዳለ ሊገነዘብ ይገባል።

ግራር፣ የጠቢባን መናኸሪያ ከተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) – አሽበርግ ፕሮግራም ጋር በመተባበር፣ “ሠዓሊትን ፍለጋ የተሰኘ ሴት ሠዓሊያንን  ማብቃት ላይ ያተኮረ ፕሮጀክት በይፋ አስጀምሯል።
ይህ ፕሮጀክት ሁሉን አቀፍ የሴት የሥነ ጥበብ ሙያተኞችን ብራንዳቸውንና የዲጂታል ሰብዕና ከማጎልበት ባሻገር ሚዛናዊ የባህል ምርቶችና አገልግሎቶች ስርጭት እንዲሁም የአርቲስቶችና የባህል ሙያተኞች ተንቀሳቀሶ የመስራት ዕድሎችን ለማጎልበት አንዲቻል፣ ሴት ሠዓሊያን በብራንዲንግ፣ ዲጂታል አካታችነትና የንቅናቄ መፍጠሪያ መድረኮች ያካተተ ነው።
“ሠዓሊትን ፍለጋ” የዘመኑ የዲጂታል አሰራር የፈጠረውን ዓለም አቀፍና የባሕልና ጥበብ እንዱስትሪ ትስስር ያለውን ዕድል በአግባቡ የተገነዘበ ፕሮጀክት ነው። በመሆኑም በዚህ ፕሮጀክት የሴት ሠዓሊያንን የብቃት ደረጃ ማጎልበትን፣ መሰረታዊ መብቶቻቸውን ለመጠበቅና በዲጂታል ሥነ ምህዳር ያለውን የተሳትፎ  ክፍተት ማጥበብ፤ የአርቲስቶች የፈጠራ ሃሳቦቻቸውን በነፃነት የሚገልፁበትን፣ በነፃነት ተንቀሳቅሶ የመስራትና ተመጣጣኝ  የገበያ እድሎችን ተደራሽ ማድረግን፣ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ጥበቃን እንዲሁም ፍትሃዊ ክፍያ ለጥበብ የፈጠራ ስራዎች እንዲኖር  አስተዋጽኦ ያበረክታል  ተብሏል። ይህ ፕሮጀክት የዲጂታል ክህሎት ስልጠናን በመስጠት የ20 ሴት ሠዓሊያንን በዲጂታል ስርዓት ውስጥ ያለውን የሥርዓተ ጾታ  ኢ-ፍትሃዊነት በማጥበብ፣ ስኬታማ የሙያ እድገት እንዲኖራቸው  እንደሚያስችል ተገልጿል ።
በፕሮጀክቱ  ለ20ዎቹ ሴት ሠዓሊያን ጋር በቅርበት በሚሰሩና ድጋፍ በሚያደርጉ ባለሙያዎች  በብራንዲንግ፣ በማህበራዊ ሚዲያ አመራር፣ ድረ ገጽ አጠቃቀም የይዘት ዝግጅትና የገበያ ልማት ስልቶች ላይ ያተኮሩ ስልጠናዎች  እንዲያገኙ ይደረጋል። ይህም ሠዓሊያኑ ስራዎቻቸውን ለታዳሚ ለማቅረብ ለሰፊው የጥበብ አፍቃሪው ማህበረሰብ ተደራሽ ለመሆንና በዓለም አቀፍ የዲጂታል ሥነ ምህዳር ውስጥ ያሉ አዳዲስ የገበያ ዕድሎችን ለመጠቀም ያስችላቸዋል።
ፕሮጀክቱ በፈጣን እድገት ላይ የዲጂታል ሽግግርና የሰብዕና ግንባታ ያለውን ሚና በመገንዘብ የሴት የጥበብ ሙያተኞችን ተሰሚነትን ከማጎልበት ባሻገር፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የባህል ምርቶች ማስፋፋትና የባህል ትውውቅን ለማጎልበት ይሰራል።
በተጨማሪም ሠዓሊትን ፍለጋ ለ100 በጥበብ ና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ወጣቶች የሥራ ዕድሎች የሚፈጥር ነው። ፕሮጀክቱ እያደጉ  የመጡ የቴክኖሎጂና ፈጠራ አቅሞችን በመገንዘብ፣ ቀጣዩን ትውልድ ለፈጠራ ማነሳሳትን ታሳቢ አድርጎ ይሰራል ተብሏል። ይህ ፕሮጀክት የባህልና የጥበብ ዘርፉ ላይ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ የፈጠራና ጥበባትን ስራዎች በማበረታታት፣ ብዝሃ ባህልን የሚያጎለብቱ ስራዎች ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነት  በተግባር የሚያሳይበት እንደሆነም ተነግሯል ፡፡
የግራር፣ የጠቢባን መናኸሪያ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሴሚናስ ሀደራ እንደገለፁት፤ “ ሠዓሊትን ፍለጋ ፕሮጀክት ሴት ሠዓሊያን ያላቸው ፈጠራና ተሰጥኦ ተገቢውን እውቅና አንዲያገኙ የሚያስችል ፕሮጀክት  ሲሆን   ግራር፣ የጠቢባን መናኸሪያ  ከዩኔስኮ - አሽበርግ ፕሮግራም ጋር በመተባበር  ሴት የሥነ ጥበብ ሙያተኞችን አቅም ለማጎልበትና ለማብቃት እንሰራለን ብለዋል ።
በዚህ ፕሮጀክት የዲጂታል ክህሎት ስልጠናን በመስጠት፣ የዲጂታል ሰብዕና መገንቢያ አሰራሮችን በማልማትና በመተግበር የሴት ሠዓሊያ በዲጂታል ስርዓት ውስጥ ያለውን የሥርዓተ ጾታ ኢፍትሃዊነት በማጥበብ እንዲሁም አካታች እና ፍትሃዊ የጥበብ እና ፈጠራ ሥነ ምህዳር እንዲጎለተ በመስራት ሴት ሠዓሊያኑ በዘመናዊው የዲጂታል ዓለም ውስጥ ጉልህ ድርሻ አንዲኖራቸው ድጋፍ ይደረግላቸዋል ተብሏል፡፡

Saturday, 09 March 2024 20:06

11ቢሊየን

ሰሞኑን ለመጀመሪያ ጊዜ 20 ግዙፍ ቦይንግ 777X-9 አውሮፕላኖች ለመግዛት ከቦይንግ ጋር ተፈራርሟል።
የአውሮፕላኖቹ ዋጋ እስከ 11ቢ. ዶላር ይገመታል
አውሮፕላኑ 50 የቢዝነስና 390 የኢኮኖሚ መቀመጫዎች አሉት
አየር መንገዱ አውሮፕላኖቹን በማዘዝ ከአፍሪካ ቀዳሚው ነው
እ.ኤ.አ ከ2027 እስከ 2030 አውሮፕላኖችን ይረከባል

መልዕክተኛው የፕሪቶሪያው ስምምነት አፈጻፀምን ይገመግማሉ ተብሏል

የአሜሪካ መንግሥት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሐመር፣ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች የተከሰቱ  ግጭቶች በድርድር እንዲፈቱ ለማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮችና   በመንግሥትና  በህወሓት መካከል የተደረሰው ስምምነት አፈጻጸም  ግምገማ ዙሪያ በአዲስ አበባ እየመከሩ ነው ። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ይፋ ባደረገው መግለጫ ላይ እንደተጠቆመው፤ ልዩ መልዕክተኛው  በአሁኑ ጊዜ በተባባሰው የአማራ ክልል ግጭትና ዓመታትን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ክልል አለመረጋጋት ዙሪያ ሰላም ለማምጣት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት ጋር  ይመክራሉ ተብሏል፡፡
በትግራይ ሲካሄድ የነበረውን ጦርነት ለማስቆም በተደረገው ጥረት ውስጥ ጉልህ ሚና እንደነበራቸው የሚነገርላቸው አምባሳደር ማይክ ሐመር፤ ደም አፋሳሹን የሰሜን ኢትዮጵያን የእስር በርስ ጦርነት ያስቆመውን የፕሪቶሪያውን ስምምነት አፈጻጸም በተመለከተ በአፍሪካ ኅብረት አስተናጋጅነት፣ ከየካቲት 28 አስከ መጋቢት 4 ቀን 2016 ዓ.ም. በሚካሄደው ግምገማ ላይ ተሣታፊ እንደሆኑም ተገልጿል። ከተፈረመ አንድ ዓመት ያለፈውን የፕሪቶሪያው ስምምነት የአፈጻጸም ሂደት በተመለከተ የስምምነቱ አሸማጋዮችና ታዛቢዎች የሚሳተፉበት ግምገማ እንደሚካሄድ ሲነገር ቆይቷል፡፡ ልዩ መልዕክተኛው  አምባሣደር ሐመር፣ ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ጋር  በመገናኘት  በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ ያለውን ግጭት ለማብቃት የሚደረጉ ጥረቶችን ለማፋጠን በሚያስችሉ ሁኔታዎችንና ግጭቱን በድርድር ለመፍታት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ እንደሚመክሩ የአሜሪካው  የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት፣ የአምባሳደር ሐመርን ጉዞ በተመለከተ ባወጣው መግለጫ ላይ አመልክቷል።
ካለፈው አመት ሐምሌ ወር ጀምሮ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር በሚገኘውና  ከፍተኛ አለመረጋጋት ውስጥ በገባው የአማራ ክልል ውስጥ በፌደራል መንግሥቱ ኃይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የሚካሄደው ግጭት መባባሱን ተከትሎ ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት  አሜሪካ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ  እንደምትገኝም መግለጫው ጠቁሟል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በመንግሥትና ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት እያለ በሚጠራው ታጣቂ ኃይል  መካከል  ያሉ ግጭቶችን ለማስቆምና ሰላም ለማውረድ የተደረጉ ሙከራዎች ውጤት ሳያመጡ መቅረታቸው አይዘነጋም፡፡ የፊታችን ረቡዕ ይጠናቀቃል ተብሎ በሚጠበቀው ውይይት፤ ግጭት ውስጥ ያሉ ሃይሎች ወደ ሠላማዊ  መንገዶች የሚመጡበትንና ችግሮቻቸውን በውይይት ለመፍታት የሚችሉበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ዕድል ይፈጠራል ተብሎ ይጠበቃል።

Page 2 of 695