Administrator

Administrator

መንግስት ለአስቸኳይ እርዳታ 33 ሚ. ዶላርቢያሰባስብም፣ ተመድ 230 ሚ. ዶላር ያስፈልጋል ብሏል
• “አብዛኛው ተረጂ የሚገኘው በኦሮምያ ክልል ነው”

   የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ በተከሰተው የዝናብ እጥረት ሳቢያ የምግብ እህል እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከዚህ በፊት ከተገመተው በላይ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንና 4.5 ሚሊዮን መድረሱን አስታወቀ፡፡
አንድ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣን በበኩላቸው፤ ችግሩን ለመፍታት ክልሎች ራሳቸው ከሚመድቡት በጀት በተጨማሪ መንግሥት 700 ሚ. ብር መድቦ ለተረጂዎች ድጋፍ ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ጠቅሰው ከተረጂዎች መካከል 40 በመቶ ያህሉ በኦሮምያ ክልል እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ አጃንስ ፍራን ፕሬስ ትናንት እንደዘገበው፣ በአመቱ የዝናብ መጠኑ ከተገመተው በታች መሆኑን ተከትሎ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከተገመተው 2.9 ሚሊዮን የ55 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 4.5 ሚሊዮን ደርሷል፡፡
በኢትዮጵያ የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሃላፊ ዴቪድ ዴል ኮንቴ እንዳሉት፤ በዝናብ እጥረቱ ክፉኛ የተጎዱት የአገሪቱ አካባቢዎች ምስራቃዊ አፋርና ደቡባዊ ሶማሌ ክልሎች ሲሆኑ በአንዳንድ የኦሮምያ፣ የትግራይና የአማራ ክልሎች አካባቢዎችም፣ ባልተለመደ ሁኔታ የከብቶች ግጦሽና የውሃ ሃብቶች እጥረት ተከስቷል፡፡በአሜሪካ መንግስት የሚደገፈው “ፋሚን ኧርሊ ዋርኒንግ ሲስተምስ ኔትወርክ” የተባለ የርሃብ ቅድመ ማስጠንቀቂያ የሚሰጥ ተቋምም፤ በኢትዮጵያ በርካታ እንስሳት በመኖ እጥረት ተጠቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ማስጠንቀቁንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡የኢትዮጵያ መንግስት ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ 33 ሚሊዮን ዶላር አሰባስቧል ያለው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ መንግስት በመጪዎቹ አራት ወራት ጊዜ ውስጥ 230 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው ማስታወቁን አመልክቷል፡፡የእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ሃላፊዎች ችግሩ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ምግብ የማከፋፈሉ እንቅስቃሴ ፈጣን አለመሆኑ እንዳሳሰባቸው ጠቁሞ፣ ለዚህ ችግር መከሰት አስተዋጽኦ ካበረከቱ ጉዳዮች መካከልም በጅቡቲ ወደብ ያለው መጣበብ አንዱ ነው ብሏል፡፡

- ፖሊስ በህገ ወጥነት የተጠረጠሩ 66 ሺህ ያህል ድረ ገጾችን እየመረመረ ነው
       - ቻይናውያን በአሜሪካ ላይ 700 ያህል የኢንተርኔት ጥቃቶችን ፈጽመዋል


     የቻይና ፖሊስ የአገሪቱን ደህንነት አደጋ ላይ በሚጥሉ አገር አቀፍና አለማቀፍ የኢንተርኔት ወንጀል ተግባራት ላይ ተሰማርተው ተገኝተዋል ያላቸውን 15 ሺህ ያህል ዜጎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የቻይና የደህንነት ሚኒስቴርን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ የአገሪቱ ፖሊስ ከኢንተርኔት ጋር የተያያዙ 7 ሺህ 400 የወንጀል ክሶችን ሲመረምር ቢቆይም የተጠቀሱት 15 ሺህ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር የዋሉት በምን ያህል ጊዜ ውስጥ እንደሆነ አልገለጸም፡፡
የቻይና መንግስት ባለፈው ወር ኢንተርኔትን ማጽዳት የተሰኘ መሰል ወንጀሎችን መከላከል የሚያስችል የስድስት ወራት ብሄራዊ ዘመቻ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን የጠቆመው ዘገባው፤ ተጠርጣሪዎችን በማሰር የተጀመረው እርምጃ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአገሪቱ የደህንነት ሚኒስቴር ማስታወቁን ገልጿል፡፡
ዘመቻው በኢንተርኔት የሚሰሩ ወንጀሎችን ከመከታተልና ተጠርጣሪዎችን ለፍርድ ከማቅረብ በተጨማሪ ተደራጅተው በኢንተርኔት ወንጀል የሚሰሩ ቡድኖችን የማጥፋት ተልዕኮ እንዳለውም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የቻይና ፖሊስ ህገወጥና ጉዳት የሚያስከትሉ መረጃዎችን በሚያስተላልፉ እንዲሁም የወሲብ፣ የጦር መሳሪያዎችና የቁማር ማስታወቂያዎችን በሚያሰራጩ 66 ሺህ ያህል የአገሪቱ ድረገጾች ላይ ምርመራ ሲያደርግ መቆየቱንም አስረድቷል፡፡
ኤንቢሲ ኒውስ በበኩሉ፤ የተደራጁ ቻይናውያን የኢንተርኔት ዘራፊዎች የአሜሪካን ከፍተኛ የደህንነት ባለስልጣናት የኢሜይል ቁልፍ ሰብረው በመግባት የተለያዩ የወንጀል ድርጊቶችን እንደፈጸሙ መረጋገጡን ዘግቧል፡፡
ቻይናውያን የኢንተርኔት አጭበርባሪዎች ባለፉት አምስት አመታት በአሜሪካ ላይ ለ700 ጊዜያት ያህል ጥቃት ፈጽመዋል ያለው ዘገባው፤ ከ600 በላይ የሚሆኑት ስኬታማ ጥቃቶች የተፈጸሙትም በአሜሪካ የመንግስት፣ የግልና የኩባንያ ድረገጾችና የኢሜል አድራሻዎች ላይ መሆኑንም ገልጿል፡፡

20 ኪሎ ሜትር ቁመት ይኖረዋል፣ “የጠፈር አሳንሰር” ይገጠምለታል
   ቶዝ ቴክኖሎጂ የተሰኘው የካናዳ የጠፈር ምርምር ቴክኖሎጂ ኩባንያ በዓለማችን ትልቁ እንደሚሆን የተነገረለትንና 20 ኪሎ ሜትር ቁመት ያለውን ሰማይ ጠቀስ ማማ በመገንባት፣ ረጅሙን የጠፈር አሳንሰር ሊዘረጋ መሆኑን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
የጠፈር ተመራማሪዎችን ያለ መንኮራኩር በቀጥታ ወደ ጠፈር ማጓጓዝ የሚችለው  አሳንሰር፤ ጠፈርተኞችን በመንኮራኩር ወደ ጠፈር ለመውሰድ ከሚያስፈልገው ነዳጅ 30 በመቶ ያህል ያነሰ ነዳጅ እንደሚጠቀምና ወጪ ቆጣቢ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
የጠፈር አሳንሰሩ ዲዛይነር የሆኑት ዶ/ር ብሬንዳን ኩይኔ እንዳሉት፣ ጠፈርተኞች በአሳንሰሩ ተሳፍረው ከመሬት በ20 ኪሎሜትሮች ርቆ ከሚገኘው የማማው አናት ላይ ከወጡ በኋላ፣ በቀላሉ በጠፈር አውሮፕላኖች እየተሳፈሩ ወደ ጠፈር ጠልቀው የሚገቡበትና ስራቸውን የሚያከናውኑበት ዕድል ይፈጠርላቸዋል፡፡
አሳንሰሩ የሚገጠምበት ሰማይ ጠቀስ ማማ፣ በአሁኑ ወቅት የአለማችን ረጅሙ ህንጻ በመሆን ክብረ ወሰን ይዞ ከሚገኘውና 830 ሜትር ርዝማኔ ካለው የዱባዩ ቡርጂ ከሊፋ ህንጻ በ20 እጥፍ ያህል ቁመቱ እንደሚረዝም የጠቆመው ዘገባው፤ ማማው  ከዚህ በተጨማሪም ለነፋስ ሃይል ማመንጫነት፣ ለኮሙኑኬሽንና ለቱሪዝም አገልግሎት እንደሚውልም ገልጿል፡፡
ማማው ቁመተ ረጅም ከመሆኑ ጋር በተያያዘ በንፋስ የመገንደስ አደጋ ሊገጥመው አይችልም ወይ ለሚለው የብዙዎች አስተያየት ምላሽ የሰጡት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ካሮሊን ሮበርትስ፤ ስጋት አይግባችሁ፣ መሰል አደጋዎችን መቋቋም እንዲችል አድርገን ነው ንድፉን የሰራነው ብለዋል፡፡
የአሜሪካ የፈጠራ መብቶች ቢሮ፤ የካናዳው ኩባንያ ላቀረበው ልዩ የሆነ የጠፈር ማማና አሳንሰር ፈጠራ እውቅና መስጠቱንና ፕሮጀክቱም ተቀባይነት ማግኘቱን ዘገባው አክሎ ጠቁሟል፡፡ 

  ፌስቡክ  በግማሽ ደቂቃ 5 ሺ 483 ዶላር ገቢ ያገኛል

   በድረ-ገጾች አማካይነት በአለማቀፍ ደረጃ የሚከናወነው “የኤሌክትሮኒክ ንግድ” በየግማሽ ደቂቃው በድምሩ የ1.2 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እያስገኘ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ዘ ሂንዱ ታይምስ ረቡዕ ዕለት ዘገበ፡፡
አሶቻም ዲሎይት የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም ሰሞኑን ይፋ ያደረገውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ላይ በሚገኘውና ትርፋማነቱ እየጨመረ በመጣው የኤሌክትሮኒክ ንግድ ከፍተኛ ገቢ እያገኙ ካሉት የአለማችን ታላላቅ ኩባንያዎች መካከል ቀዳሚነቱን የያዘው ታዋቂው የማህበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ ነው።
ፌስቡክ በኤሌክትሮኒክ ንግድ በየሰላሳ ሰከንዱ 5 ሺህ 483 ዶላር ገቢ ያገኛል ያለው ጥናቱ፤ ፒንተረስት እና ትዊተር የተባሉት የማህበራዊ ድረ ገጾችም በ4 ሺህ 504 እና በ4 ሺህ 308 ዶላር የግማሽ ደቂቃ ገቢ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃዎችን የያዙ የአለማችን የኤሌክትሮኒክ ንግድ ገቢ ቀዳሚ ኩባንያዎች ናቸው ብሏል፡፡
ማህበራዊ ድረገጾች መስፋፋታቸው በአለማቀፍ ደረጃ በኤሌክትሮኒክ ንግድ ገቢና ትርፍ ረገድ ከፍተኛ እድገት እንዲመዘገብ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል ያለው ዘገባው፤ ማህበራዊ ድረ ገጾቹ የኩባንያዎችን ምርቶችና አገልግሎቶች በተመለከተ ፈጣን መረጃዎችን በማሰራጨትና ንግዱን በስፋት በማቀላጠፍ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ዘገባው ገልጿል፡፡
ኤሌክትሮኒክ የክፍያ ስርአቶች በስፋት መዘርጋታቸውም ንግድ በአለማቀፍ ደረጃ የተቀላጠፈ እንዲሆንና ገዢና ሻጮችን ለአደጋ ከሚያጋልጠው የካሽ ግብይት ወደ ኤሌክትሮኒክ ክፍያ ፊታቸውን እንዲያዞሩ ያደረገ ሲሆን የኤሌክትሮኒክ ንግድ እንዲስፋፋም የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል ተብሏል፡፡

 ሌላ የልጅ ልጃቸውም በድብደባ ወንጀል ተከስሶ ነበር
   የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንትና የጸረ አፓርታይድ ታጋይ የኔልሰን ማንዴላ የልጅ ልጅ የሆነው ማንዴላ፣ አንዲትን ደቡብ አፍሪካዊት የ15 አመት ልጃገረድ አስገድዶ በመድፈር ወንጀል ተከስሶ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት መቅረቡን ዘ ጋርዲያን ዘገበ።
ልጃገረዷን ጆሃንስበርግ ውስጥ በሚገኝ አንድ መጠጥ ቤት ውስጥ አስገድዶ ደፍሯል በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው የ24 አመቱ ቡሶ ማንዴላ፤ ባለፈው ሰኞ  ለመጀመሪያ ጊዜ ፍርድ ቤት የቀረበ ሲሆን በሳምንቱ መጨረሻ በጆሃንስበርግ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርቦ ጉዳዩ እንደሚታይ ይጠበቃል፡፡
ቡሶ ማንዴላ ከሁለት ሳምንታት በፊት ልጃገረዷ በመጠጥ ቤቱ መጸዳጃ ቤት ውስጥ ሳለች ተከታትሏት ሄዶ አስገድዶ ደፍሯታል መባሉን የጠቆመው ዘገባው፣ ጥቃቱ የደረሰባት ልጃገረድ ክስ መመስረቷን ተከትሎ ባለፈው ሳምንት በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉንም አስታውሷል፡፡
ተጠርጣሪው የማንዴላ የልጅ ልጅ ስለሆነ ብቻ ከሌሎች ወንጀለኞች ተለይቶ የሚታይበት ምክንያት የለም ያለው የጆሃንስበርግ ፖሊስ፤ እንደማንኛውም ተጠርጣሪ እንደሚያዝና ጉዳዩ በፍርድ ቤት ተጣርቶ የአገሪቱ ህግ ባስቀመጠው መሰረት ተገቢው ውሳኔ እንደሚሰጠው አስታውቋል፡፡
ተከሳሹ ማንዴላ ከሶስቱ ሚስቶቻቸው የመጀመሪያዋ ከሆነችው ኤቭሊን ማሴ ከወለዷቸው ልጆች ከአንዷ እንደተወለደና አያቱ ማንዴላ በህይወት ሳሉ በተናዘዙለት መሰረት 300 ሺህ ዶላር እንደወረሰ ያስታወሰው ዘገባው፤ ማንድላ ማንዴላ የተባለው ሌላ የኔልሰን ማንዴላ የልጅ ልጅም ከወራት በፊት አንድን የ40 አመት ደቡብ አፍሪካዊ ደብድቧል በሚል ተከሶ ፍርድ ቤት ቀርቦ እንደነበርም አክሎ ገልጿል፡፡

  ባለፈው ሳምንት ለገበያ የቀረበው ሌላው መፅሐፍ በደራሲ ተስፋዬ ገብረሥላሴ የተደረሰው “ጣፊናስ” የተሰኘ ልብወለድ ነው፡፡ አሁን በህይወት የሌለው ደራሲና ሃያሲ መስፍን ኃብተማርያም በመጽሐፉ የጀርባ ሽፋን ላይ በሰጠው አስተያየት፤ “…በታሪኩ ሂደት ለጥቅም የቆሙና ከአገርና ከህዝብ እንቅደም ያሉ ኢትዮጵያውያን የመኖራቸውን ያህል ለአገራቸው የሚሟገቱና መስዋዕትነት ለመክፈል የቆረጡ ውድ የኢትዮጵያ ልጆችም ስሜትን ወጥረው ይይዛሉ…” ብሏል፡፡ የቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ ያሳተመው “ጣፊናስ”፤ 308 ገፆች ያሉት ሲሆን ዋጋው 68 ብር ነው፡፡

የጥበብ መጀመሪያ ነገሮችን በትክክለኛ ስማቸው መጥራት ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል
ሃቀኛ ዜጋ በራሱአገር ስደተኛ ነው፡፡
የአሜሪካውያን አባባል
ላንተ ሲል የዋሸ፣ ባንተ ላይም መዋሸቱ አይቀርም፡፡
የቦስንያ አባባል
ተረት ወደ እውነታ የሚያሻግር ድልድይ ነው።
የአረቦች አባባል
የእውነት ባሪያ የሆነ ሰው ነፃ ነው፡፡
የአረቦች አባባል
ሁልጊዜ እውነትን በቀልድ መልክ ተናገር፡፡
የአርመናውያን አባባል
ከሚያቆስል እውነት የሚፈውስ ውሸት ይሻላል፡፡
የቼኮች አባባል
እውነት ሁልጊዜ ቤት አልባ ናት፡፡
የዳኒሾች አባባል
ያለጊዜው የሚነገር እውነት አደገኛ ነው፡፡
የግሪካውያን አባባል
እውነትን አለመግለፅ ወርቅን መደበቅ ነው።
የግሪካውያን አባባል
እውነትን በራሷ ድምፅ ታውቃታለህ፡፡
የይሁዳውያን አባባል
ከዋሾ ጓደኛ ሃቀኛ ጠላት ይሻላል፡፡
የጀርመናውያን አባባል
የጎረቤትህን ሃቀኝነት በራስህ አትለካ፡፡
የአሜሪካውያን አባባል
እግዚአብሔር በሃቀኛ ልብ ውስጥ ይኖራል።
የጃፓናውያን አባባል

[የመጽሐፍ ቅኝት በአብነት ስሜ ]

    መቅድም
ወሪሳ በሚል ርእስ በሐምሌ ወር መጨረሻ ላይ 240 ገጾች ያሉት የአማርኛ ልቦለድ ታትሟል። የልቦለዱ ደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ ይባላል። ይህ ብእሮግ የዚህ መጽሐፍ ቅኝት ነው። ቅኝቱን የማደርገው ልቦለድን-እንደ-ህልም-መፍታት በሚል ጽንሰ-ሐሳባዊ ማእቀፍ ውስጥ ነው። አንድ ደራሲ ከግለሰብ፣ ከቤተሰብና ከማህበረሰብ አልፎ የኅብረተሰብንም ህልም የሚያልምበት ጊዜ አለ። ይህ ሲሆን ደግሞ ደራሲ እንደ ህልም ዓላሚ፣ ድርሰት እንደ ህልም፣ ኀያሲ ደግሞ እንደ ህልም ፈች ይታያል።
ህልም እና ልቦለድ
የሰው ልጅ ሆኖ ህልም የማያልም የለም ይባላል። ችግሩ ምን ያህሉን ያስታውሰዋል ነው እንጂ ሁሉም ሰው ያልማል። ህልም ለጤናችንም ወሳኝ ነው ይባላል። የበቂ እንቅልፍ እጦት ጤናን እንደሚያቃውስ ይታወቃል። የዚህ ችግር ሁነኛው መንስዔ የእንቅልፍ ጊዜ ማጣቱ ሳይሆን እንዲያውም የህልም ጊዜ ማጣቱ እንደሆነ ከቅርብ ጊዜ ጥናትና ምርምሮች መረዳት ይቻላል። የህልም አስፈላጊነት እስከዚህም ይደርሳል።
በመስኩ ያሉ ባለሙያዎች ህልምን በየጊዜው መመዝገብ መቻል ጠቀሜታው የትየለሌ ነው ይላሉ። ከህልም ጥቅሞች ውስጥ አንዱ ላይ ብቻ እናትኩር። የሰው ልጅ በዕለት ተዕለት ህይወቱ በውጣ ውረዶች ውስጥ ያልፋል፤ ከአስጨናቂ ጉዳዮችና ጣጣዎች ጋር ይጋፈጣል። ታድያ አንዳንዴም ቢሆን ችግሩንና ህመሙን በግላጭ አፍርጦ ለማየት ጊዜ ያጣል። ያንን ስውሩ አእምሮ የሚባለው መዝግቦ ይይዝለታል።  ከጊዜ ማጣት ሌላ ድፍረትም የሚጠፋበት ጊዜ አለ።  የሰው ልጅ ጭንቁን፣ ጣሩንና  ሰቆቃውን ሆን ብሎ ለመርሳትና ከህይወቱ መዝገብ ውስጥ ለመሰረዝና ላለማስታወስ የሚጥርበትም ጊዜ አለ። ንቁው የአእምሮ ክፍል የሸሸውንና ያሸሸውን ስውሩ አእምሮ ደብቆ ይይዘዋል። ስለዚህ ችግሩ ይሸሸጋል እንጂ ጠፍቶ አይጠፋም፤የተረሳ ይመስላል እንጂ ተረስቶ አይረሳም።
ቀላሉንም ሆነ ከባዱን (አንዳንዴ ሰቅጣጩንም) ችግር ማታ አረፍ ባልን ጊዜ እየተግተለተለ ከፊታችን ይደቀናል። በዚህ ወቅት ሐሳብን እናመነዥካለን። የቻልነውን እንቆቅልሽ እንፈታለን፤ያልቻልነውን ለጊዜውም ቢሆን እናልፈዋለን። የፈራነውን ደግሞ እንሸሽገዋለን፤እንርቀዋለን።
በእውን ያልፈታነውን የህይወትና የኑሮ እንቆቅልሽ በህልም እናገኘዋለን። ለችግራችን መፍትሔ ስለምናገኝበት ነው ህልማችንን የምንመረምረው። አንዳንዱ ህልም ፊት ለፊትና ግልጽ ስለአልሆነ ህልም-ፈቺ እንፈልጋለን። የእእምሮ ጤና ችግር ያጋጠማቸውን ህሙማንም በህልማቸው ለመርዳት የሚደረግ የህክምና ሳይንስ አለ።
በህልም ውስጥ ትውስታ አለ። ትውስታው የትላንት፣ የበቀደም ብቻ ሳይሆን ያምና እና የካችአምና ሊሆን ይችላል። ከዚያም አልፎ ሀያና አርባ ዓመት ወደ ኋላ  የምንጓዝበት አጋጣሚ አለ። ይህ እንግዲህ በህይወት ዘመናችን ስለሆነው ነው። ትውስታ ከህይወት ዘመን ያለፈም እንደሚሆን በዘርፉ ጥናቶች በተደጋጋሚ ተጠቁሟል።
ይህ ምን ማለት ነው? አንድ ሰው የራሱን ብቻ ሳይሆን የአያቱን፣ የቅድመ አያቱንና  በጣም ወደ ኋላ ሔዶ የዘርማንዘሩን ወይም የነገዱን የጥንት ውሎና ክራሞት የሚያስታውስበት አጋጣሚ የትየለሌ ነው። ታዲያ ትውስታው ከሚገለጥባቸው መንገዶች ውስጥ ህልም አንዱና ዋነኛው ነው።
አሁን የህልምና የድርሰትን ቁርኝት እንይ። አንድ ደራሲ በፈጠራ ጽሑፉ ላይ በሚያተኮርበት ጊዜ ተመስጦው ህልምን ከማየት ጋር ይመሳሰላል። በዚህ አተያይ ደራሲው በድርሰቱ የሚያቀርብልን ህልሙን ነው ማለት ይሆናል። ህልሙ ደስ የሚልና ግልፅ የሚሆንበት ጊዜ አለ። በዚህ ጊዜ ፍችና ትንታኔ ውስጥ አንገባም። የአንዳንዱ ደራሲ ህልም ግን ከተራ ህልም ያለፈ ይሆናል። እንደዚህ ያለው ደራሲ የሀገሩን ህልም ነው የሚያልመው። በሌላ አነጋገር ደራሲው “ነቢይ” ነው፤ድርሰቱም “ትንቢት” ነው።
የአእምሮ ጤና ችግር ያጋጠመውን ግለሰብ ለማከም ህልሙ እየተመዘገበ ይመረመራል። የችግሩ ነቅ የት ነው? ህመሙን ያመጣው እሾህ የተተከለው ከምን ስፍራ ነው? በሌላ አነጋገር ሰንኮፉ ይፈለጋል። ሰንኮፉ ሲነቀል ብቻ ነው ቁስሉ ሙሉ በሙሉ ሊሽርና ህመሙም ሊድን የሚችለው።
የግለሰቦች ስብስብ ነችና ሀገርም እንደ ግለሰብ ትጨነቃለች፤በሰቆቃ ውስጥ ታልፋለች፤ ትቃትታለች፤ትጓጉራለች። በአንድ ቃልም ትታመማለች። ወይም ደግሞ ሁላችንም እንደ ሀገር እንደ ኅብረተሰብ እንታመማለን። ሁሉም ሰው ግን ሊታመም አይችልም። የሀገርን ህመም የሚታመም ደራሲ አለ። እንዲህ ዓይነቱ ደራሲ ህመማችንን ይታመማል፤ ህመማችንን ያልማል። ህልሙ ውስጥ ህመሙ አለ። ድርሰቱ ውስጥ ደግሞ ህልሙ አለ። ድርሰቱ የሀገር ህልም ነው። የሀገርን ችግርና ህመም ደግሞ በድርሰቱ ህልም ውስጥ መመርመር አለብን። የድርሰቱን ፍችና አንድምታ ትርጓሜ መውጣት ማለት ህመማችንን መመርመር ማለት ነው፤ መድኃኒትም ከዚያ ይገኛል። እኛ አልታመም ያልነውን ህመም ደራሲው ይታመማል። እኛ አላልም ያልነውን ህልም ደራሲው ያልማል። ህልሙን መስማትና መፍታት የኛ ፈንታ ነው። መፍታቱ ቢቸግረን እንኳ መስማቱን ግን መስማት አለብን። መፍታቱ ባስቸገረ ጊዜ ኀያሲ የዚህን ሥራ መስራት አለበት። ይህ የሒስ አንዱ ፈርጅ ነው።
በሀገራችን ተንሰራፍቶ ያለው የልቦለድ ሒስ ስልት በአብዛኛው መዋቅራዊ ነው። የትልም፣ የግጭት፣ የገፀባህርያት አሳሳል፣ የቋንቋ አጠቃቀምና የትረካ ቴክኒክ በመሳሰሉት ላይ ያተኩራል። ከዚህ የሚያፈነግጠው አልፎ፣ አልፎ ነው።
በቀደሙት ዘመናት በነበሩ አንዳንድ የአማርኛ ልቦለዶች ውስጥ ማኅበራዊ ሕፀፆች በተምሳሌታዊ አካሔድ ተገልጠዋል። በቅድመ-ሳንሱርና በድኅረ-ሳንሱር (አንዳንዱ የብዙኃኑ ሳንሱርና ትርጓሜ ነው) ይኼ ንጉሡን ለመንካት ነው፤ይኼ ፕሬዚደንቱን ለማሽሟጠጥ ነው እየተባለ ተነግሯል። የልቦለዱ ደራሲ ከዋናው ገፀባህሪ ጋርም እየተነፃፀረ ሲታይ ቆይቷል። በበዓሉ ግርማ ኦሮማይ ውስጥ ያሉ ገፀባህርያትም በወቅቱ ከነበሩ ባለሥልጣናት ጋር ያላቸው ተመሳስሎ በየደረጃው ተተንትኗል። ሒስ ግን ከዚህም በላይ መሄድ አለበት። ለምሳሌ በዳኛቸው ወርቁ አደፍርስ ውስጥ በመጨረሻ ወደ ገዳም የምታመራው ፂወኔ፤በሀገር ደረጃ ደራሲው እንደ ኢትዮጵያ ሳያያት አልቀረም ተብሎ እንደተገመተው ዓይነትና ከዚያም ያለፈ የአንድምታ ትርጓሜ ያስፈልገናል።
የዓለማየሁ ገላጋይ ወሪሳ
ወሪሳ በአንደኛ መደብ የተተረከ ልቦለድ ነው። ተራኪው የአማርኛ አስተማሪ ነኝ ይላል፤ ሊቅነቱ ግን ተረት ላይ ነው። በታሪኩ ውስጥ በቅርቡ ከክፍለሀገር ወደ አዲስ አበባ የተቀየረ አስተማሪ ነው። የተራኪው የአክስት ልጅ እስር ቤት ገብቷል። አክስት ስትሞት፣“ልጇ ከከርቸሌ እስኪወጣ ቤቱን እንድጠብቅላት ተናዘዘችብኝ” ይላል ተራኪው። ተራኪው በዚህ አኳኋን ነው ወሪሳ የሚባል ሰፈር የገባው። ወሪሳ ከእሪ በከንቱ የሚጎራበት የ“ወሮበሎች” ሰፈር ነው። እንዲህ የሚባል ሰፈር አዲሳባ ውስጥ ይኑር-አይኑር አላቅም። ከሌለ  የደራሲው ምናባዊ ፈጠራ ነው። የሰፈሩ የአስፈሪነት ገለፃ በመጽሐፉ የመጀመሪያ ዓረፍተ ነገር ይጀምራል። ተራኪው ገና ሲጀምር፣ “እኔ እንደ ኢየሱስ በወንበዴዎች መካከል ተቸንክሬአለሁ”ይለናል። ሰፈሩ ባጭር ቃል ሲዖል ነው፤ያስፈራል፤በጣም ያስፈራል። ተስፋ ያስቆርጣል።
ወሪሳ ተከታታይነትና ተለጣጣቂነት ያላቸው አስፈሪ ህልሞች የታጨቁበት ማህደር ነው። ህልሞቹ የተዘፈቅንበት ማኅበራዊ ውጥንቅጥ ነፀብራቅ ናቸው። ምን ያህል ወርደናል! ምን ያህል ተዋርደናል! ምን ያህል በክተናል! ያስብላሉ። የወሪሳ ህልሞች “እገሌ የጎዳና ተዳዳሪውን፣እገሌ የተማረውን፣ እገሌ ካድሬውን፣ እገሌ ተቃዋሚውን፣ እገሌ ገዥውን ፓርቲ፣ እገሌ ቤተክህነቱን ይወክላል” በሚል ብዙም ረብ በሌለው ፈሊጥ መፈታት ያለባቸው አይደሉም።
ህልሞቹ በትእምርታዊነት (ሲምቦሊዝም) የተሞሉ ናቸው። ተራ ቅዥት አይደሉም። በቅጡ ሊተነተኑ ይገባል። በትንተናው ደግሞ ደራሲው እንዲህ ሊል ፈልጎ ነው የሚለውንም አካሄድ ለጊዜውም ቢሆን ወደ ጎን ገፋ ማድረግ አለብን። እኔ እንደሚመስለኝ ደራሲው ምንም ሊል አልፈለገም። ህልሙን ነው የጻፈው። ህልሙ ደግሞ የሀገርና የኅብረተሰብ ህልም ነው። እኛ ማድረግ የሚገባን ህልሙን ማንበብና  መፍታት፣አንድም እንዲህ ማለት ነው እያልን ከሦስትና ከአራት የዘለሉ ትርጓሜዎች ማውጣት። ህልሙ ውስጥ ያገር ህመም አለ። ያን ያገር ህመም ሰንኮፍ መመርመር፣ ማመልከትና መንቀልም አለብን። ሌላው አማራጭ ሸፋፍኖ መተው ነው። ወይም ደግሞ ህመማችንን የታመመልንን ደራሲ ማንቋሸሽና ማውገዝ። ሌላ ደራሲ እስኪታመምልን መጠበቅ።
የወሪሳ ጥቂት አንድምታዎች
በወሪሳ ታሪክ ውስጥ ተራኪውን በብዙ ሺህ ትብታቦች አስረው የቁም ስቃዩን የሚያሳዩት አንድ ገፀባህሪ አሉ። አምበርብር ይባላሉ። በአባትም ሆነ በእናት ከሰው ልጅ የተወለዱ አይመስልም። ዋናውን አስማዲዮስ ቁጭ ነው። ለነገሩ የሰው ልጅ ከዲያብሎስ ተንኮልና ክፋት በላይም እንደሄደ እናውቃለን። አምበርብር ሥጋ የለበሰውን ዲያብሎስ ያስንቃሉ። አንደበታቸው ውስጥ ሀምሳ ሺህ እባብ ያለ ይመስለኛል። እንደዚህ ዓይነቱ ሰው በምድራችን ላይ ይኖራል ወይ ብዬ ለመገመት አልቸገርም፤ሞልቷል። ሁላችንም ወደዚያው እያመራን ይመስለኛል። አንበርብር የሁላችንም ወኪል ናቸው። ለነገሩ የወሪሳ ሰፈር ሰዎች ሁሉ ከሰውነት ክብር ወርደዋል። ሁሉም ደግሞ የኅብረተሰባችን ነፀብራቅ ናቸው። ገሀዱን እውነታ ነው በወሪሳ ህልም ውስጥ የምናየው።
ተራኪው የአማርኛ አስተማሪ የገባበት ውጥንቅጥ በጣም፣ እጅግ በጣም የሚያስፈራ ብቻ አይደለም። የሚሰቀጥጥና የሚዘገንን ነው። መጽሐፉን ሳነብ ከአስፈሪ ህልም ውስጥ ለመባነን እንደሚጓጉር ሰው ሆኜ ነው። እንደዚህ ስል በዕድሜ ገፋ ያልኩ ጎልማሳ እንደሆንኩ ልብ በሉ። ተራኪው ታምሟል፤ ይጓጉራል፤ ዛር እንደሰፈረበት ሰው መውጫ ቀዳዳ አጥቷል። ህመሙ የሁላችንም ህመም ነው። ተራኪው የታመመውን ህመም ሁላችንም ታምመናል። አምበርብር ተራኪውን እንደ ክፉ ዛር ተቆራኝተውታል። ተራኪው የገባበት ጣጣ በክፉ ዛር ተይዞ ባርያና አገልጋይ ከሆነ ሰው ጋር ይመሳሰልብኛል። የተራኪው ታላቅ ተስፋ የሚያንሰራራው አምበርብር ታመው ለሞት የተቃረቡ በመሰሉ ጊዜ ነው። ሰውዬው የበደሏቸውን ሰዎች እየጠሩ ይቅርታ ይጠይቃሉ። የይቅርታቸው መቋጫ ግን እርግማን ነው። ተበዳዩን መልሰው አጥፊና ተፀፃች ያደርጉታል። ይባስ ብለው ሊጠይቃቸው የተሰበሰበውን የጎረቤት ሰው ራእይ አየሁ ይሉታል። የእሪ በከንቱ ሰው አምበርብርን ታመው ባለመጠየቁ ምክንያት እግዚአብሔር እንዲህ ይላችኋል፤ “የእሪ በከንቱ ሰው ታምሜ ጠየቅኸኝ? ተርቤ አበላኸኝ? ታርዤ አለበስኸኝ? ይላል እግዚአብሔር” በዚህ ሳቢያ የሰፈሩ ሰው አምበርብርን ምግብ እየያዘ መጠየቅና መንከባከብ ይጀምራል። በሦስት ቀን ውስጥ እሰበሰባለሁ ያሉት ሰውም ዕድሜያቸው እየረዘመ ይሔዳል።
እኔ ህልም ነው ባልኩት የወሪሳ ልቦለድ ውስጥ ያሉት የአምበርብር ባህሪ በብዙ መልኩ ሊተረጎም የሚችል ነው። አምበርብር የአንድ በሽታ ትእምርት ናቸው። ይኼ በሽታ ክብራችንን የገፈፈ የትንሽነት፣ የአጭበርባሪነት፣ የተንኮል፣ የሤራ ነቀርሳ ነው። አምበርብር በሽታችን ናቸው። ጣጠኛው ተራኪ፣እንደዚሁም የወሪሳና የእሪበከንቱ ሰው አምበርብርን ሊገላገላቸው አልቻለም። ይባስ ብሎ እሳቸው ባጠፉት ጥፋተኛ፣ እሳቸው በበደሉት በደለኛ ሆነ። በኩነኔያቸውም ተኮነነ፤ ተፀፀተ። ከሞት ደጃፍ ነኝ ያሉትን ሰው (ይኸ ሌላው ተንኮላቸው ነው) እድሜ ሊቀጥልላቸው ይሮጥ ገባ።
ይኸ ቀድሞ የገባንበትና አሁን የምንዳክርበት ጣጣ ነው። ለዘመናት የነበሩንን ገዢዎች ጥፋትና ኀጢአት እኛው ተሸክመናል። ክፉ መሪ ሲነሳ አምላክ ስለ ጥፋታችን ያመጣብን ቅጣት ነው እንላለን። ስለ አረመኔ መሪዎቻችን እንማልዳለን፤ እንፀልያለን። የእግዚአብሔር ሥዩም ነኝ ካለ ለዲያቢሎስም እንሰግዳለን። መቼም ዲያብሎስማ፣ ዲያብሎስ ነኝ ብሎ አይመጣም።
ሶሻሊዝም የሚባል ሥርዓት አምጥተን መከራችንን በላን። አይ፣ ጥፋቱ የኛ ሆነ እንጂ “ሶሻሊዝም” የተባለ ሥርዓትማ እንከን አይወጣለትም ነበር ብለን ሙሾ ተቀመጥን። መንግሥቱ ኃይለማርያም “ጥሎን ጠፋ፤ ጥሎን ፈረጠጠ” ብለን እስከ አሁንም ድረስ የምናላዝን አለን። ሌሎችም፣ “ጥሏችሁ ጠፋ” እያሉ ሆድ ያስብሱናል። ኃይለሥላሴ ከሞቱ ፀሐይ ትጨልማለች፤ መንግሥቱ ሥልጣን ከለቀቀ ኢትዮጵያ ትፈርሳለች እያልን ዘምረናል። ሰው እንዴት ከበሽታው መገላገልን ይፈራል? በሽታ ተውሳክ ነው፤ ተደራቢ ነው፤ ይበላናል። ቀስ በቀስም ያጠፋናል። ከበሽታ አምጪ ተውሳኮች ውስጥ ቫይረስና ባክቴሪያ የሚባሉ አሉ ሲባል እሰማለሁ። ታዲያ በሽታ አምጪ ለሆኑ (ሰላማዊዎችም አሉ ይባላል) ባክቴሪያዎችና ቫይረሶች የምናዝን ህዝቦች አይምሮአችን ጤነኛ ነው? ለሚያሳድዱኣቸው ጅቦች የሚፀልዩ አህዮች ጤነኞች ናቸው? ሙጀሌን መንግሎ ማውጣት እንጂ ማስታመም ያስፈልጋል? ለሙጀሌ ይፀለያል?
የዛሬ አስር ዓመት ገደማ የኤችአይቪ ምርመራ አድርገው ነፃ የተባሉ ሴት “ባይልልኝ ነው” ብለው እንዳዘኑ በቀልድ መልክ የተነገረ እውነተኛ ታሪክ ሰምቻለሁ። ይኸ ነገር የብዙዎቻችን አባዜ እንደሆነ እገምታለሁ። ለሌላው ከማዘን ተቸግረን እንዲታዘንልን የምንፈልግ ብዙ አለን። በዘመኑ ቋንቋ የተረጂነት መንፈስ የሚሉት ይኸ ሳይሆን አይቀርም። በእዚሁ በእኛ አገር ባህታዊያንና መናኞች ዓለምን የናቁ ናቸው። ገላቸውንና ልብሳቸውን አያጥቡም፤ ቅማልም አይገድሉም። ዓለምን ያልናቅን ደግሞ ሌሎች የቅማል ዓይነቶችን ነው ይዘን የምንዞር።ይኸ ነገር በሁሉም የሰው ልጅ ውስጥ ያለ የባህሪ እንከን ነው። ፈረንጅና ሀበሻ አይልም። በሥነልቦና ትንተና ውስጥ የስኬታማነት ፍርሀት የሚባል ነገር አለ። ስኬታማ መሆንን፣ ማሸነፍን፣ መበልፀግን የሚፈሩ ሰዎች አሉ። ፍርሀታቸው ከነሱ በላይ ያሉ ሰዎች እንዳይጠሏቸው ነው። እነዚህ ስኬታማ ከሆኑ የሌላ ባርያ መሆናቸው ያቆማል። የባርያ አሳዳሪዎችም ይታመማሉ። ነገሩ፣“ሞኝን ማን ይጠላዋል” ዓይነት ነው።
አንድ የዛሬ ሀያ አምስት ዓመት ገደማ ያነበብኩት መጽሐፍ አለ። “Flowers for Algernon” ይባላል። የሳይንስ ልቦለድ ነው። ዋናው ገፀባህሪ የአእምሮ ዕድገት ዝግመት አለበት። ተራኪው እሱ ራሱ ነው።  በአንድ ዳቦ ቤት ተላላኪ ሆኖ ይሠራ ነበር።  የሰውን ልጅ የአእምሮ ችሎታ በህክምና ከፍ ማድረግ ይቻላል ብለው የተነሱ ሳይንቲስቶች፣በተራኪው አእምሮ ላይ የቀዶ ጥገና ያደርጋሉ። የልጁ የአእምሮ ችሎታ ሰማይ ጥግ ይደርሳል። በዚያው ልክ ደግሞ ቁጡ ይሆናል። ብቸኛ ይሆናል። ልቦለዱ የዚህ ሰው የዕለት ማስታወሻዎቹ ስብስብ ነው። ታዲያ በአንደኛው የዕለት ማስታወሻው ላይ ከዚህ ቀጥሎ ያለውን የሚመስል ሐሳብ ይጽፋል፤ “ድሮ “ሞሮን” እያለሁ ሰዎች ይወዱኝ ነበር። ዙሪያዬን ከበው ይስቃሉ። እኔም ደስተኛ ነበርኩ። አሁን ግን ብቻዬን ነኝ። ይከፋኛል። ሰው እንደ ድሮው አይወደኝም፤ አይጠጋኝም።”
እንግዲህ መወደድ የፈለገ ሰው ከሰውነት ተራ ይወጣል። ዝቅ ይላል። ትንሽ ይሆናል። ፍቅርና ሀዘኔታ አይጠገብም። ሱስ ይሆናል። ትንሽ ያደርጋል። ሁሌም ህፃን ሆኖ የመቅረትን አደጋ ይጋርጥብናል። ስንኩል ያደርገናል። ለማኝ እንሆናለን።
ኢትዮጵያ ክፋትና ክፉ ሰው አሸንፎ የሚኖርባት አገር ነች። ጀግና ነን እንላለን እንጂ እንደኛ ያለ ፈሪ ህዝብ የለም። ትንሽ ክፋትና ትንሽ ድፍረት ያለው ሁሉ ነው እያርበደበደ ሲገዛን የኖረው። ጀግና ብንሆንማ ሁላችንም እንነግሥ ነበር፤ ሁሉም ወንድ ንጉሥ፣ ሁሏም ሴት ደግሞ ንግሥት ትሆን ነበር። ጀግና ብንሆንማ መሪነት የሥራ ድርሻ ብቻ ይሆን ነበር። ጀግና ብንሆንማ መሪያችን ደመወዝ የምንከፍለው አገልጋይ ብቻ ይሆን ነበር። ጀግና ጠቢብም ነው፤እኛ ጥበብ የሚባል ነገርም አልነበረን። ክርስትናን ከማንም ቀድመን ተቀበልን እንላለን። ሁለት ሺህ ዓመት ግን ሰይጣን ነው በእግዚአብሔር ስም ሲገዛን የኖረው። ይህ ጥበብ ቢኖረን ኖሮ እንዲያ አይሆንም ነበር። አሜሪካ ጀግና ናችሁ ብትል ጠላትዋን እንድንወጋላት ነው። አምበርብርም መጣባቸው የተባለውን ባላንጣቸውን እንዲገድልላቸው ሲሉ ተራኪውን ያልሆነውን ጀግንነት ያላብሱታል። ፈረንጆች ጥበበኞች ናችሁ ቢሉን ሸቀጣቸውን ለመሸጥ ነው። ከተራበ ልጁ አፍ ቀምቶ ወተት የሚሸጥና መጫወቻ ቆርቆሮ የሚገዛ ህዝብ ሞኝና ተላላ እንጂ ጥበበኛና ጀግና አይደለም። ከባድ የሆነውን የምድር ወገብ የፀሐይ ግለት እንዲከላከልበት ተፈጥሮ የቸረችውን አፍሪካዊ ጥቁርነትና ከርዳዳ ፀጉሩን፣ የምድር ዋልታ ሰዎች የብርድ መከላከያ ወደሆነው ፈረንጃዊ ነጭና ለስላሳ ፀጉር የሚቀይርለት ቀለምና ቅባት ለመግዢያ ሲል መሬቱን፣ ክብሩንና ነፍሱን የሚሸጥ ህዝብ፤ጥበበኛና ጀግና አይደለም። እርስ በራሱ እየተፈጃጀ የፈረንጅ ታንክና ጠመንጃ የሚያሻሽጥና የሚሸምት፣በርሱም የሚፎክር ህዝብ ጥበበኛና ጀግና አይደለም። ነብር ሲያይ ፍየል፣ ጅብ ሲያይ አህያ፣ ፍየል ሲያይ ቅጠል፣ ድመት ሲያይ አይጥ፣ ተኩላ ሲያይ በግ፣ እሳት ሲያይ ገለባ የሚሆን ህዝብ ጥበበኛና ጀግና አይደለም። ዲሞክራሲን፣ ልማትንና ትምህርትን በልመና አገኛለሁ የሚል ህዝብ ጥበበኛና ጀግና አይደለም።
ይኸ ሸፍነንና ደብቀን የምናባብለው ቁስላችን ነው።  ይኸ ቁስል መገለጥ አለበት። መታጠብ አለበት። መታከም አለበት። መሻር አለበት። ቁስላችን በተነካ ቁጥር የምንጮህ ከሆነ ግን ምን ግዜም አንድንም። ምናልባት አንዱ ጀግንነታችን ቁስላችንን በነካውና በገለጠው ላይ ይመስለኛል። ለዚያ ጊዜ እንበረታለን። ውዳሴ ከንቱ ለሚመግበን ብቻ የምናጨበጭብ ተላላዎች ነን።
(ይቀጥላል)

ሻይ አይጠጡ
ሻይ በሰውነታችን ውስጥ ከፍተኛ መጠን ያለው አሲድ እንዲፈጠር ያደርጋል፡፡ ይህ አሲድም በተመገብነው ምግብ ውስጥ ያሉ ፕሮቲኖች እንዲጠነክሩና አልፈጭ እንዲሉ ያደርጋቸዋል፡፡
አያጭሱ ምግብ ከተመገቡ በኋላ ወዲያውኑ ሲጋራ ማጨስ እጅግ አደገኛ ነው፡፡ ከምግብ በኋላ የሚያጨሱ ሰዎች በሳንባ ካንሰር የመያዝ እድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡
ፍራፍሬ አይመገቡ
ከምግብ በኋላ ወዲያውኑ ፍራፍሬ መመገብ አንጀታችን በአየር እንዲወጠር ያደርገዋል፡፡ ፍራፍሬ መብላት ከፈለጉ፣ ምግብ ከመመገብዎ ከአንድ ሰዓት በፊት ወይንም ከተመገቡ ከአንድ ሰዓት ተኩል በኋላ ቢሆን ይመረጣል፡፡
ገላዎን አይታጠቡ
ምግብ እንደተመገቡ ወዲያውኑ ገላን መታጠብ በእግርና በእጃችን አካባቢ የደም ፍሰት (ዝውውር) መጠኑን እንዲጨምር የሚያደርግ ሲሆን ይህም በሆዳችን አካባቢ ያለውን የደም ፍሰት ይቀንሰዋል፡፡ በዚህ ምክንያትም የምግብ ስልቀጣ ስርዓቱ ይዳከማል፡፡
ቀዝቃዛ ውሃ አይጠጡ
ከምግብ በኋላ ቀዝቃዛ ውሃ መጠጣት በበላነው ምግብ ውስጥ የሚገኙትን ዘይት ነክ ነገሮች ወደ ጠጣርነት ይቀይራቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ የምግብ መፈጨት ሂደቱን ከማጓተቱም በላይ ወደ ጠጣርነት የተቀየረው ዘይትና ቅባት ጨጓራ ውስጥ ከሚገኝ አሲድ ጋር በመገናኘት በፍጥነት ተሰባብሮ ወደ አንጀት ውስጥ እንዲገባ ያደርገዋል፡፡ ይህም ወደ ስብነት ተቀይሮ ለካንሰር መከሰት ሰበብ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህም በተቻለዎ መጠን ከምግብ በኋላ ቀዝቃዛ ውሃን ከመጠጣት ይቆጠቡ፡፡ በምትኩ ለብ ያለ ውሃ ቢጠጡ የምግብ መፈጨት ሥርዓቱ የተሳካ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡
የእግር ጉዞ አያድርጉ
ከምግብ በኋላ ወዲያውኑ የእግር ጉዞ ማድረግ የምግብ ስልቀጣ ሂደቱ በአግባቡ እንዳይከናወን ያደርገዋል፡፡
ወዲያውኑ አይተኙ
በልተን ወዲያውኑ ከተኛን የተመገብነው ምግብ በአግባቡ አይፈጭም፡፡ ይህ ደግሞ ለጨጓራ ህመምና ለአንጀት ቁስለት ይዳርገናል፡፡

በኒውዝላንድ እየተመረተ በአገራችን የሚቀነባበረውና ከ30 በላይ የንጥር ምግብ ይዘት አለው የተባለ የህፃናት የዱቄት ወተት ለገበያ ሊቀርብ ነው፡፡
በፋፋ ፋድስ እና በኒውዝላንድ ሞይሪ ከኦፕሬቲቭ ፎንቴራ የጋራ ትብብር ተመርቶ ለገበያ የሚቀርበው ይኸው የህፃናት የዱቄት ወተት የላቀ ጥራት ያላቸውና በስፈላጊ ንጥረ ምግቦች የዳበረ መሆኑንና ፕሮቲን፣ ካልሲየም ቫይታሚን ኤ እና ዲ፣ አይረንና ዚንክን ጨምሮ ከ30 በላይ የሆኑ ንጥረ ምግቦቹን የያዘ መሆኑን የኒውዝላንድ ሚልክ ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዚኮ ቃሲም ተናግረዋል፡፡
ምርቱ ከነሐሴ 16 እስከ ጳጉሜ 6/2007 ዓ.ም ድረስ በኤግዚቢሽን ማዕከል በሚካሄደው የአዲስ አመት ኤክስ9 ላይ በነፃ ለጐብኚዎች ይቀርባል፡፡