Administrator

Administrator

ባለፈው ቅዳሜ ነሐሴ 7 ቀን 2008 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ እትም ላይ ‹‹የድሬዳዋ 10ኛ ዓመት የጎርፍ አደጋ አከባበር ከፍተኛ ቅሬታ አስነሳ›› በሚል ርዕስ በትክክለኛ መረጃ ላይ ሳይመሰረት ለቀረበው ዘገባ እንደሚከተለው ምላሽ ለመስጠት እንወዳለን፡፡
የድሬዳዋ አስተዳደር ከዛሬ 10 ዓመት በፊት ሐምሌ 28 ቀን 1998 ዓ.ም ሌሊት በከተማው ተከስቶ በነበረው የጎርፍ አደጋ የበርካታ ሰዎች ህይወት የቀጠፈና በሺዎች ለሚቆጠሩ ነዋሪዎች መጠለያ ማጣትና ንብረት መውደም ምክንያት የሆነበትን ቀን ከዚህ በፊት በሐይማኖት ተቋማት፣ በበጎ አድራጊ ግለሰቦችና ማህበራት በየዓመቱ ሲከበር መቆየቱ የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡ የዘንድሮውም የአደጋውን 10ኛ ዓመት መታሰቢያ አስመልክቶ፤ አስተዳደሩ ለተጎጂዎች ያለውን አጋርነት  በልዩ ሁኔታ እንዲታሰብ ለማድረግና የጎርፍ አደጋውን በዘላቂነት ለመፍታት በአስተዳደሩ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን ህብረተሰቡ እንዲያውቃቸው በማድረግ፣ከአደጋው ስጋት ተላቆ የተረጋጋ ሕይወት እንዲመራ ማድረግን ያለመ ተግባር በመሆኑ፣ ይህን ቅዱስ ዓላማ ከሚደግፉ ድርጅቶች ጋር በመሆን አክብሯል፡፡
በዚሁ የተቀደሰ አላማ መሰረት ነው፤‹‹በጎርፍ የተጎዱ ወገኖቻችን ሁሌም እናስባለን፤ስጋቱንም ለመቀነስ ተግተን እንሰራለን›› በሚል መሪ ቃል በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እንዲከበር የተደረገው፡፡ በመታሰቢያ ዝግጅቱ ላይም በድሬደዋ የጎርፍ አደጋና ጎርፉንም ለመቀነስ ባለፉት አስር ዓመታት በተሰሩት ስራዎች ዙርያ፤ ከብሄራዊ አደጋ ስጋት ሰራ አመራር ኮሚሽን የተዘጋጀ ጽሁፍ እንዲሁም በስነ ልቦና ባለሙያ የቀረበ  ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርቦ የተጎጂ ቤተሰቦች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ተጋባዥ እንግዶችና የአስተዳደሩ ኃላፊዎች በተገኙበት የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡ በሌላ በኩል የጎርፍ አደጋውን በዘላቂነት ሊቀንሱ ከሚችሉ ተግባራት አንዱ በሆነው የችግኝ ተከላ ላይ የአስተዳደራችን ነዋሪዎች፣ የሰራዊት አባላት፣ ታዋቂ የሀገራችን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች ከ4ሺህ በላይ ችግኞችን የተከሉ ሲሆን በጎርፉ ጉዳት ደርሶባቸው የነበሩ ግለሰቦች ያሉበት ሁኔታ የተጎበኘና በአስተዳደሩ በወቅቱ የነበረውን አደጋ የሚያስታውሱና የሚዘክር ታዋቂ የፊልም ባለሙያዎች የተሳተፉበት የፊልም ምርቃትና የኪነ-ጥበብ ስራዎች በማቅረብ እንዲታሰብም ተደርጓል፡፡ በዚህም የአስተዳደሩ ኃላፊዎችና የአገሪቱ ታዋቂ የኪነጥበብ ባለሙያዎች በየዝግጅቱ ላይ በመገኘት ለአደጋው ተጎጂ ቤተሰቦች አጋርነታቸውን ማሳየት ችለዋል፡፡ በዚህም የተሳካ የአብሮነትና ፍቅር የተንፀባረቀበት የማይረሳ ቀን ሆኖ ተጠናቋል፡፡
እውነታውና አላማው ይሄ ሆኖ ሳለ ምንም ዓይነት ተጨባጭ መረጃዎች ባልቀረቡበት የአስተዳደሩን የአብሮነት፣ የመቻቻል፣ የፍቅርና ማንንም አግላይ ያልሆነ እንዲሁም የህዝቡን ባህልና እሴት የሚሸረሽርና መልካም ስማችንንና ገፅታችንን የሚያበላሽ ፅሁፍ በጋዜጣችሁ ላይ ወጥቷል፡፡ በፅሁፉ ለወጡት ለእያንዳንዱ ምላሽ መስጠቱ አስፈላጊ ባይሆንም ለዋና ዋናዎቹ በመረጃ ላይ ላልተመሰረቱት ሃሳቦች መረጃ መስጠቱ አስፈላጊ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
ጋዜጠኛዋ የጎርፍ አደጋውን 10ኛ ዓመት አስመልክቶ 13 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት መታሰቢያ ተደርጓል በማለት ፅፋለች፡፡ የጠቀሰችው የቁጥር አሃዝ ከየት የመረጃ ምንጭ እንደተገኘ ያልገለጸች ሲሆን መረጃው የግለሰቦች ጥያቄና ቅሬታ ምንጭም ከሆነም በግልጸኝነት ከሚመለከተው አካል ተጠይቆ መረጃው መሰረተ ቢስ መሆኑ ምላሽ የተሰጣት ቢሆንም፣ ይህን መግለጽ ለምን አልተፈለገም? በተጨማሪም አስተዳደሩ ከህዝቡ የሚነሱትን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ጥረት እያደረገ ባለበት ወቅት ለሁለት ቀን ፕሮግራም 13 ሚሊዮን ብር ያወጣል ብሎ ማሰቡ ትልቅ ስህተት ነው፡፡ ሌላው አደጋው ከፍተኛና ሰፊ የህብረተሰብ ክፍሎችን የነካካ ከመሆኑ አንፃር ምን አልባትም ሁሉም ተጎጂዎች በመታሰቢያ ቀኑ ተካትተው ላይሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን 3 ተጎጂዎችን ብቻ አናግሮ፣ ከፍተኛ ቅሬታ አስነሳ ሊባል የሚችል አይደለም፡፡ በ10 ሺዎች ባፈናቀለና ከመቶዎች በላይ የሚቆጠር ሕይወት ለቀጠፈ አደጋ የ3 ሰዎች ሀሳብ ብቻ ተወስዶ የአብዛኛውን ተጎጂ ባልወከለ ሁኔታ ከፍተኛ ቅሬታ አስነሳ በሚል ርዕስ ሰጥቶ መፃፍ፣ ከጋዜጠኝነት ፅንሰ ሃሳብ ጋር የሚጣረስና ስነ ምግባር የጎደለው ተግባር ነው ብለን እናምናለን፡፡
ሌላው አርቲስቶችን በባለ 5 ኮከብ ሆቴል ሰብስቦ በማስጨፈር መከበሩ ተጎጂዎችን ማሳዘኑን ገልጻለች። ነገር ግን በየሆቴሉ ጭፈራ መካሄድ አለመካሄዱን ከአዘጋጆቹ ማጣራት ተገቢ ነበር፡፡ ታዋቂ የሀገራችን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች በፕሮግራሙ የተገኙበት ዋና ዓላማ፣ አደጋው በደረሰ ጊዜ ተጎጂዎችን በመልሶ ማቋቋም ወቅት በአካል ተገኝተው ማጽናናታቸውና ድጋፍ ማድረጋቸው የሚታወስ ሲሆን አሁንም  አስተዳደሩ በዘላቂነት የጎርፍ አደጋ ለመከላከል የሚያደርገውን ጥረት ባላቸው አቅም ሁሉ ለመደገፍና ለድሬደዋ ህዝብ ያላቸውን አጋርነት ለመግለጽና ለማገዝ እንጂ ዘጋቢዋ  እንዳሉት ለመጨፈር አይደለም፡፡
በሌላ በኩል የጎርፍ ተጎጂዎችን በማቋቋም ረገድ በርካታ ድጋፎች የተደረጉ ሲሆን አስተዳደሩ ከጎርፍ አደጋ በኋላ ሰብዓዊና ቁሳዊ ድጋፎች አድርጓል፤ ዋና ዋናዎቹም 14 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ 699 የአጣዳፊ ቤቶች ተገንብተው ለተጎጂዎች ተላልፈዋል፤ቀሪዎቹን በካምፕ የነበሩ ለእያንዳንዳቸው የ6 ወራት የቤት ኪራይ በመስጠት ወደ ቀድሞ ኑሮአቸው እንዲመለሱ ተደርጓል። የግል መኖሪያ ቤታቸው በከፊል ለወደመባቸውና ጠግነው ሊኖሩበት ለሚችሉት በመሀንዲስ ግምት መሠረት የጥገና ወጪ ክፍያ እንዲፈፀምላቸው ተደርጓል። አደጋውን በዘላቂነት ለመቀነስ ከ10 ኪ.ሜ በላይ ሪቴይንግ ዎል ማሰራት የተቻለ ሲሆን ዘንድሮ  በድጋሚ በመጣ ጎርፍ በተወሰነ አካባቢዎች በግድቡ ላይ መጠነኛ ጉዳት ደርሶበት በድጋሚ ጥገና ተደርጎለታል፡፡ የጎርፍ መሄጃ የሆኑትን የደቻቱና ጎሮ ወንዞች ግራና ቀኝ ተከትሎ  የጎርፍ መከላከያ ተሰርቷል፤ በተጨማሪም  የመልካጀብዱ መሄጃ ድልድይም በቅርቡ በጣለው ከባድ ዝናብ በጎርፍ ጉዳት የደረሰበት እውነት ቢሆንም፣ ከድሬዳዋ መልካጀብዱ የ8 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ በፌደራል መንገዶች ባለስልጣን በ2009 በጀት ዓመት ከሚሰሩ አራት መንገዶች አንዱ ሲሆን  በአስፓልት ደረጃ በአዲስ የሚሰራና ቅድመ ሁኔታው ተጠናቆ ስራው ሊጀመር ያለበት ሁኔታ እንጂ የአስተዳደሩ ቸልተኝነት ተደርጎ መቅረቡ ትክክል አይደለም፡፡  
አስተዳደሩ የጎርፉን አደጋ ለመቀነስ ባሰራው ጥናት ላይ ተመስርቶ ከከተማዋ አጎራባች ወረዳዎች የሚመጣውን የጎርፍ ጉልበት ለመቀነስ ባለፉት 5 ዓመታት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በመስራት፣ ከ75 በመቶ በላይ የነበረው የአካባቢ መራቆት ወደ 33 በመቶ ዝቅ ለማድረግ የተቻለ ሲሆን በቅርቡ በኢሊኖ ሳቢያ የተፈጠረው የአየር ንብረት ለውጥ ያስከተለው ጎርፍ በከተማዋ ላይ ያስከትል የነበረውን ከፍተኛ አደጋ መቀነስ ተችሏል፡፡ ዘጋቢዋ ይህን የአስተዳደሩን ተግባር ለማወቅ የፈለገች አትመስልም፡፡
ለእያንዳንዱ ሀቅን መሰረት ያላደረገ ፅሑፍ ምላሽ እየሰጡ መሄድ አስፈላጊ ነው ባንልም በድሬዳዋ አስተዳደር ነዋሪው ዘንድ ያለውን የመተሳሰብና የመረዳዳት ባህልና እሴት ካለማወቅና ካለመረዳት እንዲሁም ተቆርቋሪና አሳቢ መስሎ የምንታወቅበትን አብሮ የመኖር ባህል ለመጉዳት መነሳሳት በቀላሉ የሚሳካ አይሆንም፡፡ ዘጋቢዋ ለጽሁፉ በቂ ትኩረት ያለመስጠቷን የሚያሳየው የአስተዳደሩን የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ስም እንኳን በትክክል አጥርታ ያለመፃፏ ነው፡፡
በመጨረሻም ጎርፍን በዘላቂነት መከላከልና በሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት እንዳያደርስ ማድረግ የአስተዳደራችን ትኩረት ከመሆኑ ባሻገር፤ ከተማችን ድሬደዋ ለነዋሪዎቿ ምቹ፣መልካም አስተዳደር የሰፈነባት በንግድ፣ በኢንዱስትሪና አገልግሎት ዘርፍ ላይ ያተኮረ ዘላቂ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያስቀመጠችውን ራእይ እናም የምስራቅ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ኮሪደር እንድትሆን በፌደራል መንግስት በተወሰነው ውሳኔ መሰረት፣ በቀጣይ ግዙፍና ትልልቅ ኢንዱስትሪዎች የሚገነቡባት፣ ለሀገራችን ህዝቦች ሰፊ የስራ እድል የምትፈጥር ከተማ ናት፡፡ በመሆኑም ከዚህ አኳያ ያለተጨባጭ ማስረጃ የሚቀርቡ ፅሁፎች የአስተዳደሩን በጎ ገፅታ ከማጉደፍ በተጨማሪ የአስተዳደሩን ህዝብ ካለማክበር የሚመነጭ እንዲሁም የአዘጋጆቹን ልፋትና ድካም ሞራል መንካት እንደሆነ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡  
የድሬደዋ ከተማ አስተዳደር

  የቀድሞው የ“አውራምባ ታይምስ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረውና በሽብርተኝነት ወንጀል 14 ዓመት እስር ተፈርዶበት ዝዋይ ማረሚያ ቤት የሚገኘው የጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፤“ሞጋች እውነቶች” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሀፉ ስለ አገራችን ወቅታዊ ሁኔታ፣ “ጉዋንታናሞ ቃ” ስለተባለው እስር ቤት፣ ስለ ዝዋይ ማረሚያ ቤት፣እድሜ ልክ ስለተፈረደባቸው ሰዎች ታሪክና ተያያዥ ጉዳዮችን የሚዳስስ ነው፡፡
በ216 ገጾች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ71 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው የመፅሀፉን መታሰቢያነት ለዲሞክራሲ፣ ለነፃነትና ለፍትህ ልዕልና አክብሮት ላላቸው፣አጋርነታቸውን ለሚያሳዩና ለሚታገሉ የሰው ዘሮች ይሁንልኝ ብሏል፡፡
ጋዜጠኛ ውብሸት፤ከዚህ ቀደም በእስር ላይ እያለ “የነጻነት ድምፆች” የተሰኘ መጽሐፍ ለንባብ ያበቃ ሲሆን የ2012 የሂውማን ራይትስ ዎች ሄልማን ሃሜት እና የ2013 የሲኤንኤን አፍሪካን ጆርናሊስት አዋርድ አሸናፊ መሆኑ ይታወሳል፡፡
 በሌላ በኩል በአንተነህ አየለ የተፃፈውና በተለያዩ ሱሶች ምክንያት ከመስመር ስለወጡ ወጣቶች፣ ስለ ሱስ አጀማመር፣ ስለ ሱስ ማዘውተሪያ አካባቢዎችና ሱስን ተከትለው ስለሚመጡ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ስነ-ልቦናዊ ቀውሶች የሚያስቃኘው “ጃጃ ሲቲ” የተሰኘው መፅሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ ፀሐፊው ስለ ሱስና መዘዞቹ ለመፃፍ የተነሳሳው ቾምቤ የተባለ ጓደኛው በሱስ ምክንያት ጓደኞቹ ከዩኒቨርሲቲ ሲመረቁ እሱ ሳይመረቅ በመቅረቱ የተሰማውን ቁጭትና ለቅሶ በማየት እንደሆነ በመግቢያው ላይ ገልጿል፡፡ በ216 ገጾች የቀረበው መፅሐፉ፤አገር ውስጥ በ76 ብር ከ90 ሳንቲም፣በውጭ አገራት በ20 ዶላር እየተሸጠ ይገኛል፡፡

የታላቁ ገጣሚና ፀሐፌ-ተውኔት ደበበ ሠይፉን ‹‹የብርሃን ፍቅር (ለራስ የተፃፈ ደብዳቤ )›› በድጋሚ ማሳተሙን የገለጸው ሐሳብ አሳታሚ፤ከነገ ወዲያ ሰኞ በ10፡30 በተለያዩ የጥበብ መሰናዶ በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን አዳራሽ ያስመርቃል፡፡ በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ በደበበ ሠይፉ ስራዎች ላይ ዳሰሳዊ ቅኝት የሚያቀርብ ሲሆን በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በሚከትባቸው ጥበባዊ ጽሁፎቹ የሚታወቀው ተፈሪ መኮንን፣ ስለ ደበበ ሠይፉ መምህርነት፤ ተዋናይ ተፈሪ አለሙ፣ ስለ ፀሐፌ-ተውኔት ደበበ ሠይፉ፤እንዲሁም ገጣሚ ታገል ሰይፉ ስለ ደበበ ሠይፉ አንዳንድ ትዝታዎች እንደሚያወጉ ታውቋል። አንጋፋና ወጣት ገጣሚያንም ስራዎቻቸውን ለታዳሚው ያቀርባሉ፡፡ የሥነጽሁፍ ወዳጆች በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ እንዲገኙ ሐሳብ አሳታሚ ጋብዟል፡፡  

በታደሰ ፀጋ ወ/ስላሴ የተፃፈውና “የመናፍስቱ መንደር” የተሰኘው መፅሐፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ውሏል፡፡ መፅሀፉ በዋናነት በአይን የማይስተዋሉ ስውራን መናፍስትንና የሰዎችን ዘመናት ያስቆጠረ ህቡዕ እንቅስቃሴ አሻራን በስፋት ያስቃኛል ተብሏል። በሰንሰለታማው የሰሜን ተራሮች የሰፈሩ ጥንታዊ ህዝቦች ስልጣኔ፣ባህላዊና መንፈሳዊ ቅርስ እንዲሁም ያልተነገሩ ድብቅ ታሪኮችም በመጽሐፉ ተዳስሷል። በ10 ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ275 ገጾች የተቀነበበው መፅሐፉ፤በ77 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ መጽሐፉን የሚያከፋፍለው እነሆ መፅሐፍ መደብር እንደሆነ ታውቋል፡፡  

በደራሲ እንዳልካቸው ወሰን የተፃፈውና “ያልበራ ብርሐን” የተሰኘው መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡
 ዓመተ ፍዳ አልፎ አመተ ምህረት መምጣቱንና በአሁኑ ወቅት የሰው ልጅ አዕምሮ የሚፈጥራቸውና የሚገልፃቸው በርካታ ምስጢራት፣ ዘመኑን ከዓመተ ምህረት ወደ “ዓመተ ግልፀት” ለውጦታል ይላል - ደራሲው በመጽሐፉ፡፡ ይህ ግን የግል አስተሳሰቡ መሆኑን አልሸሸገም፡፡
በ118 ገጾች የተመጠነው  መፅሐፉ፤በ40 ብር ከ50 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡  

ለአራተኛ ጊዜ የሚካሄደውና ለሀገራቸውና ለወገናቸው ላቅ ያለ አገልግሎት የሰጡ ዜጎች የሚከበሩበት የዓመቱ በጎ ሰው ሽልማት ሥነሥርዓት ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም በአዲስ አበባ አቤል ሲኒማ ይከናወናል፡፡
በ10 ዘርፎች ለ2008 የዓመቱ በጎ ሰው ሽልማት መብቃት አለባቸው የተባሉ ዜጎች በሕዝቡ የተጠቀሙ ሲሆን በየዘርፉ ከተጠቆሙት ዜጎች መካከልም ሥራዎቻቸው ተመዝነው በሽልማት ኮሚቴው አማካኝነት ሦስት ሦስት ዕጩዎች ተለይተዋል፡፡
በእነዚህ እጩዎች ላይ አምስት አምስት ዳኞች (በየዘርፉ) ድምጽ እየሰጡ መሆኑ የታወቀ ሲሆን የየዘርፉ ተሸላሚዎችም ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም በሚኖረው ሥነ ሥርዓት ይታወቃሉ ተብሏል። ሚዲያዎችና ሌሎች የመገናኛ አካላት፣እጩዎችን በማስተዋወቅና በማክበር፣ ለሀገራቸው በጎ የሚሠሩ ዜጎችን ለማብዛት የበኩላቸውን እንዲወጡ የበጎ ሰው ሽልማት ኮሚቴ ጠይቋል፡፡ ከዚህ በታች እጩዎቹ በየዘርፋቸው ቀርበዋል፡፡
መምህርነት
ተ/ ፕሮፌሰር ዘሪሁን አስፋው
ተ/ ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና
መ/ር አውራሪስ ተገኝ
ንግድና ሥራ ፈጠራ
አቶ ብዙአየሁ ታደለ
አቶ ሳሙኤል ታፈሰ
አቶ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ
ማኅበራዊ ጥናት
ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ
ዶክተር አንዳርጋቸው ጥሩነህ
ፕሮፌሰር ባየ ይማም
ሳይንስ
ሎሬት ዶክተር መላኩ ወረደ
ዶክተር ዓለማየሁ ዋሴ
ዶክተር ውዱ ዓለማየሁ
ቅርስና ባሕል
የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም (አዲስ አበባ     
           ዩኒቨርሲቲ)
ኢንጅነር ታደለ ብጡል
መ/ር ካሕሳይ ገብረ እግዚአብሔር
መንግሥታዊ የሥራ ኃላፊነትን በብቃት መወጣት
ኢንጅነር ዘውዴ ተክሉ
ዶክተር ተወልደ ብርሃን
          ገብረእግዚአብሔር
ዳኛ ስንታየሁ ዘለቀ
ስፖርት
አቶ ጌቱ በቀለ
ጋቶች ፓኖ
ዶክተር ይልማ በርታ
ኪነጥበብ (ድርሰት)
አቶ አስፋው ዳምጤ
ወ/ሮ ፀሐይ መላኩ
አቶ አውግቸው ተረፈ
ሚዲያና ጋዜጠኛነት
መንሱር አብዱልቀኒ
አቶ አጥናፍሰገድ ይልማ
አቶ ደረጀ ኃይሌ
በጎ አድራጎት
ዶክተር ቦጋለች ገብሬ
ወ/ሮ ፀሐይ ሮቺሊ
ወ/ሮ ዘውዲቱ መሸሻ

ቶታል ኢትዮጵያ ከኤም ብር ጋር በመተባበር አዲስ የተቀላጠፈ የሞባይል ክፍያ አሰራር መተግበር የጀመረ ሲሆን ደንበኞች ካሉበት ሆነው የድርጅቱን አጠቃላይ አገልግሎቶች በተመለከተ የተሟላ መረጃ የሚያገኙበት “ቶታል ሰርቪስስ” የተባለ አዲስ የሞባይል ስልክ አፕሊኬሽንም አስመርቋል፡፡
የቶታል ኢትዮጵያ የሽያጭና የማርኬቲንግ ስራ አስኪያጅ ክሪስቶፊ ፌራንድ ባለፈው ረቡዕ በተከናወነው የምረቃ ስነስርዓት ላይ እንዳሉት፣የሞባይል ክፍያ አሰራሩ የኩባንያው ደንበኞች በማንኛውም ጊዜ የተለያዩ ክፍያዎችን መፈጸም፣ ገንዘብ መላክ፣ የሞባይል ካርድ መግዛት፣ ገንዘብ ማስቀመጥ ወይም ማውጣትና መገበያየት የሚችሉበት ነው፡፡
የኩባንያው ደንበኞች በተመረጡ የቶታል ማደያዎች ይህን አስተማማኝ፣ ጊዜ ቆጣቢና ቀልጣፋ የሞባይል ክፍያ ዘዴ በመጠቀም ነዳጅ መግዛት፣ መኪና ማሳጠብ፣ የመኪና ዘይት መግዛት፣ የሱፐር ማርኬትና የካፌ አገልግሎቶችን መጠቀም ወዘተ ይችላሉ ያሉት ዳይሬክተሩ፤በቅርቡም ይህን አገልግሎት በሁሉም የቶታል ማደያዎች ለማስጀመር እየተሰራ እንደሚገን አስታውቀዋል። ቶታል ኢትዮጵያ ከዚህ በተጨማሪም ለደንበኞቹ ያለውን ተደራሽነት ለማስፋት በማሰብ፣ ደንበኞች ካሉበት ሆነው የሞባይል ስልኮቻቸውን በመጠቀም የድርጅቱን አገልግሎቶች በተመለከተ የተለያዩ መረጃዎችን ማግኘት የሚችሉበትን ቶታል ሰርቪስስ የተባለ አዲስ የሞባይል ስልክ አፕሊኬሽን አስመርቋል፡፡  
አዲሱ የሞባይል አፕሊኬሽን፣ የቶታል ኢትዮጵያ ደንበኞች ባሉበት ሆነው በስልኮቻቸው አማካይነት ያለ ውጣ ውረድ በአቅራቢያቸው  የሚገኘውን የቶታል ማደያ ለማወቅና የሚሰጡ አገልግሎቶችን የተመለከቱ መረጃዎችን ለማግኘት የሚችሉበት ነው፡፡ ደንበኞች አዲሱን የቶታል ሰርቪስስ የሞባይል አፕሊኬሽን፣ ከጎግል ስቶር ላይ ማውረድ እንደሚችሉ በመጠቆም፣ ቶታል ኢትዩጵያ ለደንበኞቹ ያለውን ተደራሽነት ለማሳደግ ትኩረት በመስጠት በፀሐይ ብርሀን የሚሠሩ መብራቶች በማደያው እንዲሁም በህዳሴ ሱቆች ላይ ማቅረቡንም አስታውሰዋል፡፡
ኤምብር በአገሪቱ የሚገኙ አምስት ታላላቅ የብድርና ቁጠባ ተቋማትን በማቀፍ የጀመረውን ዘርፈ ብዙ የሞባይል የፋይናንስ አገልግሎት በማስፋፋትና የደንበኞቹን ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ በማሳደግ፣ የተቀላጠፈ አገልግሎቱን በስፋት እየሰጠ እንደሚገኝም በምረቃ ስነስርአቱ ላይ ተገልጧል፡፡

 - ያለቅጥ ወፍራችኋል፤ ሸንቀጥ እስክትሉ ህዝብ ፊት አትቀርቡም ተብለዋል
   የግብጽ መንግስት የብሮድካስቲንግ ተቋም የሆነው “ኢርቱ”፤8 ሴት የአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋዜጠኞችን “ያለቅጥ ወፍራችኋል፣ የምትመገቡትን ምግብ መጠን ቀንሳችሁ እስክትከሱና ሸንቀጥ እስክትሉ ድረስ ከህዝብ ፊት አትቀርቡም” በሚል ለአንድ ወር ያህል ጊዜ ከስራ ማገዱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
“ዘ ኢጂፕሺያን ሬዲዮ ኤንድ ቴሌቪዥን ዩኒየን” የተባለው ተቋም ይሄን አስቀያሚ ውፍረታችሁን ይዛችሁ ከተመልካች ፊት አትቀርቡም በሚል በጋዜጠኞቹ ላይ የወሰደው ከስራ የማገድ እርምጃ፣የሴቶች መብቶች ተከራካሪ ቡድኖችን ማስቆጣቱን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
“ዘ ውሜንስ ሴንተር ፎር ጋይዳንስ ኤንድ ሌጋል አዌርነስ” የተባለው የአገሪቱ የሴቶች መብት ተከራካሪ ቡድን፣ ውሳኔው ህገ-መንግስትን የሚጥስና በግብጻውያን ሴቶች ላይ የተቃጣ ጾታዊ ጥቃት ነው ሲል ተቃውሞውን በማሰማት ውሳኔው እንዲሻር ጥያቄ ማቅረቡን ዘገባው አመልክቷል፡፡ ጥያቄው የቀረበለት ተቋም ግን ውሳኔው በምንም አይነት መንገድ እንደማይሻር ማስታወቁን ቬቶ ኒውስ የተባለው የግብጽ ድረገጽ የዘገበ ሲሆን፣ የአገሪቱ የመገናኛ ብዙሃን ተቋማትና ጋዜጠኞች በጉዳዩ ዙሪያ እየተከራከሩ እንደሚገኙም ተነግሯል፡፡

   በቅርቡ ከተቃጣበት የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር በተያያዘ ከ26 ሺህ በላይ ዜጎችን ያሰረው የቱርክ መንግስት፣ ባጋጠመው የእስር ቤቶች መጨናነቅ ሳቢያ፣ ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር ባልተያያዙ ወንጀሎች የታሰሩ ነባር 38 ሺህ ያህል እስረኞችን ሰሞኑን እንደሚፈታ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፕሬዚዳንት ጣይብ ኤርዶጋንን ከስልጣን ለማስወገድ የተካሄደው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ መክሸፉን ተከትሎ የአገሪቱ ፖሊስ በርካታ ቁጥር ያላቸውን ዜጎቹን እያፈሰ ወደ እስር ቤቶች ማጋዙ በእስር ቤቶች ላይ ከፍተኛ መጨናነቅ መፍጠሩን የጠቆመው ዘገባው፤የአገሪቱ የፍትህ ሚኒስትር በኪር ቦዝዳግ፣ ችግሩን ለመፍታት በማሰብ 38 ሺህ እስረኞችን ለመፍታት መወሰናቸውን እንዳስታወቁ ገልጧል፡፡በተለያዩ የወንጀል ክሶች ተጠርጥረው የታሰሩት እነዚህ 38 ሺህ እስረኞች ከእስር ይለቀቁ እንጂ ምህረት አልተደረገላቸውም ያሉት ሚኒስትሩ፤ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ተመርምሮ ተገቢው ቅጣት እንደሚጣልባቸው ማስታወቃቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡

ለአመታት በእርስ በርስ ጦርነት ስትታመስ የቆየችው የመን በመሰረተ ልማት አውታሮች ላይ በደረሰ ውድመትና በኢኮኖሚ ድቀት ሳቢያ በድምሩ 14 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ እንደደረሰባት ሮይተርስ ዘገበ፡፡
በየመን ላለፉት 16 ወራት በዘለቀው የእርስ በእርስ ጦርነት ከ6 ሺህ 500 በላይ ሰዎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውንና ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ማፈናቀሉን የሚጠቁም ይፋ ያልሆነ ሪፖርት ማግኘቱን ያስታወቀው ሮይተርስ፤ከግማሽ በላይ የሚሆነው ህዝቧም የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ተጠቂ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ በአገሪቱ የእርስ በርስ ጦርነት ሳቢያ በርካታ መሰረተ ልማቶች መውደማቸውንና የኢኮኖሚ ድቀት መድረሱን የጠቆመው ዘገባው፤በአገሪቱ የሚገኙ 1 ሺህ 671 ትምህርት ቤቶች መውደማቸውንና ውድመቱ 269 ሚሊዮን ዶላር ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት አስረድቷል፡፡
የህክምና አገልግሎት ሲሰጡ ከነበሩ የአገሪቱ 3 ሺህ 652 ተቋማት መካከል 900 ያህሉ አገልግሎት መስጠት ማቆማቸውን የገለጸው ዘገባው፤በዚህም 2.6 ሚሊዮን የአገሪቱ ህጻናት ለበሽታ የመጋለጥ አደጋ ላይ መውደቃቸውን አስረድቷል፡፡