Administrator

Administrator

የሰሜን ኮርያ መንግስት፤ ከአገሪቱ ከፍተኛ ሚኒስትሮች አንዱ የነበሩትንና  በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የትምህርት ዘርፍ ሃላፊ ሆነው ሲሰሩ የቆዩትን ኪም ዩንግ ጂንን፣ባለፈው ወር ገድሏል ስትል ደቡብ ኮርያ መናገሯን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሚኒስትሩ ባለፈው የካቲት ወር ላይም ተገድለዋል ተብሎ ተወርቶ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ይሄም ሆኖ ግን ከቀናት በኋላ በፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ሲካፈሉ መታየታቸውን ጠቁሞ ይሄኛው የደቡብ ኮርያ መረጃም አጠራጣሪ ሊሆን እንደሚችል ገልጧል፡፡
ሰሜን ኮርያ ተገደሉ የተባሉትን ሚኒስትር በተመለከተ እስካሁን ያለቺው ነገር እንደሌለ የጠቆመው ዘገባው፣ የአገሪቱ መንግስት በቅርቡ የሚኒስትሩን ቦታ ተክቶ የሚሰራ ሌላ ሚኒስትር ከሾመ የመሞታቸው ነገር እርግጥ ሊሆን ይችላል መባሉን አመልክቷል፡፡
የሰሜን ኮርያ መንግስት ከዚህ ቀደምም ከፍተኛ ባለስልጣናቱንና ሚኒስትሮችን በድብቅና በይፋ በወሰዳቸው እርምጃዎች መግደሉን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ትዊተር ባለፈው አመት ብቻ ሽብርተኝነትን የሚያስፋፉ መልዕክቶችን አሰራጭተዋል ያላቸውን የ360 ሺህ የትዊተር ተጠቃሚዎች አካውንቶችን በመዝጋት ከአገልግሎት ውጭ ማድረጉን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡ እነዚሁ አካውንቶች ሽብርተኝነትን የሚያስፋፉ መልዕክቶችን በማስተላለፍና ግለሰቦችን በማስፈራራት ተግባር ላይ ተሰማርተው በመገኘታቸው እንዲዘጉ መደረጉን ያስታወቀው ኩባንያው፤ከእነዚህም መካከል 235 ሺህ የሚሆኑት ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ እንደተዘጉ ገልጧል፡፡
ተቀማጭነቱን በሳን ፍራንሲስኮ ያደረገው ትዊተር የሚተዳደርበት ፖሊሲ፣ ሽብርተኝነትን ማስፋፋትን እንደማይፈቅድ ገልጾ፣ በቀጣይም በተመሳሳይ ህገወጥ ተግባራት ላይ የተሰማሩ ተጠቃሚዎቹን እየተከታተለ አካውንታቸውን እንደሚዘጋ አስታውቋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ቀበሮ ጉሮሮው ውስጥ አጥን ተቀርቅሮበት በጣም ሲሰቃይ ዋለ፡፡ ወደማታ ላይ አንዲት ረዝም ኩምቢ ያላት ወፍ አገኘና እንዲህ አላት፡-
“ወፊት ሆይ”
“አቤት” አለች ባለ ኩምቢዋ ወፍ፡፡
“አንድ ነገር ልለምንሽ?”
“የምችለው ከሆነ ምን ቸገረኝ”
“የምትችይው ነገር ነው፡፡ በዚያ ላይ ለውለታሽ ዋጋሽን እከፍላለሁ”
“ምን ትከፍለኛለህ?”
“የፈለግሺውን፡፡ ብቻ ከአቅሜ በላይ አይሁን”
“እሺ፡፡ እንግዲያው እኔን የሚያሳድዱኝ ጠላቶች አሉኝ፡፡ እነሱን አሳደህ ታጠቃልኛለህ?”
“ይሄማ በጣም ቀላል ነው፡፡ ብቻ አንቺ የምጠይቅሽን ፈፅሚልኝ”
“ምንድን ነው እንዳረግልህ የፈለግኸው?” ብላ ጠየቀችው፡፡
“ጉሮሮዬ ውስጥ አጥንት ተቀርቅሮ እያሰቃየኝ ነው፡፡ ስለዚህ ኩምቢሽን አፌ ውስጥ አስገብተሸ እንደ ምንም ብለሽ አውጪልኝ” አላት፡፡
“ይሄ ለእኔ ቀላል ነው፡፡ ፊትህን ወደ ብርሃን መልስና አፍህን በደምብ ክፈተው” አለችው፡፡
ወፊቱ ኩምቢዋን እጉሮሮው ድረስ አስገብታ አጥንቱን ጎትታ አወጣችለት፡፡ እፎይ አለ ቀበሮው፡፡
ከዚያም ወፊቱ፤ “በል እንደተዋዋልነውና ቃል እንደገባህልኝ ወደ ጠላቶቼ ልውሰድህና ተበቀልልኝ” አለችው፡፡ ቀበሮም ቃሉን አጠፈና፤
“ቀበሮ አፍ ውስጥ ገብቼ በሰላም ወጥቻለሁ፤ ብለሽ በኩራት መናገርሽ ይበቃሻል፡፡ ከፊቴ ጥፊ!” አለና አባረራት፡፡ ወፊቱም አቅራቢያዋ ወዳለው ዛፍ ላይ ወጣችና፤
“ሌላ አጥንት ጉሮሮህ ላይ የማይቀረቀር እንዳይመስልህ፡፡ ያኔ ምን እንደሚውጥህ እናያለን” አለችው፡፡ ከአካባቢው በርራ ጠፋች፡፡
*             *          *
በአንድ አገር ሶሺዮ-ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሂደት ውስጥ አንዱ ትልቅ ቁምነገር ለህዝብ ቃል መግባት ነው፡፡ ይህን ቁምነገር የሚያረክሰው ደግሞ የገቡትን ቃል ማጠፍ ነው፡፡ የገቡትን ቃል ማጠፍ ዕምነትን ያጠፋል፡፡ ዕምነተ-ጎዶሎ አመራር ደግሞ በጄ ብሎ መንግሥትን አምኖ የሚገዛ ህዝብ እንዳይኖር ያደርጋል፡፡ ሰላምን ያደፈርሳል፡፡ ጥርጣሬንና እየተገላመጡ መኖርን ያገዝፋል፡፡ መረጋጋት እንዳይኖር ያደርጋል፡፡ ከሀገር መሰደድን ያበዛል፡፡ ማንም ማንንም የማያምንበት፣ ነፃነቱን የሚጠራጠርበት፣ እኩልነቱን የማይቀበልበት፣ የሕግን የበላይነት በወጉ የማይረዳበት፣ ለምንም ነገር ብቃት እንዳለው የማይተማመንበት፣ አልፎ ተርፎም ኢትዮጵያዊነቱን ለጥያቄ የሚዳርግበት ሁኔታ ውስጥ እንዲገባ ሊገደድ የሚችልበት ደረጃ ሊደርስ ይችላል። ስለዚህም ልንፈፅም የምንችለውን ቃል ብቻ በአደባባይ መናገር ብልህነት ነው፡፡ መንገዶች ሁሉ ሁሌ አልጋ ባልጋ ላይሆኑ እንደሚችሉ እንገንዘብ፡፡ መንገዶች ሁሉ ሁሌ ወደ ሮማ አይወስዱም፡፡ ሁሌም “የአፈፃፀም ችግር ነው” እያልን እንደማንዘልቅ እናስብ፡፡ ይልቁንም እቅዳችንን እንፈትሽ፡፡ ራሳችንን ወደ ውስጥ እንይ። እርስ በርሳችን ምን ያህል እንተማመናለን፤ ብለን እንጠይቅ፡፡ ስንወሻሽ እንጠያየቅ፡፡ በችግር ላይ ችግር ለምን ይደራረብብናል? ብለን እንጠይቅ፡፡ ቀውስ በተፈጠረ ቁጥር ወደ ኃይል መሄድ ከትርፉ ኪሳራው የሚያመዝን ሁነት መሆኑን እንይ፡፡ ከቶውንም ኃይል ከቀውስ ወደቀ ውስ ሊከተን እንደሚችል ልብ እንበልና ልብ እንግዛ፡፡ “መካር የሌለው ንጉሥ፣ ያለ አንድ ቀን አይነግሥ” የሚለውን ተረት እናስታውስ። “እንደ ንጉሡ አጎንብሱ” የሚለው ተረትም ሁልጊዜ አያበላም፡፡ ጊዜው ያለፈበት ነውና፡፡ ይልቁንም ሐምሌት የሚለንን ከአንጀታችን እናዳምጥ፡-
“በንጉሥ ፍርፋሪ የፋፋን ትል
አሣ አገኘችና፤ ቅርጥፍ
አሣ-አጥማጅ፣ እሷን ቅርጥፍ!
ሆድን ሞልቶ እንደስልቻ
በልቶ ለመበላት ብቻ!!”
ከሀገራችን የችግር ቁንጮዎች አንዱ አድር - ባይነት ነው፡፡ የጥንቱ የጧቱ ወዳጃችን ሌኒን፤ ‹‹The Pendulum of Opportunism never stops Oscillating›› ይላል፡፡ የአድር-ባይነት ፔንዱለም ዥዋዥዌውን አይተውም፤ እንደ ማለት ነው፡፡ አድር-ባይነት፣ ብቃት የጎደላቸው ሰዎች የኑሮ ዘዴ ነው። አጉል መካሪ ሀገር ያጠፋል፡፡ አድር - ባዮች አጉል መካሪ ናቸው፡፡ የራሳቸውን ጥቅም ለማካበት ሲሉ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለምና፡፡ ልታይ ልታይ ያበዛሉ፡፡ አደባባይ ይደፍራሉ፡፡ በአደባባይ ቃል መግባት አይፈሩም፡፡ ልሳናቸው ስል ነው፡ በሀገር ተቆቋሪነት ስም የማይዘላብዱት ነገር የለም! እንደ እስስት መልካቸውን ይለዋውጣሉ፡፡ በሠርግ ላይ ዘፈን አውጪ፣ በልቅሶ ቤት ሙሾ አውራጅ ናቸው! ሁሉንም የሚያደርጉት ለግል ጥቅማቸው ነው፡፡ ስለሆነም የሙስና ፈታውራሪ ናቸው፡፡ ሆኖም ደግሞ ሙሰኞችን ሲኮንኑ ይሰማሉ፡፡ የግምገማ መሪ ተዋንያን ናቸው፡፡ አልባሳት የመቀያየር ክህሎት አላቸው፡፡ ከነዚህ ያልተጠነቀቀ አመራር ወይም መሪ ለአደጋ የተጋለጠ ነው፡፡ ተንሸራታችና አንሸራታች ናቸውና፡፡ አፋቸው እንጂ ግብራቸው እኩይ ነውና!
‹‹አጓጉል ምላስ ብቻ ናት
ማሞካሸት የማይደክማት፤
ቀን አዝላ ማታ እምታወርድ
ንፉግን ልመና እምትሰድ!››
ይለናል ጋጣሚ ፀጋዬ ገብረመድህን፡፡ ይህን ልብ ማለት ይበጃል፡፡ ሌላው የሀገራችን ቁንጮ ችግር፤ ብሶትና ምሬትን ቸል ማለት ነው፡፡ ውስጥ ውስጡን የሚቀጣጠል እሳት አንድ ቀን የማይጠፋ ቋያ ይሆናል፡፡
‹‹ከጥንት ጀምሮ እኛ እንደምናውቀው
ሲነድ ሲቃጠል የሚስቅ እሳት ነው
ነገሩ አልሆን ብሎ ሁኔታው ሲጠጥር
ጠጣሩ እንዲላላ፣ የላላውን  ወጥር!››
ዛሬም ያው በረከተ-መርገም ነው! የህዝብን ብሶት እናዳምጥ፡፡ ችግርን ፊት ለፊት መጋፈጥና ተነጋግሮ፣ ተመካክሮ መፍታት እንጂ መሸፋፈኑ፤ ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ›› የሚለውን የአበው ብሂል መዘንጋት ነው፡፡ ‹‹እንደ ድመት አሥራ ሶስት ነብስ ነው ያለን!›› ማለት አያዋጣም፡፡
‹‹እኛ አድገናል ሌሎች ችግር ገጥሟቸዋል›› ማለትም ብዙ አያራምድም፡፡ ያለው›› ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ..›› ነው፡፡ ህዝብ እየተቃወም ነው ሲባል፤ ‹‹በእነ እገሌ ምክንያት ነው› ማለትም ያው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ…›› ነው፡፡ የተቃውሞዎች ሁሉ ማጠንጠኛ ‹‹የመልካም አስተዳደር ችግር ነው›› ማለትም ያነው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ…›› ነው፡፡ የአባዬን እከክ ወደ እምዬ ልክክ (Blame-shifting) ያው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ…›› ነው፡፡ የሕግ የበላይነት በአፍ ቀላል ቢሆንም፣ በተግባር ግን እየተፈፀመ አለመሆኑን አለማመንም ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ›› ነው፡፡ ከሁሉም ይሰውረን! አዲሱ ዓመት አዲስ አድማስ ያሳየን! ልብና ልቦና ይስጠን!!

የሆላንዱ ኩባንያ በባህር ዳር ተቃውሞ የ11.1 ሚ. ዶላር የአበባ እርሻ ተቃጠለብኝ አለ

   የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዜጎቹ ተቃውሞ ወደተስፋፋባቸው የአማራና የኦሮምያ ክልል አካባቢዎች እንዳይጓዙና ህዝብ ከተሰበሰበባቸውና ተቃውሞ ከተቀሰቀሰባቸው አካባቢዎች እንዲርቁ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስጠነቀቀ፡፡
ተቃውሞ ወደተቀሰቀሰባቸው የአማራና የኦሮምያ ክልል አካባቢዎች መሄድ ለአደጋ ያጋልጣል ያለው ሚኒስቴሩ፤ ከዚህ በተጨማሪም ኢትዮጵያ ከኤርትራ፣ ከሱዳን፣ ከደቡብ ሱዳንና ከኬንያ ጋር በምትዋሰንባቸው የድንበር አካባቢዎች በ10 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ውስጥ መገኘት እጅግ አደገኛ ነው ሲል ለዜጎቹ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ባለፈው ሰኞ በባህር ዳር በተቀሰቀሰው ተቃውሞ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተቃዋሚዎች የአበባ እርሻ ኢንቨስትመንቱን በእሳት በማጋየት፤ ሙሉ ለሙሉ እንዳወደሙት “ኢስሜራልዳ ፋርምስ” የተባለው የሆላንድ ኩባንያ በድረገጹ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡11.1 ሚሊዮን ዶላር ያወጣሁበት የአበባ እርሻ ኢንቨስትመንት በእሳት ወድሞብኛል ያለው ኩባንያው፣ ሌሎች በአካባቢው የሚገኙና ንብረትነታቸው የእስራኤል፣ ጣሊያን፣ ህንድና ቤልጂየም ኩባንያዎች የሆኑ ዘጠኝ ያህል የአበባ እርሻዎችም በተቃዋሚዎች ጥቃት ደርሶባቸዋል ብሏል፡፡ የኩባንያው ረዳት ስራ አስኪያጅ ሬምኮ ቤርካምፕ ለአልጀዚራ በሰጡት መግለጫ፣ ኩባንያው የተቃጠለውን እርሻ እንደገና አቋቁሞ፣ ኢንቨስትመንቱን ከማስቀጠል ይልቅ ኢትዮጵያን ለቅቆ የመውጣት እርምጃ ሊወስድ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡

ውዳሴ ዲያግኖስቲክ ሴንተር በየዓመቱ የሚያከናውነውና “ጳጉሜን ለጤና” የተሰኘው ነፃ የምርመራ አገልግሎት የፊታችን ማክሰኞ ይጀምራል፡፡
ማዕከሉ ከትናንት በስቲያ በሸራተን አዲስ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫና የፓናል ውይይት ላይ የማዕከሉ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ዳዊት ኃይሉ እንደተናገሩት፤ ማዕከሉ ያለበትን ማህበራዊ ኃላፊነት ለመወጣት ላለፉት ሰባት ዓመታት የሲቲስካን፣ ኤምአርአይ እና ሌሎች የተለያዩ የምርመራ አገልግሎቶችን ገንዘብ ከፍለው መታከም ለማይችሉ ህሙማን ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ከአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች እና ከአዲስ አበባ ከተማ የሚመጡና የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች በሀኪሞቻቸው ታዞላቸው በገንዘብ ማጣት ምክንያት ምርመራውን ለማግኘት ያልቻሉ ህሙማን፤ ከጳጉሜ 1-5/ 2008 ዓ.ም ድረስ በማዕከሉ በሚሰጠው ነፃ የምርመራ አገልግሎት ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
ማዕከሉ ላለፉት ሰባት ዓመታት በየዓመቱ በሚሰጠው በዚህ ነፃ የምርመራ አገልግሎት፣ ከ15ሺህ በላይ ህሙማን ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለፁት ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፤ በቀጣይም አገልግሎቱን በስፋት ለመስጠት ዕቅድ መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ በማዕከሉ ዓመቱን ሙሉ ገንዘብ ከፍለው አገልግሎቱን ማግኘት ለማይችሉ ወገኖች ከሚሰጠው ነፃ የምርመራ አገልግሎት በተጨማሪ “ጳጉሜን ለጤና” በሚል መሪ ቃል፣ በየዓመቱ በሚሰጠው ነፃ የምርመራ አገልግሎት ከ800-1000 ወገኖች ተጠቃሚ እንደሚሆኑም ገልጸዋል፡፡ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች በሃኪሞቻቸው ታዞላቸው በአቅም ማጣት፣ አገልግሎቱን ማግኘት ያልቻሉ ህሙማን በተጠቀሱት ቀናት ወደ ማዕከሉ በመሄድ፣ ምርመራውን በነፃ ማግኘት እንደሚችሉም አቶ ዳዊት ተናግረዋል፡፡
ማዕከሉ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ከመወጣት አንፃር በክፍለ ከተማው ለሚኖሩ ወገኖች ነፃ የአንቡላንስ አገልግሎትን ከመስጠቱም ሌላ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች የለሚያስፈልጋቸው የክፍለ ከተማው ነዋሪዎች መታወቂያቸውን ይዘው በመቅረብ፣ የ20 በመቶ ቅናሽ ለማግኘት እንደሚችሉ ጨምረው ገልፀዋል፡፡ 

   በርካታ ታላላቅ ዓለማቀፍ የሙዚቃ ሽልማቶችን በማስገባት ስኬታማ የሙዚቃ ጉዞውን የቀጠለው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ፤ በ2017 የዓለም የክብረወሰን መዝገብ በሁለት ክብረ ወሰኖች መመዘግቡን ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ዘ ዊክንድ በሚል ቅጽል ስሙ የሚታወቀው የ26 አመቱ ድምጻዊ፤ “ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” በሚለው የሙዚቃ አልበሙ ባለፈው የፈረንጆች አመት በ“ስፖቲፋይ” ድረገጽ ተጠቃሚዎች በብዛት በመታየቱና ሙዚቃዎቹ በቢልቦርድ የሙዚቃ ሰንጠረዥ ለረጅም ተከታታይ ሳምንታት በምርጥ አስር ዝርዝር ውስጥ በመቆየታቸው፣ በአለም የክብረ ወሰን መዝገብ ላይ በሁለት ክብረ ወሰኖች ስሙን ማስፈሩ ተገልጧል፡፡
“ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” የተሰኘው የአቤል የሙዚቃ አልበም ከታህሳስ 2014 እስከ ታህሳስ 2015 ባለው አንድ አመት ጊዜ ውስጥ በ60 ሚሊዮን የ“ስፖቲፋይ” ተጠቃሚዎች በመታየት ክብረ ወሰን ማስመዝገቡን የጠቆመው ተቋሙ፣ የድምጻዊው ዘፈኖች ከመጋቢት 2015 እስከ ጥር 2016 ባሉት ጊዚያት፣ ለ45 ተከታታይ ሳምንታት በቢልቦርድ የሙዚቃ ሰንጠረዥ ምርጥ አስር ደረጃ ውስጥ ተካትተው መቆየታቸውን ገልጧል፡፡

1- ኢህአዴግ ያለፉት 15 ዓመታት የተሃድሶ ጉዞውን ገምግሞ ሲያበቃ ያወጣው መግለጫ ግርታን ፈጥሯል፡፡ እርስዎስ የገዢውን ፓርቲ መግለጫ እንዴት አዩት?
ሀ) በህዝብ ተቃውሞ ከሚናጥ ፓርቲ የወጣ መግለጫ አይመስልም!
ለ) በስህተት ያለፈውን ዓመት መግለጫ ደግመውት እንዳይሆን!
ሐ)  ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ!!
መ) ኢህአዴግ ራሱን በራሱ በመሸወድ የሚደርስበት የለም!
ሠ) የሌላ አገር ፓርቲ ያወጣው መግለጫ ሳይሆን አይቀርም!
2- ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ፤ባለፈው ሳምንት የመኢአድ መሪዎችን በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዳወያይዋቸው ተዘግቧል፡፡ በኢህአዴግ የ25 ዓመት የሥልጣን ታሪክ፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችን በቤተ-መንግስቱ ጋብዞ ሲያነጋግር የአሁኑ የመጀመሪያው ነው ተብሏል፡፡ እርስዎ ዜናውን ሲሰሙ ምን አሉ?  
ሀ) እቺ አገር ተስፋ አላት!!
ለ) ግብዣ ነው ውይይት?
ሐ) ከውይይቱ የተገኘው ውጤት አልተነገረንም!!
መ) ግን እስከ ዛሬ ለምን ዘገዩ!?
ሠ) “የቱርክ ኢንቨስተሮችን ሲባሉ ከተቃዋሚዎች ጋር ተሞዳሞዱ” በሚል እንዳይገመገሙ ሰጋሁ!
3- በሪዮ ማራቶን 2ኛ በመውጣት ድል ያስመዘገበው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ፤ ለኦሮሞ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ያለውን የትግል አጋርነት ለማሳየት እጆቹን ወደ ላይ በማጣመር ተቃውሞውን ለዓለም ገልጧል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ አትሌቱ ወደ አገሩ ቢመለስ የተለየ ችግር እንደማይገጥመው አስታውቋል፡፡ እውነት ወደ አገሩ ቢመለስ  ችግር ሳይገጥመው በነጻነት የሚኖር ይመስልዎታል?
ሀ) ይሄን ለማወቅ ኢህአዴግን መሆን ይጠይቃል!
ለ) “አልበላሽምን ምን አመጣው?!” አለች ጦጢት!!
ሐ)መንግስት እንዳይምልለት ፕሮቶኮሉ አይፈቅድም!   
መ) ቆይ ግን ምን ፍለጋ ወደ አገሩ ይመለሳል!?
ሠ) ኢህአዴግ ገና አሁን ንግግር ተሳካለት!
4- በአማራና በኦሮምያ ክልሎች ህዝባዊ ተቃውሞ በተቀሰቀሰበት በአሁኑ ወቅት የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትር ቢሆኑ ምን ዓይነት የመፍትሄ እርምጃ ይወስዱ ነበር?
ሀ) እስካሁን በኦሮምያ ቢያንስ 4፣በአማራ 2 ህዝባዊ ውይይቶችን አደርጋለሁ!
ለ) በቀውጢ ሰዓት ጠ/ሚኒስትር መሆን አልፈልግም!
ሐ) ተቃውሞውን ተከትሎ የታሰሩ ዜጎችን በሙሉ እፈታለሁ!!
መ) ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር መደበኛ ውይይት እጀምራለሁ!
ሠ) “ከበሮ በሰው እጅ ሲያዩት ያምር፣ሲይዙት ያደናግር!; የሚለው ተረት ትዝ አለኝ!!
5- የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፤በህዝቡ ላይ ፍርሃት ላለመፍጠር በሚል በአተት የሞቱ ሰዎችን ቁጥር አንድም ያስተባብላል አሊያም ጨርሶ ከመናገር ራሱን ያቅባል፡፡ ይሄን የሚያደርገው ለምንድን ነው ብለው ያስባሉ?
ሀ) እንደ ኢህአዴግ የቁጥር ፎቢያ ይኖርበታል!!
ለ) ወረርሽኙ ሲቆም ለተረፍነው “ሰርፕራይዝ” ሊያደርገን ፈልጎ ነው!
ሐ) አተትም ፖለቲካ ሆናለች ማለት ነው!!
መ) የአገር ገጽታ እንዳይበላሽ ተብሎ ይሆን?
ሠ) ፍርኃት እኮ ህዝቡን የበለጠ እንዲጠነቀቅ ያተጋዋል!
(N.B- ከተሰጡት ምርጫዎች ውስጥ ለእርስዎ የሚስማማ ከሌለ፣
የራስዎትን ምርጫ (ረ) የማካተት መብትዎ የተጠበቀ ነው!!!)

   በኦሮሚያና በአማራ ክልል እየተካሄዱ ያሉ ተቃውሞዎች፣የተጠራቀመ የህዝብ ብሶት ፈንድቶ የታየባቸው ናቸው፡፡ አመፁ የህዝብ ብሶት የወለደው ምሬት ነው፡፡ የኢህአዴግ ሰርአት አንገሽግሾት የወጣ ነው፡፡ ለብዙ ጊዜ የነበረ በደልና ጭቆና፣ ትንሽ ወቅታዊ ምክንያት በመፈለግ ሲፈነዳ የታየበት ነው። ለምሳሌ በኦሮሚያ ማስተር ፕላኑ መነሻ ምክንያት ነው፡፡ መሠረታዊ መነሻ አይደለም፡፡ በአማራ ክልልም መሠረታዊ መነሻው የወልቃይት ጉዳይ አይደለም፡፡ እሱ መነሻ ምክንያት ነው እንጂ ዋና ምክንያቱ ጭቆና ነው፡፡ የተደራጀ አመራር ወይም ሃይል የሌለውም በዚህ የተነሣ ነው፡፡ ህዝብ ያለ መሪ ስሜቱን የገለፀበት አመፅ ነው፡፡
 ይሄን አመፅ የሚመራው ድርጅት ከሌለና ካልተደራጀ ዝም ብሎ ንብረት መውደምና የሠው ህይወት መጥፋት ብቻ ነው የሚያስከትለው፡፡ ምክንያቱም ከኢህአዴግ ተፈጥሮ አንፃር ስናየው፤ ለህዝብ ጥያቄ መልስ ከመስጠት ይልቅ የሃይል እርምጃ መውሰድ ነው የሚቀናው፡፡ ህዝቡ ደግሞ እየተነቃቃ ለውጥ እየፈለገ ሲሄድ፣ ዝም ብሎ ንብረት መውደምና ህይወት መጥፋት ይሆናል። መጨረሻም ለውጥ ላይኖረው ይችላል፡፡ ለውጥ የሚኖረው የተደራጀና መሪ ሲኖረው ብቻ ነው፡፡ ህዝብ የሚተማመንበት ሃገራዊ የፖለቲካ ድርጅት ሲኖር ነው መነሳሳቱ ለውጥ ሊያመጣ የሚችለው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ፓርቲዎች በተለያየ አቅጣጫ ተደራጅተው፣ እርስ በእርስ ከመናቆር በመላቀቅ፣ ለሃገሪቱ መድህን መሆን አለባቸው። የህዝብ ችግር የኛ ችግር ነው ብለው ህዝቡን ለመምራት አንድነት ፈጥረው፣ሃገሪቷን ከአደጋ ለመጠበቅ መንቀሳቀስ አለባቸው፡፡ ይህን ካደረጉ ህዝቡን ይዘው ከኢሕአዴግ ጋር የመደራደር አቅም ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ ወደ ድርድርና የፖለቲካ ውይይት እንዲገባ የማስገደድ ዕድል ያገኛሉ፡፡ ኢህአዴግም ከህዝቡ የተነሳው ተቃውሞ ሰፊ መሠረት ያለው መሆኑን አውቆ፣ ለድርድር ራሱን ሊያዘጋጅ ይችላል፡፡
ያለበለዚያ ኢህአዴግም እርምጃ እየወሰደ መቀጠሉ ስለማይቀር፣ዝም ብሎ መጠፋፋት ነው የሚሆነወ፡፡ ወደ እርስ በእርስ ግጭት ነው ሊያመራ የሚችለው፡፡፡ የህዝቡ የለውጥ ፍላጎት በሚገባ ካልተደራጀ፣ መጨረሻ ላይ ደግሞ እየተዳከመ ይሄዳል፡፡ ኢህአዴግ የህዝብን ሃሳብና ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ በህዝብ ላይ የሃይል እርምጃ መውሰድ መፍትሄ መሆን እንደማይችል መገንዘብ ይኖርበታል። ሃገሪቷንና ህዝቡን ከአደጋ የማዳን ሁኔታ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ስራ ነው የሚሆነው። አሁን ህዝቡን መምራት መቻል አለባቸው። የመደራደር አቅማቸውን ማሳደግ ይገባቸዋል፡፡ እነሱም አንድ ሆነው፣ሁሉንም የኢትዮጵያ ህዝብ በአንድነት እንዲቆም ማድረግ አለባቸው፡፡

    ችግሩ በውይይት ይፈታ ሲባል የምሁራን የቃላት ስንጠቃና የፖለቲከኞች ውይይት እንዳይሆን ነው። ችግሩ በዚህ አንቀፅና በዚህ ንዑስ አንቀፅ በሚል ሳይሆን ዕድት ያለ አዕምሮ ይዞ፣ በመሰብሰብ ሁሉንም አሳትፎ፣ ምን እናድርግ? ይህቺ ሀገራች ነች፤ለሀገራችን ለህዝባችን የሚበጀው የቱ ነው? ብሎ እንደ አዲስ ማሰብ ያስፈልጋል ባይ ነኝ፡፡ ይሄ ደግሞ የምሁራኑና የፖለቲከኞች ብቻ መሆን የለበትም። የሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ሀሳብ የሚወከልበት መድረክ መኖር አለበት፡፡ በተቻለ መጠን በተለይ በመንግስት በኩል በሰፊው ሊታሰብበት ይገባል።  የብልጣ ብልጦች ውይይት መሆን የለበትም። ለኢትዮጵያ ህዝብ እኛ ነን የምናውቅልህ ማለት አያስፈልግም፡፡ ሰፊው ህዝብ በሚገባ ይናገር፤እሱን እናዳምጠው፡፡ ይሄን ስናደርግ ደግሞ እየተቋሰልን እየተጋደልን መሆን የለበትም፡፡ በሁሉም በኩል ሰፊ ልብ ያስፈልጋል፡፡ በፅሞና ለመነጋገርም ጊዜ ያስፈልጋል፡፡ ታግሶ ነው መወያየት የሚያስፈልገው።

    በ97 ምርጫ ማግስት መንግስት በተቃዋሚዎች ላይ ከመጠን በላይ ኃይል መጠቀሙን በተመለከተ ያቀረበው ምክንያት ዘመናዊ የአድማ መበተኛ መሳሪያዎች የሉኝም የሚል ነበር፡፡ ዛሬም በዘመናዊ መንገድ አድማ መበተን አልቻለም። ለነገሩ በመጀመሪያ ደረጃ መበተንስ ያስፈልጋል ወይ? የሚለው መታየት አለበት፡፡ በእኔ እምነት ተቃውሞዎቹን እየበተነ ያለው የፖሊስ ሰራዊት አይመስለኝም፡፡ ወታደር ሲሰለጥን ግደል ሊባል ይችል ይሆናል፡፡ ፖሊስ ግን ሲሰለጥን ወንጀለኛን መግደል የወንጀሉን ምንጭ ለማጣራት ስለማይጠቅም ግደል አይባልም፡፡ ወንጀለኛ ከተገደለ ወንጀሉ አይታወቅም፡፡ ረበሹ የተባሉ ሰዎችን ከነሙሉ አካላቸው ይዞ ነው፣ ለምን ይህን አደረጋችሁ? በሚል የሚያጣራው፡፡ አሁን ግን ግንባርና ደረት እየመቱ ነው የሚገድሉት፡፡ ይሄ በምንም አይነት ሁኔታ ተቀባይነት የለውም፡፡
ሰዎች ረብሸው ጎማ አቃጥለው፣ ቤት ሰብረው ቢሄዱ በካሜራ አጣርቶ፣ እንደዚህ ሲያደርጉ ተይዘዋል ተብሎ ፍ/ቤት አቅርቦ ማስወሰን የሚቻል ነው፡፡ አሁን ግን ሽብር በመንዛትና በማስፈራራት አፈና እየተካሄደ ነው ያለው፡፡ ወላጆች፤ ልጆቻቸው መብታቸውን እንዳይጠይቁ፣ ቤታችሁ እሰሯቸውና ቀልቧቸው ነው እየተባለ ያለው፡፡ በአጠቃላይ እየተደረገ ያለውን ተቃውሞ መንግስት የሚያስተናግድበት መንገድ የመንግስት አይመስልም፡፡ ልጅ ቢያጠፋ ዝም ብሎ አይደበደብም፤ምንድን ነው ተብሎ ተጠይቆ ይመከራል፡፡ መንግስት ግን በዚህ መንገድ አይደለም ህዝብን እየያዘ ያለው፡፡
እንደኔ ሰላማዊ ተቃውሞዎቹ በኦሮሚያና በአማራ ክልል ብቻ ሳይሆን በብዙ የሀገሪቱ ክልሎች አሉ፡፡ ትግራይ ውስጥ ከምንግዜውም በላይ ሰው ተረብሾ ያለበትና በትክክለኛ መንገድ መተዳደር ያልቻሉበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በደቡብም ተመሳሳይ ነው። ግን ጎልተው እየወጡ ያሉት የኦሮሚያና የአማራ ክልል ናቸው፡፡ ከምንም በላይ የአማራ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር ነፍስ ዘርቶ፣ እግርና እጅ አውጥቶ እየተንቀሳቀሰ ነው ያለው። ይሄን እንግዲህ ኢህአዴግ የኔ ፍሬ ነው ሊል ይችል ይሆናል፡፡ ምክንያቱም የአማራ ብሄርተኝነት እፈልጋለሁ ሲል ነበር ተፈጠረለት። የአማራ ብሄርተኝነት ሲፈጠር ደግሞ የአማራ የሚባሉ ጥያቄዎችን ያመጣል፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በአግባቡ መመለስ አለበት ማለት ነው። የፈጠረው የአማራ ብሄርተኝነት የሚያመጣውን ጥያቄ መመለስ አለበት። እነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ ዝም ብሎ ከዚህም ከዚያም የሚነሱ አይደሉም፡፡ እነሱ እንደሚሉት፤ ሰው መሬት አስተዳደር ሄዶ ካርታ ስለተከለከለ፣ የኑሮ ውድነት ስላሰቃየው ወዘተ----የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ብቻ አይደለም፡፡ የነፃነት ጥያቄዎች ናቸው፡፡ የአዲስ አበባ ዙሪያ ማስተር ፕላን፣ ወለጋ ላለ ወጣት ይሄን ያህል ስሜት የሚሰጠው አይሆንም፡፡ አባይ አጠገብ ላለ የጎጃም ሰውም ጠረፍ ላይ ያለ መሬት ብዙም ሊያሳስበው አይችልም ነበር፤ ግን እነዚህ መነሻ ሰበቦች ናቸው፡፡
አፄ ኃይለሥላሴ በመጨረሻው ሰዓታቸው ላይ ጥያቄው የደሞዝ ይመስላቸውና ለወታደሩ ደሞዝ ይጨምራሉ፤እንደገና የነዳጅ ዋጋ ጥያቄ ይመስላቸውና የነዳጅ ዋጋ ያስተካክላሉ ግን በወቅቱ የነበሩት ጥያቄዎች እሳቸው ያሰቧቸው አልነበሩም፡፡ የነፃነትና መሰረታዊ የሆኑ የስርአት ለውጥ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ አሁንም ዋና ዋና የሚባሉትን ጥያቄዎች ከዚህ አንፃር መመልከት ያስፈልጋል እንጂ ዝም ብሎ በግምት መልስ በመስጠት ብቻ የሚገላገሉት አይደለም፡፡
ስልጣኑን የያዙት ሰዎች በባህሪያቸው የሚሰጣቸውን ምክረ ሀሳብ የሚቀበሉ አይደሉም፡፡ አይሰሙም አያነቡም፤ ቢሰሙም ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን ነው። እሱንም የሚሰሙት ያስተላለፉት መልዕክት በትክክል መነገሩን ለማጣራት ነው እንጂ ለማወቅ አይደለም፤ስለዚህ የመማር እድላቸው ሰፊ አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች እነሱ መስማት የሚፈልጉትን ብቻ ሳይሆን መስማት የማይፈልጉትንም ማድመጥ ይኖርባቸዋል፡፡ መፍትሄውን ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ እየተናገርን ነው፡፡ አዳምጠው ራሳቸውን ለለውጥ ዝግጁ የማያደርጉ ከሆነ፣ ሁኔታው ወደ አልሆነ አቅጣጫ ሊጓዝ ይችላል፡፡  እነሱም ክብር በሌለው ሁኔታ የሰሩት አንድም ሁለትም የሆነ ጥሩ ነገር ካለ ጠፍቶ ለውጥ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ስለዚህ ሁኔታው ወደዚያ እንዳያመራ ስርአት ያለው ሽግግር የሚፈጠርበትን ሁኔታ ማመቻቸት አለባቸው፡፡
በእጅጉ መማር ያለባቸው እነሱ ያላቸውን እውቀትና ኃይል ተጠቅመው፣ ጥሩ ነገር እንሰራለን ብለው የፈጠሩትን ስህተት፣ አሁን እነሱ ባላቸው የእውቀት ደረጃ ሊፈቱት አይችሉም፡፡ ስለዚህ ተጨማሪ እውቀትና አስተሳሰብ ማዳበር አለባቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች አዲስ አስተሳሰብና እውቀት ለመያዝ ዝግጁ እንዳልሆኑ የሰሞኑ መግለጫቸው ያመላክታል፡፡ መግለጫቸውን የሰማ ሰው፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ መሞታቸውን እርግጠኛ ይሆናል፡፡ አንድም እንኳ አዲስ መልዕክት የለውም፡፡ ከዚያ ሁሉ ገፅ መግለጫ አንድም የተጨበጠ መልዕክት አላገኘሁበትም፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነው፣ ይህን አይነቱን ውስብስብ ችግር ሊፈቱ አይችሉም። ስለዚህ ህዝቡ አመኔታ ሊጥልበት የሚችልበትን የመፍትሄ አቅጣጫ መከተል አለባቸው፡፡ ለዚህ ደግሞ ምሁራን የሚሰነዝሩትን የመፍትሄ ሃሳቦች በሚገባ ማዳመጥ አለባቸው፡፡