Administrator

Administrator

ብዙ የናፈቁን ዜናዎች አሉ!

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሁለቱ ልጆች እያወሩ ነው፡፡ አንደኛው ልጅ ምን ይላል… “አባዬ የሁሉም ነገር ዋጋ እየጨመረ ነው ሲል ሰማሁት፡፡”
“ምንድነው የጨመረው?”
“የምግብ፣ የልብስ፣ የቤት ኪራይ ሁሉ ጨምሯል አለ፡፡ ደግሞ ምን አለ መሰለህ!”
“ምን አሉ?”
“የሆነ ነገር ቁጥሩ ቀንሶ ማየት ጓጉቻለሁ አለ፡፡”
ጓደኝየው ምን ቢለው ጥሩ ነው… “ግዴለም፣ የአንተን ሰርተፊኬት ሲያዩ በደንብ የሚቀንስ ቁጥር ያገኛሉ፡፡
ሀሳብ አለን…የኑሮ ማስተካከያ ይደረግልን፡፡ ልክ ነዋ…ለምንም ነገር ማስተካከያ ይደረግ የለም አንዴ!
እናላችሁ…ሥጋ እንኳን በሩብ ኪሎ መሸጥ መጀመሩን ወዳጄ ሲያጫውተኝ ነበር፡፡ እየደረስን ያለንበትን ዘመን እዩልኝማ፡፡ ገና በኪሎና በግራም መለካቷ ቀርቶ በጉርሻ ሊሆን ይችላል፡፡ “ሁለት ጉርሻ ሥጋ ስጠኝ…” ማለት እንጀምር ይሆናል! አይሆንም የሚባል ቃል እየጠፋ ያለባት አገር ነቻ!
እናማ…የኑሮ ማስተካከያ ይደረግልን፡፡
ስሙኝማ…በቲቪ ላይ እኮ የምግብ አሠራር እያየን መጎምጀት ከተውን ከረምን፡፡ ልክ ነዋ… ቦምቦሊኖ ባረረብን ዘመን የምናየው ሁሉ እንቁልልጭ ሆነብና!
የምር ግን… አለ አይደል… የፈጠራ ጊዜ አሁን ነው። በሬድዮና በቲቪ ስለምግብ አሠራር የምታስተምሩን ፈጠራ ቢጤ ጨምሩበታ፡፡ ለምሳሌ ‘ያለበርበሬ ቀይ ወጥን መሥሪያ ዘጠኝ ዘዴዎች’ አይነት ነገር። ደግሞላችሁ… ‘ሹሮ ሽንኩርትና ዘይት ሳይገባባት ውሀና ሹሮዋ ብቻ ተበጥብጠው ጣት የሚያስቆረጥም ወጥ የመሥሪያ ምስጢሮች…’ የሚል ፈጠራ፡፡ ልክ ነዋ…ትንሸ ቆይተን ጣት የምንቆረጥመው ምግብ ስለጣፈጠን ሳይሆን ጉርሻችን ከማነሷ የተነሳ ጣት እየተቀላቀለችብን ሊሆን ይችላል፡፡
ሀሳብ አለን…የምግብ አሠራር የቲቪ ትምህርቱ በመደብ ይከፋፈልልን፡፡ አለ አይደል…
‘በወር አንዴ ሥጋ ለሚበሉ…’
‘በወር አንዴ ሥጋ በህልማቸው ለሚያዩ…’
‘በወር አንዴ ሥጋ የሚባለው ቃል መዝገበ ቃላት ላይ መኖሩ ትዝ ለሚላቸው…’  በሚል መደብ ይከፋፈልልን። ወይንም እንደ ግብር ከፋዮች ‘ሀ’ ‘ለ’ እና ‘ሐ’ ተብለን እንከፋፈል፡፡፡ “የዛሬው የምግብ አሠራር ለ‘ለ’ ምድቦች ብቻ የሚሆን ነው…” ስንባል ቁርጣችንን አውቀን አርፈን እንቀመጣለና!
እናላችሁ… ዘንድሮ… አለ አይደል… “አንተ ምነው ባለቤትህ ከሳችብኝ!” ብሎ አስተያየት አሪፍ አይደለም። አሀ…ነገርዬው ሁሉ ‘ጣራ ነክቶ’ እንዴት ትወፍር! በፊት እኮ “በሽታ እንኳን ያወፍራል…” ይባል ነበር፡፡ ዘንድሮ ኩሽናው ሁሉ ምነዋ ይሄን ያህል መአዛ የለውሳ!
እናማ… “አንተ ምነው ባለቤትህ ከሳችብኝ!” ብሎ አስተያየት ‘ወቅቱን ያላገናዘበ’ ይሆናል፡፡ አሀ… በብር ሦስትና አራት ይገዛ የነበረ እንቁላል አንዱ ሦስት ብር ከሀምሳ ሳንቲም ምናምን ሲሆን እንዴት ሆና ‘ሥጋ’ ታውጣ፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ ባል ራሱ ‘አርፎ አይቀመጥ’!  ቂ…ቂ…ቂ….
እኔ የምለው…“ዳየት ላይ ነኝ…” ምናምን የምትሉ እንትናዬዎችን ሌላ ሰበብ አምጡማ፡፡ ኑሮ ራሱ ሁላችንንም ‘ዳየት ላይ’ አድርጎናላ! እናማ…‘ዳየት ላይ’ መሆኑ የግዴታ እንጂ የውዴታ ባልሆነበት…“ዳየት ላይ ነኝ…” አይነት ምክንያት አይሠራም፡፡
ስሙኝማ…በፊት የሆነ ነገር ዋጋው ጣራ ነካ ሲባል የሆነ መሥሪያ ቤት ለ‘ፐብሊክ ኮንሰምሺን’ ለሚሉት ነገርም ቢሆን… “የዋጋ ንረቱን ለማረጋጋት ሥራዎች እየተሠሩ ነው…” ምናምን  የሚባለው ‘ልብ አንጠልጣይ ልብ ወለድ’ እንኳን አሁን፣ አሁን እየቀነሰ ነው፡፡
“እነሱ አንድ ነገር ያደርጉልናል…ዋጋውን ወደ ቦታው መልስው ያረጋጉልናል…” ስንል ተስፋ ቆረጡ እንዴ! አሀ…ወንበር ብቻ ሳይሆን ዋጋም ይረጋጋልና!
እናማ…“በተለይ በምግብ ሸቀጦች ላይ የሚደረገውን ምክንያተ ቢስና ኢፍትሀዊ ዋጋ ንረት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስተካከል የማያዳግም እርምጃ መውሰድ ሊጀመር ነው…” አይነት ዜና መስማት ናፍቆናል፡ ልከ ነዋ…በሆዳችን ‘ድንቄም ተወሰደ!’ ብንል እንኳን ለጊዜውም ቢሆን ለጆሯችን አሪፍ ዜማ ይሆናላ!
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ልንሰማቸው የናፈቁን ዜናዎች መአት ናቸው…
‘ከወሩ መግቢያ ጀምሮ በመላ አገሪቱ የጤና አገልግሎት ሙሉ፣ ለሙሉ ነጻ ሆኗል…’
‘ከመጪው ሰኞ ጀምሮ አንድ ኩንታል ጤፍ ከአምስት መቶ ብር በላይ ሲሸጥ የተገኘ ነጋዴ ፈቃዱ ተነጥቆ ከመፋቂያ በላይ የሆነ ምርት እንዳይሸጥ የአራተ ዓመት እገዳ ይጣልበታል…’
‘በበዓላት ወቅት ቀበሌዎች ቤት ለቤት እየዞሩ ኪሎ ቅቤ በሀያ አምስት ብር ማከፋፈል ይጀምራሉ…’
‘የአንድ ኪሎ በርበሬ ከፍተኛ ዋጋ አሥራ አምስት ብር ከሃያ አምስት ሳንቲም እንዲሆን እንትን መሥሪያ ቤት ወሰነ…’
‘ከፍተኛ ባለስልጣኖች በአሥራ አምስት ቀን አንድ ጊዜ መርካቶና ሾላ ገበያ እየሄዱ ራሳቸው እንዲገበዩ የውዴታ ግዴታ ተጥሎባቸዋል…’ (ያን ጊዜ…አለ አይደል…“እንዲህም የሚኖር ሰው አለ!” ይሉ ነበር፡፡)
እንደ እነዚህ አይነት ‘ዜናዎች’− “ካልተረጋገጡ የወሬ ምንጮች…” እንኳን− የምንሰማበት ዘመን ይመጣ ይሆን! መመኘትም የ‘ክላስ’ ጉዳይ እስኪሆን ድረስ እኛም እንመኝ እንጂ!
ካነሳነው አይቀር…ሌሎች የናፈቁን ዜናዎች አሉ…
‘እንትንና እንትን ድርጀቶች ከእንግዲህ መዘላላፍና ትርፍ ቃላት መወራወር ትተው ቁም ነገር ላይ ለማተኮር ተስማምተዋል…’
‘ባለስልጣኖች ለሜዲያ መግለጫ በሚሰጡበት ጊዜ የማስፈራሪያና የንቀት ቃላት ሲናገሩ ቢገኙ የተሰጣቸውን ወንበርና የተሰጣቸውን ቤተ ይነጠቃሉ…’ (ቂ…ቂ…ቂ…. ታየኝ!)
‘በሆነ ባልሆነው ትንሹንም ትልቁንም የሚዠልጡ ስነ ስርአት አስከባሪዎች በእጃቸው አርጩሜ እንኳን እንዳይዙ ይከለከላል…’
አሪፍ አይደል! ያኔ እንዴት አይነት ‘ነፍስ የሆንን’ ሰዎች ይወጣን ነበር፡፡
ደግሞላችሁ ሌሎች የናፈቁን ዜናዎች አሉ…
‘የሰው ሚስት የሚያማግጥ ጭቃ ሹም ሆነ ምስለኔ አይደለም ሴት፣ የሴት ፎቶ የማያይበት በረሀ ለአምስት ዓመት እንዲቀመጥ ይገደዳል…’
‘ሥራ አስኪያጆች ኤክሲኪዩቲቭ ሴክሬታሪዎችን ፊት ለፊት በአካል ሳይሆን በስልክ ብቻ እንዲያገኙ ተወሰነ…’ (ቂ…ቂ…ቂ…)
‘በየመጠጥ ቤቱ መቶና መቶ ምናምን ብር ለመክፈል የመለስተኛ መሥሪያ ቤት ተከፋይ ደሞዝ የሚመስል የብር መአት የሚመዙ ሰዎች ሌላው ተገልጋይ ላይ ለሚደርሰው ማንኛውም የብሽቀት፣ የመጎምጀት፣ የደም ብዛት ችግር ሁሉ ተጠያቂ ይሆናሉ…’
‘ከእንትናዋ ጋር የምትሄደውን እንትናዬ ከሦስት ሰከንድ በላይ ትክ ብለው የሚያዩ ባለመኪኖች መኪናቸውን ተነጥቀው ለአሥራ አንድ ወር በእግራቸው ብቻ እንዲሄዱ ይደረጋሉ…!’ የሚል ዜና ናፍቆናል፡፡ (እግረኞቹ ሁሉ እየተሳቀቁ አሳዘኑና!)
መአት ልንሰማቸው የምንፈልጋቸው ዜናዎች አሉ፡፡ “ሰበር ዜና…ዋጋዋ አልቀምስ ብሎ ሃያ ምናምነኛ ፎቅ ላይ የወጣችው ቲማቲም አንድ ኪሎ በብር ተሀምሳ እንደገባች ተገለጸ…” አይነት ዜና መስማት ናፍቀናል፡፡
“ከፍተኛ የአገሪቱ ባለስልጣናት በመርካቶ፣ በአትክልት ተራና በሾላ ገበያ ባደረጉት ጉብኝት ባዩት የምግብ ግብአቶች ዋጋ ከፍተኛ ድንጋጤ እንዳደረባቸው ምንጮቻችን ገለጹ፡፡ በተለይ አንዱ ባለስልጣን… ‘ኑሮ ይህን ያህል መክበዱን በህልሜም ጠርጥሬ አላውቅም፡፡ ዕንባዬ ነው የመጣው…’ ማለታቸው ተዘግቧል…” አይነት ዜና ናፍቆናል፡፡
የኑሮ መክበድን በተመለከተ ብዙ ልንሰማቸው የምንፈልጋቸው ዜናዎች አሉ፡፡
የከበደውን ኑሮ የሚያቀልልን ዘመን ያፍጥልንማ!
ጀርባችን ሳይሰበር፣ ሰማይ የወጣውን የሸቀጦች ዋጋ የሚሰብር ተአምር ይላክልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

ከዕለታት አንድ ቀን እመት ጦጢት ምግብ ስትሰራ እንስሳት አገኟትና፤
“እመት ጦጢት?”
“አቤት” አለች፡፡
“ሽሮና በርበሬ ማን ያመጣልሻል?” አሏት፡፡
“ባሌ” አለች
“ከየት ያመጣል?”
“ሠርቶ፣ ወጥቶ፣ ወርዶ”
“ሰርቆስ እንደሁ የሚያመጣው በምን ታውቂያለሽ?”
“አምነዋለሁ”
“ቂቤስ ከየት አመጣሽ?”
“ባሌ አመጣልኝ”
“ከየት ያመጣል?”
“ሰርቶ፣ ወጥቶ - ወርዶ”
“ሰርቆስ እንደሁ በምን ታውቂያለሽ”
“ባሌን አምነዋለሁ”
“ከዕለታት አንድ ቀን ሌላ ጦጢት ይዞብሽ ቢመጣስ?”
“ተገላገልኳ! አጋዥ አገኘሁ፡፡ እሷ ምግብ ትሰራለች፤ እኔ እሱን አቅፌ እተኛለሁ”
“እስከ ዛሬ ጦጣ ብልጥ ናት ሲባል ነበር፡፡ ለካ አንደኛ ደረጃ ጅል ነሽ?!”
“ጅልስ እናንተ፡፡ እየሰረቃችሁ መዋችላሁ አንሶ ወደሌላ ለማዛመት ሌብነት፣ ከቤት - ቤት ይዛችሁ የምትዞሩ!! በሉ ሌብነታችሁን ሌላ ቤት ይዛችሁልኝ ሂዱ!” ብላ ከቤት አስወጣቻቸው፡፡
*   *   *
እንደ ጦጣ አለመመቸት ብልጥነት ብቻ ሳይሆን ብልህነትም ነው!
ጥርጣሬ፣ ቅጥፈትና ሌብነት አንድ ህብረተሰብ ውስጥ ሲነግሥ ዕድገት መቀጨጩ አሌ አይሉት ነገር ነው፡፡ የተዋሃደውን ለመነጣጠል፣ የተጋባውን ለማፋታት፣ የተደራጀውን ለመበታተን መሞከርን ያህል እኩይ ተግባር ያጥጣል። የተማረው እንዳልተማረ ይናቃል፡፡ የመንገዱን መነሻ እንጂ መድረሻውን አለማስተዋል የዕለት የሰርክ ህፀፅ ይሆናል፡፡
ሮበርት ግሪን፤
“ፍፃሜውን የማትገምተው ነገር አትጀምር” ይለናል፡፡
ያቀድነው ዕቅድ ከየት ያስጀምረናል? ወዴት ያመራናል? ወዴትስ ያደርሰናል? ግብዐቶቹ ምን ምንድናቸው? ብሎ በቅጥ በቅጡ እያዩ መከታተል፤ እናም እፍፃሜ ሳይደርስ ሌላ ምዕራፍ አለመጀመር፣ በተለይ ትግል ውስጥ ለገባ ቡድን፣ ስብስብ፣ ማህበር ወይም ድርጅት፤ ዋና ነገር ነው፡፡ ሁለተኛው በቂ ዝግጅት ማድረግ ነው። ባጭሩ በአገርኛ ግጥም፡-
“ቀድሞ ነበር እንጂ፣ መጥኖ መደቆስ
አሁን ምን ያደርጋል፣ ድስት ጥዶ ማልቀስ” የሚለውን ማስታወስ ነው፡፡
“ሌሎች አዝመራውን ስለሚሰበስቡት ሰብል ማለም ከንቱ ህልም ነው፡፡ ይልቅ ራስህ መጨረሻውን የምትጨብጠውን ህልም ዛሬውኑ አልም!” ይላሉ አበው፡፡
ህልማችን ዕውን እንዳይሆን እፊታችን የሚደቀኑትን እንቅፋቶች ለይቶ ማስቀመጥ፣ እንቅፋቶቹን አልፎ ለመሄድ የሚገባውን ያህል አቅም መፍጠርና ጉልበትን ማጠራቀም፤ ሳይታክተን ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ በፅናት መጓዝ፤ ያስፈልጋል፡፡ ምንጊዜም ቢሆን ሙሉ በሙሉ ማሸነፍና ሙሉ ለሙሉ መሸነፍ አለመኖሩን፣ ማመንና ይልቁንም፤ ጠንካራና ደካማ ጎን ሁሌም መኖሩን ማስተዋል የተሻለ ዕውነታ ነው፡፡
ሁኔታዎች ተለዋዋጭ መሆናቸውንና አዲስ አሸናፊ ምንጊዜም መብቀሉን ለአፍታም አለመዘንጋት ነው፡፡ ተስፋ አለመቁረጥ የሚመነጨው ከዚህ ዕሳቤ ነው። ያለ ሁሌም የሚኖር ይመስለዋል፤ ይላሉ አበው፡፡ ሆኖም ያልፋል፤ ማለታቸው ነው። የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የፍትህ አካላት፣ የአስተዳደር ወኪሎች እና ፍርድ ቤቶችም ጭምር፣ ከህብረተሰብ ጋር የሰፋ ግንኙነት መፍጠርና በመዋቅርም፣ በመንፈስም የበለጠ ዲሞክራሲያዊነት እንዲኖራቸው መጣር፤ ዛሬ የዓለም ሁሉ ትጋት ነው፡፡ ከዚህ የድርሻችንን መውሰድ ነው፡፡ ክሊንተን ሮዚተር የተባለው ምሁር፤ “አገር ያለ ዲሞክራሲ፣ ዲሞክራሲ ያለ ፖለቲካ፣ ፖለቲካ ያለ ፓርቲዎች አይኖርም” ይለናል። ይህን እንዲሰራ ለማድረግ ግን ቀና ልቡና ይጠይቃል፡፡ ጤናማ ፓርቲና ጤናማ ፖለቲካዊ ስነ - ልቦናም እነዚህ ውስጥ ወሳኝ ናቸው፡፡ ያሉት ቀና ፓርቲዎች እጅግ ጥቂት ናቸው፡፡  ያሉንን የፖለቲካ ፓርቲዎች ካመናመንንና ካጠፋናቸው     “ከርከሮ አንዲት ፀጉር አለችው፣ እሷን ለማጥፋት ይተሻሻል” የሚለውን ተረት በታሳቢነት ያዝን ማለት ነው፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መቀመጫ የኾነችው የቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፥ ጥፋቶች ታርመው ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሰራር እንዳይሰፍን በሚሹ ጥቂት የአስተዳደር ሰራተኞች፣ በህይወት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድር ከአድማ ያልተናነሰ እንቅስቃሴ እየተደረገበት መኾኑን አስታወቀ፡፡ የመልካም አስተዳደር ጅምሩን ከፍጻሜ ለማድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ የአስተዳደር ክፍሎች እገዛ እንዲያደርጉለትም ጠይቋል፡፡
ለብክነት፣ ለዘረፋ እና ለሙስና ከተመቻቸ አሰራር እንዲሁም በገዳሟ ቀደም ሲል ከመልካም አስተዳደር ዕጦት የተነሳ የተከሰቱ ጥፋቶችን ለማረም ልዩ ልዩ መመሪያዎችንና የውስጥ ደንብ ረቂቆችን ማዘጋጀቱን ሰበካ ጉባኤው ለሀገረ ስብከቱ የዋና ሥራ አስኪያጅ ጽ/ቤት ባቀረበው ሪፖርት ገልጿል፡፡ ይኹንና ለቁጥጥር የሚያመች ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለበትን አሰራር ለማስቀጠልና ለማስፈጸም እንዳይቻል ጥቂት የአስተዳደር ሰራተኞች ማኅበረ ካህናቱን በመከፋፈል፣ “ከሰበካ ጉባኤው ጋር ተባብራችኋል” በሚል ከሥራና ከደመወዝ በማገድ፣ በማስጠንቀቂያዎች በማሸማቀቅ፣ መረጃዎችን በማዛባት የሚፈጥሩት ግጭት ኹኔታውን አስቸጋሪ አድርጎብኛል ብሏል፡፡
መመሪያዎቹ እና የውስጥ ደንቡ “ቀድሞ ሲዘርፉበት የነበረውን አካሄድ የሚያስቀር እና አለአግባብ የሚያካብቱትን ጥቅም የሚያስቆም ነው” ያለው ሰበካ ጉባኤው፤ ለህይወት አስጊ ባላቸው ተፅዕኖዎች ሳቢያ በገዳሟ ጽ/ቤት ተገኝቶ በሰላማዊ መንገድ ስራዎቹን ለማከናወንና ሐላፊነቱን ለመወጣት ከማይቻልበት ደረጃ መድረሱን በሪፖርቱ አስታውቋል፡፡  
እንደ ሰበካ ጉባኤው ገለጻ፥ ቃለ ዐዋዲውን መሰረት አደርጎ ለቤተ ክርስቲያን በሚበጅ መልኩ ያዘጋጃቸው የሰው ኃይል አስተዳደር፣ የፋይናንስ፣ የንብረት እና የግዥ መመሪያዎች በጽ/ቤቱ ልዩ ትርጉም እየተሰጣቸው በመደበኛ ስብሰባ ላይ እንኳን አስተያየት እንዳይሰነዘርባቸው  ዕንቅፋት ተፈጥሯል፤ ማኅበረ ካህናትና ሰራተኞች ገንዘብንና ንብረትን የሚቆጣጠር አካል ቢመርጡም፣ የቆጠራ ሥርዓትን አስመልክቶ ከወራት በፊት በሀገረ ስብከቱ የተላከው መመሪያ ለኮሚቴው ቀርቦ ወደ ተግባር ሳይተረጎም በቢሮ ተሸሽጎ እንደተቀመጠ ነው፤ የቆጠራ ደንቡንና መመሪያውን ከማስፈጸም ይልቅ ከመመሪያው የተነሳ ህገ ወጥ ጥቅም የቀረባቸውን ግለሰቦች በማነሣሣት ለተቃውሞ እንዲቆሙ ይደረጋል፡፡ያለፉት ስድስት ዓመታት የገንዘብ እና ንብረት እንቅስቃሴ በገለልተኛ ኦዲተር እንዲመረመር በፓትርያርኩ ቢታዘዝም “ከቃለ ዐዋዲው ውጭ ነው” በማለት ሒደቱ በሒሳብ ክፍሉ እና በጽ/ቤቱ ተጓትቷል፤ ይልቁንም የሒሳብ ፍተሻ ሒደቱ እና የሰበካ ጉባኤው የተሻሻሉ አሰራሮች ትግበራ ከሚያስከትሉት ተጠያቂነት ለማምለጥ የአስተዳደር ሐላፊዎቹ፣ “ሰበካው እየረበሸን ነው፤ የደመወዝና ጥቅማ ጥቅሞች ዕድገት እንዳናደርግላችሁ ዕንቅፋት ሆኖብናል፤ ከእኛ ጎን ከቆማችሁ ቢሮ አካባቢ እንመድባችኋለን፤ ወዘተ…” በማለት ከማኅበረ ካህናቱ ጋር ማጋጨትና መከፋፈል ስራዬ ብለው ከመያዛቸውም በላይ በዓመት ፈቃድ ሰበብ ከቢሯቸው ይሸሻሉ፡፡
በግንቦት ወር መጨረሻ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ አስኪያጅ ጽ/ቤት የተላከው ይኸው የሰበካ ጉባኤው ሪፖርት፤ ከተደጋጋሚ ጥያቄ በኋላ በቁጥጥር ክፍሉና በሒሳብ ክፍሉ በቀረቡ የገዳሟ የፋይናንስ አቋም ማሳያ ሪፖርቶች ላይ የተካሔደው ንጽጽራዊ ግምገማ፤ ገዳሟ በ2006 ዓ.ም ከየካቲት እስከ ነሐሴ ባሉት ሰባት ወራት ብቻ ከብር 1.5 ሚሊዮን በላይ ተመዝብራለች፤ በዚህ ከፍተኛ የገንዘብ ጉድለት እንቅስቃሴ ሂሳብ ሹሙ፣ ገንዘብ ያዡ፣ ፀሐፊው፣ ቁጥጥሩና የቀድሞው አስተዳዳሪ ተጠያቂዎች እንደሆኑ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
በተጨማሪም ከንዋያተ ቅድሳት ወርኀዊ ሽያጭ ጋር በተያያዘ ገዳሟ ከታህሣሥ ወር 2007 ዓ.ም በፊት ባሉት ጊዜያት በየወሩ በአማካይ ከብር 100ሺህ በላይ ስትመዘበር መቆየቷን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ለዚህም በዋናነት ተጠያቂው የንብረት ክፍል ሐላፊው እንደሆኑ ገልጿል፡፡
በገዳሟ በገንዘብ ዝውውርና በንብረት አጠባበቅ የሚታየው ከፍተኛ የአሠሰራር ድክመትና የሠራተኞች የአቅም ማነስ የመግባባት ችግር ከመፍጠሩም ባሻገር በልዩ ልዩ የአስተዳደር ክፍሎች ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን ሪፖርቱ አክሎ አብራርቷል፡፡
የገዳሟ ጸሐፊ መጋቤ ስብሐት ኃ/ጊዮርጊስ ዕዝራ በበኩላቸው፣ ሪፖርቱ እንዳልደረሳቸው ቢናገሩም የተጠቀሰውን የገንዘብ ጉድለት ጨምሮ የሪፖርቱ ይዘት “ሙሉ በሙሉ ውሸት ነው” በሚል አስተባብለዋል፤ ተጨማሪ ጥያቄዎችንም በስልክ ለመመለስ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡  

የጆሊ ጁስ አምራች የሆነው ቴስቲ ፉድስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግ. ኩባንያ፤ በጥራት የስራ አመራር ብቃት ጥራቶችን አሟልቶ አለማቀፉን የISO 9001/2008 ሰርተፊኬት ተሸላሚ መሆኑን የኩባንያው ሃላፊዎች ገለጹባ የተለያዩ የሚበጠበጡ የዱቄት ጣፋጭ መጠጦችንና ቴስቲ ስናክን የሚያመርተው ኩባንያው፤ የአለማቀፉ ጥራት ተሸላሚ መሆኑ፣ ምርቶቹን ወደ አለማቀፍ ገበያ ይዞ እንዲቀርብና ተቀባይነት እንዲያገኝ ይረዳዋል ተብሏል፡፡ ከ8 ዓመት በፊት የተቋቋመው ኩባንያው፤ታዋቂውን የጆሊ ጁስ መጠጥ ጨምሮ የተለያዩ የፍራፍሬ ጣዕም ያላቸውን በውሃ ተበጥብጠው የሚጠጡ ፍሌቨሮች የሚያመርት ሲሆን ደረቅ ቴስቲ ስናክ በማምረትም ከሃገር ውስጥ በተጨማሪ ለውጪ ገበያ እንደሚያቀርብ ተጠቁሟል፡፡  
ኩባንያው ለወደፊት የምርቶቹን የጥራት ደረጃ ጠብቆ በኢትዮጵያ ያለውን የገበያ አድማስ ለማስፋት እንደሚተጋ የስራ ኃላፊዎቹ ገልፀዋል፡፡

ኢትዮጵያ በነፍስ ወከፍ ገቢ ከ213 አገራት 203ኛ ሆናለች
- መንግስት የነፍስ ወከፍ ገቢያችን ከ550-700 ዶላር ደርሷል ይላል
- ሞናኮ በ100 ሺህ ዶላር ስትመራ፣ ማላዊ በ250 ዶላር መጨረሻ ላይ ትገኛለች
           በየአመቱ ሃምሌ ወር መጀመሪያ ላይ የዓለማችንን አገራት ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ይፋ የሚያደርገው የአለም ባንክ፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት የኢትዮጵያ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ 550 ዶላር እንደነበር ገለፀ፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ፤ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢያችን ከ550-700 ዶላር ደርሷል ማለቱ ይታወቃል፡፡የዓለም ባንክ ከትናንት በስቲያ ያወጣው የአለማችን አገራት የኢኮኖሚ ሁኔታ መረጃ እንደሚያሳየው፣ ኢትዮጵያ በአመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከዓለማችን 213 አገራት 203ኛ ደረጃን ይዛለች፡፡
የባንኩ ያለፈው ዓመት የአገራት አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ መረጃ እንደሚያሳየው፤ 10 የአለማችን አገራት፣ በ2013 ከነበራቸው የነፍስ ወከፍ ገቢ ጭማሪ ያሳዩ ሲሆን፣ ካላደጉ የአለማችን አገራት መካከል ባንግላዴሽ፣ ኬንያ፣ ማያንማር እና ታጂኪስታን የነፍስ ወከፍ ገቢያቸውን በማሻሻል ወደ አነስተኛ መካከለኛ ገቢ አገራት ሲቀላቀሉ፣ ደቡብ ሱዳን በበኩሏ፤ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በመቀነሱ ከዝቅተኛ ገቢ አገራት ጋር ተቀላቅላለች ብሏል የአለም ባንክ፡፡ሞንጎሊያና ፓራጓይ በ2013 ከነበሩበት አነስተኛ መካከለኛ ገቢ፣ ዘንድሮ ወደ ከፍተኛ መካከለኛ ገቢ አገራት ተርታ መቀላቀላቸውን የገለጸው የአለም ባንክ፤ አርጀንቲና፣ ሃንጋሪ፣ ሲሸልስና ቬንዙዌላ በበኩላቸው ደረጃቸውን በማሻሻል አምና ከነበሩበት ከፍተኛ መካከለኛ ገቢ ወደ ከፍተኛ ገቢ አገራት ሸጋግረዋል ብሏል፡፡በአመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከአለማችን አገራት ዝቅተኛውን ደረጃ የያዘችው ማላዊ ናት ያለው የአለም ባንክ፤ በ2014 የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 250 ዶላር ብቻ የሆነው ማላዊ፣ ባለፉት 24 አመታት
የነፍስ ወከፍ ገቢዋ የጨመረው በ70 ዶላር ብቻ ነው ብሏል፡፡ በአንጻሩ በአመቱ ከፍተኛውን የአለማችን አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ያገኘችው የፈረንሳዩዋ ከተማ ሞናኮ ስትሆን፣ የነፍስ ወከፍ ገቢው ከ100 ሺህ ዶላር በላይ ነው ተብሏል፡፡በአለም ባንክ መስፈርት መሰረት፤ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢያቸው ከ12ሺህ ዶላር በላይ የሆኑ፣ ከፍተኛ ገቢ፤ ከ12 ሺ 735 እስከ 4ሺህ 126 ዶላር የሆኑ፣ ከፍተኛ መካከለኛ ገቢ፣ ከ4ሺህ 125
እስከ 1ሺህ 46 ዶላር የሆኑ፣ ዝቅተኛ መካከለኛ ገቢ፤ ከ1ሺህ 45 ዶላር በታች የሆኑ፣ ዝቅተኛ ገቢ
ያላቸው አገራት ተብለው ይመደባሉ፡፡

 መንግስት ም/ፕሬዚዳንቱ ከአገር የወጡት ለስራ ጉዳይ ነው ብሏል

   የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ፤ ህገ መንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጭ በቅርቡ በሚካሄደው የአገሪቱ ምርጫ ለሶስተኛ ዙር ለመወዳደር መወሰናቸውን በመቃወማቸው ከመንግስት አካላት ማስፈራሪያ እየተደረገባቸው እንደሆነ የገለጹት ምክትል ፕሬዚዳንቱ ጌርቪያስ ሩፊኪሪ፣ ለህይወታቸው በመስጋት አገር ጥለው መሰደዳቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የአገሪቱ መንግስት ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ምክትል ፕሬዚዳንቱ ከአገር የወጡት ለስራ ጉዳይ ነው፤ ምንም አይነት ማስፈራሪያ አልተደረገባቸውም ብለዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ዘንድሮም በምርጫ እንደሚወዳደሩ መግለጻቸውን ተከትሎ፣ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው ግጭት እየተባባሰ ነው፤ የህዝቡ ተቃውሞም እንደቀጠለ ነው፤ ያሉት ምክትል ፕሬዚዳንቱ ጌሪያስ ሩፊኪሪ፣ መንግስት በሌሎች ተቃዋሚዎች ላይ እንደሚያደርገው ሁሉ በእኔ ላይም ዛቻና ማስፈራሪያ እያደረገብኝ ስለሆነ አገሬን ጥዬ ተሰድጃለሁ ብለዋል ከፍራንስ24 የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፡፡
በቅርቡም የብሩንዲ የህገ መንግስታዊ ጉዳዮች ፍርድ ቤት ዳኛ እና የምርጫ ኮሚሽን አባልን ጨምሮ ሌሎች የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ የፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛን ውሳኔ በመቃወም አገር ጥለው መሰደዳቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ በመጪው ሐምሌ ወር አጋማሽ ላይ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው የብሩንዲ ምርጫ ሳቢያ የተቀሰቀሰውን ግጭትና የተፈጠረውን ውጥረት ለማርገብ፣ የብሩንዲን ገዢ ፓርቲና ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለማደራደር እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡
የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅቶችም ላለፉት ሁለት ወራት በአገሪቱ ፖሊስና በተቃዋሚዎች መካከል በተደረጉ ግጭቶች፣  ከ70 በላይ ዜጎች መሞታቸውንና 500 ያህልም መቁሰላቸውን አስታውቀዋል ብሏል ዘገባው፡፡

 በፓኪስታን በተከሰተው ከመጠን ያለፈ የሙቀት አደጋ ከሰባት መቶ በላይ ሰዎች ህይወታቸው ማለፉን ሲኤንኤን ከዋና ከተማዋ ካራቺ የዘገበ ሲሆን የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ናዋዝ ሸሪፍ የአስቸኳይ የአደጋ ጊዜ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
ሙቀቱ በድንገት የመታት የመጀመሪያዋ ከተማ፣ ከፓኪስታን በደቡባዊ አቅጣጫ የምትገኘዋን የሲንድ ግዛትን ነበር፤ ባለፈው ሳምንት ማገባደጃ ላይ፡፡ ወሩ በእስልምና ሀይማኖት ተከታዮች ዘንድ የሮመዳን ፆም  የተያዘበት እንደመሆኑ አደጋው እጥፍ ድርብ ችግሮችን እንዳስከተለ ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡  ህይወታቸውን በሙቀቱ ያጡት ሰለባዎች ቁጥር የአስከሬን ማቆያዎች ከሚቀበሉት በላይ በመሆኑ ሆስፒታሎች በሬሳ ተጨናንቀው በዜና ማሰራጫዎች ታይተዋል፡፡  እስከ ትላንት በስቲያ ድረስ ወደ 750 የፓኪስታን ዜጎች ሲሞቱ፣ ከሺ በላይ የሚገመቱት ደግሞ ከሙቀቱ ጋር በተያያዘ እንደ ሀይለኛ ትኩሳትና የሰውነት ፈሳሽ ድርቀት (Dehydration) መሰል የጤና ቀውሶች ተጠቅተው፣ አስከፊ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የሙቀቱ አደጋ ከፍተኛ የህይወት መጥፋት ያስከተለው በሀገሪቱ ትልቅ በምትባለው የካራፒ ከተማ ሲሆን ወደ ስድስት መቶ ነዋሪዎችም ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡
ከአደጋው ጋር በተያያዘ በተከሰተ የትራፊክ መጨናነቅ ሳቢያ ነዋሪዎች  የሟች ዘመዶቻቸውን አስከሬን ወደ ቀብር ቦታ ለማድረስ መቸገራቸውን ገልፀዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በሀይል እጥረት ምክኒያት እየተዛባ ይዳረስ የነበረው የውሀ አቅርቦት ጊዜያዊ መፍትሄዎች እንዳይወሰዱ አድርጓል። አንዳንድ ነዋሪዎች የተከሰተውን ሙቀት በውሀ ለማብረድ ቢፍጨረጨሩም  … በከተማው ያሉ የውሀ መስመሮች በመሰባበራቸው መፍትሄ ሊሆኑዋቸው አልቻሉም፡፡ የፓኪስታን ክልል አስተዳዳሪ ከዌም አሊ ሻህ፤ የሙቀቱ አደጋ ጋብ እስከሚልበት ጊዜ ድረስ ትምህርት ቤቶችና የመንግስት መስሪያ ቤቶች ተዘግተው እንዲቆዩ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል፡፡ አስተዳዳሪው ለተቀጠፉት ነፍሶች ተጠያቂው መንግስት እንደሆነም ሲገልጹ፤ “ሀይል ማሰራጫ መስመሮች እንዲታደሱ አስቀድመን ብንወተውትም፣ የሚመለከታቸው ባለሥልጣናት ምላሽ ባለመስጠታቸው አደጋው ከመጠን ያለፈ ጥፋት አድርሷል” በማለት ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡

 በያዝነው የፈረንጆች አመት በርካታ ሰራተኞችን ቀጥረው እያሰሩ ከሚገኙ የዓለማችን ተቋማትና ድርጅቶች መካከል፣ 3.2 ሚሊዮን ሰራተኞችን የሚያስተዳድረው የአሜሪካ መከላከያ ሚንስቴር ፔንታገን በሠራተኞች ብዛት መሪነቱን መያዙን ፎርብስ መጽሄት ዘገበ፡፡
የአለም የኢኮኖሚ ፎረም ሰሞኑን ይፋ ያደረገውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ፎርብስ ባለፈው ማክሰኞ እንዳስነበበው፣ የቻይና ህዝቦች የነጻነት ጦር 2.3 ሚሊዮን ሰራተኞችን በመያዝ በሁለተኝነት ሲከተል፣ ታዋቂው አለማቀፍ የሸቀጣሸቀጥ ሱፕርማርኬት  ዎልማርት በ2.1 ሚሊዮን ሰራተኞች ሶስተኛውን ደረጃ ይዟል፡፡ በአመቱ በርካታ ሰራተኞችን በስሩ ቀጥሮ በማስተዳደር ከአለማችን አራተኛውን ደረጃ የያዘው ደግሞ 1.9 ሚሊዮን ሰራተኞች ያሉት ታዋቂው የምግብ አምራች ኩባንያ ማክዶናልድ ነው፡፡
የእንግሊዝ ብሄራዊ የጤና አገልግሎት ድርጅት በ1፣7 ሚሊዮን ሰራተኞች አምስተኛ ደረጃን እንደያዘ የገለጸው ዘገባው፣ የቻይና ብሄራዊ የነዳጅ ኮርፖሬሽን በ1.6 ሚሊዮን፣ የቻይናው ስቴት ግሪድ ኮርፖሬሽን በ1.5 ሚሊዮን፣ የህንድ ምድር ባቡር ኩባንያ በ1.4 ሚሊዮን፣ የህንድ የጦር ሃይል በ1.3 ሚሊዮን እንዲሁም ሆን ሃይ ፕሪሲዥን የተባለው ኩባንያ በ1.2 ሚሊዮን ሰራተኞች እስከ አስረኛ ደረጃ ይዘዋል ብሏል፡፡

 በናይጄሪያ መንግሥት ከፍተኛ ተከፋይ እንደሆኑ የሚነገርላቸው የህግ አውጪ ባለሙያዎች (ሴናተሮች) የገዛ ራሳቸውን ደመወዝ ለመቀነስ የሚደነግግ ህግ ለማፅደቅ ሀሳብ እንዳቀረቡ ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ናይጄሪያ የህግ አውጪ ሆነው የሚሰሩ 469 የከፍተኛ ፍትህ አባላት አሏት፡፡ እነዚህ ህግ አውጪዎች በዓመት የሚቀበሉት የደመወዝና ጥቅማ ጥቅም በጀት በሀገሩ ላይ ያሉት 36 ክልሎች በአመት ከሚመደብላቸው ገንዘብ የበለጠ እንደሆነ ማወቅ ተችሏል፡፡ እነዚህ ክልሎች በአማካይ እያንዳንዳቸው ከሚሊዮን ነዋሪዎች በላይ የሚያስተዳድሩ ናቸው፡፡  
 ለአስር አመታት ያህል በተለይም ከአለፉት አራት አመታት ጀምሮ የናይጄሪያ ኢኮኖሚ ባሽቆለቆለው የዓለም አቀፍ ነዳጅ ገበያ መንስኤነት አጣብቂኝ ውስጥ መግባቱን ሮይተርስ ጠቁሟል፡፡ የናይጄሪያ መንግስት የሚተዳደረው ነዳጅ ተሸጦ ከሚገኘው ቀረጥ በመሆኑ፣ ከወደቀው የዓለም ነዳጅ ዋጋ ጋር የመንግስት የበጀት አቅምም ላሽቋል፡፡ በዚህም ምክኒያት በሌጎስ የሚገኝ ገለልተኛ ተቋም ቡድን የነዋሪዎቹን የገንዘብ አወጣጥ በቅርብ ሆኖ እየገመገመ ይገኛል፡፡
የዚሁ ተቋም መስራች የሆነው ኦሊሲዮን አጓበንዴ፤ ከሌላው መንግስታዊ ተከፋይ በተለየ ሁኔታ ገንዘብ የሚያገኙትን የፍትህ ስርዓት ባለሙያዎች፣ የህዝብ አገልጋይ መሆን ሲገባቸው ከመጠን ያለፈ የመንግስት በጀት ተጠቃሚ መሆናቸውን በመጠቆም አቤቱታ ያሰማል፡፡
ባለፈው ሳምንት በሌጎስ የወጣው ዴይሊ ሪፖርት፤ እያንዳንዱ የሴኔት አባል በዓመት ለልብስ መግዣ እንዲሆነው 105 ዶላር እንደሚሰጠው ዘግቧል፡፡ ባለፈው ሚያዚያ አዲሱን የፕሬዚዳንት ወንበር የተረከቡት ሞሀመድ ቦሀሪ፤ በሀገሪቱ ላይ የተንሰራፋውን የአባካኝነት ባህል እንደሚለውጡ ቃል መግባታቸው ይታወሳል፡፡ የሀገሪቱ ብሔራዊ ምክር ቤት አባላትም ከፕሬዚዳንቱ ጋር ሆነው ለመስራት በከፊል ተስማምተዋል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ የህግ አውጪ ባለሙያዎቹም የፕሬዚዳንቱን አቋም በመደገፍ የሚከፈላቸውን ወርሀዊ ደሞዝ ዝቅ ለማድረግ ሀሳብ ማቅረብ ጀምረዋል፡፡ ከሀሳብ አቅራቢዎቹ መካከል የኮጂ ክልል ተወካይ በሰጠው አስተያየት፤ “በመንግስት ወጪ የተትረፈረፈ ህይወት ከእንግዲህ ልንመራ አንችልም” ሲል ተደምጧል፡፡ “የናይጄሪያ ህዝብ ይኼንን የደመወዝ አከፋፈል በአንድ ድምፅ ማውገዝ ይኖርበታል” ብሏል፡፡
በ2013 (እ.ኤ.አ) የአንድ በዝቅተኛ እርከን ላይ የሚገኝ ሴናተር (ህግ አውጪ) ዓመታዊ ገቢ 13,000 ዶላር ነበር። ግን በዚህ ደመወዙ ላይ ለመኖሪያ ቤት፣ ለቤት ቁሳቁስ እና መሰል ጥቅማጥቅሞች ከሚፈቀድለት ተጨማሪ ገቢ ጋር ተዳምሮ ወደ 115,000 ዶላር በዓመት እንደሚያገኝ የናይጄሪያ ጋዜጦች ጽፈዋል፡፡  
ከ2013 በኋላ ተጨማሪ ጥቅማ ጥቅሞች ተፈቅደውላቸዋል፡፡ ለምሳሌ፤ የውሎ አበል 930 ዶላር በእየለቱ፣ እንደዚሁም በየአራት ወሩ ደግሞ 38, 000 ዶላር --- በአመታዊው ደሞዝ ላይ ተጨማሪ መውሰድ ይችላሉ፡፡  
ከእነዚህ የህግ ባለሙያዎች የተጋነነ ደመወዝ ጋር የሀገሩ ዝቅተኛ የገቢ መጠን ሲነፃፀር በጣም ማስደንገጡ አልቀረም፡፡ የሀገሩ ዝቅተኛ ተከፋይ 18,000 ኒራ ወይንም 90 ዶላር በወር ነው የሚያገኘው፡፡
በናይጄሪያ ያለ ሴናተር በአሜሪካ በዝቅተኛ እርከን የሚከፈል ሴናተር ከሚያገኘው ገቢ ጋር ሲነፃፀር … በመካከላቸው ጥቂት ልዩነት ብቻ እንዳላቸው መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ እንደ ናይጄሪያ አይነት 75 በመቶ የመንግስት በጀት ከዘይት ቀረጥ ላይ በሚተማመን ሀገር፤ የዓለም የነዳጅ ገበያ ሲያሽቆለቁል… እንደ ቀድሞው ተንደላቀው ህይወታቸውን የሚመሩ ባለስልጣናት በአንፃራዊ ሁኔታ መለወጥ እንዳለበት የሚያመለክት ነው፡፡ 

“The power of Negative Thinking” የተሰኘው የስነልቦና መጽሐፍ “የአሉታዊ አስተሳሰብ ልዩ ሃይል” በሚል ርዕስ በአሸናፊ ሰብስቤና በእሩቅነህ አደመ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ ለገበያ ቀረበ፡፡
“ለህይወት ወይም ለመኖር ከውስጥህም ሆነ ከውጭ ወይም ለሁለቱም ምንም ዓይነት ዋስትና ሳትሰጥ ስትቀር መኖር ወይም ህይወት በራሱ በመከራ፣ በስቃይ፣ በሀዘን፣ በፍርሃትና ባልተጠበቁ ክስተቶች የተሞላች ትሆናለች” ይላል - መፅሃፉ። በ183 ገፆች የተቀነበበው ይሄው መጽሐፍ፤ በ11 ምዕራፎች ተከፋፍሏል፡፡ “የአሉታዊ አስተሳሰብ ልዩ ሃይል” በ50 ብር ከ65 እየተሸጠ ነው፡፡