Administrator

Administrator

ቤትና ንብረቶችን በኢንተርኔት ለመሸጥና ለመግዛት የሚያስችል ዘመናዊ የግብይት ሥራ የሚሰራና ላሙዲ የተባለ አለምአቀፍ የኦንላይን ሪልስቴት ኩባንያ ሥራ ጀመረ፡፡
ደንበኞች ንብረታቸውን በቀላሉ ለመሸጥና ለመግዛት ያስችላቸዋል የተባለውና ዘመናዊው የኢንተርኔት የመገበያያ መንገድ ሥራ መጀመሩን አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ በኩባንያው ቢሮ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተገለፀው በአገሪቱ የሪል ስቴቶች መስፋፋትና ማደግ ከጊዜ ወደ ጊዜ ለውጥ እያሳየ መጥቷል፡፡ ስለዚህም ደንበኞች ስለሚፈልጓቸው ቤቶችና ንብረቶች በቂና ጥልቀት ያለው መረጃ ለማግኘት የሚችሉበት መንገድ በስፋት ሊኖር ይገባል፡፡
ኩባንያው በገዢና ሻጭ በኦንላይን ተገናኝተው ቤትና ንብረታቸውን ለመገበያየት እንዲችሉ ዕድሉን ያመቻቻል፡፡
ኩባንያው ከዚህ በተጨማሪ ዳያል 4 ሆም የተሰኘ ሆት ላይንን ያስተዋወቀ ሲሆን ይህም ሆትላይን ንብረት ፈላጊዎች ያለ ኢንተርኔት ትስስር ተጠቃሚዎችን በስልክ እንዲገናኙ ለማድረግ የሚያስችል አሠራር ማዘርጋቱንም በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተገልጿል፡፡
ላሙዲ በኬንያ፣ በታንዛኒያ፣ በናይጀሪያ፣ በጋና፣ በኡጋንዳና ሩዋንዳ ቢሮዎቹን ከፍቶ እየሠራ የሚገኝ ኩባንያ ነው፡፡   

“ኦባማ አሻፈረኝ ብለው ስለዚህ ጸያፍ ነገር ካወሩ፣ ማዕቀብ እንጥልባቸዋለን!” - የኬንያ ፓርላማ አፈ ጉባኤ
   የኬንያ ከፍተኛ ባለስልጣናት በቅርቡ አገሪቱን ለመጎብኘት ቀጠሮ የያዙትን ባራክ ኦባማን፣ “አደራዎትን በጉብኝትዎ ወቅት የግብረ-ሰዶማውያንን መብት የተመለከተ ነገር እንዳይናገሩ” ሲሉ አበክረው ማስጠንቀቃቸውን ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
የኬንያ ምክትል ፕሬዚደንት ዊሊያም ሩቶና የአገሪቱ ፓርላማ አፈጉባኤ ለኦባማ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የግብረ-ሰዶማዊነት ጉዳይ ከክርስትና እምነት ጋር የማይሄድ ጸያፍ ነገር ነውና፣ ሊጎበኙን ሲመጡ ጉዳዩን በተመለከተ ምንም ነገር ትንፍሽ እንዳይሉ ሲሉ አስጠንቅቀዋቸዋል ብሏል ዘገባው፡፡
ከሳምንታት በፊት በመላው ግዛቷ የግብረ-ሰዶማውያንን ጋብቻ በህግ የፈቀደችውን አሜሪካን የሚመሩት ኦባማ ግን፣  ከዚህ ቀደምም ደቡብ አፍሪካ፣ ታንዛኒያ እና ሴኔጋልን ሲጎበኙ እንዲህ ያለ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው፣ አሻፈረኝ ብለው ስለ ግብረ-ሰዶማውያን መብቶች በአደባባይ እንዳወሩት ሁሉ፣ የኬንያን ባለስልጣናት ማስጠንቀቂያንም ጆሮ ዳባ ልበስ ሊሉት ይችላሉ ተብሏል፡፡
ባለፈው እሁድ ናይሮቢ ውስጥ በሚገኝ አንድ ቤተክርስቲያን በተካሄደ ስነስርዓት ላይ፣ በርካታ ምዕመናን ለግብረ-ሰዶማዊነት ያላቸውን ተቃውሞ የገለጹ ሲሆን፣ ኦባማ እና ኦባማ ወይም ሚሼል እና ሚሼል እንዲመጡ አንፈልግም ሲሉ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን ነቅፈዋል፡፡
በስፍራው የተገኙት ምክትል ፕሬዚዳንቱ ሩቶም፣ የምዕመናኑን ተቃውሞ በመደገፍ፣ እንዲመጡልን የምንፈልገው ኦባማ እና ሚሼልን ነው፤ ልጅ እንዲወለድልንም እንፈልጋለን ሲሉ በመናገር፣ አገራቸውን ከእንዲህ ያለው ጸያፍ ሃሳብ እንደሚከላከሉ ለምዕመናኑ ቃል ገብተዋል፡፡
የኬንያ ፓርላማ አፈ ጉባኤ ጀስቲን ሙቱሪ በበኩላቸው፣ አገራቸውና ህዝባቸው ጸያፍ ነገሮችን እንደማይፈልጉ በመግለጽ፣ ኦባማ ወደ አገራችን ከገቡ በኋላ የግብረ-ሰዶማውያንን መብቶች በተመለከተ ንግግር እንዳያደርጉ እናግዳቸዋለን፣ አሻፈረኝ ብለው ከተናገሩም ማዕቀብ እንጥልባቸዋለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡   
ኦባማ ከሁለት ሳምንታት በኋላ የአባታቸው እትብት የተቀበረባትን ኬንያን ይጎበኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሶርያ ለአመታት የዘለቀውን የእርስ በእርስ ግጭት በመሸሽ ወደተለያዩ አገራት የተሰደዱ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር ከ4 ሚሊዮን በላይ መድረሱንና ይህም ከአገሪቱ ህዝብ አንድ ስድስተኛ ያህሉን እንደሚሸፍን ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በሶርያ በ2011 የተቀሰቀሰው ግጭት እየተባባሰ መቀጠሉ የአገሪቱን ዜጎች ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ እንደከተታቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፉት አራት አመታት በግጭቱ ለህልፈተ ህይወት የተዳረጉ ዜጎች ቁጥር ከ230 ሺህ በላይ መድረሱንና አገራቸውን ጥለው ከተሰደዱት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በተጨማሪ፣ ከ7 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑትም በአገራቸው ውስጥ መፈናቀላቸውን ገልጧል፡፡
በሶርያ የሚታየውን አስከፊ ሁኔታ፣ “የዚህ ትውልድ አስከፊው የሰብአዊ ቀውስ” ሲሉ የገለጹት የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ሃላፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ፣ የእርስ በእርስ ግጭቱ እያደረሰ ያለው ጥፋት እየከፋ መምጣቱንና ስደቱ በዚሁ ከቀጠለ፣ የስደተኞቹ ቁጥር በመጪዎቹ ስድስት ወራት 4.27 ሚሊዮን ሊደርስ ይችላል ብለዋል፡፡
የተመድ መረጃ እንደሚለው፤ በርካታ ሶርያውያን በተሰደዱባት ቱርክ፣ የስደተኞቹ ቁጥር 1.8 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን፣ በድንበር አካባቢ ያለው ግጭት እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ የስደተኞቹ ቁጥር እንደሚያሻቅብ ይጠበቃል፡፡ በሊባኖስ 1.2 ሚሊዮን፣ በዮርዳኖስም 629ሺህ ያህል ሶርያውያን ስደተኞች እንደሚገኙ ተመድ አስታውቋል፡፡ በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ጥገኝነት የጠየቁ ሶርያውያን ስደተኞች ቁጥር 270 ሺህ ያህል መድረሱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 7ሺህ 800 ሰራተኞቹን ለመቀነስ ወስኗል

    ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ በኖኪያ የስማርት ሞባይል ቀፎ ንግዱ ላይ 7 ነጥብ ስድስት ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ ማጋጠሙን ተከትሎ፣ 7ሺህ 800 ሰራተኞችን ከስራ ገበታቸው እንደሚቀንስ ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ከሁለት አመታት በፊት ኖኪያን በ7.3 ቢሊዮን ዶላር የገዛውና የሞባይል ቀፎዎችን እያመረተ ለገበያ ማቅረብ የጀመረው ማይክሮሶፍት፣ ቢዝነሱ አላዋጣው ማለቱን በማየት ባለፈው አመት ብቻ 12 ሺህ 500 ሰራተኞቹን እንደቀነሰ ያስታወሰው ዘገባው፣
ማይክሮሶፍት ከለመደው የኮምፒውተር ዘርፍ ወጣ ብሎ የተሰማራበት የሞባይል ቀፎ ንግድ ኪሳራ ላይ ጥሎታል ያሉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ሳትያ ናዴላ፣ ቢዝነሱ ለምን አክሳሪ እንደሆነና በቀጣይ መወሰድ የሚገባቸውን እርምጃዎች በተመለከተ ግምገማ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡
ኩባንያው በቅርቡ የስማርት ፎን ንግዱን አዋጭ በሆነ ሁኔታ ማስቀጠል የሚችልበትን አዲስ አቅጣጫ እንደሚዘረጋና 18ሺህ ሰራተኞቹን መቀነስን ጨምሮ ሰፊ የመዋቅር ለውጥ እያደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
ማይክሮሶፍት የፊንላንዱን ኖክያ የገዛው፣ ከዚህ በፊት ያመርታቸው የነበሩትን የዊንዶውስ ሞባይሎች ከአፕል አይፎኖችና ከጎግል አንድሮይድ ሲስተሞች ጋር በገበያ ላይ ተወዳዳሪ ለማድረግ በማሰብ እንደሆነም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡

የዘመድ ችግር የሚፈታው በዘመድ ነው፡፡
የስዋሃሊ አባባል
በጋራ ጀልባ ወንዙን ተሻገሩ፡፡
የቻይናውያን አባባል
እዩኝ እዩኝ ማለት ለትችት ያጋልጣል፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ማስታወቂያ የንግድ እናት ነች፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ልብ ትክክል ሲሆን ስራም ትክክል ይሆናል፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ብዙ የምታስካካ ዶሮ ብዙ እንቁላል አትጥልም፡፡
የኮሪያውያን አባባል
የዛፍ ፍሬ ከዛፉ ርቆ አይወድቅም፡፡
የኮሪያውያን አባባል
በእጅህ መዳፍ መላውን ሰማይ ልሸፍን አትበል፡፡
የኮሪያውያን አባባል
ብዙ እጆች የሥራ ጫናን ያቀላሉ፡፡
የሰሜን አሜሪካውያን አባባል
አንድ ግንዲላ ብቻውን ምድጃ እንኳን ለማሞቅ በቂ አይደለም፡፡
የእስያውያን አባባል
መቶ ሰዎችን ለማስፈራራት አንዱን ግደል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ውሃ ጀልባን ማንሳፈፍ ብቻ ሳይሆን ማስመጥም ይችላል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ባዶ ጆንያ ቀጥ ብሎ መቆም አይችልም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
አንድ ምሰሶ ቤት አያቆምም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ብዙ ካፒቴኖች ያሏት መርከብ መስጠሟ አይቀርም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ሁለት እርምጃ መንገድ አይሆንም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ወላጆችህ ጥርስህን እስከምትነቅል ከተንከባከቡህ፣ አንተም ጥርሳቸውን እስኪ ነቅሉ ትንከባከባቸዋለህ፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል

      ለ31ኛው የአፍሪካ ዋንጫና ለ4ኛው የቻን ውድድር ለማለፍ በሚደረጉ ማጣርያዎች አመርቂ ውጤት ያስመዘገበው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 2ኛ ምእራፍ ዝግጅቱን ከሁለት ሳምንት በኋላ እንደሚቀጥል ታውቋል። በሁለቱ አህጉራዊ ውድድሮች ዋልያዎቹ  ሦስት ጨዋታዎች በማድረግ በሁለቱ አሸንፈው በአንዱ አቻ ወጥተዋል፡፡ በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ በምድብ 10 ከአልጄርያ፤ ሌሶቶ እና ሲሸልስ ጋር የሚገኙት ዋልያዎች በምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸው ሌሶቶን በሜዳቸው 2ለ1 በማሸነፍ   በ3 ነጥብ በግብ ክፍያ በአልጄርያ  ተበልጠው መሪነቱን ተጋርተዋል፡፡ በቻን ቅድመ ማጣርያ ደግሞ ባለፈው ሰሞን ናይሮቢ ላይ ከኬንያ አቻቸው ጋር 0ለ0 ከተለያዩ በኋላ በ2ለ1 የደርሶ መልስ ውጤት ጥለው በማለፍ ለመጨረሻው ማጣርያ አልፈዋል፡፡ በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ቀጣይ ተጋጣሚያቸው ከሜዳ ውጭ ሲሸልስ ስትሆን በቻን የመጨረሻ ማጣርያ ደግሞ በደርሶ መልስ ከብሩንዲ ጋር ይገናኛሉ፡፡
ዋልያዎቹ ከሁለት ሳምንት ዕረፍት በኋላ ወደ ዝግጅታቸው ሁለተኛ ምእራፍ እንደሚገቡና  ለቀጣዩ ግጥሚያዎቻቸው መስራት እንደሚጀምሩ እና  በነሐሴ ወር ሁለት የወዳጅነት ጨዋታ በማድረግ አቋማቸውን እንደሚፈትሹ ይጠበቃል፡፡ ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሜዳው ላይ እና ከሜዳው ውጭ የወዳጅነት ጨዋታዎች ለማድረግ የሚፈልጉ አገራት መበርከታቸውን ከፈዴሬሽኑ የሚወጡ መረጃዎች ይገልፃሉ፡፡
በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ከኢትዮጵያ ጋር ከተደለደሉት ቡድኖች በቻን ማጣርያቸው ሲሸልስ ስትወድቅ፤ ሌሶቶ ግን አልፋለች፡፡ ሲሸልስ በሞዛምቢክ 9ለ1 በሆነ የደርሶ መልስ ውጤት ተሸንፋ ስትወድቅ ፤ ሌሶቶ ደግሞ ቦትስዋናን ጥሎ በማለፍ ለመጨረሻ ዙር ማጣርያ በቅታለች፡፡ በመጨረሻ ዙር የቻን ማጣርያ የኢትዮጵያ ተጋጣሚ የሆነችው ብሩንዲ በቻን ውድድር ለመጀመርያ ጊዜ በ2014 ተሳትፋ የነበረ ሲሆን ሱዳንን በመለያ ምቶች 4ለ3 ጥላ በበማፍ ነበር፡፡ በ2009 እኤአ በደርሶ መልስ ማጣርያ ብሩንዲን ያሸነፈችው ሩዋንዳ ስትሆን በ2011 እኤ ደግሞ ኡጋንዳ ነበረች፡፡ ሲሸልስ በ2017 አፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ 2ኛ ጨዋታ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በሜዳዋ ከመገናኘቷ  በፊት ጠንካራ ዝግጅት ለማድረግ ወስናለች፡፡ አሰልጣኙ ማቲዮት ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ ቡድናቸው ዛሬ እና ነገ ወደ አልጄርያ በማቅናት  የሁለት ሳምንት ዝግጅት በካፕ ተቀምጦ ያደርጋል፡፡ ከዚህ ዝግጅት በኋላም በኢንድያን ኦሽን ጌምስ በመካፈል ከማዳጋስካር ፤ ከማልዴቪስና  ከማዮቴ ደሴት ብሄራዊ  ቡድኖች ጋር በምድብ ማጣርያ ይጫወታል፡፡

    አዲሱ የተጨዋቾች ደረጃና የዝውውር መመሪያ ባለድርሻ አካላትን ሳያስማማ ተግባራዊ መሆን ጀምሯል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን አፅድቄዋለሁ የሚለውን ይህ መመርያ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ሕጋዊ ሰነድ ሆኖ እንደሚቀጥል ገልፆ እየሰራበት ነው።  ከመመርያው ተግባራዊነት በፊት ተጨማሪ ውይይት እንደሚያስፈልግ የተጨዋቾች ተወካዮች  በደብዳቤ ቢጠይቁም ምላሽ አልተሰጣቸውም፡፡ ለፕሪሚዬር ሊግ  ክለቦችም የመመርያው አፈፃፀም በቀጣዩ የውድድር ዘመን በሚኖራቸው ዝግጅት  ላይ እንቅፋት እየሆነባቸውም ይገኛል፡፡
መመርያው ተግባራዊ ከመሆኑ 1  ሳምንት ቀደም ብሎ በክለቦች መካከል የተፈጠሩ ውዝግቦች ነበሩ፡፡ ይህን ተከትሎ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በመመርያው ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ላይ ለመነጋገር ስብሰባ ቢቀመጡም ሳይስማሙ እንደተለያዩ ተነግሯል፡፡
መመርያው ተጨዋቾችንና ቀጣሪዎቻችንን በዋናነት ይመለከታል በማለት የተጨዋቾች ማህበር ተወካዮች ያቀረቡት  ግልፅ ደብዳቤ ትኩረት ስለተነፈገው  ቅር ተሰኝተዋል፡፡  ተጨዋቾቹ በመመርያው የሚመክሩበት ጊዜ እንዲሰጣቸው ፣ በአገሪቱ የአሠሪና ሠራተኛ ውል መሠረት በሁለት ባለጉዳዮች መካከል በሚደረገው ስምምነት ሦስተኛ ወገን እንደማያስፈልግ፣ የክፍያውን መጠንና የአከፋፈሉ ሒደትን በተመለከተም በሁለቱ ባለጉዳዮች ስምምነት የሚወሰን እንጂ በሦስተኛ ወገን ወይም ፌዴሬሽን ሊሆን እንደማይገባ በመጠቃቀስ መስተካከል ስላለባቸው አንቀፆች እንነጋገር ብለው ነበር።   በተለይ ሰኔ 30 ከሆነ በኋላ በሁሉም የፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ክለቦች    ብዙ ተጨዋቾች ኮንትራታቸው ስለተጠናቀቀ ክፍት በሆነው የዝውውር ገበያ ውላቸውን ለማደስም ሆነ ክለብ ለመቀየር  በፊርማ ክፍያ በተፈጠሩ አለመግባባቶች እየተስተጓጎለ ይገኛል፡
በተለይ በመመርያው እያንዳንዱ ክለብ በስብስቡ ሊኖረው የሚገባን የውጭ ተጫዋቾችን በተመለከተ ቁጥሩ ከአምስት ወደ ሦስት ዝቅ እንዲል መባሉ እና የፊርማ ክፍያ የሚለው አሰራር ተቀይሮ ተጨዋቾች በደሞዝ አገልግሎት እንዲሰጡ በመመርያው መደንገጉ በቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብና በተጨዋቾች ማህበር ተቀባይነት አልነበራቸውም፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የውጭ ተጨዋቾችን ለመገደብ ደንብ ያስፈለገው ለአገር ውስጥ እግር ኳስ ተጫዋቾች የተሻለ ትኩረት መስጠት ያስችላል ብሏል፡፡  የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ሃላፊዎች በበኩላቸው የውጪ አገር ተጫዋቾች ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ያሉትን ጠቀሜታዎች በመዘርዘር ለማስረዳት ሙከራ አድርገዋል፡፡ የውጭ አገር ተጨዋቾች በክለብ ስብስብ መካተታቸው የአገር ውስጥ ተጨዋቾችን በተፎካካሪነት ጎልተው እንዲወጡ እንደሚያደርግና የፕሮፌሽናልነት ዕድል እንዲፈጠርላቸው ያደርጋል የሚሉ ማስረጃዎችንም ገልፀዋል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በኢትዮጵያ ለመጫወት ከአፍሪካ 6 አገራት የተውጣጡ ከ26 በላይ ተጨዋቾች በ7 ክለቦች በመቀጠር ህጋዊ እውቅና በማግኘት ለመጫወት ችለው ነበር፡፡ የውድድር ዘመኑ ከመጀመሩ በፊት የእግር ኳስ ፌደሬሽን ይፋ አድርጎት በነበረው ዝርዝር መሰረት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጫወቱ የነበሩት 26 የሌላ አገር ተጨዋቾች 8 ከካሜሮን፤ 7 ከናይጄርያ፤ 6 ከጋና፤ 3 ከኡጋንዳ እንዲሁም ከኬንያ እና ከደቡብ አፍሪካ የመጡ ናቸው፡፡ ከ26ቱ የሌላ አገር ተጨዋቾች ጊዮርጊስ 7፤ ኤልፓ እና ሀረር ቢራ እያንዳንዳቸው 5፤ ደደቢት 4፤ ኢትዮጵያ ቡና እና ድሬዳዋ ከነማ እያንዳንዳቸው 2 እንዲሁም ኒያላ ለ1 ተጨዋች ቅጥር ፈፅመው በፌደሬሽኑ የእውቅና ማረጋገጫ የውድድር ዘመኑን አሳልፈዋል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ እየተሟሟቀ የመጣው በተለይ ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ነው፡፡ በተለይ የፊርማ ክፍያ ከተባለው አሰራር ጋር ተጨዋቾች ከፍተኛ ጥቅም እያገኙ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ የዝውውር ገበያ ካለፈው 4 ዓመት ወዲህ በ50ሺ ብር የፊርማ ክፍያ ተጀምሮ፤ ወደ 100ሺ ብር ከዚያም ወደ 200ሺ ብር፤ 300ሺብር በአማካይ ወደ 500 ሺ ብር ደርሷል፡፡
የተጨዋቾች ደረጃና የዝውውር መመርያ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ባቀረበው ጥያቄ በተለይም የመመርያው ዋና ተዋንያን ተብለው በሚጠቀሱት ተጨዋቾች ባቀረቡት ግልፅ ደብዳቤ ሳይፀድቅ ለውይይት በድጋሚ ይቀርባል የሚለው ተስፋ ባለመሳካቱ  ሁኔታዎች የተድበሰበሱ መስሏል፡፡   የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ይፋ ባደረገው መግለጫ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም የመመሪያው ተግባራዊነት እንደሚጀመር አረጋግጦ፤ መመሪያው እንደተሻሻለ ወይም ተግባራዊ እንደማይሆን ከአንዳንድ ወገኖች እየተሠነዘረ የሚገኘው አስተያየት መሠረተ ቢስ ብሎታል፡፡ በመመርያው  የአፈጻጸም ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን መሰረት በማድረግ በየጊዜው በሚደረግ ፍተሻ የማሻሻያ እርምጃዎች እንደሚወሰድ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አቋም መሆኑን ያመለከተው የፌደሬሽኑ መግለጫ፤  በቀጣይነትም መመሪያውን በተመለከተ ከተለያዩ አካላት የሚቀርቡትን ገንቢ አስተያየቶች ፌዴሬሽኑ እየተቀበለና እያጤነ በማሻሻል አስፈላጊውን መግለጫ የሚሰጥ መሆኑ እንዲታወቅ መመሪያውን በተመለከተ የተለወጠ ወይም የተሻሻለ ሁኔታ ባለመኖሩ ተግባራዊነቱ የሚቀጥል መሆኑን አሳስቧል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን  በአገሪቱ የሚፈፀመው የእግር ኳስ ተጨዋቾች ደረጃና ዝውውር በሕግና በሥርዓት እንዲመራ ባለው ፍላጎት መፅናቱን አረጋግጧል፡፡ መመርያው በፊፋ ዝቅተኛውን የተጨዋቾች ደረጃና ዝውውር መስፈርት ያሟላ እንዲሆን፣ በተጨማሪም አሠራሩ በሕጋዊ ወኪል እንዲመራና ሒደቱም ተጨዋቾችን፣ ክለቦችንና መንግሥትን ተጠቃሚ በማድረግ ለአገሪቱ የእግር ኳስ ዕድገት መፋጠን የራሱን አወንታዊ ሚና እንዲጫወት ይፈለጋልም ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ ከተጨዋቾች ዝውውር ጋር ተያይዞ እየተሠራበት የነበረው አሠራር ለአገሪቱ እግር ኳስም ሆነ ለክለቦች፣ ተጨዋቾችና መንግሥት ምንም ዓይነት ጥቅም እንዳላስገኘ የሚገልፀው ፌደሬሽኑ፤ የዝውውር ሂደቱ የክለቦችን የፋይናንስ አቅም ማዳከሙን፤ ለተጨዋቾችም እንደተከፈለ የሚነገረው ገንዘብ ሙሉ በሙሉ እንደማይደርሳቸው፤ ህገወጥ የዝውውር ደላሎች እንደበዙበት፤  በፕሮፌሽናል ስም የሚመጡት ብዙዎቹ ተጨዋቾች የችሎታቸው ጉዳይ ጥያቄ እንደሚያስነሳ፤ ተጨዋቾች ከደመወዝ ይልቅ ትኩረት ሰጥተው የሚከራከሩት ለፊርማ ተብሎ ስለሚሰጣቸው ገንዘብ መሆኑ፣ ገንዘቡን ከወሰዱ በኋላ ለክለባቸው ተገቢውን አገልግሎት እንደማይሰጡ፣  ክለቦች ታዳጊዎችን አሳድገው ማግኘት የሚገባቸውን ጥቅም በማሳጣቱ፣ አዲሱ ደንብ ተግባራዊ መሆኑ ይህን እነዚህን ችግሮች ለማስተካከል መፍትሄ እንደሚያመጣ በዝርዝር አብራርቷል፡፡

Saturday, 11 July 2015 11:56

የፀሐፍት ጥግ

የራሳችንን ጭብጦችና ታሪኮች ለመግለፅ
የምዕራባውያንን ዘይቤ ተጠቅመን ፅፈናል።
የሥነ ፅሁፍ ቅርሳችን ግን “አንድ ሺ አንድ
ሌሊቶች”ን እንደሚያካትት እንዳትዘነጉ፡፡
ናጂብ ማህፉዝ
· ጭብጦች በሥራዬ ላይ በተደጋጋሚ እያሰለሱ
ይመጣሉ፡፡
ኢቭ አርኖልድ
· ለእኔ ህይወት እና ሞት በጣም ወሳኝ ጭብጦች
ናቸው፡፡ ሞት በሌለበት ህይወት የለም፡፡ ለዚያ
ነው ለእኔ በጣም ወሳኝ የሆኑት፡፡
ቲቴ ኩቦ
· ለእኔ ጭብጥ፤ ፍቅርና የፍቅር እጦት ነው።
ሁላችንም ፍቅርን እንፈልገዋለን፡፡ ግን እንዴት
እንደሚገኝ አናውቅም፡፡ እያንዳንዱ ድርጊታችን
እሱን ለመጨበጥ የሚደረግ ሙከራ ነው፡፡
ርያን ጐስሊንግ
· እውነት አንድ ብቻ ብትሆን ኖሮ፣ በተመሳሳይ
ጭብጥ መቶ ሸራዎች ላይ አትስልም ነበር፡፡
ፓብሎ ፒካሶ
· የእንግሊዝ ገጠራማ ክፍል እድገትና ውድመት
እውነተኛና አሳዛኝ ጭብጥ ነው፡፡
ኢ.ኤም.ፎርስተር
· አገራት ገንዘብ በመፈለጋቸው የተነሳ ባህላቸውን
አጥተዋል፡፡ በየአገሩ ገንዘብ የወቅቱ ጭብጥ
የሆነበት ጊዜ ነበር፡፡ በዚህም ሳቢያ ባህል
መስዋዕት ተደረገ፡፡
ዩኮ ኦኖ
· አንድ ጭብጥ ውሰድና አድምተህ ስራው …
ጉዳዩ ታዲያ አንድም ከልብህ የምትወደው
አሊያም ከልብህ የምትጠላው መሆን አለበት፡፡
ዶሮቲያ ላንጅ
· ፍቅር፤ በሥራዬ ላይ እየተመላለሰ የሚመጣ
ጭብጥ ነው፡፡
ትሬሲ ቻፕማን
· ቁጭ ብዬ በሴራ እና ጭብጥ መካከል ያለውን
ልዩነት አስቤ አላውቅም፡፡ ለእኔ ያ ጨርሶ
አስፈላጊ ሆኖ አያውቅም፡፡
ሌን ዌይን
· ፀሐፊያን ቁጭ ብለው ስለ አንድ ዓላማ ወይም
ጭብጥ አሊያም ስለሆነ ነገር ለመፃፍ ማሰብ
ያለባቸው አይመስለኝም፡፡ ስለራሳቸው
የህይወት ተሞክሮ ከፃፉ፣ አንድ የሆነ እውነት
ብቅ ይላል፡፡
ዶሪስ ሌሲንግ
· ያለጥርጥር የምማረክበት ጭብጥ ሞት ነው።
አላን ቦል
· ጭብጥህ ውሎ አድሮ ያገኝሃል፡፡ አንተ እሱን
ፍለጋ መውጣት አይኖርብህም፡፡
ሪቻርድ ሩሶ
· ፊልም ሰ ሪዎች፤ “ ስለዚህ ጉ ዳይ ወ ይም በ ዚህ
ጭብጥ ላይ ፊልም መስራት እፈልጋለሁ” ይላሉ፡
፡ እኔ ግን ፈፅሞ እንደዚያ ብዬ አልጀምርም፡፡
አንድሪያ አርኖልድ


በጋዜጣችሁ የሰኔ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ዕትም ላይ አልፋ የትምህርትና ስልጠና አ.ማህበርን በተመለከተ ባቀረባችሁት ዜና፤ “ቅሬታው” በአንድ ግለሰብ የቀረበ መሆኑ እየታወቀ “የአልፋ ባለ አክስዮኖችና አመራሮች እየተወዛገቡ ነው” የሚል ርዕስ መስጠታችሁ አሳሳች፣ ለጋዜጣው አንባቢያን ስለ አክስዮን ማህበሩ የተዛባ መግለጫ የሚሰጥና የአክስዮን ማህበሩን መልካም ስምና ዝና የሚያጐድፍ አቀራረብ በመሆኑ በብዙኃን ባለአክስዮኖች ዘንድ ጥያቄ አስነስቷል፡፡
በተጨማሪም በዘገባችሁ፣ በማንኛውም የበጀት ዓመት በአክስዮን ማህበሩ ተገኝቶ የማያውቀውን ብር 30.000.000 (ሰላሳ ሚሊዮን ብር) የተጣራ ትርፍ ማስረጃ ባላገናዘበ ሁኔታ ተገኝቶ ነበር ብላችሁ መግለፃችሁ እንዲሁም በ2006 በጀት ዓመት የተገኘው የተጣራ ትርፍ ብር 4.5 ሚሊዮን እንደሆነ ተገልፆ እያለ፣ በመጨረሻው በጀት ዓመት ብር 1.5 ሚሊዮን ብቻ እንደተገኘ አድርጋችሁ ማቅረባችሁና ቅሬታ አቅራቢው የገለፀውን አመራሩ ከሰጠው መልስ ጋር በማነፃፀር አለመዘገባችሁ ቅሬታ እንደፈጠረብን ልንገልፅ እንወዳለን፡፡
(ቢኒያም ሀይሉ የዳይሬክተሮች ቦርድ ፀሐፊ)

ከዕለታት አንድ ቀን በደጋው አገር የሚኖሩ ሁለት ጐረቤታም ገበሬዎች ነበሩ። ሁለቱም በሣር ቤት የሚኖሩና ኑሮ አልለወጥ ያላቸው ግን ታታሪ ሰዎች ነበሩ፡፡
“አንድ ቀን አንደኛው በድንገት የኑሮ ለውጥ አሳየ፡፡ የግቢውን አጥር አጠረ። የቤቱን የሣር ክዳን ወደ ቆርቆሮ ጣራ ለወጠ፡፡ ልጆቹ ደህና ደህና ይመገቡ፣ መልካም ልብስም ይለብሱ ጀመር፡፡
ጐረቤትየው ያየውን ለውጥ ማመን አቅቶት ወደ ወዳጁ ሄደና፤
“አያ እገሌ?” አለው፡፡
“አቤት” አለው፡፡
አብረን አንድ አካባቢ እያረስን እየኖርን በድንገት ምን ተዓምር ተፈጥሮ ነው እንዲህ የበለፀግከው?”
የተለወጠው ገበሬም፤
“ሚሥጥሩ ምን መሰለህ ወዳጄ፤ ታች ቆላ ወርጄ ማጭድ፣ ዶማ፣ አካፋ፣ ማረሻ ወዘተ ብዙ ብረታ ብረት ገዝቼ አመጣሁና ለደገኛው ገበሬ ቸበቸብኩት። ትርፉ ትርፍ እንዳይመስልህ! አንድ ሁለት ሶስቴ ተመላልሼ ይሄንን ሥራ ስሠራ ገንዘብ እንደ ጉድ እጄ ገባ!” አለው፡፡
ያም ገበሬ አመስግኖት ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ በነጋታው፤ በሬዎቹን ሸጠና ብሩን ይዞ ወደ ቆላ ገበያ ወረደ፡፡ ቆላ ያለ የብረታ ብረት ዘር አንድም ሳይቀረው ገዛና ተሸክሞ ወደ ደጋ ሊመለስ መንገድ ጀመረ፡፡ መንገዱ ወደ ቆላ ሲሄድ ቁልቁለት ነበረ፡፡ አሁን ግን ዳገት ነው፡፡
ግማሽ መንገድ እንኳ ሳይጓዝ በሸክሙ ብዛት ወገቡ ሊቆመጥ ደረሰ፡፡ መቀጠል አልቻለም፡፡ ተዝለፍልፎ፣ ላብ በላብ ሆኖ ወደቀ፡፡
መንገደኛ የሰፈሩ ሰው ወድቆ አየውና፤
“አያ እንቶኔ?”
“አቤት”
“ምነው ምን ገጠመህ?”
“ኧረ ተወኝ ወዳጄ፤ ያ ጐረቤቴ ስለ ብረታ ብረት ንግድ አማክሮኝ፣ እዚህ ወድቄ ቀረሁልህ፡፡”
“እንዴት?”
“ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳይነግረኝ!”
*   *   *
በህይወት ውስጥ፣ ደረጃው ይለያይ እንጂ መስዋዕትነትን የማይጠይቅ ምንም ነገር የለም፡፡ ይህንን ልብ ያላለ ፖለቲከኛ ብዙ ዕድሜ አይኖረውም፡፡ በትንሽ በትልቁ ሲበሳጭ፣ ሲነጫነጭ፣ አቤቱታ ሲያበዛ፣ ነገረ ሥራው ሁሉ የዕድል እንጂ የትግል ሳይመስል፣ ማማረር እንጂ መማር ሳይዳዳው፤ በአጭር ይቀጫል፡፡ በዱሮ ጊዜ “ትግላችን እረዥም፣ ጉዟችን መራራ” የሚል መፈክር ነበር፡፡ ጣፋጭና አጭር ትግል የለም ለማለት ነው፡፡ ትግል ጠመዝማዛ እንጂ ቀጥ ያለ መስመር እንደሌለው የሚያፀኸይ ጭምር ነው፡፡ በታሪክ ዕውነተኛ ትግል ያካሄዱ የዓለም ድርጅቶች ወይም የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያስተምሩን ይሄንን ነው፡፡ ሳይታክቱ መታገል፣ ሽንፈትን በፀጋ መቀበል፣ ጉድለትን መመርመር ለቀጣዮቹ ዓመታት፣ ከአሁኑ መዘጋጀት! ዕቅድን እጥጉ ድረስ ማቀድና የትላንቱን እንቅፋት እስከመጨረሻው ማጽዳት ተገቢ ነው፡፡ ባላንጣን አለመናቅና እስከፍፃሜው መገላገል ተገቢው የጉዞው ፋይዳ ነው፡፡ ይሄንን ሳንገነዘብ ትግሉ ውስጥ ከገባን ፀፀት ማትረፋችን አይቀሬ ነው፡፡ ሮበርት ብራውን የተባለ ፀሐፊ እንዲህ ይለናል፡-
“ከሙሴ ጀምሮ የኖሩ ታላላቅ መሪዎች የፈሩትን ጠላት ሙሉ በሙሉ መደምሰስ እንዳለባቸው ያውቃሉ፡፡ (ይህንን የተማሩት በከባድ መንገድ ይሆናል አንዳንዴ) ከተዳፈነ እሳት ውስጥ አንዲት ፍም ካለች ምንም ደብዛዛ ብትሆን ቀስ በቀስ እሳት ማስነሳቷ አይቀሬ ነው፡፡ ግማሽ መንገድ ሄዶ ማቆም ከጠቅላላ ማጥፋት የበለጠ ኪሣራ ላይ ሊጥለን ይችላል፡፡ ጠላት አገግሞ ሊበቀል ይችላል። ስለዚህ በአካልም፣ በመንፈስም ማድቀቅ ያስፈልጋል”
ግማሽ መንገድ ተጉዞ መቆምን የመሰለ አደጋ የለም፡፡ “የነብርን ጅራት አይይዙም፤ ከያዙም አይለቁም” የሚለውን የአበሻ ተረት በጽኑ ማስተዋል ብልህነት ነው፡፡
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“…የተወጋ በቅቶት ቢኛ፣ የወጋ መች እንቅልፍ አለው፤
የጅምሩን ሳይጨርሰው፡፡” የሚለን ይሄንኑ ነው፡፡
ገና በጠዋት መንገድ ስንጀምር ትርፉን ሲነግሩን መከራውንም አብረን ማስታወስ፣ ትግልን ስናስብ መስዋዕትነትን አብረን ማሰላሰል፤ እጅግ ወሳኝ መሆኑን ከልባችን እናጢን፡፡ አለበለዚያ “መሳም አምሮሽ፣ ጢም ጠልተሽ” እንዲሉ ይሆናል!!