Administrator

Administrator

ጨጨሆ የባህል አዳራሽ የተመሰረተበትን አንደኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በአገሪቱ ላይ በባህል፣ በቱሪዝምና በበጐ ሥራ አስተዋፅኦ ላበረከቱ ሰዎች ሽልማት ሰጥቷል፡፡
“የጨጨሆ ባህል ሽልማት” በሚል ርእስ በተዘጋጀው ፕሮግራም ላይ አንጋፋው የማስታወቂያ ባለሙያ ውብሽት ወርቃለማው የአስር ሺህ ብር እና የዋንጫ ሽልማት ሲያገኙ፣ በውዝዋዜ የምትታወቀውና በቅርቡ ከአሜሪካ ወደ ሀገር ቤት የተመለሰችው እንዬ ታከለ የአስር ሺህ ብርና የዋንጫ ሽልማት አግኝታለች፡፡ እንዲሁም ከአራት ሺህ በላይ የባህል ግጥምና ዜማ የሰራው ሙሉጌታ አባተ፤ተመሳሳይ ሽልማት ሲያገኝ፣ተወዛዋዥዋ ዳርምየለሽ ተስፋዬም ተሸላሚ ሆናለች፡፡
በሽልማት ፕሮግራሙ ላይ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፤ በቆዳ የተሰራ ምስላቸው የተበረከተላቸው ሲሆን የቱሪዝም አባት የሚባሉት አቶ ሃብተስላሴ ታፈሰም ተሸልመዋል፡፡
የሽልማት ፕሮግራሙ ልዩ ተሸላሚ የሆነው የመቄዶኒያ የአረጋውያንና አዕምሮ ህሙማን ማዕከል መስራች ወጣት ቢኒያም በለጠ ደግሞ 20 ሺህ ብር ተበርክቶለታል፡፡ አርቲስት መሰረት መብራቴ፤የጨጨሆ የባህል አዳራሽ አምባሳደር ሆና ለአንድ ዓመት ለመስራት ተፈራርማለች፡፡

የአለም ኢኮኖሚ እድገት ከተገመተው በታች ይሆናል ተብሏል
             አዝጋሚው የቻይና ኢኮኖሚ በአለማችን ኢኮኖሚ ላይ ተጽዕኖ ያሳድራል
                           አህጉረ እስያ በአለም ኢኮኖሚ መሪነቷ ትቀጥላለች ተብሎ እንደሚጠበቅ አለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስቲያን ላጋርድ ማስታወቃቸውን ዘ ሂንዱ ታይምስ ዘገበ፡፡
አለማቀፉ የኢኮኖሚ እድገት ከዚህ በፊት ተገምቶ ከነበረው አነስ ባለ መጠን በመካከለኛ ደረጃ ላይ ሆኖ እንደሚቀጥል የገለጹት ክርስቲያን ላጋርድ፣ በአለማችን የኢኮኖሚ እድገት መሪነቱን የያዘችው እስያ፤ ምንም እንኳን የእድገት መጠኗ እየቀነሰ ቢሆንም በመሪነቷ ትቀጥላለች ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡
ለሁለት ቀናት ይፋዊ የስራ ጉብኝት ወደ ኢንዶኔዥያ ያመሩትና ከአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆኮ ዊዶዶ ጋር በአለማቀፉ የኢኮኖሚ ሁኔታ ዙሪያ የመከሩት ላጋርድ፣ ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ ዩኒቨርሲቲ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፣ አለማቀፉ የኢኮኖሚ ሁኔታ ኢንዶኔዢያን በመሳሰሉ ያላደጉ አገራት ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እንደሚያሳርፍ ገልጸዋል፡፡
የአምናው የአለማችን የኢኮኖሚ ዕድገት 3.4 በመቶ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ አይ ኤምኤፍ ባለፈው ሃምሌ ወር ላይ የዘንድሮው የአለማችን የኢኮኖሚ ዕድገት 3.3 በመቶ ሊያድግ ይችላል ብሎ መገመቱንና ዕድገቱ ግን ያነሰ ሊሆን እንደሚችል ዳይሬክተሯ መናገራቸውን አስረድቷል፡፡ አምና 2.4 በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት ያስመዘገበችው አሜሪካ፤ ዘንድሮ በ2.5 በመቶ ታድጋለች ተብሎ መገመቱን የጠቀሰው ዘገባው፣ ባለፈው አመት 7.4 በመቶ ያደገችው ቻይና በበኩሏ፤ የዕድገቷ መጠን ቀንሶ 6.8 በመቶ ሊደርስ ይችላል ተብሎ እንደተገመተ ጠቁሟል፡፡
ያደጉ አገራት ኢኮኖሚ በተወሰነ መጠን ማገገም ይታይበታል ቢባልም፣ በማደግ ላይ ያሉ ኢኮኖሚዎች ግን ከነበሩበት ደረጃ ዝቅ ይላሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ክርስቲያን ላጋርድ ተናግረዋል፡፡
ቢቢሲ በበኩሉ፤ ክርስቲያን ላጋርድ አዝጋሚው የቻይና ኢኮኖሚ በአለማቀፉ የኢኮኖሚ እድገት ላይ ተጽዕኖ ማሳደሩ አይቀርም ሲሉ ማስጠንቀቃቸውን ዘግቧል፡፡
“የቻይና ኢኮኖሚ እድገት በሌሎች የአለማችን አገራት ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ፣ ከዚህ በፊት ከተገመተው በላይና የከፋ ሊሆን እንደሚችል ሁኔታዎች ያመለክታሉ፡፡ ስለሆነም ቻይና የጀመረቻቸውን የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ማስቀጠል ይገባታል” ብለዋል ላጋርድ፡፡
በቻይና ኢኮኖሚ ላይ የሚታዩ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ነዳጅና ማዕድናትን የመሳሰሉ ሸቀጦች ዋጋ እንዲቀንስ ማድረጉን የጠቆመው ዘገባው፣ በዚህም ሸቀጦቹን ለውጭ ገበያ የሚያቀርቡ ብራዚልና ሩሲያን የመሳሰሉ አገራት ክፉኛ እየተጎዱ እንደሚገኙ አስታውቋል፡፡

     የዚምባቡዌው ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ሚስት ግሬስ ሙጋቤ፤ ከሃራሬ የጎዳና ላይ ነጋዴዎች የተዘረፉ ልባሽ ጨርቆችንና አልባሳትን ያለአግባብ ለፖለቲካ ደጋፊዎቻቸው በማከፋፈላቸው ክስ ሊመሰረትባቸው እንደሆነ ተዘገበ፡፡
የሃራሬ ከተማ የጎዳና ላይ ነጋዴዎች ፖሊስ የወረሰባቸውን ልባሽ ጨርቆችና አልባሳት ቀዳማዊ እመቤት ግሬስ ሙጋቤ፣ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ሲሉ ለደጋፊዎቻቸው አከፋፍለዋል በሚል ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውን ተከትሎ፣ የዚምባቡዌ መደበኛ ያልሆኑ ዘርፎች ድርጅት በሴትየዋ ላይ ክስ እንደሚመሰርት ማስታወቁን ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ህገወጥ የጎዳና ላይ ነጋዴዎችን እንቅስቃሴ ለመግታት በሚል ልባሽ ጨርቆችና ጫማዎች ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ መከልከሉን ያስታወሰው ዘገባው፣ የሃራሬ ከተማ ፖሊስም በቅርቡ ባደረገው አሰሳ፣ በሺህዎች ከሚቆጠሩ የጎዳና ላይ ነጋዴዎች በርካታ ቶን የሚመዝኑ ልባሽ ጨርቆችና ሌሎች ቁሳቁሶችን መንጠቁን ገልጧል፡፡
ቀዳማዊ እመቤት ግሬስ ሙጋቤ፣ ባለፈው ሳምንት በሰሜናዊ ዚምባቡዌ በተከናወነ የፖለቲካ ቅስቀሳ ላይ፣ ፖሊስ ከነጋዴዎቹ የነጠቃቸውን 150 ቦንዳ ልባሽ ጨርቆችና አልባሳት ዛኑፒኤፍ ለተባለው ፓርቲያቸው ደጋፊዎች በነጻ ሲያከፋፍሉ መታየታቸውን የጠቀሰው ዘገባው፤ ድርጊቱን ያወገዘው የዚምባቡዌ መደበኛ ያልሆኑ ዘርፎች ድርጅትም ክስ ለመመስረት እየተዘጋጀ መሆኑን ማስታወቁን አስረድቷል፡፡
ቀዳማዊ እመቤት ግሬስ ሙጋቤ፤ የግል ንብረታቸው ያልሆነን ልባሽ ጨርቅና አልባሳት ለደጋፊዎቻቸው ማከፋፈላቸው ህገወጥ ድርጊት በመሆኑ፣ ይሄን ድርጊታቸውን እንዲያቆሙ በአፋጣኝ ክስ እንመሰርታለን ብለዋል፣ የድርጅቱ ዳይሬክተር ፕሮሚዝ ክዋናንዚ፡፡
ግሬስ ሙጋቤ ከነጮች የተወረሱ ሰፋፊ መሬቶችን የግል ይዞታቸው በማድረግ በአገሪቱ አቻ እንደማይገኝላቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ልባሽ ጨርቆቹን ሲያከፋፍሉ በደስታ ተውጠው ገዝተው እንዳመጡላቸው ለደጋፊዎቻቸው ሲናገሩ እንደነበርም አመልክቷል፡፡
በርካታ የአገሪቱ የጎዳና ላይ ነጋዴዎች በፖሊስ እየታደኑ እየተደበደቡና ንብረቶቻቸው እየተወረሰባቸው መሆኑንና  በ17 ያህል ነጋዴዎች ላይ ክስ መመስረቱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

    የፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ መንግስት ሞሃመድ ሙርሲን ከመንበረ መንግስቱ አስወግዶ ስልጣን ከያዘ በኋላ በአገሪቱ የመጀመሪያው በሚሆነውና ከሚጠበቀው ጊዜ ዘግይቷል በሚል ሲተች ቆይቶ በጥቅምት ወር ሊካሄድ ቀን በተቆረጠለት የግብጽ ፓርላማ ምርጫ፣ በውጭ አገራት የሚገኙ ዜጎች ድምጽ እንዲሰጡ መፈቀዱ ተዘገበ፡፡
ኦል አፍሪካን ዶት ኮም ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በርካታ ግብጻውያን በሚኖሩባቸው 139 የተለያዩ የአለማችን አገራት በሚቋቋሙ የምርጫ ጣቢያዎች፣ ዜጎች ድምጻቸውን እንዲሰጡ ለማስቻል አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረገ ይገኛል፡፡
በምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሃምዲ ሳንድ ሎዛ የሚመራ ኮሚቴ ተቋቁሞ፣ በ139 አገራት ውስጥ በሚገኙ የግብጽ ኤምባሲዎች የምርጫ ጣቢያዎች ተቋቁመው ዜጎች ድምጽ እንዲሰጡ አስፈላጊው ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝም ዘገባው ገልጧል፡፡
ማክሰኞ በተጀመረው የአገሪቱ የምርጫ ዕጩ ተወዳዳሪዎች ምዝገባ፣ 2 ሺህ 745 ያህል ዜጎች በተወዳዳሪነት መመዝገባቸውንና ምዝገባው ለ10 ቀናት ያህል እንደሚቆይ የግብጽ ከፍተኛ የምርጫ ኮሚሽን ያስታወቀ ሲሆን፣  55 ሚሊዮን ያህል ዜጎች ድምጽ ለመስጠት መመዝገባቸውንም አሃራም የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የምርጫ ኮሚሽን፣ በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ምርጫው በጥቅምት ወር አጋማሽ እንደሚካሄድና የድምጽ አሰጣጡም ለሁለት ቀናት እንደሚካሄድ ማስታወቁን የጠቆመው የቴሌግራፍ ዘገባ፣ አገሪቱ ከሰኔ ወር 2012 አንስቶ ፓርላማ እንደሌላትና ምርጫ እንድታካሄድ የተወሰነው ቀደም ብሎ ቢሆንም በፕሬዚዳንቱ ቸልተኝነት መዘግየቱን አመልክቷል፡፡
ፕሬዚዳንት አል ሲሲ፤ ከነባር የአገሪቱ የፖለቲካ ፓርቲ ጋር ለመቀላቀልም ሆነ አዲስ ፓርቲ ለመመስረት ፈቃደኛ ሳይሆኑ መቆየታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ በቀጣዩ ምርጫም ዋነኛ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደማይወዳደሩ ጠቁሟል፡፡
ምርጫው ከተያዘለት ጊዜ እንዲራዘምና ባለፈው መጋቢት ወር እንዲካሄድ ቢወሰንም፣ የአገሪቱ ፍርድ ቤት አንዳንድ የምርጫ ህጎች ህገመንግስቱን የሚጥሱ ናቸው በማለት ምርጫው ዳግም እንዲራዘም መወሰኑን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ጆሃንስበርግ 23‚400፣ ካይሮ 10‚200፣ ሌጎስ 9‚100 ሚሊየነሮች አሏቸው
            አፍሪካ በድምሩ 670 ቢ. ዶላር ሃብት ያካበቱ 163 ሺህ ሚሊየነሮች አሏት

   የደቡብ አፍሪካዋ ጆሃንስበርግ በአፍሪካ አህጉር በርካታ ሚሊየነሮች የሚገኙባት ቀዳሚ ከተማ መሆኗን አፍርኤዥያ ባንክ እና ኒው ወርልድ ዌልዝ የተሰኙ ተቋማት ሰሞኑን ይፋ ያደረጉትን አህጉራዊ የጥናት ውጤት ጠቅሶ ቢቢሲ ዘገበ፡፡ “የወርቅ ከተማ” ተብላ የምትጠራው ጆሃንስበርግ፤ 23 ሺህ 400 ሚሊየነሮች የሚኖሩባት የአፍሪካ የባለጸጎች ከተማ መሆኗን የገለጸው ዘገባው፣ ደቡብ አፍሪካ በአህጉሩ ከሚገኙ ሚሊየነሮች 30 በመቶው የሚገኙባት አገር መሆኗንም አስታውቋል፡፡
10 ሺህ 200 ሚሊየነሮች ያሏት የግብጽ መዲና ካይሮ፤ በሚሊየነሮች ብዛት ከአህጉሩ ከተሞች ሁለተኛ ደረጃን የያዘች ሲሆን 9 ሺህ 100 ሚሊየነሮች ያሏት የናይጀሪያዋ ሌጎስ ደግሞ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች፡፡
ባለሃብቶቹ በዝርዝሩ ውስጥ ለመካተት ቢያንስ 1 ሚሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ሊኖራቸው እንደሚገባ የጠቆመው ዘገባው፣ አፍሪካ በድምሩ 670 ቢሊዮን ዶላር ሃብት ያካበቱ 163 ሺህ ሚሊየነሮች እንዳሏትም አክሎ ገልጿል፡፡

 ጋዜጠኛ የደስደስ ተስፋ በቅርቡ ያሳተመው “እንጀራ ከመከራ” የተሰኘ የግጥም መድበል በዛሬው ዕለት ከቀኑ 9 ሰዓት በሀገር ፍቅር ትንሿ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በ72 ገፆች የተቀነበበው መድበሉ፤ በ25 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

  በዶክተር ምህረት ደበበ በተፃፈውና በቅርቡ ለንባብ በበቃው “ሌላ ሰው” የተሰኘ ልቦለድ መጽሐፍ ሃሳብ ላይ የአንባቢያን ውይይትና የመጽሐፍ ማስፈረም ዝግጅት ዛሬ ከቀኑ 9፡30 ጀምሮ በደሳለኝ ሆቴል ይካሄዳል፡፡ መጽሐፉም ለሽያጭ ይቀርባል ተብሏል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “የተቆለፈበት” የተሰኘ በተደጋጋሚ የታተመ ልብ ወለድ መጽሐፍ ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

     ክሮሲንግ ባውንደሪ” የተሰኘ ዓለም አቀፍ የትውን ጥበባት ፌስቲቫልና ጉባኤ በመጪው መስከረም ወር አጋማሽ ላይ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ የቲያትር ባለሙያዎች ማህበር አስታወቀ፡፡
በፌስቲቫሉ ላይ ከሐገር ውስጥ 9 ትያትሮች የሚቀርቡበት ሲሆን ከውጪ ሀገራትም ከአፍሪካ  እንዲሁም ከአሜሪካና ከእስራኤል የሚመጡ የቴአትር ቡድኖች ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል፡፡ ፌስቲቫሉ በክውን ጥበባት ላይ የሚካሄድ ዓለም አቀፍ ጉባኤንም ያካትታል ተብሏል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ በሚካሄደው በዚህ ጉባኤ ላይ ከተለያዩ ሀገራት የተጋበዙ የዘርፉ ምሁራን ጥናታዊ ፅሁፎችን እንደሚያቀርቡ ተጠቁሟል፡፡
በፌስቲቫሉ ላይ የሚካፈሉት ትያትሮች በብሄራዊ ቴአትር፣ በሀገር ፍቅር፣ በአዲስ አበባ ቴአትርና ባህል አዳራሽ፣ በኦሮሞ ባህል ማዕከል፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሴዝና በአስኒ አርት ጋለሪ ለዕይታ ይቀርባሉ፡፡
የትውን ጥበባት ፌስቲቫሉን የኢትዮጵያ የቲያትር ባለሙያዎች ማህበር፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከብሄራዊ ቴአትርና ከሰንዳንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር እንዳዘጋጁት ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 05 September 2015 10:03

ገጣሚ ወንድዬ አሊ ስለ ግጥም…

“የአገራችን ግጥም በተስፋና በፅልመት መካከል ያለ ግራጫ ሆኖ ይታየኛል!”
             እንባና ሳቅን አሥማምቶ፣ ያለ ሸንጎና ፍርድ በሀረጋትና ስንኞቹ ትከሻ ለትከሻ ትቅቅፍ ህይወትን አዲስ የሚያደርግ ሰው - ገጣሚ ነው፡፡ ሰማይና ምድርን አሳስሞ ባንድ መኝታ ላይ የሚያጋድም ተዓምረኛም እንደዚሁ … ገጣሚው ነው፡፡ የመላዕክት ክንፎችን ላንብብ፣ የእግዜርን ጓዳ ልፈትሽ ብሎ መጋረጃ ገለጣ የሚደፍር ገጣሚ ነው፡፡
የጠፋን ነገር አሥሶ፤ የራቀን ነገር አቅርቦ የሚያሳይ ንሥር ዓይን ያለው ገጣሚ ከአደባባይ ሲጠፋ፣ … “የት ገባ?” ማለት ያገር ነው፡፡ “የወፌ ቆመች” እና የ “ውበት እና ህይወት” የግጥም መጽሐፍት አባት የሆነው ወንድዬ ዓሊ-የት ጠፋ? የአዲስ አድማስ ፀሐፊና ሃያሲ ደረጀ በላይነህ፣ ከገጣሚ ወንድዬ ዓሊ ጋር በሕይወቱና በግጥም ጥበብ ዙሪያ ተከታዩን ውይይት አድርገዋል፡፡

    ወንድዬ፡- ከአሥር ዓመታት በላይ በግሌ እየሰራሁ ነው፤ ቤቴ ቢሮዬም ሆኗል፡፡ ሥራ ለመቀበል፣ ለማስረከብም ካልሆነ ወይንም የጥናት ወረቀት ከሌለ በስተቀር ከቤቴ አልወጣም፡፡ በየቀኑ ከ12 - 16 ሰዓታት ድረስ እሰራለሁ፤ ይኼ አሰረኝ፡፡ በተለይ ደግሞ ሥነ ጽሑፍ የሕይወትህ ጥሪ - እንጀራህም ሲሆን የበለጠውን እርጋታና ፀጥታ ፍለጋ ከአደባባይ ትጠፋለህ፡፡
በጠፋህባቸው ዓመታት ምን ምን ሰራህ ታዲያ?
በትምህርት (ሙያዬ ልበል ይሆን) ደረጃ ኮሚዩኒኬሽን አጠናሁ - በማስተርስ ደረጃ፡፡ በዚህ ረገድ ከበራሪ ወረቀቶች አንስቶ እስከ ትልልቅ ጥናቶችና መጻሕፍት ዝግጅት ድረስ (እንደ ደንበኞቼ ፍላጎት) ስሰራ ከረምኩ፡፡ አጫጭር ዘገባዊ ፊልሞችም አሉ፣ ሦስት አራት የሚሆኑ፡፡ ይዘታቸውን በተመለከተ የግንዛቤ ማስጨበጫ (ኤችአይቪ፣ የሴት ልጅ ግርዛት፣ የልጆች አስተዳደግ፤ የህይወት ክህሎት) እስከ ግለታሪክ ዝግጅቶችና ህትመቶችን ይጠቀልላሉ፡፡ ለነገሩ ኮሚዩኒኬሽን ስትማር ብፌ እንደተመገብክ ቁጠረው፣ ሳይኮሎጂው፣ ስነ ሰብዕ (Anthropology)፣ ስነ - ጽሁፍ እንዲሁም ወደፍልስፍናና አንዳንድ ደረቅ ሳይንሶችም ትጠጋለህ፡፡ ልባም ከሆንክ በንባብና ጥናት አሳድገህ ባለብዙ ፈርጅ ባለሞያ ትሆናህ፡፡ ይህ ደግሞ ኮሚዩኒኬሽን በመማር የሚገኝ ትሩፋት ብቻ ሳይሆን የምንማርበት ተቋም ሥርዐተ ትምህርት፣ የመምህራኑ አቅምና መሰጠት እንዲሁም ተማሪዎች በትምህርት ቤት ቆይታቸው እውቀትን ለመበዝበዝ ባላቸው ዝንባሌና ጥረት የሚወሰን ይሆናል፡፡
አንዳንድ ሰዎች ጠነን ያለ፣ ምናባዊ ሸጋ ቋንቋ የሚጠቀም ገጣሚ ነው - ይሉሃል፡፡  ምን ዓይነት ግጥሞች ነው የምትወድደው?
ከስነ ግጥም ዓይነቶች ይልቅ የሚገደኝ ምንጫቸውና አፈጣጠራቸው ነው፡፡ ሰይፉ መታፈሪያ፤ “ግጥም ምንጩ ግለሰባዊ፣. ባፈጣጠሩ ዐይነ - ልቡናዊ፣ ባቀነባበሩ ጭምቅ፣ በቋንቋው ስልታዊ ነው” የሚለው አባባላቸው ይጥመኛል፡፡
ጋሼ ጸጋዬ ደግሞ ማቲው አርኖልድን ጠቅሶ፤ “ሥነ ግጥም ያው የገዛ ሕይወቱ ሂስ ነው” ይላል፡፡ ይህም ግሩም ነው፡፡ ሥነ ግጥም የገዛ ህይወት ሂስ ከመሆኑ ጋር የምደምረው ቁም ነገር አለኝ፤ ይኸውም ከደበበ ሰይፉ የተማርኩት ነው፡፡ “ባድማ ልቡን አድምጦ የሚጽፍ ጸሐፊ ከማህበረሰቡ የተጣላ ነው፡፡” የሚለውን አነጋገሩን እወድለታለሁ፡፡
ከጸጥታና እርጋታ ባሻገር በራስህ ዓለሙን ረስተህ፣ ዓለሙም አንተን ሸጉሮብህ (ቀርቅሮብህ) የምትጽፈው ግጥም የምድረበዳ ምኞት ዓይነት ነው፡፡ በጠየቅኸኝ መሰረት፤ ባብዛኛው የምወደው የግጥም ዓይነት ምሰላን ትርጉም ያላቸውን ይመስለኛል፡፡ የአንድ ቀን ክስተት ተንተርሰው የሚገጠሙ የአዝማሪ ዓይነት ግጥሞችን ብዙም አልወድም፡፡ የአንድ ቀን ገጠመኝ ግን ወደ ህይወት ምሰላ ተለውጦ፣ ሁለንታዊነትን ተላብሶ፣ ሳነብበው ደስ ይለኛል፡፡ ውበት እና ሕይወት ውስጥ “በጥላዬ” የሚለውን ግጥም የጻፍኩት ኃይሌ ገብረስላሴ በኦሎምፒክ መድረክ አንደኛነቱን ለቀነኒሳ ባስረከበበት ቀን ውድድሩን በቴሌቪዥን ካየሁ በኋላ ነበር፡፡ ግና በግጥሙ ውስጥ ኃይሌም ቀነኒሳም የሉም፣ ህይወት ግን ነበረች፡፡ እኔም ነበርኩ፡፡
“ጥላዬ”
የቀደመው ቀረ
   ጀማሪው ፊተኛ
   ፊተኛው ከኋላ
   የኋላው አንደኛ፡፡
    ያልዘቀጠው ወጣ
    የወጣው ዘቀጠ፡፡…
ፊት የወጣች ፀሐይ
    በ-ምዕራብ ሰማይ
    መጥለቂያው በር ላይ፡፡
አዲሷ ከምሥራቅ
    በንጋት አልፋ ላይ
በማለዳ ‘ርከን ላይ፡፡
    እርከኑ እስቲሰበር
    በጭለማ በትር፡፡
የቀደመው ሲቀር፣
የወጣው ሲዘቅጥ፣
ምዕራብ ሲጠልቅበት፣
ጐህ ሲቀድ ለምሥራቅ፣
እነሱን ሲታዘብ … በወጣ … ዘቀጠ
ከገቡበት መቅረት
ከወጡበት መግባት
እንዴት ባመለጠ!?
“ውበትና ሕይወት”ን ካሳተምክ ዘጠኝ ዓመታት አለፉ፤ አሁንስ ግጥም፣ ትጽፋለህ?
ባልጽፍማ ሞቼአለሁ ማለት ነው፡፡ “ውበት እና ሕይወት” በ1998 ዓ.ም ታተመች፡፡ “ወፌ ቆመች” ረቂቁ ለኩራዝ አሳታሚ ድርጅት የተሰጠው በ1982 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ ነበር፡፡ የታተመችው በ1984 ዓ.ም ይመስለኛል፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮተቤ የመምህራን ትምህርት ኮሌጅ እንደተጨማሪ ማስተማሪያ ሆነች፡፡
“ወፌ ቆመች ቅጽ 2 (ውበት እና ህይወት)” ስትታተም ድፍን አገሩ በነፃ ፕሬሶች የተጥለቀለቀበት ጊዜ ነበር፡፡ ስለዚህ ድምፅዋ ሳይሰማ ከገበያ ጠፋች፤ ተሸጠች፡፡ አዳዲሶቹን ግጥሞች “ወፌ ቆመች ቅጽ 3” ለማሳተም የዘመኑን ነገር እያደባሁ ነው፡፡
በዚህ ዘመን በግጥም ሥራዎች ረገድ ምን ገረመህ?
ያልተዘመረላቸው ጀግኖች እንዳሉ ሁሉ ያልተዘመረላቸውም መጻህፍት መኖራቸው! … የኔ መጽሐፍ “ውበት እና ሕይወት” እንኳ በጎምቱ አንባቢዎች እጅ ብቻ ገብታ ለአዲሱ ዘመን ገጣሚያን የስልትና የፍልስፍና ግብዐት ሣትሆን ልሂቃን ልብ ውስጥ መቅረቷ ገርሞኛል፡፡ ጥቂት የተጠቀመበትና ወደ ቀጣዩ ትውልድ ልብ ያሻገራት ሟቹ ብርሃኑ ገበየሁ ብቻ ይመስለኛል፡፡ በነገራችን ላይ የሥነ - ግጥምን ጥበብ የሚመለከት “ወፌ ቆመችን እንደ ዘሪሁን አስፋው (የሥነ ፅሁፍ መሰረታዊያን በሚለው መጽሐፍ) “ውበት እና ህይወት”ንና “ወፌ ቆመች” ን አዳብሎ በመተንተን እንደ ብርሃኑ ገበየሁ ያሉ ምሁራን አላገጠሙኝም፡፡
“ፎክር ፎክር አለኝ”
ፎክር!
ፎክር!
    አለኝ፣
ነዘረኝ
ነሸጠኝ
ፎክር - ፎክር አለኝ፣
    ሽለላ - ሽለላ፣
አለ ይሆን ዛሬ
    ግብር የሚበላ!? …
ፎክር
ፎክር
አለኝ፡፡
እንዴ …. !
በነ አባጃሎ አገር
በጀግኖቹ ጎራ፣
ገዳይ በጎራዴ
ገዳይ በጠገራ፡፡
በሾተለ አንደበት
    ገዳይ በአፈር ሳታ፣
በነገር ነጎድጓድ
            ገዳይ በቱማታ፤ …
በነዘራፍ ስንቁ
    ባለ ብር ሎቲ፣
በተሞላች አገር ፡-
ጅረት ባበጀባት
ዘንቦ የደም ዕምባ፤
ተራህ ነው ይለኛል፣
ተሠራ ሹርባ፡፡
በአማርኛ ሥነ ግጥም ምን ይታይሃል?
በተስፋና በፅልመት መካከል ያለ ግራጫ ነገር ሆኖ ይታየኛል፡፡
(ይቀጥላል)

Saturday, 05 September 2015 09:55

የግጥም ጥግ

 የዕንቁጣጣሽ አበባ!

           -ነ.መ.
አንዳንድ ህፃን ዕድሏ፣
ያስታውቃል ከብቅሏ
አበቅቴዋ አይስትም ውሉን
ለእንቁጣጣሽ ልትወለድ፣ ተፅፏል ቃሉ
  ቀድሞውን!
በአበባ ወር የመጣች፣ የዕንቁጣጣሽ አበባ
ትስቃለች ታለቅሳለች - ፣
      የዕድሏን ያህል ለዕማማ!
    የዕድሏን ያህል ለአባባ!!
እንኳን መጣሽ አንች አበባ፣
እንኳን መጣሽ አንች ወለባ!
የጎመንም፣ የገንፎሽም፤ ምንቸቱ
       አንቺው ቤት ይግባ!!
(ለኪዳኔና ለጤና አዲሷን
የዕንቁጣጣሽ
አበባይቱን ለሚቀበሉ፣
ልጆቻቸው ሁሉ)
                 - ነሐሴ 29 2007 ዓ.ም.