Administrator

Administrator

 እስካሁን ከተሞከሩት የተሻለ ውጤታማ ነው ተብሏል
   ከዚህ በፊት ከተሞከሩት የኤችአይቪ/ ኤድስ መከላከያ ክትባቶች ሁሉ የተሻለ ውጤት አስገኝቷል የተባለ አዲስ ክትባት በመጪው ህዳር ወር ላይ በደቡብ አፍሪካ ሊሞከር እንደሆነ ኤንቢሲ ኒውስ ዘገበ፡፡ የኤችአይቪ/ኤድስ ኢንፌክሽንን በአንድ ሶስተኛ ያህል የመከላከል አቅም አለው የተባለው ይህ ክትባት በቀጣይ ሊደረግ በታሰበው ሙከራ የበለጠ ውጤታማ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ክትባቱ የሚሞከረው በ5ሺህ 400 ሰዎች ላይ እንደሚሆንም ገልጧል፡፡
ቫይረሱ በአለማቀፍ ደረጃ 35 ሚሊዮን ሰዎችን እንዳጠቃ የጠቆመው የኤንቢሲ ኒውስ ዘገባ፤በየአመቱ 1.2 ሚሊዮን ሰዎችን ለሞት እየዳረገ እንደሚገኝም አስረድቷል፡፡

Tuesday, 24 May 2016 08:29

የዘላለም ጥግ

- ድል አንድ ሺ አባቶች ሲኖሩት፤
ሽንፈት ግን ወላጅ አልባ ነው፡፡
ጆን ኤፍ.ኬኔዲ
- ድል፤ የዝግጁነትና የቁርጠኝነት
ልጅ ነው፡፡
ሳን ሃምፕተን
- ረዥም ዕድሜ ከኖርክ እያንዳንዱ
ድል ወደ ሽንፈት እንደሚለወጥ ታያለህ፡፡
ሳይሞን ዲ ቢዩቮይር
- ጠላት ባይኖር ትግል አይኖርም፡፡
ትግል ባይኖር ድል አይኖርም፡፡ ድል ባይኖር
ደግሞ ዘውድ አይኖርም፡፤
ቶማስ ካርሊሌ
- ከድል ጥቂት ነገሮችን ልትማር
ትችላለህ፡፡ ከሽንፈት ግን የማትማረው ነገር
የለም፡፡
ክሪስቲ ማቴውሶን
- በጦርነት ውስጥ ድልን የሚተካ
ምንም ነገር የለም፡፡
ዳግላስ ማክአርተር
- ድል ጣፋጭ የሚሆነው ሽንፈትን
ስታውቀው ነው፡፡
ማልኮም ፎርብስ
- ወደ ድል በሚደረግ ጉዞ
የመጀመሪያው እርምጃ ጠላትን መለየት ነው፡

ኮሪ ቴን ቡም
- ያለ ዕቅድ ጥቃት የለም፡፡ ያለ ጥቃት
ድል የለም፡፡
ኩርቲስ አርምስትሮንግ
- እውነተኛው ድል የዲሞክራሲና
የብዝኃነት ድል ነው፡፡
ሆስኒ ሙባረክ
- አሸንፋለሁ ብለህ ካሰብክ
ታሸንፋለህ፡፡ እምነት ድል ለማድረግ ወሳኝ
ነው፡፡
ዊሊያም ሃዝሊት
- ዲሞክራሲ፤ ዲሞክራት ያልሆነን
ቡድን ወደ ስልጣን ካመጣ፣ ያንን
የዲሞክራሲ ድል ልንለው እንችላለን?
ሪቻርድ ኢንጄል
- ድል ጣፋጭ የሚሆነው ያንተ
ወገን በማሸነፉ ነው - ወይስ የጠላት ወገን
በመሸነፉ?
ጆን ፓድሆሬትዝ
(ስለ ድል)



ይህ ጽሁፍ ሚያዝያ 21 ቀን 2008 ዓ.ም የአቶ አሰፋ ጫቦ ”የትዝታ ፈለግ” መጽሐፍ በጣይቱ የባሕልና ትምህርት ማዕከል አዳራሽ
በተመረቀበት ወቅት መጽሐፉን ለማስተዋወቅ ካደረግሁት ንግግር አጥሮና ተስተካክሎ (Edited) የቀረበ ነው፡፡

ዓለም ፀሐይ ወዳጆ
(Silver Spring, Maryland USA)

   የተወደዳችሁ እንግዶች፤ በቅድሚያ የዛሬው እንግዳችን አቶ አሰፋ ጫቦ ‹የትዝታ ፈለግ› በሚል ርዕስ ያሳተመውን መጽሐፍ ለምርቃት በማብቃቱ በጣይቱ የባህልና የትምህርት ማዕከል ስም ‹እንኳን ደስ አለህ!› እላለሁ::
በዛሬው ምሽት የትዝታ ፈለግ  በሚል ርዕስ ለንባብ ያበቃውን መጽሐፉን ልንመርቅ ነው የተሰባሰብነው:: መጽሐፉን በማነብበት ወቅት ብዙ ወደ ማውቃቸው ጊዜያትና ግለሰቦች የወሰደኝ ሲሆን የአጻጻፍ ውበቱም እጅግ አስደንቆኛል፤ የባህሪይ አቀራረፅ ችሎታውና የአካባቢ ስዕላዊ መግለጫውም አርክቶኛል::
አቶ አሰፋ ጫቦ፤ ከተራራ አናት ላይ ከሚገኝ ሜዳማ ቦታ ላይ ጨንቻ ከተማ ነው የተወለደው:: ከጋሞ ሰንሰለት ተራራዎች አንዱ ጫፍ ላይ የሚገኝ ጠረጴዛ ነው ይላታል፤ጨንቻን ሲገልጣት፡፡  ከ 2ኛ- 6 ኛ ክፍል እዚያው ጨንቻ የተማረ ሲሆን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በአዲስ አበባ ኮከበ ጽባህ እስከ ፲ኛ ክፍል ተምሮ አቋረጠ። ሆኖም በራሱ መንገድ ህግ ተምሮ መመረቅ ብቻ ሳይሆን በአለም አቀፍ ውድድሮችም ሁለቴ ተካፍሎ፣ከንጉሱ እጅም የወርቅ ኦሜጋ ሰአት ለመሸለም በቅቷል፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ በወህኒ ቤት ሳሉ፣ በሙሉጌታ በቀለ አካሚነት (ገጽ15-18) ሰለሞን ደርቤን በእግሩ ማቆም መቻልን አልፎም ፈጣን ሆኖ የእስረኛ ምግብና ቡና አመላላሽ ተደርጎ መመደቡን አሳይቶ አስደምሞኛል:: የአገራችንን የአብያተ ክርስቲያኑንም ጭምር ድንቅ ውበት በማስቃኘት፣ ለቱሪዝም አዳዲስ አካባቢዎችን ለማስተዋወቅ ሞክሯል፡፡
በመጽሐፉ ላይ በጠቀሳቸው (ገጽ 25-34) በረዘነና በወይናይ ባለው ችግር መነሻነት በትግራይና በኤርትራ መካከል የነበረው ቅራኔ ምን እንደሚመስል እንድናይ ያደረገበት ዘዴ አስገርሞኛል:: የሕግ አዋቂነቱን ለአቀራረቡ ማነጻጸሪያ ተጠቅሞበታል፡፡ “ረዘነ ወልዱና ወይናይ ሁለት የተለያየ ባህርይ ያላቸው ሰዎች ናቸው። ረዘነ ተጫዋች፤ተግባቢ፣ደግ፤ገራገር፤ተናጋሪና በመጠኑም ቢሆን ችኩልም ነው። ፈጣን ነው ማለት ይቻላል። ሀብታም ነው ማለትም ይቻላል። ወይናይ ምስኪን ነው። ሁለመናው ምስኪን ነው። ከ3 አመት በላይ ሲኖር ከመንሾካሸክ ያለፈ ድምጽ ሲወጣው አልሰማሁም። -----” ይለናል።
በመጽሐፉ (ገጽ19-24) ጎንደሬውን፤ቀናና የዋሁን፤እንደወጣ የቀረውን ዶ/ር ካሳሁን መከተን ያነሳዋል፡- ‹‹ በቀን ቢያንስ አንዴ ሳያነሳቸው የማይውላቸው ሁለት ነገሮች አሉ። አንደኛው ስለደባርቅ/ዳባት ነው። የኢትዮጵያን ኋላ ቀርነት ማስረጃ ያደርጋቸዋል። እስከ ዛሬ ማብራት እንኳን አልገባላቸውም! ይላል። “ሶሻሊዝም፤ሶሻሊዝም!” ይላሉ ደባርቅ መብራት መች ገባ ?” ይላል። ይህችው ነች! አይለዋውጥም!”
ብዙ ባለታሪኮና ተረቶች መጽሐፉን አጣፍጦለታል፡፡  እናቱን አክብረው “እንዬ” እያሉ ባደጉት ጓደኞቹ በእነ ዶክተር ገዛኸኝ በላይና በፍስሀ ዘለቀ ታሪክ ውሰጥ አጥልቆ የመንፈስን ከመንፈስ ጋር መዋሃድ እንዲሁም የህዝብን ሥነልቦናዊ አመለካከትን እንድናይ ያደርገናል::
“ነፍጠኛ” ማለት አማራ ብቻ ነው ማለት እምነት እንጂ እውነት እንዳልሆነና “ነፍጠኛ” (117-151) በሚል የሚበጠብጠንን ጥያቄ ለመመለስ ናችሁ የተባልነውን ሳይሆን ውስጣችን ገብተን ሆነን ያለነውን እንድናስተውል ይጎተጉተናል፡፡ ጋሽ አሰፋ፤“አቅብጦኝ ከደርግ ጋር ገጠምኩ” ብሎ አያውቅም:: አምኖ እንጂ ምናምን ፍለጋ ወይም ሰው ገፍቶት እንዳልገባ በግልጽ አስቀምጦልናል:: እንዲያውም “በመሸ በጠባ ቁጥር በጥሼ የምቀጥለው ማተብ የለኝም !” ይለናል::
በትረካዎቹ ጸሃፊው በንባብ የዳበረና የበሰለ መሆኑን ከማሳየቱም ሌላ ወደ አሜሪካ ስለ መምጣትና መኖር ያካፈለው ምክርም በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ ስለ ስደቱ ዓለም ችግርና ውጥንቅጥ ሲጽፍም፤ ስደተኛው በሃብት ድህነትና በአእምሮ  ድህነት መካከል ያለው ልዩነት የጠፋበት መምሰሉን ፍንትው አድርጎ ያሳየናል፡፡ በአጠቃላይ ጆሮ ጠገብነት ማወቅን አለመተካቱን ይገልጽልናል፡፡   
ጀግና ፍለጋ ጦር ሜዳ መሪዎች አምባ፣ የፖለቲካ ሰዎች አምባ እንሄዳለን:: ጀግና ሲገኝ አገር ያውቀዋል፤ ፀሃይ ይሞቀዋል:: ያልታወቁ በየቤቱ የታጨቁ ተራ ሰው የሆኑ ጀግኖች አሉ በማለት፣ በዕለት ተዕለት ኑሮአችን ያልተሰጣቸውን በመፈጸም የበለጠ ጀግና ስላደረጋቸው የአማቾቹ የቤት ሠራተኛ ስለሆነችው ስለ ወሎየዋ ዘውዲቱ አስማረ “የኔይቱ ጀግና!” (63-67) በሚል ርዕስ ይተርክልናል፡፡  “ጋሞ” ይላል “ጋሞ ግብር ገበረ እንጂ ሥርዓቱን አልገበረም” በማለት ጥፋቱን ስህተቱን በማመን መቀበልና ባደባባይ ይቅርታ መጠየቅ የጋሞነት መገለጫና አብሮ የተወለደ የውስጥ ባህርይ መሆኑን በመተንተን፣ ለየት ስላለው የአገርና የህዝብ አስተዳደር ሥርዓት ሲያጫውተን፤ አንዳንዶቻችን በአገራችን ውስጥ ይህ መኖሩን ባለማወቃችን እንቆጫለን:: ወደ ዛሬያችን ለማምጣት በምኞት እንጋልባለን::
 ሌላው የጋሽ አሰፋ ትልቅነቱ፣ እንደ አንዳንዶቹ ፀሃፊዎች በራሱ አራት ነጥብ ዘግቶ እመኑልኝ ሳይለን፣ “ያየሁትና የኖርኩት እንጂ ያጠናሁት አይደለም” ማለቱ ነው:: በትዝታዎቹ ውስጥ እየሾለከ የሁላችንንም ትዝታ ይቆሰቁሰዋል፡፡ በተለይ በመጽሃፉ የጠቀሳትን፣ ይህንን ማዕከል ‹‹ጣይቱ›› ብዬ እንድሰይም ምክንያት የሆነችኝን Empress Taytu and Menilik the II of Ethiopia ደራሲ ክሪስ ፕራውቲን  (Chris Prouty 111-115)  እንደኔው አግኝቶ ስላደነቃትና ስላሞካሻት ይበልጥ ተደስቻለህ::
ዛሬ በአገራችን ስለተንሰራፋው ሥርዓትም በማዘን እየገለጸ ወደተሻለ እንድንጓዝ ይማፀነናል:: በእስራት ብዛት የህዝብ ነጻነት ታፍኖ የቀረበት ዘመንም አገርም አለመኖሩን በማስረገጥ፣ለ“የጋራ ቤታችን ” የሚፈለገውን መጠነኛ ጥገና በማካሄድ ፈንታ መናድ የመረጡትን ያወግዛቸዋል፡፡ አገራቸውን ባለማወቅ ወይም ለማወቅ ባለመፈለግ፣ ነቀዝ የበላው ቤት እንድትሆን ማድረጋቸውን በመውቀስም፣የምትፈለገዋን  ከስህተቷ ልምድ የቀሰመች አዲሲቷ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እንድንገነባ ይጣራል:: የትዝታ ፈለግ ራስ ወዳዶች እራሳቸውን እንዲጠይቁና እንዲፀየፉም ይገፋፋል፡፡ በተለይም ገጽ 244 “አልዘቅጥም መባል ያለበት ወደ ታች ወደ ምድር ቤት ምን ያህል ሲዘቅጡ ይሆን?›› ሲል በመጠየቅ ‹‹ከዚህ በላይ አልወርድም በቃኝ አይባልም! በቃኝ አታውርደኝ ተብሎስ አይፀለይም …” በማለት እነዚህን ወገኖች ይሸነቁጣቸዋል:: ከቁጣ ይልቅም ወደ ዳኝነት፣ ወደ ማመዛዘን እንድናደላ  ይጋብዘናል::
 አብርሃም ሊንከን እንዳለውና ጋሽ አሰፋም በመጽሃፉ ላይ እንደጠቀሰው፤ ‹‹ማንንም ያለ ቂም እንድንመለከት፣ሁሉንም በልግስና እንድናቅፍ፣በሃቅ ላይ እንድንጸና፣አምላክም ይህንን ሐቅ እንድናይ እንዲረዳን እንማጸን”:: ኢትዮጵያውያንንም የማይመጣን ነገር ከመጠበቅ ረጅምና ዝነኛ ታሪካችን ይገላግለን !
ጋሽ አሰፋም፤ “እመለስበታለሁ “ እያለ ያለፋቸውን ጉዳዮች፡- ስለ እስረኛው ቡና ማፍያ፣ ስለ ሁለንተናዊ የኑሮ ዘርፍ ማሟያ፣ ስለ ቀኝ አዝማች ታዬና ስለ ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ማርያም፣ ስለ አሜሪካ አገር ድመትና ውሻ ዘውድ መጫን፣ ወዘተ አሰባስቦ ሁለተኛ መጽሐፉን ለአንባቢያን እንዲያደርስ ያብቃው::
  “በትዝታ ፈለግ” ምክንያት እኔም እንደ ጋሽ አሰፋ ግርጫ ቤት መስራት አማረኝ:: እኔም ጨንቻን ወደ ታች የዞዞን ተራራ ማዶ ለማዶ ማየት አማረኝ:: ጨንቻን ለመሞት ሳይሆን ለመኖር መረጥኳት!! እዚያ ሰው አይሞትምና…በዝግታ መራቅ…ባልተስተዋለ መልኩ ማለፍ…አማረኝ!
   በድጋሚ እንኳን ደስ አለህ !!!

  ይህን የማያደርጉ መገናኛ ብዙኃን እርምጃ ይወሰድባቸዋል
        በካምቦዲያ የሚገኙ መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱን ጠቅላይ ሚኒስትር በተመለከተ በሚሰሯቸው ዘገባዎች ላይ ተገቢውን ክብር መስጠት እንደሚገባቸውና ሙሉ ማዕረጋቸውን መጥቀስ እንዳለባቸው በአገሪቱ የመረጃ ሚኒስቴር ትዕዛዝ እንደተሰጣቸው ቢቢሲ ዘገበ፡፡ሚኒስቴሩ ለአገሪቱ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ እንዳሳሰበው፣ ከመጪው ነሐሴ ወር ጀምሮ በሚሰሯቸው ዘገባዎች ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩን፣ የባለቤታቸውንና የተወሰኑ ባለስልጣናትን ከእነ ሙሉ ማዕረጋቸው መጥራት ይገባቸዋል፡፡መገናኛ ብዙኃኑ የአገሪቱን መሪ በተመለከተ በሚሰሯቸው ዘገባዎች ላይ፣ “ጌታ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጠቅላይ ጦር አዛዥ ሁን ሴን” በማለት ከነ ሙሉ ማዕረጋቸው እንዲጠሯቸው ማሳሰቢያ እንደተሰጣቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ሚኒስቴሩ ይህን በማያደርጉ መገናኛ ብዙኃን ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ ቢናገርም እርምጃውን በተመለከተ የጠቀሰው ነገር እንደሌላ አመልክቷል፡፡

   16 ሚ. ድምጾችን አግኝቷል፤ ወደ አገሪቱ ፕሬዚዳንትነት ተጠግቷል ተብሏል
     ፊሊፒንሳዊው የአለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮን ማኒ ፓኪዮ ከትናንት በስቲያ ይፋ በተደረገው የአገሪቱ የላዕላይ ምክር ቤት አባላት ምርጫ ውጤት፣ ለምክር ቤት አባልነት የሚያበቃውን ድምጽ በማግኘት አሸናፊ መሆኑንና ወደ አገሪቱ ፕሬዚዳንትነት ተጠግቷል መባሉን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ባለፈው ሳምንት የአገሪቱ ምክር ቤቶች ምርጫ መከናወኑን ያስታወሰው ዘገባው፤የምርጫ ኮሚሽኑ ሃሙስ ዕለት ይፋ ባደረገው የምርጫ ውጤት፣ የአገሪቱ የላዕላይ ምክር ቤት አባል ለመሆን የሚያስችላቸውን ድምጽ ካገኙ አዳዲስ ተወዳዳሪዎች መካከል፣ ከ16 ሚሊዮን በላይ ድምጾችን ያገኘው ቦክሰኛው አንዱ መሆኑን አስታውቋል ብሏል፡፡
“በቦክሱ አለም ሳደርገው እንደቆየሁት ሁሉ፣ ወደ ፖለቲካው ስገባም፣ አገሬን ለመጥቀም በትኩረትና በስነ-ምግባር ተግቼ እሰራለሁ!... እንደ አንድ አዲስ የምክር ቤት አባልነቴ፣ በሁሉም ደረጃዎች ትምህርት በነጻ የሚሰጥበትን ሁኔታ ለመፍጠር የተቻለኝን ጥረት አደርጋለሁ” ብሏል የ37 አመቱ ቦክሰኛ ፓኪዮ፣ የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ፡፡
ፓኪዮ ባለፈው አመት በተከናወነውና የክፍለ ዘመኑ ፍልሚያ በተባለው የቦክስ ግጥሚያ ላይ ከታዋቂው ፍሎይድ ሜዌዘር ጋር ተጋጥሞ ድል ባይቀናውም ምርጫው ከመከናወኑ ከአንድ ወር በፊት ከአሜሪካዊው የከባድ ሚዛን ሻምፒዮን ቲሞቲ ብራድሊ ጋር በላስቬጋስ የቦክስ ግጥሚያ አድርጎ ድል እንደቀናውም ዘገባው አስታውሷል፡፡

    በዮናስ ሲሳይ ፕሮሞሽን የተዘጋጀውና “ሀገር፣ ባህል ማንነት” በሚል መሪ ቃል የሚቀርበው “ሄሎ ኢትዮጵያ”
የባህል ምሽት ሰኔ 20 ቀን 2008 ዓ.ም ሰኞ ምሽት በሀርመኒ ሆቴል ይካሄዳል፡፡ በዝግጅቱ ላይ በርካታ ባህላዊና ኪነጥበባዊ ድግሶች እንደሚቀርቡም አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡ በእለቱ በተለያዩ የውዝዋዜ ቡድኖች ባህላዊ ውዝዋዜ፣በሄሎ ኢትዮጵያ የባህል ሙዚቃ ቡድን የሚቀርብ የባህል ሙዚቃ ትርኢት እና የጋዜጠኛ ሰለሞን ታደሰ የተመረጡወጎች ለታዳሚ ይቀርባሉ የተባለ ሲሆን፤ የተለያዩ እውቅ የኪነ - ጥበብ ባለሙያዎች “ሀገር ማለት” በሚል መነሻ ሀሳብ ስለ አገራችን ባህልና ወግ ሀሳቦችን በማንሸራሸር ታዳሚውን እያዝናኑ እንደሚያስተምሩ የሄሎ ኢትዮጵያዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቴዎድሮስ ሲሳይ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

     በረቡኒ፣ መባ፣ ከዕለታት፣ ጢባጢቤና በሌሎችም ፊልሞቿ አድናቆትን ያተረፈችው ደራሲና ዳይሬክተር
ቅድስት ይልማ ስራ የሆነውና “ሰላም ነው?” የሚል መጠሪያ የተሰጠው ፊልም ከነገ በስቲያ በብሔራዊ
ቴአትር አዳራሽ ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ጀምሮ ይመረቃል፡፡ የ1፡25 ሰዓት ርዝማኔ ያለውና የፍቅር ኮሜዲ
ዘውግ ያለው ፊልሙ የሰውን እድሜና እድል የሰረቀ ሰው በምንና እንዴት ይቀጣል በሚለው ላይ
እንደሚያጠነጥን የፊልሙ ፕሮዲዩሰር ፀጋነሽ ሃይሉ እና የሌሊያና ፊልም ፕሮዳክሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ
ተናግራለች፡፡ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ አንድ አመት የፈጀ ሲሆን በፊልሙ ላይ ፀጋነሽ ሃይሉ ኤርሚያስ
ታደሰ አስኒክ በቀለ፣ ቴዎድሮስ ወዳጄና ሌሎችም አንጋፋና ወጣት ተዋንያን ተሳትፈውበታል፡፡

ከዝነኛው ኤዞፕ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡-
ከዕለታት አንድ ቀን ተኩላዎች ወደ ውሾች መንደር መጡ ይባላል፡፡
“እንደምናችሁ ውሾች?”
ውሾችም፤
“እኛ ደህና ከርመናል፡፡ እናንተስ ተኩላዎች እንዴት ሰነበታችሁ?” አሉ፡፡
ተኩላዎችም፤
“እናንተ ውሾች በጣም ታሳዝኑናላችሁ”
“ለምን?”
“እስከዛሬ እኛና እናንተ ጠላት መሆናችን እጅግ ያሳዝናል፡፡ አለመተሳሰባችንና              አለመነጋገራችን ነው እንጂ ተስማምተን መኖር እንችል ነበር”
ውሾችም፤
“ኑሯችን ለየቅል ሆኖ እንዴት አብረን መኖር እንችላለን” አሉ፡፡
ተኩሎችም፤
“ዋናው ችግር በእርግጥ እሱ ነው፡፡ በመልክና በሁኔታችን በጣም እንመሳሰላለን፡፡ አፋችን፣
ጆሯችን፣ እግራችን ጭራችን …ሁሉ ነገራችን ተመሳሳይ ነው፡፡
ዋናው ልዩነታችን የሥልጠና ጉዳይ ነው፡፡
1ኛ) የምንኖረው በነፃነት ነው
2ኛ) እናንተ የሰው ልጅ ባሪያ ናችሁ፡፡ የሰው ልጅ እንደፈለገ ይቀጠቅጣችኋል፡፡
3ኛ) አንገታችሁ ላይ ሠንሠለት አስሮ ሣጥን ውስጥ ከቶ ያሳድራችኋል፡፡
4) የከብት መንጋ ያስጠብቃችኋል፡፡ ያለፍላጐታችሁ የሰው ከብት ስታዩ ትውላላችሁ፡፡
5ኛ) ለዚህ ሁሉ ልፋታችሁ የተጋጠ አጥንት ነው የሚወረውርላችሁ፡፡
ስለዚህ ከዚህ መከራ መገላገል አለባችሁ፡፡ ቢበቃችሁ ይሻላል፡፡” አሏቸው፡፡
ውሾችም፤
“የተናገራችሁት ዕውነት ነው፡፡ ነገር ግን ምን ማድረግ እንዳለብን አናውቅም” አሉ፡፡
ተኩላዎችም፤
“እኛ የመጣነው ዘዴውን ልንነግራችሁ ነው” አሉ፡፡
ውሻዎች በጥድፊያ፤
“ምንድነው ዘዴው?” አሉና ጠየቁ፡፡
ተኩላዎችም፤
“ዘዴውማ ከብቶቹን ለእኛ ስጡንና ወደ እኛ ጫካ ይዘናቸው ሄደን፣ የሰቡ የሰቡትን እየበላን፣
መጨፈርና መዝናናት ነው፡፡
እዚህ የሰው ልጅ ባሪያ ከመሆን ይሄ የነገርናችሁ ዘዴ አይሻልም?” አሏቸው፡፡  
ውሾች፤
“ሀሳቡን በደስታ እንቀበላለን፡፡ ድንቅ ሃሳብ ነው፡፡ ከብቶቹን እየነዳን አብረን እንሂድና
እንደሰት፡፡ ነፃ እንውጣ” አሉ፡፡ ተኩላዎችና ውሻዎች ተያይዘው፣ ከብቶቹን እየነዱ ወደ ዱር
ሄዱ፡፡
ተኩላዎቹ ግዛታቸው መድረሳቸውን ካረጋገጡ በኋላ ግን፤ ውሻዎቹን አንድም ሳያስቀሩ
ቦጫጭቀው ጨረሷቸው፡፡
***
“የባሰ አለ አገርክን አትልቀቅ” ይላል አበሻ ሲተርት፡፡ “ጠላ አገኛለሁ ብለህ፣ ውሃ ረግጠህ አትሂድ”ም ይላል፡፡ ያ ማለት ግን የታሠርክበትን ሠንሠለት ለመበጠስ አትሞክር፤ ዘላለም በባርነት ኑር ማለት አይደለም፡፡ ከበጠስክ በኋላ የት እንደምትደርስ በትክክል ዕወቅ፤ ቀጥለህም “ከዚያ በኋላስ?” ብለህ ጠይቅ ነው፡፡ አንድ ጥቁር አሜሪካዊ የትምህርት ሰው (academician) ስለ አፍሪካውያንና ስለ ነጮች ልዩነት ሲናገር፤ “አፍሪካውያን (ጥቁሮች) እጅግ ታታሪ ናቸው፡፡ ግባቸውንም ይመታሉ፡፡ ችግሩ የሚመጣው ከዚያ ቀጥሎ ነው፡፡ ይኸውም አንድ ግብ ሲመቱ “ቀጥሎ ምን መደረግ አለበት?” አይሉም፡፡ ነጮቹ ያንን መነሻ አድርገው ገና ወደ ላይ ይስፈነጠራሉ፡፡ አይ ፈረንጅ! ፈረንጅ የነካው ነገር እኮ ተዓምር ነው የሚፈጥረው” እንላለን፤ አለ፡፡ ይህንን በአበሽኛ ማሰብ ነው የሚጠበቅብን፡፡ ከሁሉም ያገኘነውና የተረፈን የስብሰባ ባህል ነው፡፡ ደራሲ በዓሉ ግርማ፤ “ህይወት ራሷ የተራዘመ ስብሰባ መሰለችኝ” እንዳለው ነው፡፡ ዛሬ ያውም ብሶ ተባብሶ ነው!! ሁኔታዎችን ተቆጣጣሪ ጠፋ፡፡ የትራፊክ አደጋ አንዱ ምሳሌ ነው፡፡ “ለመንገደኛ ቅድሚያ ባለመስጠት የተከሰተ ነው!” እየተባለ፤ “የሞኝ ለቅሶ መልሶ መልሶ” ሆነናል፡፡ ቢያንስ የዓለም ባንክ ሪፖርት የጠቀሰውን “የኢትዮጵያ የትራፊክ አደጋ ችግር፤ ትንሽ ያለማገናዘብ (Lack of commonsense) ችግር ነው” ያለውን ልብ ማለት ያባት ነው፡፡
 የኢኮኖሚ ችግራችንም ቢሆን እጅግ ቅጥ ያጣ ነው፡፡ የኢኮኖሚ ባለሙያዎቻችንም ነገር “ቄሱም ዝም ዳዊቱም ዝም” ነው! የስኳር ኮርፖሬሽን መቀመቅ መግባት አሰቃቂ ነው፡፡ ወይ በሰዓቱ ለህዝብ አልተነገረ፣ ወይ አስቀድሞ አደጋው በባለሙያዎቻችን አልተተነበየ፤ “አይመጣምን ትተሽ ይመጣልን ጨምሪበት” የሚለውን እንኳ ተረት አለማሰብ ከተማረ የማይጠበቅ ነው፡፡ ያን ካላሰብን፤ ቢያንስ “የተማረ ይግደለኝ!” ለማለት እንኳ አቅም ማጣታችን ነው! “የተማረ ይግደለኝ የምትል ከሆነ፤ ዩኒቨርሲቲ ደጃፍ ሄደህ ተንከባለል” የሚለውን ተረባዊ አባባል ተቀበል፤ የሚለውን ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ ችግሩ ትምህርቱ ምሁር ሊፈጥር ባለመቻሉ ለሁሉም የዕቃ-ዕቃ ጨዋታ መሆኑ ነው! ጣጣችን ብዛቱ ይዘገንናል፡፡ መንገዶች ተሰሩ እንጂ ጠጋኝ የላቸውም! ኮንዶሚኒየሞች ከተሰሩ እና ከተሸጡ በኋላ ተከታታይ የላቸውም! ገበያዎች የሸማቹ ኪስ እስካለ ድረስ እንደፍጥርጥራቸው የሚባሉ ከሆኑ ውለው አድረዋል፡፡ አንድ የውጪ አገር ዜጋ እንደታዘበው፤ “የቢሮ ሰራተኞች እርስ በርስ ተቆላልፈዋል፡፡ በዚያው ሥራውም አብሮ ተቆልፏል” ብሎናል! የሀገራችንን ሁልቆ መሳፍርት የሌላቸው ችግሮች ለመፍታት የሚመሳሰሉ ሰዎች አንድ ላይ መሆናቸው ወሳኝ ነው! አፍና ልብ መገናኘታቸውም ዋና ነገር ነው፡፡ ዘይትና ውሃ ሆኖ ሥራ መስራት፣ ልማት ማልማት ብሎ ነገር እንዲያው ጨዋታ ነው! “ወመቴን ከአለሌ፣ ጨውን ከአሞሌ” መለየት ግድ ነው!” ከምትጣላው ጋር ገበታ ከመቅረብ፣ ከምትወደው ጋር መንገድ ጀምር! የሚባለው ለዚህ ነው!!

ፖለቲከኞች ምን ይላሉ?

የግንቦት 20 በዓል 25ኛ ዓመት የብር ኢዮቤልዩ በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር መንግስት አስታውቋል፡፡ ግማሽ ክፍለ ዘመን
ባስቆጠረው የኢህአዴግ መራሹ መንግስት የተመዘገቡት ስኬቶችና ውድቀቶች እንዴት ይገመገማሉ? የግንቦት 20 ትርፍና ኪሳራ
እንዴት ይገለጻል? የተለያዩ የፓርቲ አመራሮችና ፖለቲከኞች አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ
አንበሴ የሁሉንም ሃሳብና አተያይ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡

“ለኔ ግንቦት 20፣ እንደ ማንኛውም ሰኞና ማክሰኞ ነው”    አቶ ግርማ ሠይፉ - የቀድሞ የፓርላማ አባል)

  ግንቦት 1983 ላይ ምናልባት የ23 አመት ወጣት ነበርኩ፡፡ እውነቱን ለመናገር የመንግስት ለውጡ ሲመጣ ምንም የተለየ ነገር አልጠበኩም ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች ሲመጡ አገር መምራት ይችላሉ ወይም ይመራሉ የሚል ግምት አልነበረኝም፡፡ ከራሳቸው አስተሳሰብ እንኳ ስንነሣ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በወቅቱ እየተጠላ የመጣውን ሶሻሊዝም ያውም የአልባኒያ ሶሻሊዝም ተከታይና ይሄንኑ ይሰብኩ የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ለዚህች ሃገር ይጠቅማሉ ወይም ይህቺን ሃገር ይመራሉ የሚል እምነት አልነበረኝም፡፡ ሆኖም በራሳቸው ባይችሉም እንኳን ሌሎች ኢትዮጵያውያንን በማሳተፍ አገሪቷን ወደተሻለ አቅጣጫ ሊመሯት ይችላሉ የሚል ተስፋ ነበረኝ፡፡ አቅምም ስለሌላቸው ሌላውን ያሳትፋሉ የሚል ግምት ነበረኝ፡፡
በሽግግር ቻርተሩ ጊዜ ነፃ ሚዲያ፣ ሳንሱር ቀርቷል የሚሉ ቃላት የተጨመሩበት ስለነበር ጥሩ ነገር ሊመጣ ይችላል የሚል ተስፋ ነበረኝ፡፡
መጨረሻ ላይ ግን ሁሉንም ያሳተፈ ነው በሚል የራሳቸውን ኮንፈረንስ ሲያካሂዱ በዚያኑ ወቅት አንዱ ከሣሽ አንዱ ተከሳሽ ሆኖ የሚቀርብ ሣይሆን ሀገራዊ እርቅ የሚወርድበት ሁኔታን ስለአሸናፊነት ስነልቦና ወርደው ቢያመቻቹ ኖሮ ወደምንፈልገው ምዕራፍ የምንሸጋገርበት እድል ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡
ከዚያ በኋላም ይሻሻላሉ ተብለው ሲጠበቁ ብሶባቸው በ1993 ዓ.ም የኢትዮጵያ ህዝብ እስኪንገሸገሽባቸው ድረስ ደርሰዋል፡፡ እኔ እንደሚመስለኝ ያኔ ያዳናቸው በወቅቱ የተከሰተው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ነው፡፡ ጦርነቱ ለእድሜያቸው መራዘም መልካም እድል የፈጠረላቸው ይመስለኛል፡፡ ጦርነቱ ተከስቶ ኢትዮጵያውያን አንድ የሚያደርግ ነገር ባይፈጠር ኖሮ  ይገጥማቸው የነበረውን ችግር መቋቋም አይችሉም ነበር፡፡ ያ ለእነሱ አንድ እድል ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ በአለማቀፍ ደረጃም ለመጀመርና ዘልቆ ለመግባባት ጦርነቱ እድል የከፈተላቸውም ይመስለኛል፡፡
ሌላኛው በኢህአዴግ የ25 አመት ጉዞ ውስጥ በጉልህ የሚጠቀሰው የ1997 ምርጫ ነው፡፡
በወቅቱ ከህዝቡ የቀረበባቸውን ተቃውሞ ሊቋቋሙ አልቻሉም ነበር፡፡ አጋጣሚውን ለበጎ መጠቀም ሲችሉ አልተጠቀሙበትም፡፡
 ከዚያ በኋላም “ስልጣናችን የሚያበቃው በመቃብራችን ላይ ነው” ብለው ቆርጠው ተነስተው ይኸው እስከዛሬ አሉ፡፡
የግንቦት 20 ፍሬዎች
ስኬታቸው ይሄ በመሠረተ ልማት አገኘን የሚሉንን ከሆነ እኔ አልስማማም፡፡ ስኬት በቁስ ብቻ ሳይሆን በሰው ልጅ ሰብዕና እና ነፃነት ላይ የሚመሰረት ነው የሚል ዕምነት አለኝ፡፡ ከተማ ውስጥ ከምናያቸው አስፓልቶች በላይ ከ25 አመት በኋላም 20 ሚሊዮን ህዝብ በእለት ደራሽ እርዳታና በሴፍቲኔት የሚረዳ ህዝብ መኖሩን ነው የማስበው፡፡ ይሄን ሁሉ ጉድ ይዘን ተሣክቶልናል የምንል ከሆነ፣ እንደ ባህላችን ያው “ተመስገን” ብለን መኖር አለብን ማለት ነው፡፡
ከዚህ መለስ ብለን ማየት አለብን ብዬ የማስበው ጦርነት ባይኖር ኖሮ ደርግስ መሠረተ ልማት የሚባለውን መስራት አይችልም ወይ? የሚለውን ነው፡፡ በሚገባ ይሠራ ነበር፡፡ ከዚህች ድሃ ሀገር በየአመቱ በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ባይሸሽ ደግሞ ምን ሊሠራ እንደሚችል ማሠብ ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዴ በሚኒልክ ጊዜ ስልክ አልነበረም፤ዛሬ ሞባይል አምጥተናል ሲሉ ይገርመኛል፤ ሞባይልን እነሱ ባያመጡትም ማንም ሊያመጣው የሚችል ነው፡፡ ዘመኑ የፈቀደው የቴክኖሎጂ ውጤት ነው፡፡ የኢህአዴግ መንግስት ባይኖርም ሞባይል ይኖር ነበር፡፡ መንገድ ሠርተናል የሚለውም ቢሆን ጣሊያንም በሚገባ መንገድ ሠርቷል፡፡ በ5 አመቱ ብዙ መንገድ ሠርቷል፡፡ ስለዚህ ጣሊያን ይሻለን ነበር ልንል ነው?
መንግሥት ሲቀየር የነበርዎት ተስፋ ምን ነበር? ተስፋዎት ከ25 ዓመት በኋላ ተሟልቶ አግንተውታል?
እኔ እዚህ ሀገር የምኖረው በየዓመቱ ተስፋ ስላለኝ ነው፡፡ እኔ ተስፋ አልቆርጥም፤ በአገሪቱ ውስጥ ነገሮች እንዲሻሻሉ የራሴን አስተዋጽኦ ማበርከት አለብኝ ብዬም አምናለሁ፤ በግሌም ከመሰሎቼ ጋር ሆኜም፡፡ የኔ ልጆች፤ “ይህቺን ሃገር እንዲህ አድርገው ያስረከቡን አባቶቻችን ናቸው” ብለው እንዲወቅሱኝ አልፈልግም፡፡ እንዲለወጥና እንዲሻሻል ጥረት አደርጋለሁ፡፡ መለወጥና ማሻሻል ባልችል እንኳ ልጆቼ፣ “አባቴ ዝም ብሎ ቁጭ ብሎ ነው እንደዚህ አይነት ሀገር ያስረከበኝ” እንዳይሉኝ በግሌ ሙከራ አደርጋለሁ፡፡ እኔ እያንዳንዱ ሰው የሚያደርገው እንቅስቃሴ ለለውጥ የራሱ ድርሻ አለው የሚል ጠንካራ እምነት አለኝ፡፡ ግን ብንተባበር ለውጡን እናፋጥናለን፡፡
ለኔ ግንቦት 20 እንደ ማንኛውም ሠኞና ማክሰኞ ነው፡፡ በትግል ለውጥ ለማምጣት ግንቦት 20ን መጠበቅ አያስፈልገኝም፡፡ አንድ ሴትዮ ምን አሉኝ መሰለህ? “ኢህአዴግ ያመጣልን ለውጥ ሴት ልጆቻችን በቪዛ ውጭ ሀገር እንዲሄዱ ማድረግ ብቻ ነው፡፡” እኔም እሱ ባይመጣ ኖሮ ይቀርብን ነበር የምለው ዛሬ ላይ ያለ አንድም ነገር የለም፡፡ አሁን ያሉት ነገሮች ሁሉ እሱ ባይመጣም ምናልባትም በተሻለ መጠን የሚመጡና የሚፈጠሩ ነገሮች ናቸው፡፡ እንደውም የተሻሉ ብዙ ነገሮች ይኖሩ ነበር፡፡ ሞባይልም፣ ቴሌቭዥንም ሌላውም እነሱ ቢኖሩም ባይኖሩም ይመጣሉ፡፡ እኔ የሚቆጨኝ ያልመጡ ብዙ ነገሮችን ሳስብና የተበላሸውን ነገር ሳስተውል ነው፡፡
ዛሬ አንድ ሚኒስትር ሲሾም ስሙን ለመስማትና በዘር ለመፈረጅ እንድንጣደፍ ያደረጉን እነሱ ናቸው፡፡ መታወቂያችን ላይ ብሄር የፃፉልን እነሱ ናቸው፡፡ በየእለቱ ስለ ብሄር እንድናስብ አድርገውናል፤ እነዚህ ሁሉ ጥሩ አይደሉም፡፡

========================================

“አገሪቱ የባህር በር ያጣችው ከግንቦት 20 በኋላ ነው”     አቶ ልደቱ አያሌው፤ ፖለቲከኛ)

የመንግስት ለውጡ ሲመጣ የተለያዩ ጭንቀቶች ነበሩ፡፡ ይህቺ ሀገር ወደ ሁከት ሜዳ ትሸጋገራለች የሚል ፍርሃት ነበር፡፡ ኢህአዴግ ከሚያራምዳቸው አንዳንድ አቋሞች በመነሳት ደግሞ ሀገሪቱ ትበታተናለች የሚል ስጋትም ነበር፡፡ እኔም እንደ ማንኛውም የወቅቱ ወጣት በነዚህ ሀሳቦች መሃል ነበርኩ፡፡
በመጀመሪያ ግንቦት 20 ደርግ ወድቆ ኢህአዴግ የተተካበት ነው፡፡ በአንፃራዊነት በሃገሪቱ ውስጥ ለረዥም አመታት በርካታ ወጣቶችን የጨረሰው ጦርነት የቆመበት ጊዜ ነው፡፡ እሱ በራሱ ስኬት ነው፡፡ ሁለተኛው ውጤት በሀገሪቱ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅና ያገኙ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎች ተቀባይነት ያገኙበት ጊዜ ነበር፡፡ የነፃ ፕሬስ፣ የብዙሃን ፓርቲ አሰራር ቢያንስ በህግ ደረጃ እውቅና አግኝተዋል፡፡ ቆይቶ ቢሆንም የኢኮኖሚ እድገትም የታየው ከግንቦት 20 በኋላ ነው ማለት ይቻላል፡፡
 ያሳጣን ብዬ የማነሳው አንዱና ዋነኛው የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝብ የተነጣጠለው በግንቦት 20 አማካኝነት መሆኑ ነው፡፡ በታሪኳ የባህር በር ያጣችውም ከግንቦት 20 በኋላ ነው፡፡ የአንድነት ስሜት ጥያቄ ውስጥ ገብቶ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የአካባቢያዊ ስሜት የበለጠ ቦታ ያገኘበት ጊዜ የመጣው በግንቦት 20 ነው፡፡ የሀገሪቱ አንድነት ጥያቄ ውስጥ ገብቶ እስካሁን ዘልቋል፡፡ በየጊዜው አዳዲስ ቅራኔዎችና ግጭቶች እየተፈጠሩ ነው፡፡ በሂደትም ደግሞ ስልጣን በአንድ ፓርቲ የበላይነትና ሁለንተናዊ ቁጥጥር ውስጥ የወደቀበት ሁኔታ ነው የተፈጠረው፡፡ ከዚያ በኋላ ያሉት ነገሮች ሁሉ የህብረተሰቡ አመለካከቶች ነፀብራቅ ሳይሆን የአንድ ፓርቲ ነፀብራቅ ነው በአጠቃላይ የህዝቡን ህይወት እየወሰነ ያለው፡፡ በህገ መንግስቱ የሰፈሩና በጎ ናቸው ያልናቸው ነገሮች በተግባር ላይ የውሃ ሽታ የሆኑበት አጋጣሚም በሂደት ተፈጥሯል፡፡
 አንፃራዊ ሠላም መገኘቱ በሌላ ጎኑ በበጎ የሚታይ ነው፡፡ ይሄን ስል ጦርነት የለም ማለቴ አይደለም፡፡ ግንቦት 20 ማክበር ከጀመርን 25 ዓመት ሆኖናል፡፡
በዚህ መሃል በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው፣ በማህበረሰብ እድገት፣ በፍትህ … ዘርፍ ያሉ ጉዳዮች በሰፊው መገምገም አለባቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን የሚያሳስበው የሀገሪቱ አንድነት አደጋ ላይ መሆኑ ነው፡፡

==================================


“ድርጅታችን ለስርአቱ አደጋ የሆኑትን በተሃድሶ አጥርቷል”     (አቶ ሴኩቱሬ ጌታቸው፤ የቀድሞ ታጋይ)
በእነኚህ 25 ዓመታት ውስጥ በርካታ ፖለቲካዊ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ድሎች ተመዝግበዋል፡፡ እንደሚታወቀው የስርአት ለውጥ ነው የተደረገው፡፡ ያለፉት መንግስታት ህዝቦችን በተለያየ መልኩ የሚጨቁኑ ነበሩ፡፡ ያንን የጭቆና ስርአት የገረሰሰ ድል ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝቦች ለመጀመሪያ ጊዜ የሰብአዊና ዲሞክራሲዊ እድሎቻቸውን እንዲጠቀሙ፣ የራሳቸውን እድል በራሳቸው መወሰን የሚችሉበት፣ የግልም ሆነ የቡድን መብቶቻቸው እንዲከበር ያደረገ ነው፡፡
በዚያው መጠን ሀገራችን ከድህነት አረንቋ እንድትወጣ እያደረገ ያለ ድል ነው፡፡ በድህነትና በኋላ ቀርነት የምትታወቀውን ሀገራችንን በልማት እንድትታወቅ አድርጓል፡፡ የልማት አቅጣጫን በመቀየስ በሀገሪቱ ልማት የሚፋጠንበትና ህዝቡ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የሚያስችል መሰረት የተጣለበት ቀን ነው፡፡ በማህበራዊ መስኩም እንደዚሁ ዜጎች የሀገሪቱ አቅም በፈጠረው መጠን ከትምህርት፣ ከጤና፣ ተጠቃሚ የሚሆኑበት፣ ሰራተኞች የላባቸው ተጠቃሚ የሚሆኑበት፣ ጥቅማቸው እንዲከበር መሰረት የተጣለበት ቀን ነው፡ በጨቋኝ ስርአት ስር የነበረን ህዝብ ወደ ተሻለ ምዕራፍ ያሻገረ ቀን ነው፡፡
የሽግግር መንግስቱ ቻርተር የሀገሪቱን ብሄር ብሄረሰቦች ያሳተፈ ነበር፡፡ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የፕሬስ ነፃነት የታወጀበት እለት ነው፡፡ ኢኮኖሚውም ቢሆን ግብርና መር የሆነ ፖሊሲ ወጥቶ ሀገሪቱን ከውድቀት ታድጓል፡፡ ወደ እድገት ሊያመራ፣ የሠለጠነ የሰው ሃብት ሊያፈራ የሚችል ህገ መንግስት መሰረት የተጣለበት ቀን ነበር፡፡ በነዚህ አመታት አብዛኛውን ህዝብ ከድህነት ያወጣ፣ መሰረተ ሰፊ የሆነ የኢኮኖሚ እድገት መመዝገቡን ማንም የሚክደው አይደለም፡፡ በጋራ የፌደራል ስርአት ተፈጥሮ፣ ዜጎች በእኩልነት የሚኖሩበት ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ የቡድን መብት ተከብሯል፡፡
በዚያው ልክ ባለፉት 25 ዓመታት ያጋጠሙ ፈተናዎችም አሉ፡፡ የህዝቡ ተጠቃሚነት እየሰፋ በሄደ ቁጥር በጣም ብዙ ፍላጎቶች ይፈጠራሉ፡፡ ጠያቂና ሞጋች የሆነ ህብረተሰብ እየተፈጠረ ነው ያለው፡፡
የመንግስት መዋቅርን አለ አግባብ ለመጠቀም የተደረጉ ሙከራዎች ታይተዋል፡፡ ድርጅታችንም ለስርአቱ አደጋ የሆኑትን በተሃድሶ አጥርቷል፡፡ አሁንም በመልካም አስተዳደርና በኪራይ ሰብሳቢነት የሚታዩ ችግሮች የስርአቱ ፈተናዎች ናቸው፡፡ ኢኮኖሚው ባደገ ቁጥር በዚያው ልክ ፈተናዎቹ ውስብስብ እየሆኑ ነው የሄዱት፡፡ 25 ዓመቱን ሙሉ እንዲህ በቀላሉ አልዘለቅንም፡፡ እየታገልን ነው፡፡ ከዚህ በኋላም ትግላችን ቀጥሎ እቺን ሀገገር ወደ ተሻለ ምዕራፍ የማሸጋገር ስራ ይሰራል፡፡ ሀገራችን ከኋላቀርነት ወጥታ የእድገት ማማ ላይ የምትደርስበትን አቅጣጫ ስለያዘች ደስተኞች ነን፡፡ በቀጣይ ጉዟችን ፈተናዎችን እያለፍን የታፈረች፣ የተከበረችና ህዝቦቿ በነፃነት የሚኖሩባት ሀገር እንገነባለን፡፡ በዚህ መንፈስ ነው የምናከብረው፡፡

=================================

“ኢህአዴግ በ25 ዓመት ወደ ቅቡልነት አልተሸጋገረም”      (ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤የፍልስፍና ምሁር

የግንቦት 20 በአል 25ኛ ዓመት ሲታሰብ፣ ያለፉትን 25 ዓመታት በሶስት ዘርፎች መገምገም ያስፈልጋል፡፡ አንደኛ ከዲሞክራሲ አንጻር፣ በነዚህ 25 ዓመታት ውስጥ ስርአቱ የዲሞክራሲ ጅማሮ ላይ ነው ቢባልም ከጉልበት ወደ ቅቡልነት ሲሸጋገር አላየንም፡፡ አልተሸጋገርንም፡፡
ይልቁንም ወደ ፈላጭ ቆራጭነት (አውቶሪቶሪያን) የበለጠ ተሸጋግሯል፡፡ ሁለተኛ በፌደራሊዝም ዙሪያ ጅማሮው በጎ የሚባል ነበር፤ኋላ ላይ ግን ፌደራሊዝሙ ቀርቶ ወደ ብሄረሰብ ተኮር አሃዳዊነት (ethnic totalitarianism) ተሸጋግሯል፡፡
የተወሰኑ ክልሎች አሉ፤በአሃዳዊ ስርአት የሚተዳደሩ፡፡ ሶስተኛ ኢኮኖሚውን በተመለከተ ጅምሩ ጥሩ ነበር፤ኋላ ላይ የሙሰኛው ሲሳይ ሆነ እንጂ፡፡ ሙሰኛው እየበላው ነው ያለው፡፡ ሙሰኛው የደረሰበት ደረጃ ከፍተኛ ከመሆኑ የተነሳ ዝም ቢባልም  ጠንክረው እናሻሽል ቢሉም ስርአቱን የሚያፈርስ ሆኗል፡፡ በአጠቃላይ የፖለቲካ አዙሪት ውስጥ ገብቷል ብለን ልንደመድም እንችላለን፡፡ያሉትን ማህበረ-ፖለቲካዊ  ቅራኔዎች ከባድ የሚያደርጋቸው ከኋላ የወረሳቸው ሳይሆን ራሱ የፈጠራቸው ችግሮች ፈጠው ሲመጡ አደጋው የከፋ መሆኑ ነው፡፡ ኢህአዴግ እንደሚያወራው ቢሰራ ኖሮ ከየአቅጣጫው ጥያቄ ባልተነሳ ነበር፡፡   

አደጋዎቹ 100 ያህል ሰዎችን ለሞት ዳርገዋል
ጎርፉ ተጨማሪ በ10 ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ሊያፈናቅል ይችላል

   በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች በተከሰቱ የጎርፍና የመሬት መንሸራተት አደጋዎች ከ20 ሺህ በላይ ቤተሰቦች ከመኖሪያ ቤታቸው እንደተፈናቀሉ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ማስታወቁንና መንግስትም 100 ያህል ዜጎች በአደጋዎቹ ለሞት ተዳርገዋል ማለቱን አልጀዚራ ዘገበ፡፡
በአገሪቱ በመከሰት ላይ ያሉት የጎርፍ አደጋዎች ዜጎችን ከማፈናቀል ባለፈ በድርቅ ለተጎዱ አካባቢዎች እርዳታን በማከፋፈል እንቅስቃሴ ላይ እንቅፋት መፍጠሩን የጠቆመው ዘገባው፤ የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር የኢትዮጵያ ተወካይ ፖል ሀንድሊም የተፈጥሮ አደጋዎቹ በቀጣይ ሰብሎችንና እንስሳትን ከማውደም ባለፈ ዜጎችን ለከፋ ችግር ሊያጋልጡ ይችላሉ ማለታቸውን ገልጧል፡፡
የእርዳታ ድርጅቶችም የጎርፍ አደጋዎቹ ቀጣይ እንደሚሆኑና ሌሎች በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ሊያፈናቅል እንደሚችል ግምታቸውን መስጠታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የተፈጥሮ አደጋዎቹ የተከሰቱባቸው አንዳንዶቹ አካባቢዎች የድርቅ ተጎጂ መሆናቸውንና ዜጎችን ለተጨማሪ ችግር መዳረጋቸውን አስረድቷል፡፡