Administrator
Wednesday, 03 June 2026 14:23
በአርሲ ለደረሰው ጥቃት አቡነ ማትያስ ለመንግሥት ጠንከር ያለ ማሳሰቢያ አስተላለፉ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ በአርሲ ሀገረ ስብከት በኦርቶዶክሳውያንና በቅድስት ቤተክርስቲያን ላይ የደረሰውን አሰቃቂ ጥቃት ተከትሎ ጠንከር ያለ አባታዊ የኀዘንና የማሳሰቢያ መልእክት አስተላልፈዋል።
“የጸጥታ አካላትና ኃላፊዎች ከምንም በላይ በታሪክ የሚጠየቁት በሥልጣን ዘመናቸው ለዜጎች ደኅንነት በሚከፍሉት ዋጋ” መሆኑን ያስገነዘቡት ፓትርያርኩ፤ በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች የተፈጸመውን ድርጊት በተሰበረ ልብ እንደሰሙት ገልጸዋል።
መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተቃጠለበት፣ እንዲሁም የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተዘረፈበት በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖች ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት መሆኑን ጠቅሰዋል።
ፓትርያርኩ አክለውም፣ ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምእመናን በምታጽናናበት በዚህ ወቅት ራሷ በፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯም በላይ፣ በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ “እስከ መቼ?” የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን መፍጠሩን አስረድተዋል።
ቤተ ክርስቲያን ለሰላም፣ ለይቅርታና ለሰው ልጆች ክብር ሁል ጊዜ የምትቆም መሆኑን የገለጹት አቡነ ማትያስ፣ መላው ኢትዮጵያውያንና ምእመናን በወንድማማችነት መንፈስ ተጋግዘው የተፈናቀሉ ወገኖችን በቁሳቁስና በጸሎት እንዲደግፉ ጥሪ አቅርበዋል። በመጨረሻም ፈጣሪ ይህንን የኀዘን ሰዓት በምሕረቱ ያሳልፍ ዘንድ፣ በግፍ የሞቱትን ነፍሳት በመንግሥቱ እንዲቀበልና የተጎዱትንም በቸርነቱ እንዲያጽናና አባታዊ የጸሎት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 June 2026 14:06
"ቤተ-ክርስቲያን ትሙት፤ አባቶች ግን ይዳኑ፤ እንዴት ሆኖ?"
አንዳንዶች የኦርቶዶክሳዊያንን ሞት በሰሙ ቁጥር ጣታቸውን ቅዱስ ሲኖዶሱ ላይ ሲጠቁሙ አያለሁ፡፡ በእኔ ዕይታ እነዚህ ወገኖች ሁለት ስህተት እየሰሩ ነው፡፡ ቀዳሚው ቅዱስ ሲኖዶሱ ለምን ዝም ይላል ሲሉ ከዚህ ቀደም ሲታገል የኖረ ከማስመሰላቸው ይያያዛል፡፡
አቡነ ገብርኤል "የማውቀውን እናገራለሁ" በተሰኘ መጽሐፋቸው እንደነገሩን፤ የዘመናችን መራራ እውነት ኢትዮጵያዊያን ኦርቶዶክሶች እውነተኛ ሲኖዶስ የሌለን እጓለ ሙዑታን መሆናችን ነው፡፡
ስለሆነም ሲኖዶሱ ለሚጠብቃቸው በጎች ጥሩ እረኛ አልሆነም ፤ በጎቹ ሲገደሉ ለምን ዝም ይላል፤ የቤ/ክ ቴሌቭዥን ድምጹ ጠፋ ወዘተ ብለው የሚተቹ ሰዎችን ሳይ ቢያንስ እረኛ አለ ብለው በማመናቸው እገረማለሁ፡፡ የሟቾችንም ሀዘን በተለመደና የመነቸከ ወቀሳ ውስጥ እያቀለሉት እንዳይሆን እሰጋለሁ::
ዛሬ የዘመን ምጸት ሆነና ኦርቶዶክሳዊያን እየታገሉ ያሉት ከሚያሳድዷቸው ጋር ብቻ ሳይሆን ከራሳቸውም አባቶች ጋር ነው፡፡ ሩቅ ሳንሔድ ከወር በፊት የምስራቅ ወለጋ አገረ ስብከት የፃፈውን ደብዳቤ እናስታውስ፡፡ ይህ ደብዳቤ በጨዋ ቋንቋ የአገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሩፋኤል የተረከቡትን በወርቅ የተለበጠ ጥንታዊ ጽላት ሰውረዋል አልያም ሰርቀዋል ሲል ይከሳል፡፡ የሚያስደነግጠው ተራው ምዕመንና አባቶች ቦታ መቀያየራችን ብቻ አይመስልም፡፡ ትልቁ ዜና፤ ጥያቄው የደረሰው ቅዱስ ሲኖዶስ የሌባ እናት ልጇን አታማም ብሎ ነገሩን አለባብሶ መያዙ ነው፡፡
እንደ መውጫ
የቤተ-ክርስቲያን አስተምሮ መልከ ብዙ ነው፡፡ ቀነኗና ሕግጋቷም ጥልቅ ነው፡፡ ይህም ሆኖ አባቶችን አትናገሩ እያሉ ሕግ እያጣቀሱ ሊያስተምሩ የሚሞክሩ ሰዎች አይገቡኝም፡፡ ወዳጄ፤ አባቶች ከቤተ-ክርስቲያን በላይ አይደሉም፡፡ ቤተ-ክርስቲያን የምዕመናን ሕብረት ናት፡፡ ቤተ-ክርስቲያን ዐቢይ መልኳ ሰው ነው፡፡ ሰው ሲታረድ እየሞተች ያለችው ቤተ-ክርስቲያን ናት፡፡ አንዳንድ የቤተ-ክሕነት ጥቅም ተጋሪዎች ግን ቤተ-ክርስቲያን ትሙት አባቶች ግን ይዳኑ ይሉናል፡፡ እንዴት ሆኖ?
ሌሎችማ ጭራሽ በከፋው ጊዜ አንገታቸውን እንደ ሰጎን ቀብረው ግርግሩ ሲያልፍ አባቶች ላይ አፍ የሚከፍት ትውልድ መጣ ብለው ይዘባበቱብናል፡፡ እውነታችሁን ነው?
በነገራችን ላይ ከመቶ በላይ ሰው አጠመቅን የሚሉን የመስቀል አደባባይ ሐዋርያትና ተቋማት አዕላፍት ሲሞቱ የት እየተደበቁ ነው ሲያልፍ ከፊት የሚመጡት? ደግሞስ ሕንፃ ቤተ-ክርስትያን ለማሰራት በየቦታው ወንበር ዘርግተው ራሳቸው ቀድመው በሀብት የሰሩትስ የትኛው ጎሬ ውስጥ ተወሽቀው ነው ሰሞኑን የማይታዩት? የደጀሰላም በር ዘግተው ለሰው ነፍስ ድኅነት እንሰራለን የሚሉት የጉዞ ማኅበራትስ ምን ዋጣቸው?
በማእረግ ጌታቸው-
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 June 2026 14:06
ያለ ማዘዣ አንቲባዮቲክስ መሸጥ ሙሉ በሙሉ ተከለከለ
የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለሥልጣን ከግንቦት ወር 2018 ዓ.ም ጀምሮ ተፈጻሚ የሚሆን አዲስ የመድኃኒት አጠቃቀም ቁጥጥር መመሪያ (ቁጥር 1138/2026) አውጥቷል። ይህ መመሪያ ፋርማሲዎች ያለ ሐኪም ትክክለኛ ማዘዣ ማንኛውንም የፀረ-ተህዋሲያን (አንቲባዮቲክስ) እና በሕግ የተገደቡ መድኃኒቶችን ለደንበኞች እንዳይሸጡ በጥብቅ ይከለክላል። በተጨማሪም ሆስፒታሎች የክትትል ኮሚቴ እንዲያቋቁሙ የሚያስገድድ ሲሆን፣ ሐኪሞች በአንድ ወረቀት ላይ ከሦስት መድኃኒት በላይ እንዳያዙና የአንቲባዮቲክስ ማዘዣዎችም ከ7 ቀናት በላይ እንዳያገለግሉ ገደብ ጥሏል።
ይህ አሠራር ዜጎች ያለ ሐኪም ትዕዛዝ መድኃኒት በመውሰድ ለከፍተኛ የመድኃኒት መላመድ (Drug Resistance) አደጋ እንዳይጋለጡና ትክክለኛውን ሕክምና በትክክለኛው መጠን እንዲያገኙ ለማስቻል የተዘረጋ ነው። ፋርማሲስቶች መድኃኒት ከመስጠታቸው በፊት ጥራቱንና የአገልግሎት ማጠናቀቂያ ቀኑን የመፈተሽ እንዲሁም ለታካሚው በቂ የምክር አገልግሎት የመስጠት ግዴታ አለባቸው። የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሄራን ገርባ ይህንን አዲስ ሕግ በሚጥሱ ባለሙያዎችና ተቋማት ላይ እስከ ሥራ ፈቃድ መሰረዝ የሚደርስ ጥብቅ ቅጣት እንደሚጣል አስጠንቅቀዋል።
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 June 2026 14:02
ኢትዮጵያዊቷ ሳይንቲስት የሮያል ሶሳይቲ ባልደረባ ሆነው ተመረጡ
በዓለም አቀፍ የሳይንስ ዘርፍ በተመዘገበ ታሪካዊ ስኬት፣ ታዋቂዋ ኢትዮጵያዊት የዕፅዋት ፓቶሎጂ (ሞለኪውላር ፕላንት ፓቶሎጂ) ሳይንቲስት ፕሮፌሰር ሰገነት ቀለሙ፣ ስመ-ጥር በሆነው የሮያል ሶሳይቲ (The Royal Society) የክብር ባልደረባ ሆነው ተመርጠዋል።
በኢትዮጵያ ፍኖተ ሰላም ከተማ የተወለዱት ዶክተር ሰገነት፣ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የማስተርስ ዲግሪያቸውን ከሞንታና ስቴት ዩኒቨርሲቲ፣ እንዲሁም የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በሞለኪውላር ፕላንት ፓቶሎጂ ከካንሳስ ስቴት ዩኒቨርሲቲ ያገኙ ሲሆን፣ የድህረ-ዶክትሬት ምርምራቸውን ደግሞ በኮርኔል ዩኒቨርሲቲ አከናውነዋል። በግብርና ባዮ-ደህንነት እና በዕፅዋትና ረቂቅ ተሕዋስያን ግንኙነት ዙሪያ ባደረጉት እጅግ የላቀ ምርምር የሚታወቁት ፕሮፌሰሯ፣ ዓለም አቀፉን የነፍሳት ሥነ-ሕይወትና ሥነ-ምህዳር ምርምር ማዕከል (icipe) በመሪነት ያገለገሉ የመጀመሪያዋ ሴት በመሆን ታሪክ ሰርተዋል።
ሳይንቲስቷ በሮያል ሶሳይቲ መመረጣቸው በዓለም ላይ ካሉ እጅግ ልሂቃን የሳይንስ አዕምሮዎች ተርታ የሚያሰልፋቸው ሲሆን፣ ለዓለም አቀፍ የምግብ ዋስትና ያበረከቱትን የሕይወት ዘመን አስተዋጽኦ የሚያስመሰክር ነው። ከሦስት አሥርት ዓመታት በላይ በዘለቀው ስኬታማ የሥራ ዘመናቸው፣ የፕሮፌሰር ሰገነት አብዮታዊ የምርምር ሥራዎች በአፍሪካ፣ በእስያ፣ በላቲን አሜሪካና በሰሜን አሜሪካ የግብርና ልማት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አሳድረዋል። በicipe ያለውን የአመራር ሚና ከመረከባቸው በፊት፣ በኮሎምቢያ በሚገኘው ዓለም አቀፍ የሐሩር ክልል ግብርና ማዕከል (CIAT) ውስጥ በከፍተኛ ሳይንቲስትነት ለዓመታት ያገለገሉ ሲሆን፣ በዚያም አነስተኛ አርሶ አደሮችን የሚፈትኑ የሰብል ቀውሶችን በቁርጠኝነት ተከላክለዋል።
ይህ አርቆ አሳቢ የሳይንስ አመራራቸው የሉሪያል-ዩኔስኮ “ሴቶች በሳይንስ” (L'Oréal-UNESCO Award for Women in Science) ሽልማትን ጨምሮ በርካታ እውቅናዎችንና ሽልማቶችን አስገኝቶላቸዋል።
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 June 2026 14:02
የአውሮፓ ኅብረትና ኤምባሲዎች ስለ 7ኛው የኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ መግለጫ ሰጡ
በኢትዮጵያ የአውሮጳ ኅብረት ልዑክ እና በአዲስ አበባ የሚገኙ 25 የኅብረቱ አባል አገራት ኤምባሲዎች (የጀርመን እና ፈረንሳይን ጨምሮ) እንዲሁም የአውሮፓ ኅብረት አባል ያልሆኑት ካናዳ፣ ኖርዌይ እና ስዊትዘርላንድ በጋራ በመሆን ስለ ሰባተኛው የኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ መግለጫ አውጥተዋል። በግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. የተካሄደውን ምርጫ በበጎ እንደሚቀበሉ የገለጹት ዲፕሎማሲያዊ ተልዕኮዎቹ፤ ለሂደቱ ስኬት አስተዋጽዖ ላበረከቱት ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ ለምርጫ ሠራተኞች፣ ለፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ለዕጩዎች እና ለሲቪል ማኅበራት ተዋናዮች ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል። በተጨማሪም የአፍሪካ ኅብረት እና የኢጋድ የምርጫ ታዛቢዎችን ሚና በማድነቅ የዘገባዎቻቸውን ውጤት በጉጉት እንደሚጠብቁ አስታውቀዋል።
ይህ የጋራ መግለጫ ምርጫው በተካሄደ በሁለተኛው ቀን የወጣ ሲሆን፣ በትናንታው ዕለት በተለያዩ ምክንያቶች ምርጫ ያልተካሔደባቸው የምርጫ ክልሎች በሙሉ ድምጽ የመስጠት “ዕድል ይሰጣቸዋል” የሚል ከፍተኛ ተስፋ እንዳላቸውም አመልክተዋል። ዲፕሎማቶቹ በጋራ ባስተላለፉት መልዕክት ሁሉም ዜጎች በምርጫው የመሳተፍ መብታቸው ሊከበር እንደሚገባ በማሳሰብ፣ ምርጫ ባልተካሄዱባቸው አካባቢዎች ሂደቱ እንዲቀጥል ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 02 June 2026 00:00
አሜሪካ በአፍሪካ የሚገኙ የቪዛ አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ከ50 ወደ 20 ልትቀንስ ነው
የአሜሪካ መንግስት በአፍሪካ አህጉር ውስጥ የሚገኙትን የቪዛ ማረጋገጫ ማዕከላቱን ቁጥር ከ50 ወደ 20 ክልላዊ ማዕከላት ዝቅ ለማድረግ ማቀዱን አስታውቋል። እነዚህ የተመረጡት 20 ማዕከላት በ19 የአፍሪካ ሀገራት ውስጥ የሚሰራጩ ሲሆን፣ ውሳኔው በአህጉሪቱ በሚገኙ በርካታ የቪዛ አመልካቾች ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል።
በዚህ አዲስ አሰራር መሰረት እንደ ጆሃንስበርግ፣ ሌጎስ፣ ናይሮቢና አክራ ያሉ ዋና ዋና ከተሞች ለአሜሪካ ቪዛ ሂደት ቁልፍ ማዕከላት ሆነው ያገለግላሉ። በዚህም ምክንያት በአካባቢያቸው የነበረውን የቪዛ አገልግሎት የሚያጡ ሀገራት ዜጎች፣ ለቪዛ ቃለ-መጠይቅና ለቆንስላ ጉዳዮች ወደነዚህ ወደተመረጡት ዋና ዋና ማዕከላት ረጅም ርቀት ተጉዘው ለመሄድ ይገደዳሉ።
ይህንን ውሳኔ የሚደግፉ ወገኖች አዲሱ አሰራር የአገልግሎት ቅልጥፍናን እንደሚጨምርና አላስፈላጊ ወጪዎችን እንደሚቀንስ እየተናገሩ ይገኛሉ። በአንጻሩ ግን በርካታ ተቺዎች ውሳኔው ለአመልካቾች ረጅም የጥበቃ ጊዜን ከመፍጠሩም በላይ፣ ከፍተኛ የሆነ ተጨማሪ የጉዞና የሆቴል ወጪዎችን በትከሻቸው ላይ የሚጭን አድሎአዊ አሰራር ነው ሲሉ በብርቱ እየተቃወሙት ነው።
Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 02 June 2026 00:00
የቀድሞዋ የኡጋንዳ ምክትል ፕሬዚዳንት ለኢትዮጵያውያን ያስተላለፉት መልዕክት
የዘንድሮውን የ7ኛ ዙር አገራዊ ምርጫ ለመታዘብ የሚያስችለኝን ዕድል አግኝቼ ነበር። እናም በግልና የተለያዩ ተቋማትን ወክለን የመጣን የአገር ውስጥ ታዛቢ ቡድን አባላት ምርጫውን ለመታዘብ ከመጡ የአፍሪካ ኅብረት እና የኢጋድ የታዛቢ ቡድን አባላት ጋር በስካይ ላይት ሆቴል የትውውቅና ሰፋ ያለ የጋራ ውይይት አድርገን ነበር።
በዚህ ውይይት ላይም የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪና የቀድሞ የኡጋንዳ የቀድሞው ምክትል ፕሬዚደንት የነበሩት ዶ/ር ዋንዲራ ካዚብዌ በምክር መልኩ ለወጣቶች ያነሱት ሐሳብ ቀልቤን ገዛው። እናም ከእኚህ ጉምቱ ፖለቲከኛ አፍሪካዊ እናት ከሐሳባቸው ጥቂት ሰበዞችን ለመምዘዝ ወደድኹ።
በአገራቸው ኡጋንዳ ፖለቲካ ውስጥ የሴቶችን/የእናቶችን የፖለቲካ ተሳትፎ ትርጉም ባለው መንገድ በመቀየር ጉልህ አሻራ ያኖሩት የህክምና ሳይንስን ከሥነ-መንግሥት ትምህርት ጋር ያጣጣሙ እኚህ አፍሪካዊ ምሁር እናት በውይይታችን መካከል እንዲህ አሉን።
"When women lead, even water climbs uphill."
"ሴቶች ሲመሩ ውኃ ሳይቀር እንኳን ሽቅብ ይፈሳል፤" የሚል አፍሪካዊ አባባል አለ።
መቼም ለዚህ አባባል እናንት ኢትዮጵያውያን ሕያው ምስክሮች ናችሁ። ከኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ሳባ፣ የዐድዋውን ጦርነት በሴትነት ብልሃት ከመሩት እቴጌ ጣይቱ ድረስ የአገራችሁ የፖለቲካ ታሪክ በሴቶች ጉልህ ተሳትፎና አሻራ የደመቀ ነው። በእውነት በእነዚህ ጀግኖች እናቶቻችሁ ታሪክ ልትኮሩ፤ ልትደነቁ ይገባችኋል።
ዶ/ር ካዚብዌ ቁጭት በቀላቀለ ስሜት ያነሱትን ሌላኛው የሐሳባቸውን ሰበዝ ለዚህች አጭር ማስታወሻ መደምደሚያ ይሆነኝ ዘንድ መረጥኩት።
እኛ አፍሪካውያን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን እንደ ሸቀጥ ዕቃ ሙሉ በሙሉ ከምዕራቡ ዓለም ለማስገባት የምናደርገውን ልፋት ቆም ብለን መፈተሽ ይገባናል። ከሌሎች የምንቀበለውን ያህል እኛ አፍሪካውያን ለተቀረው ዓለም ልንሰጠው የምንችላቸው በርካታ ነገሮች አሉን።
አፍሪካ ለሺህ ዓመታት የቆየ የራሷ የሆነ ግዙፍ ታሪክ፤ ገናና ሥልጣኔ፤ በዘመናት ተፈትኖ ያለፈ የዳበረ ባህላዊ የፖለቲካ ሥርዓት ያላት አህጉር ናት። እናንት ኢትዮጵያውያን ደግሞ በዚህ የአኅጉራችን የአፍሪካ የሺህ ዘመናት ታሪክና ባህል ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ ትወስዳላችሁ።
ከአክሱም ገናና ሥልጣኔ የቅኝ ገዢዎችንና የተስፋፊዎችን ቅስም እስካንኮታኮተው የዐድዋ ድል ድረስ አኩሪ ታሪክ ያላችሁ ታላቅ ሕዝብ ናችሁ። አብዛኛው የታሪካችሁ ምዕራፍ ሲገለጽም- የአንድነትን፤ የኅብረትን ኃይል ቀድሞ የተረዳችሁ ጠቢባን ሕዝቦች መሆናችሁን ነው የሚመስክረው። እናም ዛሬ ልዩነታችሁን በማጥበብ አንድነታችሁን አጠናከሩ፤ ኅብረታችሁን አጎልብቱ። አንድነት ኃይል ነው!!
ኢትዮጵያ በመከፋፈል ሳይሆን በአንድነት የደመቀ፤ በጦርነት ሳይሆን በሰላም ያሸበረቀ፤ በጥላቻ ሳይሆን በፍቅር የተዋበ አፍሪካዊ ተምሳሌትነቷንና እናትነቷን ያስመሰከረች አገር ሆና እንድትቀጥል ነው ምኞታችን፤ ተስፋችንና ጸሎታችን።
እግዚአብሔር አፍሪካን ይባርክ፤ አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!!
ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ አበው፤ ጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር ዐብይ አሕመድ ወደ ሥልጣን በመጡ ማግሥት- ኢትዮጵያውያን እናቶች ይጸልዩልኛል፤ የእናቶቼ ጸሎታቸውና ምርቃታቸው ያግዘኛል፤ ጉልበት ይሆነኛል። የሚል ቃልን አብዝተን ከአንደበታቸው አንሰማ ነበር። ዛሬስ...?!
ታላቁ መጽሐፍ፤ "የእናት ምርቃት ቤትን ያጸናል፤" እንዲል በእናቶቻችን ምርቃትና ጸሎት የሁላችን ቤት የሆነች ኢትዮጵያ፤ አፍሪካ የአንድነት መሠረቷ ጸንቶና ሰላሟ ተጠብቆ በአንድነት ጸንታ ትኖር ዘንድ በመመኘት ልሰናበት።
ሰላም!!
በተረፈ ወርቁ (ዲ/ን)
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 June 2026 13:58
የኢትዮጵያዋ “አሶሳ” መርከብ የሆርሙዝ ሰርጥን በሰላም ተሻገረች
በመካከለኛው ምስራቅ ባለው ወቅታዊ ቀውስ ምክንያት ከፍተኛ የጸጥታ ስጋት በነበረበት የሆርሙዝ ሰርጥ አካባቢ የነበረችው የኢትዮጵያ ባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ንብረት የሆነችው “አሶሳ” መርከብ ሰርጡን በሰላም መሻገሯ ተሰምቷል።
መርከቧ ከሰርጡ በቅርብ ርቀት ላይ ወደምትገኘው ኮርፋካን ወደብ በመድረስ፣ ለሀገራችን እጅግ ወሳኝ የሆኑ የሕክምና እና የንግድ ጭነቶችን በተሳካ ሁኔታ በመጫን ጉዞዋን አጠናቃ በሰላም ወደ ሀገሯ ተመልሳለች።
Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 02 June 2026 00:00
አርሰናል ዋንጫ ማሸነፉን ተከትሎ የሙዚቃና የእግር ኳስ ፌስቲቫል በአዲስ አበባ ሊካሄድ ነው
የአርሰናልን የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ ድል ለመዘከር "WE CHAMPIONS 2026" የተሰኘ ታሪካዊ የእግር ኳስና የመዝናኛ ፌስቲቫል የፊታችን ቅዳሜ ግንቦት 29 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስታዲየም ሊካሄድ ነው። በቫርደስ ኢንተርቴይመንት አዘጋጅነትና በአዋሽ ባንክ (አዋሽብር ፕሮ) ዋና ስፖንሰርነት የሚከናወነው ይህ ዝግጅት፣ ከ30 ሺህ በላይ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን፣ ዓለም አቀፍ ሌጀንዶችንና የሚዲያ ባለሙያዎችን በአንድ ላይ የሚያሰባስብ ታላቅ መድረክ ነው። ዝግጅቱ የሀገራችንን ባህል፣ እንግዳ ተቀባይነትና የመዝናኛ ኢንዱስትሪ ለዓለም ለማስተዋወቅ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥርም ተገልጿል።
በዚህ ደማቅ መርሃ ግብር ላይ የቀድሞው የአርሰናል እና የኮትዲቯር ብሔራዊ ቡድን ኮከብ ተጫዋች ኤማኑኤል ኢቡዌ በልዩ እንግድነት የሚገኝ ሲሆን፣ ታዋቂው የለንደኑ "Arsenal Fan TV" (AFTV) ተወካዮችም በቦታው ይገኛሉ። ዝግጅቱ በአጠቃላይ በAFTV የዩቲዩብ ቻናልና በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በቀጥታ የሚተላለፍ በመሆኑ የሀገራችንን ገጽታ ለመገንባት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ተብሏል።
በዕለቱ መድረኩን የሚያደምቁ ከ10 በላይ ታዋቂና ወጣት ኢትዮጵያውያን ድምፃውያን የተሰለፉ ሲሆን፤ ታደለ ሮባ፣ ልጅ ሚካኤል (ፋፍ)፣ ሳሚ ዳን፣ አስጌ ዴንዳሾ፣ ራሄል ጌቱ፣ ሮቤል ሚዲቅሳ፣ ዮ ማሪዮስ፣ ሚክ ዋን፣ አማኑኤል የማነ፣ አዲስ ሙላት እንዲሁም እውቁ የአፍሮቢትስ ሙዚቃ ተጫዋች ፍራንኪዬ ዲ ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ። ለፌስቲቫሉ መግቢያ የሚሆን ትኬትን በአዋሽ ብር ፕሮ፣ በአዋሽ ባንክ ቅርንጫፎች ወይም በስታዲየም በሚገኙ ጊዜያዊ የትኬት ጣቢያዎች መግዛት እንደሚቻል አዘጋጆቹ አስታውቀዋል።
Published in
ስፖርት አድማስ
Tagged under

