Administrator

Administrator

• ከመቶ ሺሕ በላይ ተመልካቾች እንደሚጎበኙት ይጠበቃል
• ኦርቶዶክሳዊ ክውን ጥበባት ልዩ ገጽታዎቹ ይኾናሉ ተብሏል
• ለአጠቃላይ ዝግጅቱ ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ይደረጋል

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእመናን፥ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዓለም አቀፋዊነት፣ ነባራዊ ሁኔታና ተግዳሮቶች ተረድተው የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ያስችላል የተባለ ልዩ ዐውደ ርእይ በመጪው መጋቢት ወር አጋማሽ እንደሚያካሒድ ማኅበረ ቅዱሳን አስታወቀ፡፡
ማኅበሩ፣ ከመጋቢት 15 - 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የሚያካሒደው ዐውደ ርእይ፣ ለአምስተኛ ጊዜ የሚያዘጋጀው ሲሆን፣ “ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን፡ አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ” የሚል መርሕ እንዳለው የዝግጅቱ ዐቢይ ኮሚቴ ገልጧል፡፡
በዘንድሮው ዐውደ ርእይ፥ ቤተ ክርስቲያን በአደረጃጀቷ የካህናትና የምእመናን ኅብረት መሆኗን በማስገንዘብ፣ ሕዝበ ክርስቲያኑ ድርሻቸውን ዐውቀው ሓላፊነታቸውን የሚወጡበትን መንገድ የሚያስገነዝቡ፤ የኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያንን ዓለም አቀፋዊነትና አንድነት የሚያስረዱ፣ በአራት ሰፋፊ አርእስተ ጉዳዮች የተከፈሉ ትዕይንቶች ዘመኑ በደረሰበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች በመታገዝ እንደሚቀርቡ ተጠቅሷል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ማንነት፤ በዓለም፣ በአፍሪቃ እና በኢትዮጵያ ያላትን ሐዋርያዊ ተልእኮ፤ ወቅታዊ ተግዳሮቶቿንና መፍትሔውን በመለየት ምን መደረግ እንዳለበትና ከምእመናን ምን እንደሚጠበቅ በስፋትና በዝርዝር ከተካተቱበት ዐውደ ርእይ ጎን ለጎን፣ ጭብጦቹ በጥናታዊ ጽሑፍ የሚዳሰሱበት ዐውደ ጉባኤ እንደሚካሔድም ታውቋል፡፡
ዐውደ ርእዩ ለእይታ ክፍት ኾኖ በሚቆይባቸው ሰባት ቀናት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ የጥንታዊ ሥርዐተ ትምህርት የመማር ማስተማር ሒደት በደቀ መዛሙርቱና በመምህራኑ እንቅስቃሴ በተግባር የሚታይበት “የአብነት ት/ቤቶች መንደር” የሚገነባ ሲሆን በየዕለቱ ከ10 ሰዓት በኋላም ያሬዳዊ ዜማና ቅኔ ከትውፊታዊ ዕሴቶቻቸው ጋር የሚቀርቡበት መሰናዶ እንደሚኖር ተገልጧል፡፡ ኮሚቴው፣ “ኦርቶዶክሳዊ ክውን ጥበባት”/performance arts/ ሲል የገለጻቸው መሰናዶዎቹ፥ የጥበባቱን ሕያውነት፣ ገቢራዊነትና አሳታፊነት በማስገንዘብ ተመልካቾችን ለዕውቀት በማነሣሣት ረገድ ጉልሕ ድርሻ| ይኖራቸዋል፤ ብሏል፡፡
ለዐውደ ርእዩና ተጓዳኝ መሰናዶዎች አስፈላጊው ፈቃድና የድጋፍ ደብዳቤ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ ጽ/ቤት ተገኝቶ ከኤግዚቢሽን ማእከሉ ጋር ስምምነት መፈጸሙን ዐቢይ ኮሚቴው ገልጦ፤ ከአንድ ሺሕ አባላቱ በዝግጅትና በቴክኒክ ምድቦች ተከፋፍለው ቅድመ ዝግጅታቸውን በማከናወን ላይ እንዳሉና በሒደትም የሰንበት ት/ቤቶችንና ሌሎች መንፈሳውያን ማኅበራትን በአጋርነት በመያዝ እንደሚቀጥል ተጠቅሷል፡፡
ለአጠቃላይ ዝግጅቱ ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ  ወጪ የተያዘለት ሲሆን፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ተቋማት ጨምሮ የተለያዩ አጋር አካላት ምርቶቻቸውንና አገልግሎታቸውን ለግብይት በማቅረብ እንደሚያስተዋውቁበት ተመልክቷል፡፡
ከመክፈቻው ዕለት ጀምሮ ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 12፡00 ለእይታ ክፍት የሚሆነው ዐውደ ርእዩ፣ ከመቶ ሺሕ በላይ ተመልካቾች ይጎበኙታል ተብሎ እንደሚጠበቅ የተገለጸ ሲሆን የመግቢያ ቲኬት ሽያጭም ካለፈው ታኅሣሥ ጀምሮ በመካሔድ ላይ ነው፡፡ ዓላማውን የሚደግፉ አካላት አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርጉ የጠየቀው ዐቢይ ኮሚቴው፣ ሕዝበ ክርስቲያኑም ወዳጅ ዘመዶችን ወደ ዐውደ ርእዩ በመጋበዝ ስለ ቤተ ክርስቲያን እንዲያውቅና እንዲያሳውቀው ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱና በምእመኑ መካከል ያለውን መስተጋብር ለማዳበር፣ ማኅበሩ ከ1989 ዓ.ም. ጀምሮ ከዘረጋቸውና በስፋት ከተገበራቸው ሰፊ የማስተማሪያና የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብሮች መካከል ዐውደ ርእይ አንዱ መሆኑን ያስረዳው ዐቢይ ኮሚቴው፤ ያለፉት አራት ዙር ዝግጅቶች፥ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ፣ ታሪክ፣ የቅርስ ባለቤትነትና ባለአደራነት፤ በአካባቢ ጥበቃ፣ በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች ለሀገሪቱ ዕድገት ላበረከተችው አስተዋፅኦ ሰፊ ሽፋን የሰጡ እንደነበሩ አስታውሷል፡፡

አሜሪካ፣ ደ/ ኮርያና ቻይና የሰ/ ኮርያን ዕቅድ አውግዘዋል
    ሰሜን ኮርያ ለምርምር ተግባር የሚውል ያለችውን ሳተላይት ወደ ጠፈር ለማምጠቅ መዘጋጀቷን ባለፈው ማክሰኞ በይፋ ማስታወቋ በአካባቢው አገራት ውጥረት የፈጠረ ሲሆን ጃፓን፤ ሰሜን ኮርያ ይህንን እቅዷን እንድታቋርጥ መክራ፣ ካልሆነ ግን ሮኬቱን መትታ ለመጣል የጦር ሃይሏን ዝግጁ እንዳደረገች ማስታወቋን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡
የጃፓን መከላከያ ሚኒስትር ጄኔራል ናካታኒ፤ የሰሜን ኮርያ ሚሳየል የአየር ክልሏን ጥሶ የሚገባ ከሆነ፣ የባህር ሃይሏ በሮኬቱ ላይ ጥቃት ለመፈጸም መዘጋጀቱን ያስታወቁ ሲሆን፣ በጃፓን ባህር ላይ የጦር መርከቦች መሰማራታቸውና የባላስቲክ ሚሳኤል መከላከያዋም በተጠንቀቅ ላይ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
ሰሜን ኮርያ ለምርምር ተግባር አውለዋለሁ ያለችውን ሮኬት በመጪዎቹ ሳምንታት ወደ ጠፈር እንደምትልክ ለተመድ ማስታወቋን ተከትሎ፣ ጃፓን፣ አሜሪካ፣ ቻይናና ደቡብ ኮርያ የአገሪቱን እቅድ የረጅም ርቀት ተወንጫፊ ሚሳየል ለመሞከር የታቀደ ስውር ደባ ነው በማለት እንደተቃወሙት ተነግሯል፡፡
የደቡብ ኮርያ መንግስት ሰሜን ኮርያ ዕቅዷን ተግባራዊ የምታደርግ ከሆነ ትልቅ ዋጋ ትከፍላለች ያለ ሲሆን፣ ቻይናም ጉዳዩ እንደሚያሳስባት በመግለጽ ሰሜን ኮርያ ከድርጊቷ እንድትታቀብ ጥሪ አቅርባለች፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሰሜን ኮርያ ላይ ጠንከር ያለ እርምጃ እንዲወስድ ጠይቋል፡፡
አገራቱ ሰሜን ኮርያን ከድርጊቷ እንድትታቀብ ቢያስጠነቅቁም፣ የአገሪቱ መንግስት ግን ሮኬት በማምጠቅ የጠፈር ምርምር ማድረግ ሉአላዊ መብቷ እንደሆነ በመግለጽ ነቀፋውን አጣጥላዋለች ተብሏል፡፡

   ሆላንድ በጸረ-ሰላም ድሮኖች ላይ ንስሮችን ልታዘምት ነው
    እስራኤል ለስለላ ተግባር አሰማርታዋለች በሚል ተጠርጥሮ ከአስር ቀናት በፊት በሊባኖስ በቁጥጥር ስር የዋለው አሞራ፣ ከቀናት ቆይታ በኋላ ከእስር ተፈትቶ ወደ አገሩ መመለሱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
1.9 ሜትር የሚረዝም ክንፍ ያለው ይህ የእስራኤል አሞራ፤ ከሊባኖስ ጋር የሚያዋስነውን ድንበር ጥሶ ሲገባ በአካባቢው ነዋሪዎች መያዙን ያስታወሰው ዘገባው፣ ነዋሪዎቹ ከአሞራው ላባ ላይ የታሰረ የክትትል መሳሪያ ተገጥሞ ማየታቸው ለጥርጣሬያቸው መነሻ እንደሆናቸው ጠቁሟል፡፡
የእስራኤል ባለስልጣናት አሞራው ከእስር ሊፈታ የቻለው፣ የስለላ ተልዕኮ እንደሌለው በሚመለከተው አካል በመረጋገጡና በሊባኖስ የሚገኙ የተመድ የሰላም አስከባሪዎች በጉዳዩ ጣልቃ ገብተው ባደረጉት ግልግል ነው ማለታቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
የእስራኤል የአእዋፍት መስሪያ ቤት ሃላፊዎች፤ አሞራው ባለፈው አመት ከስፔን እንደመጣና ከአንድ ወር በፊትም በእስራኤል ቁጥጥር ሥር  በሚገኙት የጎላን ኮረብቶች ውስጥ በሚገኝ ጋምላ የተባለ የተፈጥሮ ክልል  ውስጥ እንዲኖር መለቀቁን ተናግረዋል፡፡
እስራኤል አሞሮችን ለስለላ ተግባር ታሰማራለች በሚል በተደጋጋሚ ስትጠረጠር እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡በሌላ በኩል ደግሞ፣ በሆላንድ እየተበራከቱ የመጡት ህጋዊነት የሌላቸው ድሮን የተባሉ ሰው አልባ በራሪዎች ለዜጎች ደህንነት ስጋት መፍጠራቸው ያሳሰበው የአገሪቱ ፖሊስ፣ መሰል ድሮኖችን በሰለጠኑ ንስሮችና ሌሎች አእዋፍት በቁጥጥር ስር ለማዋል ማቀዱን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ፍቃድ የሌላቸውና እውቀት በሌላቸው ግለሰቦች የሚንቀሳቀሱ መሰል ድሮኖች ከተፈቀደላቸው የበረራ ክልል በማለፍ ወደ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያዎችና ባለስልጣናት የታደሙባቸው ህዝባዊ ስነስርዓቶች ወደሚካሄዱባቸው ስፍራዎች ዘልቀው መብረራቸው ያሳሰበው የአገሪቱ ፖሊስ ነው እቅዱን ያወጣው፡፡  
የአገሪቱ ፖሊስና የጸረ-ሽብር ተቋም በጋራ በዘየዱት በዚህ፣ በቴክኖሎጂ የታገዘን የደህንነት ስጋት በተፈጥሮ የመመከት  መላ፣ ንስሮችና አእዋፋት ሌሎች ታዳኞችን በሚያጠቁበት ዘዴ የደህንነት ስጋት የሆኑ ድሮኖችን በመሞጭለፍ ከአካባቢው የማራቅ ተልዕኮን እንዲወጡ ለማድረግ ታስቧል፡፡
የንስሮቹ አሰልጣኝ የሆኑት የአምስተርዳም ፖሊስ ባልደረባ፣ አእዋፋቱ ድሮኖችን በቁጥጥር ስር በማዋል ከአደጋ ክልል ውጭ ለማድረግ በሚሞክሩበት ወቅት፣ ጉዳት እንዳይደርስባቸው ከሳይንቲስቶች ጋር በመተባበር እየሰሩ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡ ለዚህ የጸረ ድሮን ዘመቻ ከሰለጠኑት ንስሮች አንዱ፣ ከሰሞኑ በተደረገ ሙከራ አንድን በመብረር ላይ ያለ ድሮን ተከታትሎ በጥፍሮቹ በመያዝ ወደ መሬት እንዳወረደው የሮይተርስ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የተለያዩ የአለማችን አገራት አይሲስን ለመደምሰስ በኢራቅና በሶርያ የሚፈጽሙት የአየር ጥቃት ያሰጋቸው በርካታ የሽብር ቡድኑ ከፍተኛ የጦር መሪዎች ከጥቃቱ ሸሽተው ወደ ሊቢያ እየገቡ ነው ሲል ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ሊቢያ ለሽብር ቡድኑ አመራሮች ምቹ አገር በመሆኗ፣ በርካታ የተለያዩ አገራት ዜግነት ያላቸው የአይሲስ ከፍተኛ የጦር አበጋዞች ሲርት ወደ ተባለችውና በቡድኑ ቁጥጥር ስር ወደምትገኘው የአገሪቱ ከተማ እየገቡ እንደሚገኙ የሊቢያ የስለላ ተቋም ሃላፊ ኢስማኤል ሹክሪ መናገራቸው ተገልጿል፡፡
ከተማዋ ካለፈው አመት ጀምሮ በአይሲስ ቁጥጥር ስር እንደምትገኝ ያስታወሰው ዘገባው፣ ከቅርብ ወራት ወዲህ ከኢራቅና ከሶርያ ሸሽተው ወደ ሲርት የሚገቡ የሽብር ቡድኑ ከፍተኛ የጦር መሪዎች ቁጥር እየጨመረ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
በሽሽት ወደ ከተማዋ ከገቡት የቡድኑ አባላት አብዛኞቹ የቱኒዝያ፣ የግብጽና፣ የሱዳን ዜግነት ያላቸው ናቸው ያለው ዘገባው፣ አልጀሪያውያን፣ ኢራቃውያንና ሶርያውያንም እንደሚገኙባቸው የተነገረ ሲሆን፣ በተለይም ለቡድኑ የረጂም ጊዜ የሽብር ተልዕኮ ስኬታማነት ጉልህ ሚና የሚጫወቱ የቡድኑ አባላት ወደ ሊቢያ መሸሻቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጿል፡፡

 ማንዴላ በ2.9 ሚ. ዶላር፣ ኢምቤኪ በ1.1 ሚ. ዶላር የግል ቤታቸውን ሰርተዋል
     የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ አግባብ ባልሆነ መንገድ ከመንግስት ካዝና አውጥተው የግል መኖሪያ ቤታቸውን አሳድሰውበታል ከተባለው 23 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ የተወሰነውን ገንዘብ ለመመለስ መስማማታቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ገንዘቡን ለግል ጥቅማቸው በማዋላቸው ሰፊ ውግዘት ሲደርስባቸው የቆዩት ፕሬዚዳንቱ፤ከትናንት በስቲያ የተወሰነውን ገንዘብ ለመመለስ መስማማታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የገንዘቡን መጠን የሚወስኑት የአገሪቱ ኦዲት ቢሮ ሃላፊና የፋይናንስ ሚኒስትሩ እንደሚሆኑ አመልክቷል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ከመንግስት ካዝና ያወጡትን ገንዘብ፣  ካንድላ ተብላ በምትጠራው የአገሪቱ የገጠር መንደር ውስጥ የሚገኘውን ቤታቸውን ለማሳደስ ማዋላቸው በአገሪቱ ዋነኛ የፖለቲካ ውዝግብ ፈጥሮ መቆየቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ፕሬዚዳንቱ የተወሰነውን ገንዘብ ለመመለስ ቢፈቅዱም፣  የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና የመብት ተሟጋቾች ግን በጉዳዩ ዙሪያ የሙስና ምርመራ እንዲደረግ ያቀረቡትን ጥያቄ እንደሚገፉበት ማስታወቃቸውን ገልጧል፡፡
የተወሰነው ገንዘብ በሰፊው የፕሬዚዳንቱ ግቢ ውስጥ አምፊ ቲያትር፣ ትልቅ የመዋኛ ገንዳና ግዙፍ የከብቶች ማድለቢያ ለመስራት መዋሉ የተነገረ ሲሆን፣ የአገሪቱ ህገ መንግስታዊ ፍርድ ቤትም በቀጣዩ ሳምንት ጉዳዩን በተመለከተ የመጀመሪያውን ችሎት እንደሚሰይም ተዘግቧል፡፡
ቀደምት የአገሪቱ ፕሬዚዳንቶችም ለግል ቤቶቻቸው ከፍተኛ የመንግስት ገንዘብ ወጪ ሲያደርጉ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ዴክለርክ 22 ሺህ ዶላር፣ ማንዴላ 2.9 ሚሊዮን ዶላር፣ ምቤኪ 1.1 ሚሊዮን ዶላር ገንዘብ በማውጣት ቤታቸውን መስራታቸውን አክሎ ገልጧል፡፡

 በዓለም ላይ ነፃነቷን ለማግኘት ላለፉት 60 ዓመታት የታገለችና አሁንም ድረስ ነፃነቷን ያልተጎናፀፈች ብቸኛ አገር ፍልስጤም ናት ያሉት የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ሪያድ ማልኪ፤ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ተገቢውን ትኩረት አልሰጠንም ሲሉ ወቀሱ፡፡
ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚያደርጋቸው አንዳንድ ጥረቶች ቢኖሩም አጥጋቢ አይደሉም ብለዋል፤ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፡፡
“አሁንም ድረስ ልጆቻችን በሰላም ወጥተው በሰላም መግባት አልቻሉም፤ በእስራኤል ወታደሮች የሚገደሉ ህፃናት ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል” ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ዛሬም ከ60 ዓመት በኋላ ፍልስጤም ሰላምን እንደናፈቀች ናት ሲሉ ሰሞኑን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡ ከ11 ዓመት ዕድሜዬ ጀምሮ በፍልስጤም የሰላም ረ)ቡ እንደነበር አስታውሳለሁ ያሉት ዶ/ር ማልኪ፤ “አሁንም በ60 ዓመቴ ለነፃነት እየተዋጋን ነው፤ ወደፊትም ልጆቼ ነፃነትን ያያሉ ብዬ ዋስትና መስጠት አልቻልኩም፤ ይህ በጣም አሳዛኝ ነው” በማለት ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለስቃያችን ምላሽ ሊሰጠን ይገባል ብለዋል፡፡
እኛ ትግላችንን እንቀጥላለን፤ እንዴት እጅ እንደሚሰጥ አናውቅም ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ እኔ ተስፋ ብቆርጥ እንኳን የ13 ዓመት ልጅ በወታደር ስትገደል እያዩ ልጆቼ ተስፋ አይቆርጡም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡
እስራኤልን አንድ ሃያል አገር ስለምትደግፋት ብቻ ከህግ በላይ ልትሆን አትችልም፤ ለዚህም ነው የዓለም አቀፉን ማህበረሰብ ድጋፍ የምንጠይቀው፤ ብለዋል ዶ/ር ሪያድ ማልኪ፡፡

ባለፉት ስድስት ወራት የ91 ፕሮጀክቶችን የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰረዙን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን

አስታወቀ፡፡
የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ጌታሁን ነጋሽ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ፕሮጀክቶቹ

በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለመስራት ፈቃድ ተሰጥቷቸው የነበሩ ሲሆን ፈቃዳቸው የተሰረዘው ፈቃድ ካወጡ በኋላ

በመጥፋትና በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ወደ ሥራ ለመግባት ባለመቻላቸው ነው፡፡
የፈቃድ መሰረዙን ተከትሎም መሬት የሰጠው አካል መሬቱን፣ ገንዘብ የሰጠው አካል ገንዘቡን፣ እንዲያስመልስ

እንዲሁም መሳሪያዎችን በነፃ ለማስገባት በሂደት ላይ ያሉም እንዲከለከሉ ኮሚሽኑ ለሚመለከታቸው አካላት ሁሉ

ማሳወቁን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል፡፡
ባለፈው ዓመትም እንዲሁ በማኑፋክቸሪንግና በግብርና ዘርፎች ለመሰማራት ፈቃድ ተሰጥቷቸው በወቅቱ ወደ ስራ

ያልገቡ 357 ፕሮጀክቶች ፈቃዳቸው መሰረዙን አቶ ጌታሁን አስታውሰዋል።
ኮሚሽኑ ባለፈው ሩብ ዓመት 107 አዲስ፣ 23 የማስፋፊያ፣ በድምሩ 130 የኢንቨስትመንት ፈቃዶችን በማኑፋክቸሪንግ፣

በግብርናና በአገልግሎት ዘርፎች የሰጠ ሲሆን ከነዚህ ውስጥም 29ኙ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች መሆናቸውን አቶ

ጌታሁን ገልፀዋል፡፡

  አንድ በእድሜያቸው በግምት ወደ 60/ አመት የሆናቸው አባት ከሀያ አመት በፊት የሚከተለውን ምስክርነት

ሰጥተዋል፡፡
“...እኔ የኢትዮጵያ ሱማሌ ስሆን የምኖረው በጅግጅጋ ነው፡፡ ሴትን ልጅ መግረዝ በሕይወትዋ ላይ እንደመፍረድ

ይቆጠራል የሚል አቋም አለኝ፡፡ ከባለቤ የወለድኩዋቸው ሰባት ልጆች ሲሆኑ አራት ሴትና ሶስት ወንዶች ናቸው።

ለሶስቱ ሴቶች ባለመድረሴ መቸውንም የሚቆጨኝ ነገር ነው፡፡ ሳላስጥላቸው ልክ እንደእናታቸው ተገርዘዋል።

አንዱዋን ልጅ ግን አስጥዬ ወደዘመዶቼ አዲስ አበባ ስለላክሁዋት እሱዋ     አልተገረዘችም፡፡ ድናልኛለች፡፡
“በሴቶች ላይ የሚፈጸም ግርዛት ጀንደር ወይንም ስርአተ ጾታን መሰረት ያደረገ በሴቶች ላይ የሚፈጸም በደል ነው፡፡

ይህ ድርጊት የሴቶችን ሰብአዊ መብት የሚጋፋ መሆኑንም አለም የተስማማበት ጉዳይ ነው። ይህንንም መረጃ

በአለምአቀፍ ደረጃ ያሰራጨው የአለም የጤና ድርጅት ሲሆን አገራትም ያመኑበትና የተስማሙበት በመሆኑ ድርጊቱ

እንዲቆም ሲነገር አመታትን አስቆጥሮአል፡፡
በሴት ልጅ ላይ የሚፈጸም ግርዛት ሲባል በአይነት የተለያየ ሲሆን በብልት አካባቢ የስሜት ሰጪውን ክፍል ሳይነካ

ከሚፈጸመው ጀምሮ ጭርሱንም ሴቷን ስሜት የለሽ እስከሚያደርገው የግርዘት አይነት ድረስ በሶስት ደረጃ የተከፈለ

ነው፡፡ እንደ የአለም የጤና ድርጅት ዘገባ በግምት ከ100 እስከ 140 ሚሊዮን ልጃገረዶችና ሴቶች በአለምአቀፍ ደረጃ

ግርዛት የተፈጸመባቸው ሲሆን ወደ 3/ ሚሊዮን የሚጠጉ ልጃገረዶች  በየአመት በተለይም በአፍሪካ ድርጊቱ ግርዘቱ

ይፈጸምባቸዋል፡፡
በአፍሪካ የሚተገበረውን የሴት ልጅ ግርዛት ለመገመት እንደተቻለው ወደ 98/ በመቶ የሚሆነው በሶማሊያ የሚፈጸም

ሲሆን በንጽጽሩ ደግሞ በኡጋዳ 1/ በመቶ ብቻ ይፈጸማል፡፡የቅርብ ጊዜ ጥናት እንደሚያሳየው ወደ 91.5 ሚሊዮን

የሚሆኑ እድሜያቸው ከ9/ አመት በላይ የሆኑ በአፍሪካ ያሉ ልጃገረዶች  በግርዛት ምክንያት ከሚደርሱ የተለያዩ

ችግሮች ጋር የሚኖሩ መሆኑ ተረጋግጦአል። በኢትዮያ በተካሄደውሃመ ዲሞግራፒክ ኤንድ ኼልዝ ሰርቬይ ወደ 74/

በመቶ የሚሆኑ ልጃገረዶችና ሴቶች በተለያዩ መስተዳድሮች ከሶስቱ አንዱ አይነት ግርዘት እንደተካሄደባቸው ያሳያል፡፡

የሴት ልጅ ግርዛት በቅርብእና በርቀት ወይንም በወደፊት የጤና ሁኔታ ላይ የተለያዩ ችግሮችን እንደሚያስከትል ግልጽ

ነው፡፡ እንደየአለም ጤና ድርጅት መረጃ ግርዘት የተከናወነባቸው ሴቶች በተለይም ልጅ በመውለድ ጊዜ ለተለያዩ

ችግሮች እንደሚጋለጡ ነው፡፡ ይህ ችግርም እንደግርዘቱም አይነት ደረጃው እንደሚለያይ ተጠቁሞአል፡፡
በቅርብ ጊዜ ማለትም በ2013/ በኖርዌይ በተደረገ ጥናት መመልከት እንደሚቻለው ሴቶች በተለይም በሶስተኛ ደረጃ

ያለውን እና በከፋ ሁኔታ የሚፈጸመውን ግርዘት በመገረዛቸው ምክንያት በወሊድ ጊዜ የማህጸን መተርተር፣ በመሳሪያ

ድጋፍ መውለድ በመጎተት፣ የማህጸን መድማት እና አስከፊ በሆነ ሁኔታ ልጅን መገላገል ሊያጋጥማቸው እንደሚችል

ተገልጾአል፡፡
በኢትዮጵያ በሶስተኛ ደረጃ የሚተገበረው እና በሶማሊያ ክልል የሚፈጸመው የግርዛት አይነት እናቶች በወሊድ ጊዜ

በከፍተኛ ሁኔታ እንዲሰቃዩ እና በተራዘመ ምጥ ምክንያትም ልጆቻቸውን እንዲያጡ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል

ግልጽ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ዛሬም በሶማሊያ ክልል በሶስተኛው አይነት ግርዛት ምክንያት ብዙ ሴቶች የሚሰቃዩ ሲሆን ዲሴምበር

2015/ ይፋ በሆነው ጥናትም እንደተጠቆመው ወደ 97/ በመቶ የሚሆኑ ሴቶች የችግሩ ሰለባ ሆነዋል። በእርግጥ

በኢትዮጵያ በሶማሊያ ክልል ችግሩ በስፋት መኖሩ ቢታወቅም ከዚህ ጋር ተያይዞ በመውለድ ጊዜ ያጋጠሙ ችግሮች

በግልጽ ተመዝግበው የተቀመጡበት አሰራር ባለመኖሩ ሁኔታውን ለመረዳት አስቸጋሪ መሆኑን ጥናቱ ጠቁሞአል፡፡

በዚህም መሰረት በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ በተለይም በካራማራ ሆስፒታል እንደውጭው አቆጣጠር ከጃንዋሪ 2015/

እስከ ማርች 2015/ ድረስ የተደረገ ጥናት ወደሆስፒታሉ  ለመውለድ የሚመጡ ሴቶችን ከግርዛት ጋር በተያያዘ በምጥና

ወሊድ ወቅት ምን ችግር አንደሚከሰትባቸው ለይቶ ለማወቅ እንዲረዳ በዶ/ር ሙታሲም አብዱላሂ እና ዶ/ር ወንድሙ

ጉዱ ጥናት ተደርጎአል፡፡
ኦርጋናይዜሽን ፎር ዘ ድቭሎፐምነንት ፎር ውመን ኤንደ ችልድረን ኢትዮጵያ በሚባል በጎ አድራጊ ድርጅት

አስተባባሪነት እና ሌሎች የሚመለከታቸው እና ድጋፍ ሰጪ አካላት ትብብር የተሰራው ጥናት ይፋ በተደረገበት ወቅት

ጥናት አድራጊዎቹ ስለጥናቱ ለአምዱ አዘጋጅ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ለመሆኑ ዛሬም ግርዛት አለ? ተብለው ለተጠየቁት ዶ/ር ሙታሲም የሚከተለውን መልስ ነበር የሰጡት፡፡
“...ግርዛት በኢትዮያ ውስጥ ዛሬም አለ፡፡ ግርዛት መኖሩን በመገናኛ ብዙሀንም በተለያየ ጊዜ ሲነገር የሚሰማ ሲሆን ሃመ

በተደረገው ጥናትም  74/ በመቶ የሚሆኑ ሴቶች የተገረዙ መሆኑ ተረጋግጦአል፡፡ የግርዛት አይነቱ በሶስት ደረጃ

የተከፈለ ሲሆን 3ተኛ የሚባለው ግርዛት እጅግ አስከፊና ሴቶችን የሚጎዳ ነው፡፡ ይህ አይነቱ ግርዘት በአገር አቀፍ ደረጃ

ትንሽ ፐርሰንት ሲሆን በሶማሌ ክልል ግን ከ80/ በመቶ በላይ ሶስተኛውን አይነት ግርዛት የተገረዙ ሴቶች አሉ፡፡

በእርግጥ እኛ ያጠናነው ጥናት ዛሬ የተገረዙትን የሚመለከት ሳይሆን የዛሬ ሀያ እና ከዚያም በላይ በሆኑ አመታት

የተገረዙትንና በወሊድ ወቅት ምን ችግር እንደሚያጋጥማቸው በካራማራ ሆስፒታል ተገኝተን የተመለከትንበት ነው፡፡

በምጥ ሰአት እንደሚቸገሩ እና ልጁ በተገቢው ጊዜ የመውጣት ችግር ፣ካር ለማስገባት ችግር እንደሚያጋጥም፣

የመድማት ሁኔታ እና የመሳሰሉት እንደሚኖሩ በጥናቱ አረጋግጠናል።”
ሌላው ጥናት ያካሄዱት ዶ/ር ወንድሙ ጉዱ ናቸው። እሳቸውም አንደሚሉት፡-
“...ግርዛት በተለያዩ ጥናቶች እንደቀረበው 90/በመቶ እና ከዚያ በላይ የሚፈጸም ሲሆን አስከፊውን አይነት ግርዛት

የተገረዙት ሴቶች ደግሞ ከ84-85 በመቶ የሚሆኑት ናቸው፡፡” ብለዋል፡፡
ጥናቱ በተካሄደበት ወቅት ግርዛት የተፈጸመባቸውንና ያልተገረዙ ሴቶችን ሁኔታም ለማነጻጸር ተሞክሮአል። በወሊድ

ጊዜ የሚያጋጥሙ ችግሮች በሙሉ ማለት ይቻላል... በተደጋጋሚ የሚያጋጥሙት በተገረዙ ሴቶች ላይ መሆኑ ሲረጋገጥ

ያልተገረዙት ላይ ግን እጅግ በተራራቀ እና አልፎ አልፎ በሚባል ሁኔታ የሚታይ ነው።
ዶ/ር ሙታሲም  እንደገለጹትም ...
“...በሱማሌ ክልል ያሉ ሴቶች ግርዛቱ ትክክል እንዳልሆነ እና በተለይም በወሊድ ወቅት አደጋ እንደሚያስትል

ያምናሉ፡፡ ነገር ግን ድርጊቱን ለማስቀረት በቀላሉ የማይቻል በመሆኑ አሁንም አይደረግም ለማለት አይቻልም፡፡

ግርዛቱን ከሚፈጽሙት ግለሰቦች ጀምሮ አስፈጻሚዎቹ ቤተሰቦች በባህል በኢኮኖሚና በማህበራዊ ትስስር ምክንያት

በቀላሉ ሊያስቀሩት እንዳልቻሉ ለማየት ተችሎአል፡፡”
ጥናቱ በተካሄደበት ወቅት ግርዛት የተፈጸመባቸውንና ያልተገረዙ ሴቶችን ሁኔታም ለማነጻጸር ተሞክሮአል። በወሊድ

ጊዜ የሚያጋጥሙ ችግሮች በሙሉ ማለት ይቻላል... በተደጋጋሚ የሚያጋጥሙት በተገረዙ ሴቶች ላይ መሆኑ ሲረጋገጥ

ያልተገረዙት ላይ ግን እጅግ በተራራቀ እና አልፎ አልፎ በሚባል ሁኔታ የሚታይ ነው።
ዶ/ር ወንድሙ ከላይ የተሰጠውን አስተያየት በማጠናከር እንዴት ማስቀረት ይቻላል? ለሚለው፡-
“...በእርግጥ ግርዛቱ በኢትዮጵያ በተለያዩ መስተዳድሮች መፈጸሙ አልቀረም ቢባልም አይነቱ ግን በሶማሌ እና

ተመሳሳይ አካባቢዎች እንደሚፈጸመው 3ተኛው አይነት ማለትም አስከፊው አይደለም፡፡ ባጠቃላይ ግን የትኛውንም

አይነት በየትኛውም ቦታ በሴቶች ላይ ግርዛቱ እንዳ ይፈጸም ለማድረግ ሲፈለግ ብዙ ነገሮችን መነካካት ያስፈልጋል፡፡

ለምሳሌም፡-
ሴቶች እንዳይገረዙ የህግ ከለላ መስጠት፣ ፖሊሲ መንደፍ፣
የሴቶችን የወሳኝነት አቅም ማሳደግ፣
የሴት ልጅ ግርዛት እንዲኖር የሚያስችሉ ምክንያቶች ምን እንደሆኑ በጥናት አረጋግጦ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ፣
ወንዶች በጉዳዩ እንዲሳተፉ ማድረግና የተገረዘች ላግባ አላግብ የሚለውን ሀሳብ ለመወሰን የሚያስችላቸውን አቅም

እንዲያጎለብቱ እና ግርዘትን እንዲያወግዙ ማድረግ፣
የሀይማኖት መሪዎች፣ የቀበሌ፣ የጎሳ አስተዳዳሪዎች የመሳሰሉ ኃላፊነት ቦታ የተቀመጡ ሰዎችም የጉዳዩን አስከፊነት

ተገንዝበው ድርጊቱን ለማስቆም እንዲተባበሩ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
ባጠቃላይም በተናጠል የሚሰራ ስራ ውጤታማ ስለማያደርግ በተቀናጀ መልኩ የሚመለከተው ሁሉ ተሳትፎ የየበኩሉን

እርምጃ በመውሰድ የሴት ልጅ ግርዛት እንዲቆም ማድረግ ይቻላል፡፡ “ ብለዋል ዶ/ር ወንደሙ ጉዱ፡፡
ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ግርዛት በሶስት ደረጃ ተከፍሎአል፡፡ በኢትዮጵያ ያለውን የግርዛት አይነት ስንመለከት

በሰሜኑ እና በአንዳንድ የሐገሪቱ ክፍል ሲፈጸም የኖረው  አንዱ ሲሆን ሁለተኛውና ሶስተኛው በተለያዩ አካባቢዎች

እንደሶማሌ አፋር ከምባታ አካባቢ ሲፈጸሙ የነበሩ ናቸው፡፡ ሲፈጸሙ /ምየሚለውን አባባል የተጠቀምነው እነዚህ

ድርጊቶች በአሁኑ ወቅት ምን ያህል አይተገበሩም ለሚለው ማረጋገጨ ለጊዜው እጃችን ላይ ስለሌለ ነው፡፡

     - ፈውስም ሆነ ክትባት የለውም፤ እንደ ኢቦላ የከፋ ጥፋት ሊያደርስ ይችላል ተብሏል
                  - በ21 አገራት ተከስቶ፣ 1.5 ሚ ሰዎችን ተጠቂ አድርጓል
       ነፍሰጡር ሴቶችን በማጥቃት የጭንቅላት መጠናቸው አነስተኛ የሆኑና ውስን የአእምሮ እድገት ያላቸው ህጻናት እንዲወለዱ ምክንያት የሚሆነው “ዚካ” የተሰኘ ቫይረስ ወደተለያዩ አገራት በመሰራጨት ላይ መሆኑንና አስቸኳይ እርምጃ ካልተወሰደ እንደ ኢቦላ ቫይረስ በወረርሽኝ መልክ ተከስቶ የከፋ ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል ተዘገበ።
ዴይሊ ሜይል ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ ካለፈው ግንቦት ወር ወዲህ በ21 የካረቢያን፣ የሰሜን አሜሪካና የደቡብ አሜሪካ አገራት የተስፋፋው “ዚካ” ቫይረስ ክፉኛ ካጠቃቸው አገራት መካከል ብራዚል በቀዳሚነት የምትጠቀስ ሲሆን፣ በአገሪቱ ካለፈው ጥቅምት ወር አንስቶ በቫይረሱ ሳቢያ 4ሺህ ያህል የጭንቅላት መጠናቸው አነስተኛ የሆኑ ህጻናት መወለዳቸው ተረጋግጧል፡፡
ቫይረሱን በምትሸከም ትንኝ አማካይነት ወደ ታማሚው የሚገባው “ዚካ” ቫይረስ፣ ምንም አይነት ፈዋሽ መድሃኒትም ሆነ ክትባት እንደሌለው የጠቆመው ዘገባው፣ አሜሪካና ሌሎች አገራት ቫይረሱ በስፋት ተሰራጭቶ የከፋ ጥፋት ከማድረሱ በፊት ክትባቱን ለማግኘት በአፋጣኝ ርብርብ እንዲደረግ ጥሪ ቢያቀርቡም፣ ክትባቱን የማግኘቱ ጥረት አስር አመት ያህል ጊዜ ሊወስድ ይችላል መባሉን ገልጿል፡፡ የአሜሪካ ሳይንቲስቶች የአለም የጤና ድርጅት ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት የአስቸኳይ ጊዜ የህክምና ባለሙያዎች ኮሚቴ በማቋቋም አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስድ የጠየቁ ሲሆን፣ በቫይረሱ ክፉኛ የተጠቃችው ብራዚል ፕሬዚዳንት ዲልማ ሩሴፍም የደቡብ አሜሪካ አገራት ቫይረሱን ለመግታት እጅ ለእጅ ተያይዘው እንዲነሱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የመካከለኛውና የደቡብ አሜሪካ አገራት፣ ሴቶች በቫይረሱ ሊጠቁ ስለሚችሉ በቅርብ ጊዜ ውስጥ የማርገዝ ዕቅድ ካላቸው እንዲያራዝሙት መምከራቸው የተጠቆመ ሲሆን፣ የተለያዩ አገራት ነፍሰጡር ሴቶችም ወደ ደቡብ አሜሪካ አገራት እንዳይሄዱ ማስጠንቀቂያ መሰጠቱ ተነግሯል፡፡
እ.ኤ.አ በ1947 ለመጀመሪያ ጊዜ በኡጋንዳ እንደተገኘ የተነገረለት “ዚካ” ቫይረስ፣ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በአንዳንድ የአፍሪካና የእስያ አገራት ተወስኖ የቆየ ቢሆንም፣ ባለፈው ግንቦት ወር ላይ በብራዚል መከሰቱንና ወደሌሎች የላቲን አሜሪካ አገራት መስፋፋቱንና ከዚያ ጊዜ ወዲህም በአለም ዙሪያ 1.5 ሚሊዮን ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን አይቢ ታይምስ ዘግቧል፡፡
የአውሮፓ የበሽታ መከላከልና ቁጥጥር ማዕከል በበኩሉ፤ “ዚካ” ቫይረስ በቱሪስቶች አማካይነት ወደ አውሮፓ መግባቱንና በቅርቡ በስዊድን አንድ ታማሚ መገኘቱን፣ ሰሞኑንም አንድ የዴንማርክ፣ 6 የእንግሊዝና 2 የጀርመን ዜግነት ያላቸው ሴቶች እንደተገኙ ጠቁሞ ሁለት ጀርመናውያን ሴቶችም በቫይረሱ መያዛቸውን ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡

   ሶማሊያና ሰሜን ኮርያ በሙስና አለምን ይመራሉ
    ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው አለማቀፍ ተቋም በአፍሪካ አህጉር ያለው የሙስና ችግር መሻሻል አለማሳየቱንና ሙስና በአህጉሪቱ በሚገኙ አርባ አገራት ውስጥ እጅግ የከፋ ችግር መሆኑን ሰሞኑን ባወጣው አመታዊ ሪፖርት አስታወቀ፡፡
  በአህጉሪቱ የሙስና ችግር ስር እየሰደደ መምጣቱን እንዳስታወቀ የዘገበው ቢቢሲ፣ ሶማሊያ በአፍሪካም ብቻ ሳይሆን በመላው አለም የከፋ የሙስና ችግር ያለባት ቀዳሚዋ አገር ናት መባሉንና ሰሜን ኮርያም በሙስና ከሶማሊያ ጋር የዓለማችን ቀዳሚ ሙሰኛ አገር  መሆኗን ጠቁሟል፡፡
በአህጉሪቱ ሙስና በከፍተኛ ሁኔታ የተስፋፋባቸው አብዛኞቹ አገራት በግጭት ውስጥ ያሉ፣ ፖሊስና ፍርድ ቤትን የመሳሰሉ ተቋማት ደካማ የሆኑባቸውና ገለልተኛ ሚዲያ የሌሉባቸው ናቸው ያለው ተቋሙ፤  ከአፍሪካ አገራት በሙስና ከፍተኛው መሻሻል የታየው በሴኔጋል መሆኑንና፣ አገሪቱ የተለያዩ የጸረ ሙስና ህጎችን ተግባራዊ ማድረጓ በሙስናው ላይ መሻሻል ማሳየቱን አስታውቋል፡፡
በአለማችን ከሶማሊያና ሰሜን ኮርያ በመቀጠል በሙስና መስፋፋት ከሁለተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙት አፍጋኒስታን፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ አንጎላ፣ ሊቢያ፣ ቬንዙዌላ፣ ጊኒ ቢሳውና ሃይቲ ናቸው ተብሏል፡፡አነስተኛ ሙስና አለባቸው ከተባሉት የአለማችን አገራት መካከልም ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ደረጃ የያዙት ዴንማርክ፣ ፊንላንድ፣ ስዊድን፣ ኒውዚላንድና ኒዘርላንድስ እንደሆኑ የተቋሙ አመታዊ የሙስና ሪፖርት አስታውቋል፡፡