Administrator

Administrator

በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በሀገር አቀፍ ደረጃ የመጀመሪያው ነው የተባለለት የአንጎል የደም ስር ክሊፒንግ በተሳካ ሁኔታ ተጠናቋል።

ይህ ህክምና የተደረገላት ታካሚ ከአዲስ አበባ በጥቂት ርቀት ላይ የምትኖር ሲሆን፤ ድንገት በዕለት ሥራዋ ላይ ሳለች ከፍተኛ የራስ ህመም ይሰማት እንደጀመረና ከዚያም እራስዋን ስታ መውደቋን ታሪኳ ያስረዳል።

ህክምና ተቋም እንደደረሰችም በተደረገላት ምርመራ በአንጎልዋ ውስጥ የደም ቧንቧ መፈንዳት ምክንያት የደም መፍሰስ እንደተከሰተና የፈነዳው የደም ቧንቧ በቀዶ ጥገና ህክምና ባስቸኳይ ካልተስተካከለ ለሞት የሚዳርጋት መሆኑን ይነገራታል።

በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በኒውሮሰርጀሪ ዲፓርትመንት አስተባባሪነትና የአንጎል ደም ቧንቧ ቀዶ ጥገና ህክምና ከፍተኛ ልምድ ባካበቱት ዶ/ር ቶማስ ቦጋለ የሚመራ የህክምና ቡድን፣ ታህሳስ 10 ቀን 2016 ዓ.ም ሶስት ሰዓት ከግማሽ በወሰደ የቀዶ ጥገና፣ የተስተካከለ የአንጎል የደም ዝውውር እንዲኖራት ማድረግ ተችሏል።

ታካሚዋ በተደረገላት ህክምና እጅጉን እንደተደሰተች ገልጻ፥ ባሁኑ ሰዓት ከህመምዋ አገግማ ወደ ቤትዋ ተመልሳለች፡፡  ይህ ህክምና ከዚህ ቀደም በሀገር ውስጥ  በመንግስት ሆስፒታሎች ሲሰራ የአሁኑ  የመጀመሪያው ነው ተብሏል።

በጉብኝቱ ወቅት የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ኢንጅነር) ስለኢንስቲትዩቱ ሥራዎች ገለጻ አድርገዋል፡፡ በውይይቱ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂን ለማልማት በኢንስቲትዩቱ የሚሰሩ የምርምር ተግባራት ለሀገር የሚበጁ መሆናቸውን እንደተገነዘቡ ተመራማሪዉ ተናግረዋል።
ሳይንቲስቱ የሰዉሰራሽ አስተዉሎት ቴክኖሎጂ ለሰዉ ልጅ የሚያበረክተውን ሚና እንዲሁም በጠፈር ምርምር የቴክኖሎጂዉ አበርክቶ ጉልህ መሆኑን ገልፀዋል።
የሰዉሰራሽ አስተዉሎት ቴክኖሎጂ ቸግር ፈቺ የምርምር ዘርፍ በመሆኑ ወጣቶቸና በውጪ የሚኖሩ የዲያስፖራ አባላት በንቃት አንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።
ብርሃኑ ቡልቻ (ዶ/ር) በጨረቃ ላይ ዉሃ መኖር አለመኖሩን የሚመረምር መሳሪያ የፈጠሩ የናሳ ተመራማሪ ናቸዉ።

 ዘጠኝ ሞት ጥንቅቅ ተደርጎ የተሰራ ስነልቦናዊ ድራማ ነው። ይዞ የተነሳው ዓለማቀፋዊ ጭብጥ፣ የገጸ ባህርይ አሳሳልና የተዋንያኑ ብቃት እንዲሁም የሲኒማው የላቀ ደረጃ ተወዳጅ አድርገውታል። በዚህ ዳሰሳበፊልሙ የተነሳው ስነ-ልቦናዊ ጭብጥ ላይ በማተኮር ስለ ሞት፣ ስለ ሀዘን፣ እውነታን በመካድ ራስን ስለ መደለልና ስለ ለቅሶ ባህላችን በወፍ በረር እንመለከታለን።
          ዶ/ር ዮናስ ላቀው፤ የአእምሮ ህክምና ስፔሻሊስትና የአማኑኤል ሆስፒታል ታሪኮች መጽሐፍ ደራሲ


       ሞት-ታላቁ ምስጢር
በዘጠኝ ሞት ላይ የተነሳው  ጭብጥ  የሁሉንም ሰው ልብ የሚያንኳኳ፣ ሁሉም ሰው ላይ የሚደርስ ነገር ስለሆነ “ይሄ ጉዳይ አይመለከተኝም” የሚል ሰው አይኖርም።  ሁላችንም የምንወዳቸውን ሰዎች በአንድ ወይም በሌላ ጊዜ ማጣታችን አይቀርም።  በጅምላ ዋናውን ከመሞታችን በፊት ደግሞ ትንንሽ የችርቻሮ ሞቶች ሁልጊዜ ዙሪያችን አሉ። ከሚወዱት ሰው መለየት፣ ከሀገር መሰደድ፣ ጤና የሚነሱ ህመሞች፣ ተቀብረው የቀሩ እምቅ ችሎታዎች… ወዘተ። ዘጠኝ ሞት እነዚህን ሁላችንም አዳፍነን ይዘናቸው የምንዘራቸውን ጥያቄዎች የሚቆሰቁስ ፊልም ነው።  በነባሪያዊ የስነ-ልቦና ህክምና (ጽንሰ ሀሳብ) መሰረት፤ ሰዎች ሁሉ አራት መሰረታዊ ጥያቄዎች ጭንቀት ይፈጥሩብናል። እነዚህም ብቸኝነት፣  ነፃነት፣ የህይወት ትርጉምና ሞት ናቸው። ሞት ቢያስቡት ቢያስቡት የሚገባ ነገር አይደለም። እንደውም አተኩረው ካዩት እንደ ቀትር ጸሀይ ማጥበርበርና ግራ ማጋባት  ይጀምራል።
በአንድ መንደር የሚኖር ልጅ እናቱ ትሞትና ለብዙ ሳምንታት አምርሮ ያለቅስ ነበር። ቤተሰቦቹና ጎረቤቶቹ ሊያጽናኑት ሞክረው አልሆን ሲላቸው ለሃይማኖት አባት ይናገራሉ። እሳቸውም ልጁን፤ “ሀዘን ማብዛት ደግ አይደለም። ፈጣሪም አይወደውም” ይሉና  ይገስጹታል። ልጁም ተግሳጹን ፈርቶ ማልቀሱን ይተዋል። ከተወሰነ ጊዜ በኋላ የእሳቸው እናት ሞቱና እሳቸው አልቅሰው አልቅሰው አላቆም አሉ። ልጁ ሄዶ፤ “ምነው ሀዘን ማብዛት ደግ አይደለም ብለውኝ አልነበር?” ሲላቸው፤ “የኔ ልዩ ነው” አሉት ይባላል። ስለሞት ሲወራ ብንሰማም በኛ  ከደረሰብን ግን ልዩ ነው። ህዳር አበጋዝን እየመከረችው ነበር። “ለብሌን ንገራት፤ መዋሸት ጥሩ አይደለም” ስትለው ነበር። በራሷ ሲደርስ ግን “ልዩ” ሆነባት።
ሀዘን እና  እርም ማውጣት
ሁሉም ሀዘኖች የተለያዩ ናቸው። ሁለት ሰዎች የፈለገ ቢመሳሰሉ የሚያዝኑበት መንገድ አንድ አይነት አይሆንም። የምናዝንበት መንገድ እንደየመልካችን የተለያየ ነው።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ የሞት ጥናት (Thanatology)  ፈር ቀዳጅ የሆነችው  Elisabeth   Kiibler- Ross የነደፈችው ባለ 5 ደረጃዎች ንድፈ ሀሳብ አለ።
1.  ድንጋጤዎች ሞትን አለመቀበል  (shock and denial)
2. ንዴት (anger)    
3. ድርድር ( Bargaining)
4. መቀበል (Acceptance)
5. መከፋት (Deperasion)
 ይሄ ንድፈ ሃሳብ በቅደም ተከተል የተቀመጠ ይሁን እንጂ ሰዎች በእያዳንዱ ደረጃ ላይ የሚያሳልፉት ጊዜና ከአንዱ ደረጃ ወደ ሌላኛው የሚሻገሩበት ፍጥነት እንደሁኔታውና እንደግለሰቡ ይለያያል።
እውነታው ከባድ ሲሆን አእምሯችን ራስን መደለያ ስልቶችን  በመጠቀም ከሀዘኑ (ለጊዜውም ቢሆን) ይጋርደናል። የምንወዳቸው ሰዎች መሞታቸውን ስንሰማ እንደነዝዛለን። እውነታውን አንቀበለውም። ለቅሶ ሊደርሱ የሚመጡ ሰዎች እንኳን “አልሰማሁም! አልሰማሁም!” እያሉ ቢሆንም በርግጥ ሰምተዋል። ነገር ግን የሰሙትን ነገር ምን ያህል  መቀበል እንደከበዳቸው እየገለጹ ነው።
የህዳርን ሀዘን ያወሳሰቡ የተወሰኑ ነገሮች አሉ። የመጀመሪያው ድንገተኛ ሞት መሆኑ ነው። ጠዋት “በኋላ እንገናኛለን” ብላ በሰላም ተለይታ፣ ከስራ ስትወጣ ድንኳን ተደኩኖ መድረስ ከባድ ነው። ሰው ሲታመም አስታሞ፣ ሲሞት ወግ ነው።
ሰዎች ለሀዘኑም አእምሯቸው ስለሚዘጋጅ፣ ሞት ሲከሰት ለመቀበል ብዙ አይከብዳቸውም። ድንገት የሚከሰት ሞት ግን የገነገነ ሀዘን (Hypertrophied grief) ስለሚፈጥር ለመቀበል ከባድ ነው።
ፊልሙ ሲጀምር አካባቢ ህዳር  አበጋዝን፤ ”እናቴ ለኔ እናት ብቻ አይደለችም፤ ሚስጥረኛዬ፣ ጓኛዬም ናት።” ስትለው ይታያል። እናቷን ሚዜ ለማድረግ በቀልድ መልክም ቢሆን ስትናገር ታይቷል።  ጓደኛዋም እህቷም ነበሩ። ለእሷ ብለው ብዙ ዋጋ ከፍለዋል። በየፍርድ ቤቱ  ተከራክረዋል። የቆዳ ፋብሪካውን ክበብ ምግብ እንዳትበላ፣ ሌሊት ተነስተው ምሳ የሚቋጥሩላትን  እናቷን ስታጣ ምነው መቀበል አይከብዳት?
ህዳር “እናቷን ይኸውልሽ አግቢ አግቢ ብለሽኝ ብኋላ ብቻሽን እንድትቆራመጂ” ስትላቸው “ጽድቁ ቀርቶብኝ በወጉ በተኮነንኩኝ” ሲሏት፣ አእምሮዋ ላይ  መጥፎ ይሆን? የክበብ ምግብ ስትበላ  እናቷ የሚቋጥሩላት ትዝ እያላት አልበላ ብሏት ይሆን? ለእናቷ ቃል የገባችው፤ “የብረት መዝጊያ”  አማች ማምጣት እሳቸው ከሞቱ በኋላ ትርጉም የለሽ ነገር ሆኖባት ይሆን? የባኞ ቤቱን ገንዳ ባለማስተካከሌ፣ እኔ ነኝ እናቴን የገደልኳት ብላ ራሷን  እየወቀሰች ይሆን? ምስኪን ህዳር! እውነታውን መቀበል ቢከብዳት አይገርምም።
ፊልሙ ሊያልቅ ሲል ህዳር የእናቷን ሞት መቀበሏን አይተናል። ሆኖም እስክትወጣ ግን ብዙ የሚቀራት ይመስለኛል። ደስ ሲላት ለእናቷ ለመንገር ስልክ ታወጣ ይሆናል። ሰርግ ለማድረግ ከወሰነች ሰርጓ መሃል የምትተክዝ ይመስለኛል። በአል ሲመጣ  ሆድ ሳይብሳት አይቀርም ሀዘን እረጅም ሂደት ነው።
የለቅሶ ባህላችንና እውነታን መካድ
 ሞት አለማቀፋዊ ይሁን እንጅ የሀዘንና የለቅሶ ስነስርዓቶች በባህል የተቀኙ ናቸው። ምእራባውያን ጥቁር ሱፍና ከረባት አድርገው ጥቂት ሰዎች በተገኙበት ቀብር አስፈጽመው ወደየቤታቸው ይሄዳሉ። እንግሊዞች ጋ “እዬዬ” ብሎ ማልቀስ የለም። ኮምጨጭ ብለው (with stiff upper lip) ንግግር  ያደርጉ ይሆናል እንጂ ድምጽ አውጥቶ ማልቀስ የተለመደ አይደለም። የኛ ሀገር ሰው የእንግሊዞችን ቀብር ቢመለከት “ምን አይነት ልበ ድንጋዮች ናቸው?” ሳይል አይቀርም። በኛ አገር ደግሞ ሀዘን ሲያጋጥም ጎረቤት፣ የእድር ሰዎች፣ የስራ ባልደረቦች፣ * በጣም የሚቀርቡን  ስምንት መቶ ሰዎች ለማስተዛዘን ይመጣሉ።
*  የቀብር ስነስርዓት ላይ ሙሾ  ማውረድ፣ ደረት መምታት፣ አብሬ ካልተቀበርኩ ማለት ሊኖር ይችላል። አንድ እንግሊዛዊ የቀብር ስነ-ስርዓታችንን ቢመለከት፣ ብዙ ሰዎች ራሳቸውን ስተው (mass hysteria)ሊመስለው ይችላል።
ፊልሙ ላይ እንደተቀመጠው የዶርዜዎች የለቅሶ ባህል ደግሞ የሞተውን ሰው በጭፈራ መሸኘት ሊኖር ይችላል።
እድር፣ ጎረቤትና ዘመዶች በለቅሶ ጊዜ  የስሜት  እንዲሁም ተግባራዊ እገዛ ያደርጋሉ። ዋናው ሀዘንተኛ እንግዶችን “እንዴት  ላስተናግድ?” ብሎ አይጨነቅም። ሰጥ ለጥ  አድርገው ያስተናግዳሉ።
በሌላ መልኩ ሀዘን ላይ ያሉ ሰዎች እርም እንዳያወጡ የሚያደርጉ ክስተቶችም አሉ። ሰዎች  ስለሀዘናቸው ማውራት ሲጀምሩ አንዳንድ ሰዎች ስለሚጨንቃቸው “ያው  የፈጣሪ ስራ ነው።” ወይ “ሁላችንም ወደዚያው ነን። ምን ይደረጋል?”  የሚባሉት ጠቅለል ያሉት የማጽናኛ ንግግሮች ሀዘኑን ስለሚደፋፍኑት፣ ሀዘን ውስጥ ያለው ሰው ብቸኝነት እንዲሰማውና ስሜቱን አፍኖ እንዲይዝ ያደርጋል።  
አንዳንድ ጊዜ ሀዘን ውስጥ ያሉ ሰዎች “ግንባር ለማስመታት” መጥቶ  “ሀሙስ አይቻት አልነበር ምን አጋጠማት?” ከሚለው ሰው ሁሉ ጋር እየደጋገሙ መናገሩ ያታክታቸዋል። ከላይ  ከላይ የሆኑ ብዙ ንግግሮችን ከማድረግ የውስጥ ስሜታቸውን ከሚረዷቸው ጥቂት ሰዎች ጋር መወያየት ይመርጡ ይሆናል።
ብዙ ሺህ ህጻናትና ታዳጊዎች ልክ እንደ ብሌን  እናታቸውን እየጠበቁ ነው። አንዳንዶቹ  ሃያዎቹ ውስጥ ደርሰውም አሁንም መጠበቃቸውን ቀጥለዋል። ይህን የሚያደርጉ ወላጆች አንድም ለልጆቻቸው በማሰብ ሲሆን፣ ሁለትም እንዴት እንደሚነግሩ  ግራ ገብቷቸው ነው።
 አእምሯችን አስፈሪና አስጨናቂ ነገሮች ሲያጋጥሙት ከግንዛቤ ውጪ የተለያዩ የመከላከያ ስልቶችን በመጠቀም ጭንቀቱን ለጊዜውም ቢሆን፣ በመጠኑም ቢሆን ለማርገብ ይሞክራል። እነዚህ ነገሮች ከግለሰቡ ግንዛቤ ውጭ የሚካሄዱ ናቸው። በፊልሙ ላይ የተነሳው እውነትን መካድ ገሀዳዊውን ዓለም የምንመለከትበትን መንገድ ስለሚያዛባው እንዲሁም ግለሰቡንም በጣም ስለሚጎዳው ኋላ ቀር ራስን የመደለያ መንገድ ይባላል።
 በህክምና ውስጥ እውነታን መካድ በተለያየ መንገድ ያጋጥመናል። ለምሳሌ አንድን  ሰው እንዴት ነው ብዙ አልኮል ትጠጣለህ ብዬ ብጠይቀው፤  “በየቀኑ ብዙ አልኮል እጠጣለሁ” የሚለው እውነታ የሚያስጨንቅ ስለሆነ፣ ሳያስበው አልፎ አልፎ ከጓደኞቼ ጋር አንድ፣ ሁለት እንላለን። ሊል ይችላል። በተመሳሳይ ሱስ ውስጥ ያለ ሰው፣ ሱስ ስለማቆም ብናወራው “እኔ እኮ ሱስ የለብኝም። ከፈለግሁ ማቆም እችላለሁ።” ሊል ይችላል።
  የስኳር የደም ግፊት ህመምን መቀበል የሚያቅታቸው ሰዎች፤  መድሃኒት ከመጀመር በስፖርት እከላከለዋለሁ” ሲሉ ዜናው ስላስጨነቃቸው አእምሯቸው እውነታውን በመካድ እየደለላቸው ሊሆን ይችላል። ለማጠቃለል ዘጠኝ ሞት  በደንብ ጥናት ተደርጎ የተሰራ ስነ-ልቦናዊ  ፊልም ነው።  ለወደፊትም መታየቱ እንደሚቀጥል ጥርጥር የለኝም። የስነ-ልቦና ትምህርት ላይ እንደ ማስተማሪያ ሊያገለግል የሚችል፣ የስነ-ልቦና ህክምና ላይ ደግሞ ጠለቅ ያለ ሳይንሳዊ ጥናት እንዲደረግ  የሚጎተጉት ፊልም ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ከምንም በላይ ግን ሁላችንም ስለ ህይወትና ስለ መንታ ወንድሙ ሞት  እንድናስብ የሚያደርግ ፊልም ነው።
ስለሞትና ስለሀዘን ሁለት ስነ-ልቦናዊ  መጽሐፍትን እጠቁማለሁ።
 Mourning and Melamcholia by sigmund freud
On Death and Dying by Elisabeth  Kijbler-ross  እንዲሁም የተራዘመ (Prolonged) ወይም የተወሳሰበ (Complicated) ሀዘን ውስጥ  ላላችሁ ደግሞ ሁለት የመጽሐፍ ጥቆማ አለችኝ።
WHO DIES?  By stephen and Dndrea hevine
When bad things happen to good people by harolds. Kushner
ያለ አእምሮ ጤና፣ ጤና የለም!

Saturday, 23 December 2023 11:11

የሞት ቅኔ

ሚስቱን ማመን ካቆመ ቆየ ይህ ደግሞ የሆነው ስራ ተቀጥራ መስራት ከጀመረች ጀምሮ ነው ብሎ ነው የሚያስበው፡፡ ከዛን ጊዜ ጀምሮ የምታደርገው ነገር በሙሉ እየተከታተለ ጥልቀቱን ሊረዳው የማይችለው ቅናት ውስጥ ገባ፡፡ ቅናቱ ስር እየሰደደ ሄዶ ወደ ንዴትና ጥላቻ አደገ፡፡ ይህም የንዴት ስሜት ህይወት መስርቶ በጭንቅላቱ ውስጥ ታዛውን ከቀለሰ ቆየ፡፡ አሁን ላይ ከቁጥጥሩ ውጭ ሆኖበታል፡፡ አይኖቿ ያበግኑታል፣ ስትራመድ ማየት አይፈልግም፣ እየሳቀች ከሰማት ከዛ አካባቢ መራቅ ነው የሚፈልገው፣ እሱን መውደድ እንዳቆመች ነው የተረዳው፣ እንደ ወንድ የምታየው አይመስለውም፣ ምክንያት ፈልጋ ቤቱን ጥላለት መኮብለል እንደምትፈልግ ነው የሚገምተው፣ ቤተክርስቲያን ልሂድ ብላ ሰንበት ላይ ስትወጣ የገዛ ፈጣሪው ላይ መቅናት ይጀምራል፡፡ ሁሉም ነገር ከጤነኝነት ያፈነገጠ እና እያደገም ሲሄድ ወደ እብደት ሊከተው እንደሚችል ነው እየተረዳ ያለው፡፡
ቢንያም ይህን እያሰበ ቦሌ ካልዲስ ካፌ ውስጥ በትካዜ ውስጥ ሆኖ ተቀምጧል፡፡ ድንገት ግን አንድ ቻይናዊ እሱ ከተቀመጠበት ወንበር ጋር መጥቶ ቆመ፡፡ ዮሴፍ ቀና ብሎ ተመለከተው፡፡ ቻይናዊው ጥርት ባለ አማረኛ ያናግረው ጀመር፡፡
“ይቅርታ የኔ ወንድም አንድ ጊዜ እንዳናግርህ ፍቃደኛ ነህ?”
ቢንያም በደመነፍስ ውስጥ ሆኖ እንዲቀመጥ በአይኑ ምልክት አሳየው፡፡ ምንም ነገር ማውራት ባይፈልግም አሁን ካለበት ሀሳቡ የሚያላቅቀውን ማንኛውንም ነገር ከመሞከር ወደ ኃላ እንደማይል ስለገባው ለቻይናው እንግዳ ፈቀደለት፡፡
ቻይናዊውም አጠገቡ ከተቀመጠ በኃላ ወዲያው ወደ ጉዳዩ ገባ፡፡
“ዛሬ ላማክርህ ይዤልህ የመጣሁት ሀሳብ እጅግ ድንቅ ነገር ነው፡፡ በናዝሬት ከተማ ውስጥ አንድ የሜዲቴሽን ማዕከል አለን፡፡ የማዕከላችን ዋና አላማም የሰው ልጆችን ወደ ከፍተኛው ንቃታቸው እና የማንነት ጥጋቸው ድረስ ሄደው ራሳቸውን እንዲያገኙት ማድረግ ነው፡፡ በዚህ ሰዓት ላይ ብዛት ያላቸው ሰዎች በመመዝገብ ላይ ናቸው፡፡ በማዕከሉ ውስጥ ከሚሰጡ መንፈሳዊ እውቀቶች መካከል ነፍስን አውጥቶ መጓዝ (Astral projection) እና ነፍሰ ብርሀንን የመመልከት ጥበብ (Aura Reading) ዋነኞቹ ናቸው፡፡
ቢንያም ካቀረቀረበት ቀና ብሎ ተመለከተው፡፡ ጠበቅ ባለ ንግግርም ጠየቀው …”ነፍስን አውጥቶ መጓዝ ነው ያልከው?”
“በትክክል::” አለ ቻይናዊው፡፡ “ከጥንታዊቷ ቲቤት ውስጥ በተላለፉ አስደናቂ ጥበቦች ላይ መሰረት አድርገን ነው ትምህርቱን የምንሰጠው፡፡”
“ነፍስን አውጥቶ መጓዝ ስትል…ማለቴ ትንሽ ስለነገሩ አስረዳኝ?”
“አስትራል ፕሮጀክሽን ማለት አሁን ያለህበትን ስጋዊ ንቃትህን እንደያዝክ በነፍስህ ያሻህ ቦታ መጓዝን ያካትታል፡፡ አንድ ጊዜ ነፍስህን አውጥተህ መጓዝ ከቻልክ በአካልህ ልትደርስባቸው የማትችላቸው ቦታዎች በሀሳብ ፍጥነትህ ልክ በቦታው መገኘት ትችላለህ፡፡ ህይወትንም አሁን ከምታይበት እይታ ውጭ ሆነህ በአዲስ አይን መመልከት ትጀምራለህ፡፡ የማሰብ አቅምህም የት ድረስ መለጠጥ እንደሚችል በገዛ ጭንቅላትህ ብቻ ተጠቅመህ ትደርስበታለህ፡፡”  
“በሀሳብ ፍጥነት የፈለከው ቦታ መሄድ ትችላለህ ነው የምትለኝ? እንዴት እንዲህ ሊሆን ይችላል? ይህ እኮ ሊሆን የማይችል ሀሳብ ነው እያነሳህ ያለህው፡፡ ስለ ተሸከምኩት አካሌ ጥልቅ እውቀት የሌለኝ ሰው ነፍሴ የቱ ጋር ትሁን የት ሳላውቅ በእንዴት አይነት መልኩ ላዛት እችላለሁ?”
ቻይናዊው በእርግጠኝነት መንፈስ ፈገግ ብሎ ቢንያምን ካየው በኃላ ይህን ተናገረው…”ጥያቄህ በሙሉ ትክክል ነው፡፡ ነገር ግን ከመፈጠራችን በፊት እና ከሞትን በኃላ ያለውን ነገር ላይ ምንም እውቀት የሌለን ሰዎች ነበርን ሆኖም ባደግንበት ቦታ የሚነገሩንን መንፈሳዊ ሚስጥራቶች አድምጠን ያላየናቸውን አለማት አምነን ተቀምጠንም እናውቃለን፡፡ ይህም እውቀት እንደዛው ነው፡፡ ያልተመለከትከውን ሰው ሲጠይቅህ አላውቀውም እንደምትለው ሁሉ በውስጥህ ያለውንም ድንቅ ጥበብ በተመሳሳይ የእወቀት ቅርፅ ውስጥ ሆነህ ብትፈልገው ታገኘዋለህ፡፡”
ቻይናዊው ከተቀመጠበት እየተነሳ… “ጊዜ ኖሮኝ ስለያንዳንዱ ነገር ባስረዳህ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ሆኖም በማዕከላችን መጥተህ በራስህ መንገድ እና ኢማጅኔሽ እውቀቱን ካላገኘህ በስተቀር እኔ ያልኩህን እያሰብክ ብቻ ነው የምትጓዘው፡፡ በዚህም ውሳኔህን እፈልገዋለሁና ይህች ቢዝነስ ካርዴን ይዘህ ልክ ስትወስን ደውልልኝ፡፡”
…ቢዝነስ ካርዱን ለቢንያም አቀብሎት አካባቢውን ለቆ ሄደ፡፡
ቢንያም የዛን ቀን እንቅልፍ ሳይተኛ አደረ፡፡ በየማህሉ ሚስቱ አቅሊስያን እየዞረ እያያት መናደዱን ግን አላቆመም፡፡ እንዲሁ ጠዋት ላይ ተነስታ ጥላው የምትጠፋ እየመሰለው ነው፡፡ ምን አድርጓት እንደሆነ ግን ሊገባው አልቻለም፡፡ በእርግጥም ነፍሱን አውጥቶ ያሻው ቦታ መብረር የሚችል ከሆነ አቅሊስያ የምትረግጠውን ምድር በሙላ እየተከተለ የምታደርገውን መመልከት ይችላል፡፡ ይህን ደግሞ ከሞት በላይ እረፍት እንደሆነ ተረዳ፡፡
አንድ ጊዜ ዞሮ ተመለከታት፡፡ በህልም ውስጥ ሆና የምትማግጥበት መሰለው፡፡ ሊቀሰቀቅሳት ፈለገ፡፡ ቀስቅሶ አንቺ ጨካኝ ሊላት፤ ምን አድርጌሽ ነው ብቻዬን ልትጥዪኝ ያሰብሺው ብሎ ሊጠይቃት በንዴት ውስጥ ሆኖ ቋመጠ፡፡ ሆኖም እስካሁን አንድም ነገር ያላገኘባትን ሴት ምን ብሎ ዘሙተሸበኛል ይበላት፡፡ ምንም ነገር አይቶባት ባያውቅም እንዲሁ ግን ውስጡ እየደጋገመ ልታመልጥህ ነው ነው የሚለው፡፡ በጣም ይወዳታልና እርግጠኛ መሆን አለበት፤ ለአስራ ሶስት አመታት አብረው ህይወትን እንደመፅሀፍ እያነበቡ ኖረዋልና በድንገተኛ ስሜት ብቻ አመታቶቹን መናድ አልፈለገም፡፡
ሲነጋ ጠዋት ላይ አቅሊስያን ቀስቅሶ ለስራ ወደ ናዝሬት እንደተላከና የሶስት ወር ፕሮጀክት እንዳለበት ነገራት፡፡ ወዲያው አምናው ተስማማችለት፡፡ በፊት ግን ትታገለው ነበር፡፡ አብሬህ ካልሄድኩ ትለው ነበር፡፡ እንዴት ቀድመህ አትነግለኝም ብላው ታኮርፈው ነበር፡፡ ታለቅስ ነበር፡፡ የዛን ቀን ግን ባለው ነገር ያለማንገራገር ተስማማችለት፡፡ ይህም ደግሞ አናደደው፡፡ ምን ስለሆነች ነው ካጠገቧ ስለይ ምንም የማይመስላት ብሎ በውስጡ በገነ፡፡ ምን ያረጋጋት ነገር እንዳለ በፍጥነት ማወቅ አለበት፡፡ የዛን ጠዋት ላይ በቅጡ ሳይሰናበታት ቤቱን ጥሎ ሄደ፡፡
ናዝሬት ከደረሰ በኃላ የቻይናዊው ስልክ ላይ ደውሎ የሜዲቴሽን ማዕከሉ ጋር ከብዙ ፍለጋ በኃላ ለመድረስ ቻለ፡፡
ማዕከሉ ግዙፍ ግቢ ውስጥ የተበጀ ሲሆን በውስጡም ከቅጠሎች መገጫጨት ውጭ የሚሰማ አንዳችም ነገር አልነበረም፡፡ የሚተነፍሰው አየር ወደደው፡፡ የሚጠበቅበትን ምዝገባ ጨራርሶ አንድ ክፍል ለብቻው ተሰጠውና የመጀመሪያውን ምሽት አቅሊስያ ምን እያደረገች እንደሆነ እያሰበ አደረ፡፡
ነጋ፡፡
ብዙ ንጋቶችን ብቻውን መምህሮቹ የሚነግሩትን የአሰርምሞ ጥበብን እየተከተለ ሰነበተ፡፡
ቢንያም እጅግ የተረጋጋ መንፈስን ብቻ መተንፈስ ከሚችሉት የቡድሂስት አስተማሪ ስር ሆኖ ስለ ነፍስ አሰራር አጠና፡፡ ነፍስን ከቧት ስላለው ብርሀን (ነፍሰ ብርሀን) ምንነት ጥልቅ እውቀት ያዘ፡፡ በነፍስና በስጋችን መካከል ስላለው ድብቅ የንዝረት ህግ ጠንቅቆ ተረዳ፡፡ እንቅልፍ ሲወስደን ነፍሳችንን ይዞ ስለሚተመው ከሰውነታችን ጋር እንደ እትብት ተጣብቆ ስላለው ብርማው ገመድ ላይ እውቀቱ ተመነጠቀች፡፡ እሱና መላው አለም አንድ እንደሆኑና የእሱ እስትንፋስ አለም ላይ ህይወት እንደሚዘራ ተገለጠለት፡፡ በዚህ መሃል ግን ዋና አላማውን አልዘነጋም፡፡ በፍጥነት ይሄን ጥበብ አግኝቶ የሚስቱን መዳረሻ ነው ማወቅ የፈለገው፡፡
ለምን ሲናደድባት እንደምትረጋጋ፣ ለምን ተናዳለች ብሎ ሲያስብ እሷ ግን በተመረጡ አማርኞች ልታረጋጋው ትሞክር እንደነበር፣ የት ነህ…የት ነበርክ እያለች አስሬ የምትጠይቀው ሴት ለምን ድንገት መጠየቋን አቋርጣ በሚላት ነገሮች በሙላ መስማማት እንደጀመረች ማወቅ አለበት፡፡ አስራ ሶስት የትዳር አመታትን እንደቀልድ ማየት አልፈለገም፡፡ ብዙ ትግል ውስጡ አለበት፡፡ አቅሊስያን ነፍሱ ድረስ ወስዶ ተነቅሷታል፡፡ ራሱን ካላጠፋ በስተቀር ሊረሳት የማይችላት ሴት ናት፡፡  
ከብዙ ሙከራዎች በኃላ የመጨረሻው ቀን መጣና ይህ ተከሰተ፡፡
የቡድሂስቱ ጉሩ የማዕከሉን ሰልጣኞች ሰብስቦ ማናገር ጀመረ፡፡
“አሁን ሁላችሁም በዚህ ክፍል ውስጥ ያላችሁ ሰዎች ነፍሳችሁን አውጥታችሁ ለመጓዝ በቂ እውቀት አላችሁ፡፡ ዛሬ ላይም ስትናፍቁት የነበረው የነፍስ በረራ እና የአለማትን ጉብኝት የምትጀምሩበት ቀን ነው፡፡ ሆኖም ለጥንቃቄ ተብሎ የተነገራችሁን በሙሉ መተግበር አትዘንጉ፡፡ ምን ጊዜም ቢሆን ከዚህ አለም ውጭ ሆናችሁ የምታዩት እይታ አማሏችሁ በዛው እንድትቀሩ ሊያደርጋችሁ ይችላልና ወደ ስጋችሁ መመለሳችሁን አትዘንጉ፡፡  ሁላችሁም የተማራችሁትን ተግባር ላይ ለማድረግ በክፍላችሁ ውስጥ መግባት ይጠበቅባችኃል፡፡ በእያንዳንዳችሁ ክፍል ውስጥ ባለውም ድምፅ ማጉያ ለዚሁ ምትሀታዊ ተግባር ተብሎ የተዘጋጀላችሁን የፍሪኩዌንሲ ሞገድ ይለቀቅላችኃል፡፡ መልካም እድል ለሁላችሁም እየተመኘሁ አሁን ሁላችሁም ወደ ክፍላችሁ እንድትሄዱ በትህትና እጠይቃለሁ፡፡
ቢንያም የሚያደርገው ነገር የእብደቱን ልክ ገና መገንዘብ ሳይጀምር ነፍሱን አውጥቶ እንዲበር እየጠየቁት ነው፡፡ ሆኖም የሰው ልጅ ጥልቅ ፍላጎት መፍጠር የማይችለው ነገር እንደሌለ አድርጎ የሚያስብ የሰው አይነት ነበርና የአቅሊስያን ሁኔታዎች በሙላ ለመረዳት እና የሀሳቧ ጥጋት ስር ለመድረስ የሚራመደውን ያህል ለመራመድ ወስኗል፡፡
በክፍሉ ውስጥ ገብቶ  እንደተባለው በጀርባው ተኛ፡፡ ነፍስን እየጎተተ አለማትን በሚያስጎበኘው የሞገድ ድምፅ የሰመመን ስሜት ውስጥ ገባ፡፡ እንደተባለው አተነፋፈሱን እየቆጠረ በሰውነቱ ላይ ያውን ሀይል በሙሉ እኩል ለማድረግ ሞከረ፡፡ ሰውነቱ እንደ እፉዬ ገላ እየቀለለው መጣ፡፡ ሰውነቱ የከተመበት የስሜት ዳገት እንደ ህልም የሚመስለው ነው፡፡ ነገር ግን ህልም አይደለም፡፡ በሰውነቱ ላይ ከባድ የሆነ የኤሌክትሪክ ንዝረት ተሰማው፡፡ ልክ ይህ እንደተሰማው በፍጥነት ነፍሱ ስጋውን ለቃ ወጣች፡፡
የምትንሳፈፈው ነፍሱ ብቻ ናት እያሰበች ያለችው፡፡ ከስጋው ጋር ተዳብሎ የነበረው እውቀት አሁን ላይ የለም፡፡ በነፍስ አካሉ ውስጥ ሆኖ ዞሮ የገዛ አካሉን በአልጋው ላይ ተኝቶ ተመለከተው፡፡ ድንጋጤ ውስጥ ገባ፡፡ የሚያየውን ማመን አቃተው፡፡ የምር ሞትን ሳይሞት ሞትን እየሰለጠነው መሰለው፡፡ በህይወትም በሞትም ውስጥ ሆኖ እንዴት ራሱን ማግኘት እንደቻለ ለወራት ሰልጥኗልና እዚህ ሀሳብ ላይ በመፈላሰፍ ጊዜውን መፍጀት እንደሌለበት አውቋል፡፡ አሁን ላይ ከአዲሱ አካሉ ጋር ለጥቂት ጊዜም ቢሆን መላመድ ነው ያለበት፡፡ በክፍሉ ውስጥ ሆኖ እንደ እንግዳ ሰው በአልጋው ላይ ተኝቶ ያለው ራሱን ተመለከተው፡፡ አስቀያሚ ሰው ነኝ ብሎ ማሰብ ጀመረ፡፡ እስከዛሬ ሲያፈጥበት የነበረው መስታወት ሲዋሸው እንደከረመ ደረሰበት፡፡ ለካ እስካሁን መልኩ ምን አይነት እንደሚመስል ራሱ በራሱ አይን ነው ማየት የነበረበት፡፡
ጊዜውን ማባከን የለበትም፡፡ በፍጥነት የነፍሱ የህይወት ትንፋሽ ወደሆነችው ባለቤቱ አቅሊስያ በሮ እየሆነ ያለውን ነገር ማወቅ አለበት፡፡
በነፍሱ ውስጥ ያለውን ንቃት ተጠቅሞ አቅሊስያ ያለችበት ቦታ እንዲሰደው የገዛ እውቀቱን በሀሳብ ቃላቶች ጠየቀው፡፡ በሀሳብ ፍጥነት በአንድ ሆስፒታል ውስጥ ራሱን አገኘው፡፡ የተከሰተው ክስተት ስለፈጠረበት ድንጋጤ እኔ ደራሲውም ብሆን ለማስረዳት ይቸግረኛል፡፡ ሆኖም ቢንያም አሁን ሆስፒታል ውስጥ ባለ አንድ ክፍል ውስጥ ነው ያለው፡፡ ከፊት ለፊቱ አንድ ዶክተርና ከሱም በተቃራኒ አቅሊስያ ተቀምጣ እያያቸው ነው፡፡ የፈራው ነገር እንዳይከሰት በነፍሱ ንቃት ውስጥ ሆኖ ለፈጠሪው ቅፅበታዊ ፀሎት አደረሰ፡፡
ዶክተሩ በሀዘኔታ አቅሊስያን ሲያናግራት ተመለከተና ፀሎቱን አቋርጦ ትኩረቱን ወሬያቸው ላይ አደረገው፡፡
“አቅሊስያ አሁን በሀዘን ህይወትሽን መግፋት የለብሽም፡፡ ያለሽን ጊዜ ከምትወጂያቸው ሰዎች ጋር በደስታ ማሳለፍ ነው ያለብሽ፡፡ ብዙ የሚወዱሽና የሚያከብሩሽ ሰዎች አሉ….
አቅሊስያ አቋርጣው መናገር ጀመረች፡፡
“ባለቤቴ ቢንያምን ምን ልለው እችላለሁ? እንዴት አድርጎ ያምነኛል? ምን ያህልስ ሊያዝን ይችላል?” ቢንያም ይህንን ሲያደምጥ ከዛ አካባቢ ጥፋ ጥፋ የሚል ስሜት ውስጥ መግባት ጀመረ፡፡ ሆኖም እሱ ራሱ ያልተረዳው ሀይል ባለበት ቆሞ የባለቤቱን ንግግር እንዲያደምጥ ያዘው ጀመር፡፡ እሱም እንደዛው አደረገ፡፡
አቅሊስያ ከተከዘችበት ቀና ብላ ዶክተሩን መጠየቅ ጀመረች፡፡  “አንተ እኔን ብትሆን ምን ብለህ ነው ለቢንያም የምትነግረው?”
ዶክተሩ በሀዘኔታ እያያት መለሰላት “ መሞታችን በተፈጥሮ የተሰጠን ግዴታችን ነው፡፡ መች እንደምንሞት ማወቃችን ምናልባት በምድር ላይ ቀሩብን የምንላቸውን ነገሮች እንድናደርግ ይረዱን ይሆናል… ሆኖም አንቺ ብቻ አይደለም የምትሞቺው…ሁላችንም መንገዳችን ወደዛው ነው፡፡ ቢንያምም ቢሆን፡፡”
“ካንሰር እንዳለብኝ እኮ እስካሁን አያውቅም፡፡ ለመሞት ሁለት ወራቶች እንደቀሩኝ እስካሁን አያውቅም፡፡ እሱ የሚያውቀው ከልጅነቱ በምኞቱ ፀንሶት ያለውን ዮሴፍ ብሎ በቅድሚያ ስም ያወጣለትን ወንድ ልጁን እንደምወልድለት ነው፡፡ እሱ የሚናፍቀው አሁን ካለንበት ቤት ወጥተን የተሻለ ኑሮ መኖራችንን ነው፡፡ እሱ እየለፋ ያለው እኔ ምንም ሳልለፋ እንደልዕል እንድኖርለት በማሰብ ነው፡፡ የትኛው ድፍረቴ ነው ከሱ ፊት አቁሞኝ የዛሬ ሁለት ወር እሞታለሁ እንድለው እድል የሚሰጠኝ? የትኞቹ አይኖቼ ናቸው አይኖቹን እያዩ እስካሁን የለፋህው ልፋትህን ሞት የተባለው እርግማን ተረጋግቶ ሊያወድምብህ ነው ብዬ በድፍረት ውድቀቱን እንድተርክለት የሚሰብኩኝ፡፡ ፈራሁ እኮ ዶክተር…ገና ሳልሞት የሞትና የፍቅር ሀይል በቁሜ አሰቃየኝ፡፡ ባህሪዬን ቀይሬበትም በፀጥታው ውስጥ ያወራኝ፡፡ መውደዱን መናፈቁን ይነግረኛል፡፡ በምድር ላይ ብቻችንን ነን፡፡ ለኔም ለሱም ያለነው አንደኛችን ለአንደኛችን እየተሳሰብን ነው፡፡ አሁን ለስራ ወደ ፊልድ ሄዷል፤ ከስራ ሲመጣ ከሚለፋላት ሚስቱ ጋር ሳይሆን ጨክና ከሞት ጋር ካመለጠችው ጨካኟ ባለቤቱ ጋር ነው የሚገናኘው፡፡ ሳልነግረው ስሞትበት ምን ይለኛል፡፡ ለምን ሀዘኑን ከማይ ብዬ እውነቱን ልደብቅበት፡፡ ለምን ጨከንኩበት፡፡ አሁን እየከበደኝ ነው፡፡”
ዶክተሩ ተስፋ በመቁረጥ ባለበት ሆኖ አቀረቀረ፡፡ አቅሊስያ በቀጣይ ለማውራት ሞክራ የገዛ የእንባዋ ሳግ ስለተናነቃት ክፍሉን ለቃ ወጣች፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ማልቀስ በማይችለው ነፍሱ፣ መጮህ በማይችለው አንደበቱ፣ መሮጥ በማይችለው እግሩ ከክፍሉ ሰማይ ላይ ተንሳፎ የሚያየው ቢንያም የሚያደርገው ጠፍቶት እየጠፋች ያለችውን አቅሊስያ በአይኑ ብቻ ሸኛት፡፡
እስካሁን ሚስጥር የሆነበትን ነገር ምላሹ ነፍስን በሚሸረካክት መንገድ ደረሰበት፡፡ አቅሊስያ ልትሞት ሁለት ወር ነው የቀራት፡፡ አቅሊስያ ካንሰር ይዟታል፡፡ አቅሊስያ እየዘሞተች አልነበረም፡፡ አቅሊስያ ቢንያምን ትወደዋለች፡፡ አቅሊስያ ልትሞት ነው….እነዚህ አረፍተነገሮች እንደ ፈረስ እየጋለቡ ነፍስያውን ይዞሩት ጀመር፡፡ በነፍሳዊ ንቃት ውስጥ ሆኖ መሞትን ተመኘ፡፡ ሆኖም የማይሞተውን ማንነቱን ይዞ ነው ከዚህ እውቀት ጋር የተዋወቀው፡፡ ሁሉም ነገር አስፈራው፡፡ ሆኖም ድንገት አንድ ሀሳብ ብልጭ አለለት፡፡ ወደ አካሉ ካልተመለሰ በዛው መቅረት ይችላል፡፡ ይህንንም የቡድሂስቱ ጉሩ አስተምረውታል፡፡ አዎ…ወደ ስጋው መመለስ አይፈልግም፡፡ ምን ቀረኝ ብሎ፡፡ የምትሞተው ሚስቱን ሞቶ ይጠብቃታል፡፡ የምትሞተው ሚስቱ ጋር አብረው ሞተው ልትበትናቸው ያለችውን ህይወት ድል ይነሷታል፡፡
ከዛን ቀን አንስቶ ቢንያም በነፍሱ እየበረረ በየቤተክርስቲያ ደጃፍ እየዞረ ከአቅሊስያ ጋር አብሮ አለቀሰ፡፡ ሙሾን አወረደ፡፡ ጥሎት የሄደውን የገዛ ስጋውን ረስቶት የሚናፍቃትን ነፍስ ከነፍስ እቅፉ ውስጥ እስክትመጣለት ድረስ አብሯት ሰነበተ፡፡ የምትሞትበት ቀናት ድረስ ሞቶ ተከተላት፡፡ የጠረጠራት ድረስ አስታውሶ እየደጋገመ ወደዳት፡፡ ህይወት በግሳንግስ ትርምሶቿ የቀማቻቸው እምነት እና ፍቅራቸውን በሞት ቅኔ ውስጥ አስመለሱት፡፡

 ኢትዮ ቴሌኮም፤ የፋይናንስ ተቋማት፣ አገልግሎቶቻቸውን በቴሌ ብር ለደንበኞቻቸው ለማቅረብ የሚያስችላቸው  የዲጂታል የፋይናንስ ገበያና የዲጂታል የአክሲዮን ግዢና ሽያጭ   አገልግሎቶችን  ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በይፋ መጀመሩን አስታወቀ፡
    ኩባንያው፤ ባንኮች፣ ማይክሮ ፋይናንስ፣ ኢንሹራንስና ሌሎችም በዘርፉ ያሉ ተቋማት የቴክኖሎጂ አቅምን ተጠቅመው፣ የፋይናንስ አገልግሎታቸውን ተደራሽና አካታች ለማድረግ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ የሚያስችላቸውን የዲጂታል ፋይናንስ ገበያ (Digital Financial Marketplace) ሶሉሽን ማቅረቡን አመልክቷል፡፡  በተጨማሪም፣ በፋይናንስ ዘርፍ ያሉ ተቋማት በርካታ የአክሲዮን ባለድርሻዎች ያሏቸው እንደመሆኑ የአክሲዮን ግዢና ሽያጭ ሂደታቸውን ዲጂታል በማድረግ ወጪ ቆጣቢ በሆነ መንገድ የሚያስተዳድሩበት የዲጂታል አክሲዮን ገበያ (Digital Share Sell/Buy) ሶሉሽኖችንም ማስተዋወቁን ጠቁሟል፡፡  
ኢትዮ ቴሌኮም ባወጣው መግለጫ፤ “የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት ገበያ፤ የፋይናንስ ተቋማት የማይክሮ ፋይናንስ፡-የብድር፣ ቁጠባና ኢንሹራንስ አገልግሎቶቻቸውን ለደንበኞቻቸው በተመጣጣኝ ዋጋ በአንድ ፕላትፎርም  በዲጂታል አማራጭ እንዲያቀርቡ የሚያስችል ሶሉሽን ሲሆን፤ ደንበኞች ካሉበት ሆነው የእጅ ስልካቸውን ብቻ በመጠቀም የተሳለጠ አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ አገልግሎቱ የደንበኞችን የብድር እንቅስቃሴና በወቅቱ የመመለስ ልምድን በማገናዘብና የሰው ሠራሽ አስተውሎትን  በመጠቀም በሚሰራ የብድር ቀመር  መሰረት የሚከናወን በመሆኑ ያለምንም የንብረት መያዣ  የብድር አገልግሎትን ለመስጠት የሚያስችል ነው ተብሏል።  ከዚህ ቀደም ከዳሽን ባንክና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በጋራ በቀረጸው የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት ከ3.6 ሚሊዮን ደንበኞች በላይ በብድር አገልግሎት ተደራሽ ማድረጉን ያስታወሰው ኢትዮ ቴሌኮም፤ በዛሬው ዕለት የቀረበው የዲጂታል ፋይናንስ ገበያ ሶሉሽን፣ ባንኮች ምንም አይነት የካፒታል ኢንቨስትመንት ማድረግ ሳይጠበቅባቸው፣ ኢትዮ ቴሌኮም በገነባው ፕላትፎርም ተጠቅመው የፋይናንስ አገልግሎቶቻቸውን ከ40 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ የቴሌብር ደንበኞች በቀላሉ ተደራሽ ማድረግ የሚችሉበት አገልግሎት መሆኑን አመልክቷል፡፡ ”የዲጂታል ፋይናንስ ገበያ አገልግሎት ሁሉንም የፋይናንስ ተቋማት ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል ሲሆን፤ ባንኮች ይህንኑ እንዲያውቁ በማድረግ በአሁኑ ሰዓት ፕላትፎርሙን ለመጠቀም ከአሀዱ ባንክ፣ ከሲንቄ ባንክ፣ ከእናት ባንክና አዋሽ ባንክ ጋር ውይይት ተጠናቆ ከብሔራዊ ባንክ በሚያገኙት ይሁንታ መሰረት አገልግሎቱን በቅርቡ የሚጀምር ይሆናል፡፡” ብሏል፤ኩባንያው፡፡


  አመታዊ ምርቱን 10 ሚሊዮን ሄክቶ ሊትር ለማድረስ አቅዷል


          ቢጂአይ- ኢትዮጵያ በአሰራሩ፣ በማምረት ሂደቱና በስርጭት ሞዴሉ ላይ ወሳኝ ለውጥ ለማምጣት ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ሊያደርግ መሆኑን የገለፀ ሲሆን፤ ኢንቨስትመንቱ የኩባንያው ፋብሪካዎች የማምረት አቅም መጨመርና ታሪካዊውን  የአዲስ አበባ ፋብሪካ ሰበታና ማይጨው ወደሚገኙት ሁለቱ የቢራ ፋብሪካዎቹ ማዛወርን እንደሚያካትት   ጠቁሟል።የቢጂአይ ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሚ/ር ሄርቬ ሚልሃድ ባለፈው ማክሰኞ ታህሳስ 9 ቀን 2016 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ሆቴል በተዘጋጀው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “ይህ ኢንቨስትመንት ኩባንያችንን የበለጠ ተወዳዳሪ ለማድረግና ከፍተኛ ጥራት ያላቸውን ምርቹን ለውድ ደንበኞቹ ለማቅረብ ከምንሰራቸው ዋና ዋና ፕሮጀክቶች አንዱ ነው” ብለዋል። የቢጂአይ- ኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ለውጥ መተግበር ያስፈለገው ድርጅቱ በኢትዮጵያ ከተፈጠረው የገበያ ለውጥ፣ በኢንዱስትሪው ውስጥ ከሚታየው አጠቃላይ ተወዳዳሪነት ጋር እርምጃውን ለማስተካከል፣ እንዲሁም የኩባንያውን እድገት ለማፋጠንና ጠቅላላ አመለካከቱን ለማሻሻል ነው ተብሏል።
“በኢትዮጵያና በገበያዋ ከፍተኛ አቅም እንዳለ እናምናን” ያሉት ዋና ስራ አስፈፃሚው፤ “ኢትዮጵያ እያደረገችና እየተለወጠች ስትሄድ ከገበያው ፍላጎት ጋር የተጣጣመ አሰራር ለመዘርጋት ተዘጋጅተን ወደ ተግባር ገብተናል” ብለዋል።“ራዕያችን በሚቀጥሉት ዓመታት የማምረት አቅማችንን በእጥፍ በማሳደግ በዓመት ወደ 10 ሚሊዮን ሄክቶ ሊትር ቢራ ለማድረስ ነው” ሲሉ ሚልሃድ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።
“ይህን ትልቅ አላማ ለማሳካት በሰራተኞቻችን፣ በምርቶቻችን፣ በደንበኞቻችንና በምንኖርበት ማህበረሰብ ላይ ኢንቨስት እናደርጋለን” ያሉት ሥራ አስፈጻሚው “በመካሄድ ላይ ካሉት ዋና ዋና ተግበራት አንዱ በማስፋፊያ ፕሮጀክት ላይ ኢንቨስት በማድረግ የድርጅታንን የማምረት አቅሙን ማሳደግ ነው” ሲሉ ገልጸዋል።
“በውሃ አቅርቦት ውስንነትና የሎጅስቲክስ ተግዳሮቶች ምክንያት በአዲስ አበባ መሀል ከተማ የሚገኘውን ታዋቂውን የቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ ፋብሪካችንን ለማዛወር የተገደድን ቢሆንም፣ ይኸው ችግር ራሱ የሌሎች ፋብሪካዎቻንን የማምረት አቅም ለማሳደግ እድ ፈጥሮልናል” ብለዋል ዋና ስራ አስኪያጁ። ቢጂአይ- ኢትዮጵያ ድርጅታዊ መዋቅሩን በማደስ ተመራጭ አሰሪ ድርጅት ለመሆን እየሰራ እንደሚገኝም ዋና ስራ አስፈፃሚ ገልጸዋል።
ቢጂአይ-ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ባሉት ሰባት ፋብሪካዎች ለ3,500 ቋሚ ሰራተኞችና 2,000 ጊዜያዊ ሰራኞች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን፤ የለውጡ ግብም በእያንዳንዱ የሥራ ክፍል ውስጥ ያሉትን አስፈላጊ ክህሎቶችና ሂደቶችን በመለየት፣ የተግባር ልህቀትን በመላ ኩባንያው ማምጣት ነው ተብሏል።
ቢጂአይ- ኢትዮጵያ አገሪቱ ከሚገኙ የግል ድርጅቶች ትልቁ ግብር ከፋይ እንደሆነና በዓመት ከ7.4 ቢሊዮን ብር በላይ ታክስ ለመንግስት እንደሚከፍል ለማወቅ ተችሏል።


ማክሰኞ ህዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም  በጀርመን፣ ጎተ የባህል ማዕከል በተከናወነ  እጅግ አስደሳችና አስገራሚ በሆነ ዝግጅት ተጠናቋል። ፊልሞቹን ካዩ በኋላ በመዝጊያ ፕሮግራሙ ላይ እንዲገኙ ከተጋበዙት ብዛት ያላቸው ትምህርት ቤቶች መካከል የስምንት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች፣ በሀገራችንም ሆነ በአለማችን  ችግር ፈጣሪ  የሆኑ ፕላስቲኮችን ጠቃሚ ለማድረግ በማሰብ የሰሯቸውን አስገራሚ ስራዎችና ስለ አፈር መሸርሸርና አካባቢ ጥበቃ ለአንድ ወር ያህል ያደረጉትን ምርምር ውጤቶች ይዘው ቀርበዋል።
በዚህ አስገራሚ የመዝጊያ ፕሮግራም ላይ፣ የመሀል ግንፍሌ፣ እየሩሳሌም፣ ዳግማዊ ሚኒሊክ፣ ፎፋን/ሰላም፣ ጃካራንዳ፣ ጀርመን ቸርች ፣ ብሔረ ኢትዮጵያ እና ዋን ላቭ  አንደኛ እና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተሳተፉ፤ ሲሆን ከወዳደቁ ፕላሲኮች፣ ከቤት ማጌጫ እቃዎች ጀምሮ፣ የቤት ውስጥ ችግር መፍቻ ማሽኖች፣ የውጭ ምንዛሬ ለመቀነስ የሚያስችሉ የኮንስትራክሽን አጋዥ እቃዎችን አክሎ፣ በራሪ ሂሊኮፕተር የመስራት ጥረቶች ታይተውባቸዋል።  ተማሪዎቹ ያቀረቧቸው ስራዎች ብዙዎቹ በአለም አቀፉ የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል ላይ ተመርጠው ከመጡት ስራዎች እጅግ የተሻሉና ፍፁም የአዕምሮ ፈጠራ ውጤቶች ነበሩ። እነዚህን ስራዎች ተማሪዎቹ እንዲሰሩ ከፍተኛ እገዛ ላደረጉ መምህራንና ርዕሰ መምህራን ከፍ ያለ ልባዊ አድናቆታችንን እናቀርባለን።
የስምንቱም ትምህርት ቤት ተማሪዎች ያቀረቧቸው ስራዎችና ስለስራዎቻቸው ያቀረቡባቸው መንገዶች፣ ለሳይንስ ያላቸው ፍቅርና ለፈጠራ ያላቸው ጉጉት እጅግ አስገራሚ ነበር። በአብዛኛው ስራዎቻቸው የአካባቢያቸውን ችግር ለመፍታት ያላቸውን ልባዊ ፍላጎት በተግባር አሳይተውበታል። የህብረተሰቡን ችግሮች፣ ድክመቶች፣ ፍላጎቶች በዚህ እድሜያቸው ያስተዋሉና የተረዱ እንዲሁም ያንንም ለመቅረፍ አቅም እንዳላቸው የሚያሳዩ ነበሩ። በእርግጠኝነት ትንሽ ድጋፍ ካገኘ ሀገሩን ከፍ የሚያደርግ የተሻለ ትውልድ እየመጣ እንደሆነ የታየበት ፕሮግራም ነበር።
የአለም አቀፍ ፊልም ፌስቲቫሉን የጀርመን የባህል ማዕከል፣ ጎተ ኢንስቲቲዩት ከኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ጋር በመተባበር በየአመቱ የሚያቀርብ ሲሆን፤ ዝግጅቱን ለኢትዮጵያ ህፃናት ለማዳረስ የኢትዮጵያ ልጆች ቴሌቪዥን መስፈርት የማይገኝለት ከፍተኛ ትብብር አድርጓል።
የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል በደቡብ ምስራቅ እስያ፣ በደቡብ እስያ ፣ በአፍሪካ ፣ በመካከለኛው ምስራቅና በላቲን አሜሪካ የሚካሄድ የሳይንስ ግንዛቤ ልምድ ልውውጥ በዓል ነው። የሳይንስ እውቀትን ያስተዋውቃል እና የወቅቱን ሳይንሳዊ ቴክኖሎጂና የአካባቢ ጉዳዮች ግንዛቤን ለመፍጠር መንገዶችን ያመቻቻል። የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል ሳይንሳዊ ጉዳዮችን ተደራሽና አዝናኝ በሆነ መልኩ ለብዙ ታዳሚዎች ያቀርባል፤ እናም ሳይንስ አስደሳችና አዝናኝ ሊሆን እንደሚችል ያሳያል።  ዝግጅቱ በ2005 ተጀምሮ ዛሬ በአለም ትልቁ የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል ለመሆን በቅቷል። በ2023፣ 2015፣ የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል በአለም አቀፍ ደረጃ ከመስከረም 20 እስከ ህዳር 20 የተካሄደ ሲሆን፤ ፌስቲቫሉ በኢትዮጵያ ሲካሄድ ይህ ለሶስተኛ ጊዜው ነው። የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል በዚህ ዓመት በሥነ ምህዳር መልሶ ማቋቋም ላይ የተባበሩት መንግስታትን የአስር ዓመት ዘመቻን የሚደግፍና በአጋርነት መቆሙን ያሳየበት ነው።  የዘንድሮ የሳይንስ ፌስቲቫል ጭብጡ፤ በመላው ዓለም የሚገኙ ሥነ ምህዳሮችን ከአደጋ ለመጠበቅና  እንደገና ለማደስ የተደረገ ጥሪ ነው። የፌስቲቫሉም ዋና መልዕክቶች
ዳግም ማሰላሰል
እንደገና መጀመር
እንደነበረ መመለስ
የሚሉ ነበሩ።
የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል በዚህ ዓመት ከ 102 አገራት ከ1700 በላይ ፊልሞችን ተቀብሎ ከ35 አገራት የተላኩ 150 ፊልሞች  መርጧል።
 ከእነዚህ ውስጥ ለሀገራችን በተለይ ለወጣቶችና ህፃናት ተስማሚ የሆኑ 26 ፊልሞች ላለፉት ሁለት ወራት ሲታዩ ቆይተዋል። የአለም የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫል ከእነዚህ ከተመረጡት ፊልሞች ውስጥ አሸናፊ ለሚሆኑ ስድስት ፊልሞች ሽልማቶችንም ይሰጣል። በዘንድሮው የሳይንስ ፊልም መዝጊያ ላይ እንደታዘብነው፣ ልጆቻችን ያቀረቧቸው ስራዎች ምናልባት በሚቻለው መንገድ ታግዘው ለፊልም ፌስቲቫሉ ተልከው ቢሆን ኖሮ በእርግጠኝነት ቢያንስ ከስድስቱ ሽልማቶች አንዱን የማሸነፍ ብቃት እንደነበራቸው ነው።
በመዝጊያ ፕሮግራሙ ላይም የጀርመን የባህል ማዕከል የፕሮግራሞች ኃላፊ አቶ አማኑኤል ፈለቀ፤ በሚቀጥሉት የአለም አቀፍ የሳይንስ ፊልም ፌስቲቫሎች ላይ የኢትዮጵያ የሳይንስ ፊልሞች እንደሚካተቱ ተስፋ እንዳላቸው ገልፀው፤ በተለይ በመዝጊያ ፕሮግራሙ ላይ ስራቸውን ያቀረቡ ትምህርት ቤቶች እጅግ እንዳስገረሟቸውና ትምህርት ቤቶቹ ለቀጣዩ አመት እንደ ዘንድሮው ድንቅ ስራ ለማቅረብ ቢጥሩ፣ጎተ ኢንስቲቲዩት ከጎናቸው እንደሚቆም አረጋግጠዋል።


 የሥልጡኑ ሰው ሥነ-ልቦና የተዋቀረውና የተቃኘው በምክንያታዊ አራዳ አስተሳሰቡ [Mindset] ነው፡፡ ያ ማለት ደግሞ ሥነ-ልቦናው አንድም ምክንያታዊ [realistic] ሆኖ በማሰብ የተዋቀረ አንድም አራዳ በሆነ ጠባይ - አመለካከት [attitude] የተቃኘ ነው፤ ይቃኛልም ማለት ነው፡፡ ለእርሱ አራዳነት የነቃነት ነው፤ ብልጥነት፣ ብልህነት ነው፤ ምክንያታዊነት ደግሞ እውነታ [fact] ላይ መመስረትና ተገቢ የሆነውን ተግባሪ ሰው [practical] መሆን ነው፡፡
ምክንያታዊ አራዳነቱ
1ኛ. እውነታ ላይ የባነነ - የነቃ ያደርገዋል፡፡ እውን፣ እውነት፣ ተጨባጭ ሁኔታ የሆነውን ለመገንዘብ፣ ለማገናዘብና ለመረዳት በመጣር እውነታው ላይ ይደርሳል፡፡ ያ እውነታ የአጠቃላዩ የሰው ልጅና የህይወት የሆነ፣ ግለሰባዊና ማህበራዊ ተጨባጭ እውነታ፣ ታሪካዊ እውነታ፤ ተፈጥሯዊ - ሳይንሳዊ እውነታ እይታና እምነት መሆናቸውን በተጨባጭ መከሰት አለመከሰታቸውን፣ የእውነተኛ ተፈጥሯቸውን ምንነትን በማስተዋልና በመረዳት በእውነታ የነቃ ይሆናል፡፡
2ኛ. እውነታን አያያዝ ማስተናገድ ላይ ብልጥ ብልህ ያደርገዋል፡፡ እንዴት እውነታን መጋፈጥ፣ መቀበልና ምላሽ መስጠት እንዳለበት ያውቅበታል፡፡ ለእሱ ገሃዱን እውነታ መካድ አይታሰበውም፡፡
የሚያመልጥ መስሎት ስራውን ስሙን አካባቢውን በመቀየር እውነታን ለማምለጥ አይቃጣውም። ዐይኑን በመጨፈኑ ችግሮች ይጠፉ ይመስል እውነታን ላለማየት በመሞከር ራሱን ጉዳት ላይ አይጥልም። አንገቷን ብቻ አሸዋ ውስጥ እንደ ደበቀችው ሰጎን ከእውነታው ለመደበቅ የሞኝ ነገር አያደርግም በአልኮል መጠጥና በአደንዛዥ እፅ እውነታውን ለመርሳት ብሎ ራሱን የባሰ ችግር ውስጥ አይከትም። ከልብ ባልሆነ ሳቅ ፈገግታና የደስተኝነት አኳኋን እውነታውን ለመሸፈን ብሎ ራሱን አያታልልም፤ አይሸነግልም፡፡ ፊት ለፊት ባለመናገር ከእውነታው አይሸሽም። ነገሩን ቢገልጥ ቢናገር የሚፈጠረውን በመሥጋት እውነታን አያፍንም፡፡ ፊት ለፊት በዙሪያው ያለን እውነታን ይፈቅዳል፤ በዛ እውነታን ይገዛል ወይም እውነታን ለራሱ ያስገዛል፡፡ ከዚህ በተቃራኒው እውነታ በሌለው ነገር በመገዛት ወይም እውነታ ለሆነ ነገር ባለመገዛት ልክ ያልሆነ አእምሯዊ ስሜት ውስጥ ተዘፍቆ መቸገር አይፈቅድም፡፡
ሥልጡኑ ሰው አሉታዊ ነገሮች ሲያጋሙት ነገሮች በጠበቀው መንገድ ባልሄዱ ጊዜ፣ ያሰበው የተመኘው ባልተሳካ ቁጥር አንድ ነገር ምቾት በነሳው ጊዜ ሁሉ፣ ሰዎች በተናገሩት ባደረጉበት ልክ ያልሆነ ነገር ሁሉ ነገሮች በጠመሙ ጊዜ ሁሉ አራት ሥነ-ልቦናዊ መርሆች ምላሾች [responses] አሉት፡፡
1ኛ. በጣም ብዙውን ጊዜ ቀለል - ተወት የሚደርግ [easygoing]
ሥልጡኑ ሰው በችግር በፈተና በቀላሉ የማይፈታ ሰው ነው፡፡ እለት ተእለት ችግሮች መፈታተኖች ከሌሎች ሰዎች ከነገሮች፣ ከሁኔታዎች ቢገጥሙትም፣ እንደው እንደዘበት አይረበሽም፤ እጅ አይሰጥም፤ ነገሩን ቀለል አድርጎ ያየዋል፤ ይቀበለዋል፤ ያሳልፈዋል፡፡ ያለምሬት መታገስ መቻል ይቻለዋል፡፡ በቀላሉ ቅር ያለመሰኘት - ያለመቀየም፤ በቀላሉ ያለመከፋ በቀላሉ ያለመናደድና በቀላሉ ያለመጨነቅ ብልጠት አለው፡፡
2.ኛ አንዳንዴ የማይበርደው የማይሞቀው [emotionally non - reactive]
በህይወት ውስጥ ለአንዳንድ ነገሮች ደንታ የለውም፡፡ አንዳንድ የማይሞቁት የማይበርዱት ነገሮች አሉ፡፡ በውስጡ እንደ መሞቅ እንደ መብረድ ቢለው እንኳ ለውጪው አካል የሚሰጠው የስሜት ምላሽ፣ የሚያሳየው ስሜት የለውም፡፡ ቀለል አድርጎ በውስጡ ያሳልፈዋል፡፡ ያየውን እንዳላየና የሰማውን እንዳልሰማ የሚሆንበት ጊዜ የተፈጠረውን ምንም እንዳልተፈጠረ የሚቆጥርበት ጊዜ አለ፡፡ የግሉ ችግር ባልሆነ በማይመለከተው ነገር ሲቸገር አይገኝም፡፡ ዝም ብሎ ከመገንዘብ ውጪ ስንቱን አያውልም አያወጣዳጅም፡፡ የሚረብሽ ምቾት የሚነሳና የሚፈታተን ነገር ሲገጥመው እንኳ ምላሹ የሚሆነው ምላሽ አለመስጠት ነው፡፡ ምላሽ ሳይሰጥ ዝም ብሎ ያያል ወይም ያልፋል፤ አልያም የትኩረት ርእስ ይቀይራል፡፡ በአንዳንድ አሉታዊ ነገሮች ገጠመኞች ጨርሶውኑ ቅር ያለመሰኘት - ያለመቀየር፤ ጨርሶውኑ ያለመከፋት ጨርሶውኑ ያመናደድና ጨርሶውኑ ያለመጨነቅ ጠባይ አዳብሯል፡፡
3ኛ. ከስንት አንዴ ምክንያታዊ [realistic] አሉታዊ ስሜቶችን ማስተናገድ
ሥልጠኑ ሰው መቼስ ሰው ነውና ቅር የመሰኘት - የመቀየም የመከፋት የመናደድና የመጨነቅ የመሳሰሉ አሉታዊ ስሜቶች በምክንያት የሚፈጠሩ ድንገት ቢሰማው እንኳ በምክንያቱ የሚቆጣጠራቸው መሆናቸው ነው፡፡ ከመሬት ተነስቶ እንደው ያለ ግልፅ ምክንያት ሳይታወቀው በአሉታዊ ስሜቶች ተደጋግሞ የሚጠቃ ሥነ-ልቦና አይደለም ያለው፡፡ ከስንት አንዴ እንዲህ ያሉ አሉታዊ ስሜቶች ሲሰሙት ድብቅ - ጥልቅ ምክንያተ  ይኖራቸው ይሆን ወይም ምክንያት የለሽ ይሆኑ ይሆን ለመፈተሽ ጥቂት ጊዜ ወስዶ ያሰላስልባቸዋል፡፡ አሉታዊ ስሜቶች ምክንያት ያላቸው ከሆኑ እውቅና ለመስጠትና በየልካቸው ለማስተናገድ ይፈቅዳል፡፡ በምክንያት የሚያሳስቡት የሚያሰጉት የሚያስጨንቁት ጥቂት ነገሮችም ይኖራሉ፡፡ አሉታዊ ስሜት መሰማት ሰው ስለሆነ ብቻ ሳይሆን ተገቢ ቅር መሰኘቶች-መቀየም መከፋቶች መናደዶችና መጨነቆች እንዳሉ ያምናል፡፡
4ኛ. ብዙውን ጊዜ እንደ ቀልድ፣ እንደ አስቂኝ እንደ መሳቂያ ቂልነት መውሰድ
ለእርሱ የህይወት አብዛኛው ነገር አስቂኝ ቀልድ፣ መሳቂያ ቂልነት ሆኖ ይታየዋል፡፡ “መሳቂያ” “ቀልድ”፣ “ያስቃል” የሚላቸው አማርኛዎች አሉት፡፡ ከውልደት እስከ ሞት ባሉ ነገሮች በሚከሰቱ ነገሮች ውስጥ በብዛት የሚታየው አስቂኝ ነገር፣ መሳቂያ ቂልነት መራርና ጨካኝ ቀልድ ነው፡፡ እንዲህ ያለ ቀልድ ተፈጥሮ ስትቀልድ፣ ህይወት ስትቀልድ ማህበረሰብ ሲቀልድ መሪዎች ሲቀልዱ ይታዘባል፡፡ በሚያስቀው ነገር በጣም ይስቃል፡፡ በብዙ መፈታተኖች ችግር - ችጋሮች ላይ ፈገግ ይላል፡፡ ጉዳዩ በአንድ በኩል ጥብቅ፣ በሌላ በኩል የሚያስቅ ሲሆንበት ‘ወደው አይስቁ’ የሚለው ነገር አለው፡፡  በሰዎች በነገሮችና በሁኔታዎች ተገርሞ ፈገግ ብሎ የሚያልፍበት ጊዜ ብዙ ነው፡፡ አንዳንዴም በራሱ የቂል ሃሳብ ድርጊትና በመጃጃሎቹ ላይ ይስቃል፤ ያላግጣል፤ ፈገግ ይላል፡፡
የሥልጡኑ ሰው ሥነ-ልቦና የሚወሰነው እውነታ ላይ ባለው መንቃትና ብልህነት ነው። በመሆኑም አሉታዊ ፍላጎትና ስሜቶች ውስጥ ሲገባ፣ የእርሱ ዋናው ጉዳይ እውነታው ነው፡፡ አዕምሮ ውስጥ ጎላ ብሎ የሚታየውና የሚሰማው  ‘እውነታ’ ነው፡፡ ጨርሶውኑ ወይም በቀላሉ ቅር የማይሰኘው  - የማይቀየመው፣ የማይከፋው፣ የማይናደደውና የማይጨነቅ ከነገሩ እውነታ አንፃር ነው፡፡ ስለዚህ ሥነ- ልቦናዊ ምሾቹ እውነታን መረዳት እውነታን መቀበል ፣ እውነታን በልኩ ማየት፣ እውነታን በተለየ ማየት፣ እውነታን በገለልተኝነት ማየትና እውነታን መቀየር ላይ የተመሰረቱ ናቸው፡፡
1 እውነታን መረዳት
ሥልጡኑ ሰው መጀመሪያ ያደረገው ነገሮች በተጨባጭ መኖር አለመኖራቸውን ለመገንዘብ መሞከር ነው፡፡ በእርግጥ ህላዌ ያላቸው ናቸው ወይስ ምናልባት ቅዠቶች ይሆኑ የሚለውን ለማወቅ ጥሯል፡፡ የሰው ልጅ የአእምሮ ፈጠራ የምናቡ ውጤት፣ የገዛ ተረታተረቱ የሆኑ በተጨባጭ ኗሪነት የሌላቸው ነገሮችን ለይቶ አውቋል፡፡ በነዚህ ጨርሶውኑ በሌሉ፣ ቅዥቶች በሆኑ ነገሮች ራሱን አያስቸግርም፤ የሃሳብ የስጋት ሰበቡ እንዳይሆኑ ማድረግ ችሏል፡፡ በሌሉ ነገሮች መጃጃል ሆነ መጨነቅ አምሳያ የሌለው ቂልነት መሆኑን ተገንዝቧል፡፡
የነገሮችን እውነተኛ ተፈጥሮን ለመረዳት የራሱን ፍተሻ ያደርጋል፡፡ ሳይንሳዊ ሃቆችን ይጠቀማል፡፡ የነገሮች እውነተኛ መለያ ጠባያቸውን ውስጣዊ ይዘታቸውን ሥሪታቸውንና ምንነታቸውን ለማወቅ ይሻል፡፡ በተለምዶ ከሚታወቁበት ባሻገር ትክክለኛ ተፈጥሯቸውን ለመገንዘብ ለመረዳት ይጥራል፤ መስለው የሚታዩትን በተለምዶ የሚገለፁበትን ሳይሆን በትክክል የሆኑትን እውነተኛ ተፈጥሯቸውን ለመገንዘብ ይፈልጋል፡፡ ለአብነት የዚህን ዓለም ገሃድነትን፤ እውንነት የሃሳቦቻችን ውጤት ብሎት ቅዠቶቻችን መሆን አለመሆኑ ላይ ለመድረስ አሰላስሏል፡፡
 በዙሪያችን ያለው ዓለም የምንኖርበት ዓለም እውን መሆኑን፤ ተጨባጭ እውነታ መሆኑን ከመገንዘቡና ከመረዳቱ በተጨማሪ፣ የውጪው ዓለም የሚታየው፤ ጠባዩ በእርሱ ሃሳብ በአእምሮው የሚወሰን ሳይሆን በመሰረቱ የራሱ የሆነ ነባር ጠባይ እንዳው አምኗል።  ስለ ሰው ልጅ እውነተኛ ማንነትና ምንነት ለመገንዘብ ጥሯል። የሰው ልጅ መሰረታዊ ምንነቱ ህይወት ያለው ነገር መሆኑን ሲቀጥል፣ ከእንስሳቱ እንደ አንዱ እንደሆነ ብሎም የራሱ ‘ሰው’ ወይም ‘ሰውነት’ የሚባል ምንነት - ማንነት እንዳለው ተረድቷል፡፡ ስለ ሞትም ሲያስብ፣ ሞት የሰው ልጅ የሰውነት/ የአካል ስነ-ህይወታዊ አሰራር መቼውኑም እንዳለው ዓይነት የራሱ መልክ እንዳለው ነገር እንደ የሆነ ጨለማና አስፈሪ መንፈስ ይሰማው የነበረው አስጨናቂ የሞት ሃሳብ፣ አሁን ላይ በእሱ ሥነ-ልቦና ላይ የሚፈጥረው አንዳች ስሜት የለም፡፡
ህይወት በመሰረቱ መልካም እንደሆነችው ሁሉ፣ የራሷ መራር እውነትም እንዳላት ተገንዝቧል፤ አስቸጋሪነትም ፈታኝነትም እንዳለባት ኖሯት እያየው ነው፡፡ በህይወቱ ውስጥ ሀዘንም ደስታም ተፈራርቆበታል፤ ተመችቶት ተጎሳቁሎም ያውቃል እናም ህይወት ትራጄዲው ኮሜዲውና ትራጄዲ ኮሜዲው የሚከወንባት መድረክ መሆኗን አስተውሏል፡፡
(ከቴዎድሮስ ሎገስ ከተሰኘው መጽሐፍ የተቀነጨበ) “ሥልጡን ሰው እና የህይወት ፍልስፍናው”


Saturday, 23 December 2023 10:58

መሀል ላይ መቁለጭለጭ


          እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እኔ የምለው… መቼም ጨዋታ አይደል፣ ግራ ግብት ያለን ነገር አለ። ‘ስልጣኔ’ ማለት… አንዳንዴ ትርጉሙ ግራ አይገባችሁም! አለመሰልጠናችንን የሚነካን በዛብና። አለ አይደል… የእኛ የእኛ የሆነውን ሁሉ የ‘ፋራነት’ … የነሱ የሆነው ሁሉ የ”ስልጣኔ” እየሆነ ተቸግረናል።
ስሙኝማ… አንዳንዶቻችሁ “በአውሮፕላን የምትመጡም…” ሰዎች! ሰላም ስጡና… ‘ዋትስ አፕ’ ‘አውችን’ ይዛችሁ መጥታችሁ… ገና ከዋሻ የወጣን አታስመስሉና! ምን መሰላችሁ… የአንዳንዶቻችን ሩጫ!... አለ አይደል… ከራስ ለማምለጥ የሚደረግ ሩጫ ሆኗል። ክፋቱ ደግሞ… ስንሮጣት እንከርማታለን እንጂ መድረሻ የለንም።
‘ፈረንጅ’… ‘አይደንቲቲ ክራይስስ’ ነው… ምናምን የሚላት ነገር አለች አይደል… አንዳንዶቻችን አውላላ ሜዳ ላይ ከተንላችኋል። አለ አይደል… ከራሳችንም ሸሽተን… ‘እነሱም’ በመጤነት እንኳን አልቀበል ብለውን… አያሳዝንም! እንዴ… ኮሚክ ነገር እኮ ነው። እንትና የ‘ቺካጎ ቡልስ’ ቲሸርት ስላደረገ… እኔ በሌጣ ከኔተራ ስለሄድኩ… እሱ ስልጡን… እኔ ‘ፋራ’ እንሁን!
ምን ይመስለኛል መሰላችሁ… አለ አይደል ይሄ ስልጣኔና ‘ፍርንጅናን’ የማያያዝ ነገር አለ። እንግዲህ… እነሱ ‘ሲግቱን እኛ ስንጋት አይደል የተከራምነው! አንዳንዶቻችንማ… አለ አይደል… የፈረንጅ’ ‘ሞሮን’ ያለም አይመስለን። በእነሱ ባይብስ! እዚህ አዲስ አበባ ሞልቶ የለ። ምን ይደረግ… በቃ ‘ቆዳ’ ስልጣኔ ሆነላችሁና… ስንት የሀበሻ ባለሙያ ቆሎ ሲቆረጥም… የፈረንጅ ‘ማሞ ቂሎ…’ “ከፍ በል ዝቅ በል” ይለናል።
(እንትናየ… ያ ‘ፈረንጁ’… እንዴት ሆናችሁ? አይ…‘ልትፈነገይ’ ነበር ሲሉ ሰምቼ… ቂ…ቂ…ቂ… እስቲ ምናለ… እኛ ቤንች የተቀመጥነው ሞልተን… ምንድነው ፈረንጅ ላይ የሚያሻማችሁ! አሃ… አሁን እኛ  የእነሱን ያህል “አቅቶን” ነው!... “ቂ…ቂ…ቂ…!)
እናላችሁ… የእኛ የ‘አገር ቤት’ ሰው ስድስት ወር ሀምበርገር ሲገምጥ ከርሞ ይመጣና “በቃ አበሻም አልሰለጥን አለ…” ሲላችሁ… አለ አይደል ታዝናላችሁ። ኧረ ‘ባካችሁ… ሰልፍ ኮንፊደንስ’… ‘ከተደበቀበት’ ፈልጉልን! (በነገራችን ላይ… ይሄ ከኒዮርክ ምናምን የ‘ፈረንጅ’ መኪና እየተደገፉ… ፎቶ መላክ… እሱ ነገር ቀነሰሳ! አሃ… ተነቃቃና!... አሁን አሁንማ… ከዚያ ወደዚህ የሚመጣው ዶላር ቀንሶ… ከዚህ የሚሄደው ድርቆሽ እየበዛ ነውሳ! እንትና መቼም አንተም እንደ እኔ… ‘ኮምፕሌይን’ ማድረግ ትወዳለህ… “ከሀገሩ የወጣ እስኪመለስ…” ለሚለው አዝማሪ መሸለም እችላለሁ። እኔ የምለው… ከሀገሩ የወጣ ሰው በቅሎ ይሁን የሜዳ አህያ… መቼ ሄደህ ነው ያወቅከው … ወይስ በታሳቢነት ነው። እስከዚያው አለ አይደል… እኔ አንድ ትሪፕ ቢሾፍቱ እስፖንሰር አደርግሃለሁ) እኔ የምለው … አንዴ!... በቃ ሹካ አያያዝ ካልቻልን… አልሰለጠንንም ያለው ማነው! እኔ‘ኮ ስለቴክኖሎጂ ምናምን እሺ ያውሩ… መቼም በሱ በኩል ‘ይቅደሟችሁ… ይከተሉ’ የተባልን ነው የሚመስለን። ግን… ፖስታን መጠቅለል መቻልና አለመቻል የስልጣኔ መለኪያ ያደረገው ማነው? ‘ፈረንጅ’ ፓስታውን በዳቦ ስለበላ… እንጀራ በወጥ የበላውን ቅንጣት ታክል ዝቅ የሚያደርገን ነገር የለም። እናላችሁ… በቴክኖሎጂ ኋላ መቅረታችን ልክ ነው። ይሄ ነገር ሰውነታችንን የሚያሳንስ አይደለም… አለ አይደል… እዚሁ እንኳን ነገሬ ብላችሁ ስታዩ… የሚያበሽቃችሁ መአት ነገር አለ። ለጨዋታው ያህል ዛሬ ማርቲን ሉተርኪንግ… ምናን አይነት ሆንኩባችሁ አይደል! የምር ግን… አንዳንዴ ይሄ ራስ በራስ የሚደረግ ጭቆና ያበሳጫል።
አሃ ገና ለገና ቢላው ሹካው እንዴት እንደሚያዝ “አላውቅም…” የሚል የ‘ፈረንጅ’ ምግብ ንክች የማያደርግ ሞልቶላችኋል። እንዴ… ልክ አይደለም ወይ! አያያዙን ማወቅ የ‘እነሱን አበላል ማወቅ’ እንጂ… መሰልጠን ማለት አይደለም።
ሙዚቃ… ለምሳሌ… የ‘ዓለም ቋንቋ ነው’… አይደል! ግን አሬታ ፍራንክሊንን መስማት… ስልጣኔ… ሽሽግ ቸኮልን መስማት  ‘ፋራነት’ ያደረገው ማነው! የምር… ይገርማችኋል። የኬኒ ሮጀርስ ጊታር… የስልጣኔ  ‘ግሪን ካርድ’… የይርጋ ዱባለ ማሲንቆ… የፋራነት ‘ላይሰንስ’ ሲሆን… አለ አይደል… የሆነ ነገር አይሰማችሁም!
እናላችሁ… የ‘ስልጡንነትና’ የ‘ፋራነት’ መለኪያዎች… ራሳችንን ከመሬት በታች እነሱ ከመሬት በላይ!... ነገርየውማ ያው የምንሰማው የምናየውም… የምናነበውም… እነሱን አይደል… በጽሑፉም በአልበሙም በምኑም እንደማንረባ ነው የሚነግሩን! ክፋቱ ምን መሰላችሁ… ሳይታወቀን ተቀብለነዋል።
ይኸው… በፖለቲካውም በምኑም ‘ስንጣላ’ እንኳን  ሮጠን እነሱ ጋር አይደለንም! አሃ ‘ስልጣኔ’ መሆኑ ነዋ! እዚሁ… በአገር ባህል እኛ “አንተም ተው… አንተም ተው…” ወይም  “የበደለም ይቅርታ ይጠይቅ… የተበደለም ለእግዚአብሔር ብሎ ይቅር ይበል…” ማለት እያለ ‘ለ ፈረንጅ’ እየሄዱ “ልብ አድርጉልኝ… ብቻ! “ማለት ሆኗል። ምን መሰላችሁ በአገር ባህልኛ መስማማት ‘ፋራነት’ ነዋ!
እናላችሁ… ይሄ የ”ስልጡንነትና” የ “ፋራነት” መለኪያ አለ አይደል… ለ‘እኛ ሳይሆን ለእነሱ ሆኖ የተቀደደ ነው የሚመስለው። ስለ ላሊበላ ህንጻ ሲነግሩን ከእቁብ የማንከተው ሰዎች ስለ ‘ኢምፓየር እስቴት ቢልዲንግ’ ግን “አጀብ የሰው ስራ!” እንላለን። ይህ ደግሞ… እንዲያው አጉል “አገሬ ናፈቅሽኝ” ምናምን ሳይሆን… ይህ ‘የእኛ የሆነው ነገር ሁሉ’ ‘ያለመሰልጠን’ ምልክት መሆኑ ስለማይታየኝ ነው።
ብቻ… ከራስ መሸሽ የመሰለ እርግማን የለም። የምር… በአንድ በኩል እኛነታችንን በ‘ቪም’ ለማጠብ ስንሞክር… በሌላ በኩል  እነሱ… “ደግሞ አንተ ከእኔ ጋር ምን ያመሳስልህና!” ሲሉን በቃ መሃል ላይ መቁለጭለጭ ነው። እስቲ ልቦናውን ይስጠን።
ደህና ሰንብቱልኝማ!
    

ሩሲያ የሆነው ኢትዮጵያ ይደገማል። ወይም ሌላ አገር እንደ አዲስ ይከሰታል። ወጉ ግን ለሁሉ ይተርፋል። ሩሲያውያኑ ሲቀልዱ ይሆን አምርረው ባይታወቅም እንዲህ ይላሉ።
አትክልተኛው ሰውዬ የመስሪያ ቤቱን አትክልት በየጊዜው አላጠጣህም ተብሎ በድክመት ተገምግሞ በማስጠንቀቂያ ታልፏል። በልቡ “ይቺን ስህተት ሁለተኛ አልደግማትም” ሲል በጓዶቹ ስም ይምላል። (“ስጋ ብጽወት!” እንደ ማለት መሆኑ ነው)
በሚቀጥለው ቀን በጠዋት ይነሳና የውሃ ማጠጫ ጎማውን ከቧንቧው አገናኝቶ ሲያበቃ በረዥሙ እየረጨ አትክልቶቹን ውሃ ማጠጣት ጀመረ። በአጋጣሚ አህያ የማይችለው ዝናብ ይመጣና ዶፉን ይለቀዋል። ሰውየው ውሃውን ማጠጣቱን ይቀጥላል።
በዚያ መ/ቤት አጠገብ ዣንጥላ ይዘው የሚያልፉ ሰዎች ነገሩ ገርሟቸው፤
“ምን ሆነህ ነው ዝናብ እየዘነበ አንተ እንደገና የቧንቧ ውሃ የምታጠጣው?” ብለው ይጠይቁታል። አትክልተኛውም ስራውን እየቀጠለ፤
“መመሪያ ነው ጎበዝ! በመመሪያ ቀልድ የለም!”
***
እንደዚሁ ሌሎች ሁለት ሩስያውያን ከአለቃቸው መመሪያ ወርዶላቸዋል። መመሪያውም፡- አንደኛው ይቆፍራል፣ ሌላኛው የቧንቧውን ትቦ ይከታል የሚል ነው። ከዚያ የመጀመሪያው መልሶ ይደፍናል። እንዲህ እያሉ “በነገው እለት 200 ሜትር ርዝመት ያለው የውሃ ቧንቧ አስገብተው እንዲጨርሱ” የሚል ትዕዛዝ ደርሷቸዋል፡፡ እንደ አጋጣሚ በነጋታው ግን ቆፋሪ መጥቶ ቁፋሮውን መቆፈር ቢጀምርም ባለቧንቧው እክል ገጥሞት ትቦውን ይዞ ሳይመጣ ይቀራል። ያም ሆኖ ቆፋሪው ስራውን አላቋረጠም።
በሜትር እየለካ ሁለት ሜትር ያህል ርዝመት ይቆፍርና መልሶ አፈሩን እየከፈተ ይደፍነዋል። ይቀጥላል ሌላ 2 ሜትር። ደሞ ይደፍናል። እንዲህ እንዲህ እያለ 200ውን ሜትር ቆፍሮ ደፍኖ ይጨርሳል። ነገሩ ግራ የገባቸው የመ/ቤቱ ሰራተኞች፤ “ምን አይነት የሞኝ ስራ እየሰራህ ነው? ‘ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ’ አደረግከው እኮ?” ሲሉ ይጠይቁታል።
“መመሪያ እኮ ነው ጎበዝ! እኔ የተሰጠኝን ሃላፊነት ተወጥቻለሁ። መመሪያውን በሚገባ አክብሬአለሁ” አለና መለሰ።
***
በኢትዮጵያ ደግሞ እንዲህ ያለ ወግ አለ።
ጊዜው ጥቂት ዓመታት ቆየት እንደማለት ብሏል። ታጋዮች በአንድ መኪና ሞልተው ሲሄዱ የመኪናው ፍሬን ይበጠስና ሹፌሩ ሲቸገር  ቆይቶ የአንድ ትልቅ መ/ቤት ግንብ ጥሶ አስገብቶ ያቆማታል። ሹፌሩ ክፉኛ ይጎዳል። ደም በደም ይሆናል። ሌሎቹ ያልተጎዱት ታጋዮች በፍጥነት መኪና ቀይረው በአስቸኳይ ሹፌሩን ወደ አንድ ሆስፒታል ይዘውት ይበራሉ።
ሆስፒታሉ ደጃፍ ሲደርሱ መታወቂያ ይጠየቃሉ። ከደከመው በሽተኛ በስተቀር ሌሎቹ መታወቂያቸውን አውጥተው ያሳያሉ። ዘበኛው የሁሉንም የመታወቂያ ፎቶና መልካቸውን ካስተያየ በኋላ ወደተኛው በሽተኛ እያየ፤
“የሱስ መታወቂያ የታለ?” ሲል ይጠይቃል።
“ጓድ እሱማ በሽተኛ ነው። አታየውም ደም በደም ሆኖ መንቀሳቀስ እኮ አይችልም” አሉት።
“መታወቂያ ከሌለው እናንተ ግቡ እሱ ይቆያል!”
“እንዴ ምን ማለትህ ነው ጓድ…”
“መመሪያ ነው መመሪያ ነው! ከፈለጋችሁ እናንተ ግቡ አለበለዚያ በሽተኛችሁን ይዛችሁ ተመለሱ! መመሪያ ለሁሉም እኩል ነው የሚሰራው!”
***
አንዳንዱ መመሪያ ከጅማት ይጠነክራል። ያለ አንዳች ህሊናዊ ዳኝነት፣ ያላንዳች ማመዛዘን እንገልገልብህ ሲሉት ራሱን መመሪያ አውጪውን ጭምር እግር ተወርች ቀይዶ አላላውስ አላስተነፍስ ይላል። “የዝንጀሮ ንጉስ ራሱ ይከምራል ራሱ ያፈርሳል” ይሏይ ይሄ ነው። አንዱ ቦታ ስራ ሲቆም መላው ስራ በድን የሚሆንበት አይነት መ/ቤት አለ። ያ እንግዲህ አንድያውን ይሞታል ማለት ነው። የሚገርመው መመሪያውን በጥብቅ ስራ ላይ አውላለሁ ብሎ የሚውተረተረው ሰው መነሻ በመመሪያው ማመን ሳይሆን የግምገማ ስራቸው መሆኑ ነው። ይህ በፈንታው የሚያረጋግጥልን አንድ እውነት አለን። ግምገማ  ስህተትን ማረሚያ መሆኑ ቀርቶ የበታቶች በበላዮች አይን ደካማ እንዳይባሉ፣ አልፈው ተርፈው “የባህሪ ለውጥ አመጣ!”፣ “የሚታወቀው ስህተቱን በማመን ነበር ዛሬ አመሉን ለውጧል”፣ “የችግሩን ስሯን መዝዘን ስናያት መነሻዋ ሌላ ናት” ወዘተ እባላለሁ የሚል ፍርሃት በውስጡ በመንገሱ ነው። ይሄ ደግሞ በፈንታው የገዛ የስራ ባልደረቦችን መቆጣጠርን፣ ለአለቃ ማጎብደድን፣ የየአይነቱን ሙስና፣ የጌታና የሎሌ ግንኙነትን ወዘተ ይወልዳል። መመሳጠር ይበረክታል።
“የልቡን የሚሰራ ለእናቱ አይነግርም” እንዲል መጽሐፉ፤ የጥቂቶች ዱለታ ያይላል። ስራ ይዳከማል። ሲከፋም ከነጭራሹ ይቆማል። ባለው የቢሮክራሲ የቆላ ቁስል ላይ የአይጥና ድመት ደፈጣ ሲጨመርበት አንድያውን ወደ ልብ ድካም ያመራል። የአቅም ግንባታው የአቅም መፍረስን ጽንስ ተሸክሞ ይጓዛል። ልማቱ ንቅዘትን አርግዞ የሚራመድና ቀኑን የሚጠብቅ በሽተኛ ይሆናል። ነጻ የሲቪክ ማህበረሰብ ይፈጠርበታል የሚባለውም እቅድ ውስጡን በግንደ-ቆርቆር የተበላ አፋዊ የፖሊሲ ዋርካ ብቻ ሆኖ ይቀራል። በዚህ ሁሉ ላይ የፖለቲካ ጫና ሲጨመርበት “የማይታጠፍን እንጨት ልለምጥህ ብሎ ማንከት” እንደተባለው ይሆናል።
የማይጠየቅ መመሪያ፣ የማይሻሻል ህግ፣ የማይለወጥ እቅድና መርሃ ግብር ጥቂት ታማኞችን እንጅ እንደ ልቡ ለማሰብ የሚችል፣ የሆዱን ለመናገር የሚደክም፣ በነጻ ውይይት የሚያምን ነጻ ህብረተሰብ ለመፍጠር አያስችልም። ይልቁንም ፈሪና ግልጽነት የጎደለው፣ በራሱም በሌሎችም የማይተማመን ዜጋ ማሳደግ ነው የሚሆነው። በመሃል ጌታው ያፈጣል፣ በጨለማ ሎሌው ያፈጣል  የሚባለው አይነት ግንኙነት እየበዛ የአጥቢያ አምባገነኖች (Local dictators) እንዲፈለፈሉ ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል።
ፓርቲና መንግስት መለያየት አለባቸው በሚባልበት በአሁኑ ሰዓት የመመሪያ ትርጉም በፓርቲና በመንግስት ውስጥ ይለያይ ይሆናል ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው። የተለያዩ የቲያትር መድረክ ላይ የሚተውን ተዋናይ መብራቱና መጋረጃው ይለያይ ይሆናል እንጂ ተዋናዩ ገጸ-ባህሪው ያው ነው። ወዲህ ፓርቲያዊ ግለሰብ፣ ወዲያ መንግስታዊ ግለሰብ ለመሆን አይቻልም። በአንድ ራስ ሁለት ምላስ ከመሆን በቀር።  በሩስያ የታየውና ፓርቲውንና የመንግስትን ቢሮክራሲ ለመለየት ከማይቻልበት ደረጃ (Bureaucratization of the party) የሚባለው ማለት ነው። አስቀድሞ ነገር የፓርቲው ጤና አለመሆን ነው። ገዥው ፓርቲ ጤና ሳይሆን የሚወርዱት መመሪያዎች፣ የሚሰጡት ትዕዛዛት ጤና አይሆኑም። እንደ ኢትዮጵያ ባለው አገር ደግሞ ጭራሽ ከቢሮክራሲ ጋር ፓርቲው አንዴ ከተፈጣጠመ በኋላ እናፋታህ ቢሉት፣ ከስልጣን ናፋቂነት እስከ ጥቅም አጋባሽነት ያለውን የግለሰቦችና የድርጅቶች ህልውና ማናጋት ይሆናል።
 የውስጥ መመሪያዎችና ፖሊሲዎች ደረቅ ወይራ የሆኑበት ሰዓት አውራ ገዥ ለሆኑት ሃያላን መንግስታት የተሸበበ የበቅሎ ልጓም በቀላሉ እንደመሳብ ይሆንላቸዋልና ውሃውን ወደፈለጉት ቦይ የሚነዱበት ቀጫጭን መመሪያ ማድረግ የበለጠ ቀና ይሆንላቸዋል። ታዛዡ ያለችግር ይታዘዛል፡፡ መመሪያ ነዋ! ስለዚህ የወረደው መመሪያ መሬት አይወድቅም። በዚህም ሃያላኑ በሰሜን የተሳካውን ድል በምስራቅም ቤተ-ሙከራ ውስጥ ለመክተት የረጋ መደላድል ማግኘታቸው ነው ማለት ነው። ዲሞክራሲያዊ ያልሆነ ህብረተሰብ ውስጥ የጌቶች መዋቅር ብዙ ነው። ጌቶቹ ሰማየ ሰማያት ላይ የተቀመጡ፣ የማይታዩ  ሃያላን በሆኑ ጊዜ ደግሞ የትዕዛዙ መነሻ ጫፍ አይታይም። ውጤቱ እንጅ። ውጤቱ ምንም ይሁን ምን ህዝብ አልተዘጋጀበትምና በተደራጀም ሆነ ባልተደራጀ መልኩ እሺ ወይም እንቢ ለማለት (React ለማድረግ) አቅም አይኖረውም። የቅዱስ ጊዮርጊስ ጦር ሲወጋ እንጅ ሲወረወር አይታይም እንዲል መጽሐፉ። በተጠመደለት ወጥመድ ውስጥ ዘልሎ ጥልቅ ለማለት የሚጣደፍ ሕዝብ፣ የፖለቲካ ፓርቲም ሆነ የሙያ ማህበር ያልታደለ ነው። ከሚቀመርለት ቀመር፣ ከሚታጠርበት አጥር ማዶ ለማየት የማይችል ህብረተሰብ እንደተገለበጠች ኤሊ ነው። ወደ ጤናማው አቋሙ የሚመልሰው የውጭ እርዳታ ይጠብቃል።
ዝናብ ሊመጣ ሲል ጆሮዋን ለምታቆመው አህያ፣ ለውጥ ሊመጣ ዳር ዳር ሲል ጆሮውን የሚያነቃ፣ ለውጥ ወዳድ፣ ሀገር ወዳድ ምሁር ያስፈልጋል። ሀገር ወዳድ ምሁር የህዝብ አይን የህዝብ የጉዞ አቅጣጫ ጠቋሚ ቀስት ነው። በአንጻሩ ለውጥ ፈላጊ፣ ተንቀሳቃሽ ምሁር ያጣ ህዝብ ያልታደለ ነው። የኩሬ ውሃ ነው። አይፈስም። አይጠራም። አይጸዳም። አይሻሻልም።  ሕዝብን በመልካም አስተዳደር ንፍቀ-ክበብ ውስጥ የማይከቱና የታዘዘውን ተቀባይ የሚያደርጉ መመሪያዎች እንደተሸነቆረ እቃ ናቸው። ምንም አይነት ቀና ነገር ቢሞሉባቸው፣ ምንም አይነት የለውጥ አስተሳሰብ ቢከቱባቸው ያፈሳሉ። ይህም ውሎ አድሮ መመሪያ አውጪዎችን፣ ፖሊሲ ቀራጮችን ጥያቄ ውስጥ ማስገባቱ አይቀሬ ነው። መርማሪዎች ተመርማሪዎች፣ ጠያቂዎች ተጠያቂዎች የሚሆኑበት ጊዜ እየመጣ መሆኑ ግልጽ ነው። የማረጋገጫና የማጣሪያ መንገድ ደግሞ በህዝብ እጅ አለ።  ማ ወሳኝ፣ ማ ጽዱ፣ ማ ኢዲሞክራሲያዊ፣ ማ ዲሞክራሲያዊ፣ ማ ተቻቻይ፣ ማ ገፊ፣ ማ ለአገር የቆመ፣ ማ ራሱን የሚሰዋ መሆኑ ይለያል። ጊዜው ሲደርስ “የተሰነጠቀ ቅልን ለማወቅ ውሃ ጨምርበት” ማለት ብቻ ነው።